Quantcast
Channel: ዓለም
Viewing all 231 articles
Browse latest View live

እንወራረድ! ...ዘረኝነት ሳይሆን ኢትዮጵያዊነት ይበለጽጋል!

$
0
0

   በተፈሪ የማነ

ለወትሮ ባለታይም (ባለጊዜ ማለት ነው) እንደምነህ ብሎ ሰላም የሚለኝ ቢኒ የምንለው ጓደኛችን ሰሞኑን ስንገኛን በተደጋጋሚ አየህ የእናንተ የፖለቲካ አስተሳሰብና ውጤቱ ይለኝ ጀመር። የነማን? ብዬ ስጠይቀው የእናንተ ብሎ ይደግምልኛል። እኔም እንደ አፄ ኃይለ ሥላሴ የጥቅል ጨዋታ ለምዶብሃል። ለይተህና ወስነህ መናገር ተለማመድ ካልኩ በኋላ የትኛው አስተሳሰብ? የትኛው ውጤት? ሳልለው ነገሩን ዘልዬ ደህና ዋልክ ብዬ ጨበጥኩት። ሁሉም እንዳንተ ቢሆን ምን አለበት አለና ዛሬ ላሳየኸው የተለየ ፀባይ ደብል ማክያቶ ይገባሃል ብሎ አስተናጋጅዋን ጠራት።

ሂላሪ የሚል ቅፅል የሰጠናት አስተናጋጅ አቤት ብላ ስትመጣ ለባለታይም ደብል ማክያቶ ሲላት አንተ ግን ለምን እሱን ለቀቅ አታደርገውም? አለችው። ቢኒ የአፀፋ መልስ ለመስጠት ወደ ኋላ አይልም፡፡ ሼር አለሽ እንዴ? አላት። ምኑ ላይ? ስትለው ጠረጴዛው ላይ አላት። አልገባትም ወይም ትርጉም አልሰጠችውም መሰለኝ ጨዋታዋን እንዲህ ስትል ቀጠለች። እሱን እያየች እውነቴን ነው ከአንተና ከእሱ ማን ነው ባለታይም? አለችው። ምነው? አላት በጣም የሚያደናግርና ግልጽ ያልሆነ ጥያቄ። እኔ ጣልቃ ገባሁና መልስ አቅርብ አልኩት። የማላውቀው ነገር አለ እንዴ? ብሎ ነገሩን ሩቅ ሊወስደው ሞከረ። አጅሪት ቀላል አይደለችም መወዝወዙን ተውና ቅልብጭ ያለ መልስ ስጥ ስትለው፣ ይኼ አሁን ያልሽው ለጥያቄ ይበቃል ብለሽ ነው ብሎ ለእኔ አጭር ሻይ ሲላት፣ ዛሬ አልለቅህም እንዲያውም የሰሞኑ ግርግር ላይ ሳትኖርበት አትቀርም አለችው። አንቺ እኮ ባስሽብኝ ሲላት እውነቴን ነው ዛሬ አልለቅህም። ይኼ ምስኪን ሰው ባለታይም እያልክ ሥጋና ደሙን ጨረስከው እንዳለችው ይህን ያህል ካሰብሽለት ሥጋና ደሙም ካለቀ ኬክ ጨምሪለት ብሎ እንደተለመደው አሾፈ። ቢኒዬ ሁላችንም ባለታይም እንድንለው እንዳንተ ዓይነቱን መኪና ስጠው ወይም እንዲያገኝ አድርገው አለችው ለስለስ ባለ ድምፅ። የኔ መሰለችሽ እንዴ የእሱ እኮ ናት ሲፈልግ ይወስዳታል ሲፈልግ ይሰጠኛል ሲላት ለጠጥ ባለ አነጋገር፣ ኧረ እባክህ ካለች በኋላ ጭቃ አትርገጥ ብላ ወደ ባሬስታው አቀናች።

እንደተለመደው ባለታይም ብሎ ጠራኝና ዛሬ እኮ ኃይለኛ ደጋፊ አገኘህ ነገሩ እንዴት ነው? ሲለኝ ኢትዮጵያዊነት እንዲህ ነው አልኩት። የት ያለ ኢትዮጵያዊነት ሲለኝ ማዶ የሚጮኸው ዳያስፖራ በማለት ሁለታችንም በሚገባን አነጋገር መለስኩለት። ኧረ ዛሬ እንዴት ነው? ሲለኝ እኔም እንዴት? አልኩት። ጨዋታ ጨምረሃል ብዬ ነው ብሎ በስድ ንባብ አዜመ። ቀጥሎም ዛሬ እንዴት ተገለጠልህ? ምኑ? ስለው ኢትዮጵያዊነት አለኝ። መቸስ ተሰውሮኝ ያውቃል። ደግሞ በአገራዊነት ጉዳይ እኔ አይደለሁ የምቀድምህ? ብዬ ስጠይቀው ጨዋታችንን ወደ ኢትዮጵያዊነት ስላዞርከው ብቻ ተመቸኸኝ ብሎ ዳንስ ቢጤ መሆኑ ነው ትከሻውን ወዘወዘው።

እንወራረድ! ዘረኝነት ሳይሆን ኢትዮጵያዊነት ይበለጽጋል ብዬ ለውድድር ጃስ አልኩት። መስሎሃል ብሎ ሞጋቼ ጨዋታችንን ለማጠየም ሞከረ።

 ሙግታችን በበላ ልበልሃ እንዲሆን አሁንም ዘረኝነት ሳይሆን ኢትዮጵያዊነት ይበለጽጋል ብዬ ወጠርኩት። ሁሉም ዓይነት ጥፋት በወያኔ ላይ የሚደፈድፈው ሞጋቼ ኢሕአዴግ እያለ? በኢሕአዴግ መስመር? ኢትዮጵያዊነት ሊበለጽግ አለኝ። በቀላሉና ‘ጀንተል’ ባለድምፅ አዎን አልኩት። አይታሰብም ሲል መለሰልኝ። ምክንያት እናቅርብ ስለው ከማኪያቶ በኋላ አለኝ። የኢትዮጵያዊነት አጀንዳ ተነስቶማ ከማኪያቶ በኋላ አይባልም ብዬ ሳልጨርስ ነጠቅ አደረገና ስለሌለ ኢትዮጵያዊነት ለምን ታከራለህ ብሎ በአሪፍ ስሜቴን ለማቀዝቀዝ ሞከረ። ሩቅ መሄድ ሳያስፈልገኝ በቅርብ ያለውን ውብ ኢትዮጵያዊነት ይኸው ብዬ ካፌው ውስጥ እየተዝናና ያለውን ወጣት፣ አዋቂ፣ ጎልማሳ፣ ትግርኛ፣ አማርኛ፣ ኦሮሚኛ፣ ጉራጊኛ፣ ሶማሊኛ፣ ጋምቤሊኛ... በአጠቃላይ ኢትዮጵኛ የሚናገር ታዳሚ ላይ በዓይኔ ዞር ዞር እያልኩ አሳየሁት። ምን ማለት ነው? አለኝ። ይኸው እንደኔና እንዳንተ የተለያየ ቋንቋ ያላቸው ቀይ፣ የቀይ ዳማ...ኢትዮጵያዊያን አብረው ይጫወታሉ፣ አብረው ይስቃሉ፣ አብረው ይወያያሉ ብዬ ነገሩን ካብራራሁ በኋላ መለስ ብዬ ፊቱን ሳየው መስሎሃል ብሎ ለሁለተኛ ጊዜ ጨዋታችንን ያለ ምክንያት ለማጨለም ሞከረ። እኔም ለሁለተኛ ጊዜ በምክንያት ላይ ተመሥርተን እናውራ አልኩ።

ማኪያቶው መጣ። ሞጋቼ ዘናጭ አይፎን ሲክስ የምትባል የሌባ ቀልብ የምትስብ ሞባይል አለችው። እሷን ከፈታት። ስማቸውን መጥራት ምን ያደርጋል በዩቲብ የሚያወሩ ሰዎች አሳየኝ። ወያኔ (TPLF) አንድነታችንን ገደል ከተተው ይላል አንደኛው ተናጋሪ። ሁለተኛውም እመኑኝ ወያኔዎች ለመገንጠል እየተዘጋጁ ነው ይላል። በአዳራሹ አሥራ ስምንት የሚሆኑ ተመልካች ወይም አድማጮች ይታዩኛል፡፡ እነሱ ደግሞ ያጨበጭባሉ። ከሞባይሉ መስተዋት ቀና ስል አየህ ይኼ ነው እውነቱ አለኝ። የእነማን አልኩት? የአገሪቱ ነዋ አለኝ። ኢትዮጵያን አታውቃትም ስለው ባለታይሞች ያውቋታል አለኝ።

ሞጋቼን አገርና ፖለቲካ የተለያዩ ናቸው ብዬ አስተውሎቱን ጠራሁለት። በዚህ እንስማማለን ብዬም ጠየቅኩት። ነበር! ግን እናንተ አያያዛችሁት አለኝ። ሞጋቼን አሁንስ ጨርሰህ ዘቀጥክ ስለው ደንገጥ አለና ወዴት? አለኝ። ወደ ታወረ ዘረኝነት አልኩት። አልክ? ሲለኝ ይኸው በድፍን እናንተ፣ እነሱ እያልክ ነው። እሺ ከመዝቀጥ ልትረፍ፣ ልውጣና ልሞግትህ ሲለኝ በምክንያት ተመሥርተን ብቻ ከሆነ አልኩት። ይስማማኛል ሲለኝ እጄን ሰጠሁትና ደስ በሚል ስሜት ጨበጠኝ። ሞጋቼን ዘረኝነት መባከን፣ ቁልቁል መሄድ፣ ለአተራማሽ፣ ለዘራፊ መመቸት እንደሆነ አብራራሁለት። አንተ ደግሞ እንዲህ ዓይነት ነገር አያምርብህም ብዬ ካሟሟቅኩት በኋላ እንወራረድ! ... ዘረኝነት ሳይሆን ኢትዮጵያዊነት ይበለጽጋል አልኩት።

ተጎንብሶ ከማኪያቶው ስኒ ሁለት ጊዜ ካነሳ በኋላ እባክህ ተወኝ ወያኔ እያለ አንድነት አይታሰብም ብሎ ተመልሶ ወደ አሮጌው ዜማ ገባ። ቀጥሎ ያ ፕሮፌሰር ብሎ ትንሽ ራሱን ከነቀነቀ በኋላ ሲለው የነበረ እኮ እውነት ነው። ይኼው ዘረኝነቱ ጫፍ ደረሰ አለ። ፊቱን ኮስተር እያደረገ አሁን የምንሰማውና የምናየው ነገር የማን ልጅ ነው? እንዳለኝ የቱ? እየሆነ ያለው? አሁን የጠቀስካቸው ሰዎች ፍሬ እንጂ የወያኔ ፍሬ አይደለም ብዬ ስመልስለት ገ..ለ..በ..ጥ..ከ..ው ብሎ ቀጥሎ አታምርር አለኝ። በአገር ጉዳይማ አመራለሁ አልኩት። እውነትን እውነት፣ ውሸትን ውሸት እያልን የመሰሪና ራስ ወዳድ ሰዎች ቃላት ተቃርነን ሰንካላውን አፍራሽ ሐሳብ ካላደረቅነው ይኼ የትም አይደርስም የሚል አባባል የስንት የዋህ ህሊና እንደሚያዛባ እያየኸው ነው አልኩት። ስለዚህ አታምርርን ተውና አምርረህ ተናገር በለኝ። የሆነውን፣ የተበላሸውን፣ የቀናውን፣ የተጠቀመውን፣ የጠቀመውን፣ ቆጥረንና ሠፍረን በግልጽ እናውራ። ወያኔም አጥፍቶ ከሆነ ከአገርም ከሕግ በላይ አይደለም ይቀጣል ስለው ወያኔ ማንም አይቀጣውም ዕድሜ እስከሰጠው ድረስ እየቀጣን ይኖራል፡፡ እባክህ ተወን የሚሆነውን እናያለን አለኝ።

ይህቺ ፍርኃት ሲሰማው የሚላት መደምደሚያ ሐሳብ ናት። ሞጋቼን ሰሞኑን መንግሥት የራሴን ስህተት ለማረም ዝግጁ ነኝ፣ በእኔ ውስጥ ያለውን አጥፊ እቀጣለሁ ብሏል ስለው ቀጣ እንዴ? ካለ በኋላ የሚቀጣቸው እነማን አንደሆኑ ታውቃለህ? ትናናሾቹ ናቸው። ብዙ አትጠብቅ ብሎ አፏጨ። እሱን በቀጣይ የምናየው ይሆናል። ለጊዜው ነብይ አትሁን ብዬ ይልቅ እነዚህ አሁን ያስደመጥከኝ የዩቲብ ሰዎች ያሉትን ነገር እንዴት ታየዋለህ? እውነት እነሱ በሚሏት ኢትዮጵያ ውስጥ ነው እየኖርን ያለነው ወይስ እኔና አንተ ቀንና ሌሊት፣ ክረምትና በጋ፣ ትምህርት ቤትና ሥራ ቦታ፣ መዝናኛና ቤተ ክርስቲያን የምንሄድባት ኢትዮጵያ ናት ብዬ ወደ ጥንት ነገራችን ስመልሰው እኛ ያለንባት ኢትዮጵያ እነሱ እንደተረጐሟት ናት አለኝ። እውነትህን ነው? ብዬ ለማስረገጥ ጠየቅኩትና አዎ አለኝ። ያሳዝናል ከራስህ ጠፍተሃል ስለው እንዴት? ብሎ ሳቅ አለ። ኦ! ወዳጄ ልቤ መጀመሪያ ከራስህ ጋር ታረቅ አልኩት። ኢትዮጵያ በፌስ ቡክ፣ በዩቲብ ለጥፋትዋ እንደሚያቀነቅኑባት የኤርትራ ሕግደፍ ሰዎችና ሌሎች አይደለችም። ኢትዮዽያ ለዘመናት የኖረች ወደፊትም የምትኖር በታላላቅ እሴቶች የተገነባ ሕዝብ ያላት አገር ናት። ነጠቅ አደረገኝና ነበር አሁን ግን ነባር እሴቶቻችን ተመናምነዋል፣ አንተም አትሸወድ አለኝ። የትኞቹ ናቸው የተመናመኑት ስለው መከባበር፣ መተጋገዝ፣ ቅድሚያ ለወንድሜ ለእህቴ ይሁን እያሉ መደሰት፣ እውነት መናገርና ለእውነት መቆም፣ የራስህ ያልሆነውን መመኘት ነውር አድርጎ ማየት ቀርቷል። ስለዚህ ማሰሪያ የሌለው ዜጋ እየፈራባት ያለች አገር ናት አለና ሰማይና ምድሩን አጠቆረው። ሁሉም ለየራሱ ዘብ ቆመዋል። ይህ ደግሞ የተሸወዱ ፖለቲከኞች የፈጠሩት ነው አለኝ።

ማብራሪያ ስላስፈለገኝ እንዴት? ብዬ ሞጋቼን ጨዋታውን እንዲያደምቅ ዕድል ሰጠሁት። አየህ ለፖለቲካዊ አይዲዮሎጂ ሲባል ከዚያም ወረድ ባለ የደመቁ ፖለቲከኞች ሆነው ለመታየት ሲሉ የወያኔም ሆኑ ሌሎች የፖለቲካ ልሂቃን ነባሩን እሴት ታግለው ጥለውታል። አሁን ያለው ትውልድ በነባሩም በሰርጎ ገቡም የታመሰ ነው። ከመታመስ ለመውጣት ራሱን ብቻ የሚወድ ሆኗል። ከዚያ ከፍ ቢል ብሔሩን ይወድ ይሆናል። አገር፣ ኢትዮጵያዊነት የሚባሉ ነገሮች ለሁሉም በዚህች ቅድስት አገር ያለ ሕፃን፣ አዋቂ፣ ፖለቲከኛ፣ ሃይማኖተኛ፣ ሙያተኛና ነጋዴ በጣም ሰፊ ነገሮች ሆነውበታል። ዘረኝነት ግን በቀላሉ ራስህን የምትጠቅምበት ማረሻ ስለሆነለት ስለሰፊውና አንኳሩ ኢትዮጵያዊነት ግድ የለውም። ስለዚህ አንተ ይበለጽጋል የምትለው ኢትዮጵያዊነት መሠረቱ እየተናደ በሚያድር አገር ላይ የሞኝ ምኞት ከመሆን አልፎ ዋጋ የለውም ብሎ የሚያስፈራ የሐሳብ ናዳ አወረደብኝ።

ሁለታችንም ማኪያቶ ከያዙ ስኒዎቻችን ተጎነጨን። በተናገረኝ ነገር እጅግ ሐዘን ተሰማኝ። ተስፋዎቼን መፈለግ ጀመርኩ። ባልከው ሁናቴ ውስጥ ሆነንም ቢሆን ደማቅ ኢትዮጵያዊነት አለ ብዬ ጀመርኩ። እርግጥ ነው ለግል ጥቅማቸው ሲሉ ዘራቸውን ወይም ብሔራቸውን ለመጠቀሚያ የሚያመቻቹ መኖራቸው እጋራሃለሁ።

ግን አንተ በምትለው ደረጃ አይደለም። የኢትዮጵያ ሕዝብ ባህል፣ ሃይማኖት፣ ጋብቻ፣ ኢኮኖሚ… በጥብቅ ያስተሳሰረው በመሆኑ አገራዊ ስሜቱ አንተ እንዳልከው በቀላሉ የሚናድ የበረዶ ክምር ሳይሆን ጽኑ የብረት አጥር ነው። እነዚህ ዘር ቀለም እየቆጥሩ የሚያወሩን በመሠረቱ ዘር የሌላቸው ዘረኞች ናቸው። ዘር የሌላቸው ዘረኞች ማለት ደግሞ ምን ማለት ነው? አለኝ። መጠየቅ መልካም ነው። እነዚህ የዘረኝነት አጥር ሽቅብ የሚገነቡ ሰዎች ዘራቸው ደምና አጥንት እንዳይመስልህ። የዘረኝነት መሠረታቸው ጥቅም ነው። ገንዘብ የሚሰጣቸው፣ የሚያቀብላቸው ሁሉ ዘራቸው ነው። በመሆኑም እነዚህ ዘር የሌላቸው ዘረኞች በሕዝብ መሀል ሁሌም እሳት ያነዳሉ፡፡ ሰው እየተቃጠለ እነሱ ይዘርፋሉ፣ይዝናናሉ…ይበላሉ።

ስለዚህ እንዲህ ያሉ ሰዎችን እያየን የኢትዮጵያዊነት መሠረት የምንለካ ከሆነ በመቶና በመቶ ሃምሳ ሰው መላ ኢትዮጵያዊያንንና የኢትዮጵያ ታሪክ በተሳሳተ መሥፈርት መገመት ይሆናል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር አንዳንዶቹ መቶ ሚሊዮን ሞልቷል እያሉ ነው። ከዚህ አኃዝ ተነስተን ስናየው ዘር የሌላቸው ዘረኞች ትንሽ ናቸው። ጥቂቶች በሽተኞች ለዘመናት የተገነባውን ኢትዮጵያዊነት አይጎዱትም። ለእነዚህ ሰነፎች ምላስና ሰንበር የሚያቀርቡ ኢትየጵያዊነታችንን የማይወዱ የኤርትራ፣ የግብፅ፣ የዓረብ አገሮች እጆች ድንበር ዘለው ገብተው ያግዙዋቸው ይሆናሉ። ይህ መጥፎ ነዳጅ ነው። ባንዳ መሆን ግን አዲስ አይደለም ድሮም የነበረ ነው። ጥቁር ሕዝብ ነጭን ማሸነፍ እንደሚችል ያሳየንበት ታሪካችንም ላይ የተወሰኑት ለሆዳቸው ያደሩ  ተታለዋል። አርበኛው ኢትዮጵያዊ ግን ኢትዮጵያዊነትን ገንብቷል። እንወራረድ! ኢትዮጵያዊያን ራሳቸውን አሳልፈው ለባዕዳን መጫወቻ አይሰጡም። ሰሞኑን ያየናቸው የተሞከሩት የዘረኝነት ስሜቶች ይከስማሉ፣ ፌስቡክም ይደርቃል። በመልካም ሐሳቦች ተሞልቶ ይፀድቃል። እንወራረድ! ዘረኝነት ሳይሆን ኢትዮጵያዊነት ይበለጽጋል።

ሞጋቼ ስማ አለኝ። ዘረኝነት እኮ አንዳንድ ካድሬ የሚሰብከው የኑሮ ዘይቤ ሆኗል ሲለኝ ደነገጥኩኝ። እናም በድንጋጤ ለምን? አልኩት። በል አድምጥ እዚህ አገር ሰው የሚሾመው በመዋጮ ነው። ምን ማለትህ ነው? ስለው ኢሕአዴግ ከየብሔሩ አዋጡ እያለ ይሾማል። ስለሆነም በመዋጮ የሚሰበሰብ የሠለጠነም ያልሠለጠነም ካድሬ በየእርከኑ ያለ የመንግሥት አስፈጻሚ የሥልጣን ልጓም ይቀበላል። አስተውል ሥልጣን ያሰጠችው አቅሙ ሳትሆን ብሔሩ ናት። ስለዚህ ሥልጣን ከሰጠችው አገሩ በላይ ሥልጣን ያሰጠቸው ብሔሩን እንደ መሣሪያ ይጠቀማል። ሞጋቼ ቁም ነገር የሚመስል ነገር በማቅረቡ እንዴት? ብዬ አሁንም ጠየቅኩ። አየህ በመዋጮ የተሾመው ሰው የመንግሥት ሥልጣን ያላግባብ ሲጠቀም ቢያዝ ወይም ቢከሰስ የሌሎች ብሔር ተወላጅ ስላልሆንኩኝ እንጂ፣ ከእነሱ በላይ መቼ አጠፋሁኝ ብሎ በማንነቱ የተጠቃ አስመስሎ ያቀርባል። ሌላው ደግሞ የበለጠ ተፅዕኖ ፈጣሪ ወይም ተቆርቋሪ ሆኖ ለመታየት ሲፈልግ ወይ ደግሞ ተጨማሪ በጀትና ሥልጣን ለማግኘት ወረዳችን ወደ ሌላኛው ክልል ወይም ወደ ሌላ ዞን ይዛወርልን፣ ከወረዳነት ወደ ዞንነት ከፍ ይበልልን በማለት የዋሁን ያነሳሳሉ። ከፈለገም አንቀጽ 39 እንደ መጫወቻ ይጠቅሳል። ከሕዝብ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ሲቀርብለት እኔ ምን ላድርግ እንደ ሌላኛው ክልል እኩል መብት የለኝም ዕድል አይሰጠኝም ብሎ በሌላኛው ሕዝብ ያላክካል። መርዝ ይረጫል። ቀድሞም በችሎታው ሳይሆን የብሔር ተዋፅኦ እንዲኖር መሾሙን የሚያውቁት ነዋሪዎች ከተጠያቂነት ለማምለጥ የሚያቀርበውን የማምለጫ እንቶ ፍንቶ ባገኘው ሥልጣን ያገኘው እውነት አድርገው ይቀበሉታል። በመሆኑም ከኢትዮጵያ በላይ የሠፈራቸውን ጥቅም ይመለከታሉ። ስለዚህ እንዲህ ባለ ትስስር ያለ ሕዝብ ኢትዮጵያዊነት ያበለጽጋል ብሎ ማሰብ ከባድ ነው አለኝ።

ማኪያቶውን እየጠጣህ አልኩት፡፡ እሱ አይቀርም አለኝ። ሞጋቼ ዛሬ ቋንቋውም ሐሳቡም ጠንከር ብሏል። ይሁን እንጂ በአገራችን ነባራዊ ሁኔታ ዘረኝነት አገራዊነትን ሊያሸንፍ አይችልም። ይህ ጽኑ እምነቴ ብቻ ሳይሆን በአገራችን ተደጋግሞ ኢትዮጵያዊነት ዘረኝነትን በተግባር እያሸነፈ የመጣ በመሆኑ ልትፈጥርብኝ የፈለግኸው ሥጋት ትኩረት አልሰጠውም አልኩት። ነገር ግን የጠቀስካቸው ብሔር ቅድ የሆኑ ካባቸውን የሚያዘጋጁ ሕዝባቸውን የሥልጣንም የገንዘብ መጠቀሚያ ሊያደርጉ የሚፈልጉ ኃላፊነት የማይሰማቸው አገርን እንደ ሸቀጥ የሚያዩ የሸቀጥ ሰዎች እንደሚኖሩ አልክድም። ለምሳሌ ውድ ሞጋቼ እኔን ባለታይም ትለኛለህ። በተግባር ግን ባለታይም እንዳልሆንኩ አንተ ታውቃለህ። ነገር ግን እኔን ባለታይም እያልክ ከምናውቃቸው ሰዎች ጋር የአገሪቱን ዕድል በግዙፍ ጡጦ የምትጠባው አንተ ነህ። እንዳንተ የሚያደናግሩ ቅድም ያልካቸው በመዋጮ ወይም በጓደኝነት የተሾሙም የሾሙም አይጠፉም ብዬ ሐሳቤን ለመቀጠል ስዘጋጅ ቆይ ተረጋጋ አለኝ። እሺ ብዬ ዕድል ስሰጠው ሞጋቼ ማዶ ያለ ሕንፃ አሳየኝ። ምን ማለቱ እንደሆነ ገባኝ።እየተዝናናንበት ስላለነው ግዙፍ ሕንፃ ግን ግድ አልሰጠውም። ይኼስ አልኩት። ዝም አለ። እሱን ተውና ከእኔና ከአንተ ማን ነው ተጠቃሚ ስለው አታምርር አለኝ። ጥሩ እሺ እሱንም እንተወውና ማንም ምን ያህል ዘረኝነትን ቢሰብክ የኢትዮጵያ ሕዝብ አገራዊ አንድነቱን ለድርድር አያቀርብም አልኩት። ምን ማለትህ ነው ቀረበ እኮ አለኝ። ባንተ ትርጓሜና ምኞት ስለው እንዴ ሰው እየተፈናቀለ ብሎ ዓረፍተ ነገር ሠራ። ማምለጫ የሌለው የወቅቱ እውነት ነው።

ሞጋቼን ይህን ክፉ ተግባር ማን ያደረገው ይመስልሃል ብዬ በጥያቄ ያዝኩት። በቦታው አልነበርኩም አለኝ። አንተስ እንደዚያ ያለ ነገር ታደርጋለህ ብዬ ጠየቅኩት። እኔ አላደርገውም እንዳለኝ በህሊናህስ እንዲያው እንደ ምኞት ነገር ይኖርህ ይሆን ስለው ኧረ በጭራሽ አለኝ። ታድያ ማን ይመስልሃል ስለው ሁሉንም እያቆሰለ ያለ በሽተኛው የኢሕአዴግ የአመራር አካል ተግባር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የተገኘ አሉታዊ ውጤት ነው አለኝ። እግዚአብሔር ይስጥህ ብዬ ጨርሼ ሳላመሰግነው ሞጋቼ የበሽታው መንስዔ ግን አስተዳደራዊ ክልሎቹ ቋንቋ ተኮር በመሆናቸው ነው ብሎ ሙግታችንን ሊያሰፋው ሞከረ።        

ይኼ እንኳን አመክንዮ ሊሆን አይችልም። ምክንያቱም ያልከው የአስተዳደር ሥርዓት ዜጎች በራሳቸው ቋንቋ እንዲማሩ፣ እንዲተዳደሩና እንዲዳኙ ያስቻለ ነው። ይህ ደግሞ የዴሞክራሲ መሠረታዊ መርህ ነው። ይህ አሠራር በመተግበሩ የተገኘ ውጤት ደግሞ የአገሪቱ ልማት በአዲስ አበባና በአንዳንድ ከተሞች ብቻ ሳይሆን በመላ ኢትዮዽያ መሆን አስችሏል። ከነ ጉድለቱ ኢትዮዽያ ሁሉም ዜጎችዋ የሚጠቀሙባት ትልቅ አገር ሆናለችም ብዬ አምናለሁ። ነገር ግን አንተ ቅድም ያልካቸው በማይገባቸው ቦታ በመዋጮ የተሾሙና እኔ ያልኳቸው ዘር የሌላቸው ዘረኞች ይህን አሠራር መጠጊያ የሚያደርጉ አላጋጭ ተጠቃሚዎች ብዙ ነገር ለማመሰቃቀል ይሞክሩ ይሆናል እንጂ፣ ራስን በራስ እያስተዳደሩ አገርን መገንባት ጤነኛ አስተዳደራዊ አካሄድ ነው። ነገር ግን አስተዳደራዊ አወቃቀሩን ተገን አድርገው ብሔርተኝነትን የሚያጎለብቱ ከመተጋገዝ ጠላትነትን የሚሰብኩ ጤነኛውን አስተሳሰብ ጤና የሚያሳጡ የራሱ የድርጅቱ ጥገኞችና ሌሎች አልጠፉም። እነዚህ ሁሉ ግን ከነባራዊ እሴቶቻችንና ከተስፋዎቻችን በላይ ለመሆን የሚያስችላቸው መሠራት የላቸውም። ስለዚህ ዘረኝነት ሳይሆን ኢትዮጵያዊነት ይበለጽጋል፣ እንወራረድ!!

የሚያደርጉ የውስጥ ተጠቃሚዎች የውጭም የፌስቡክ ጦረኞቹ እንደሚሉት ትግራይና የትግራይ ሕዝብ ለብቻቸው በልጽገው ሌላው ከትግራይ በታች ከሆነ ለህሊናህ እተወዋለሁ እንዳልኩት፣ ወዲያውኑ እንደዚያ አላልኩም፡፡ ከአንዴም ሁለቴ ትግራይ ሄጃለሁ የትግራይን ሕዝብ ኑሮ አውቀዋለሁ፡፡ የዚያ የምስኪን ሕዝብ ሁኔታ ያሳዝናል አለኝ። የምታዝንለት ከሆነ ለፌስቡክ ጦረኞቹ ንገራቸው አልኩት።

አንተ ደግሞ ችግር አለብህ ነገሮችን ትደባልቃለህ ሲለኝ ምንና ምን ብዬ በጨዋነት ጠየቅኩት። የአንተ ችግር የሥርዓቱ አመራሮች ሲነኩ ትግራይ ተነካ ብለህ ነገሩን ትደበላልቀዋለህ አለኝ።

ከአዘጋጁ፡-ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው tefyem05@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡

         

 

Standard (Image)

የኢትዮጵያ ሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲ አበባው እንዳያብብ እየተሽመደመደ ሴክተሩን መደገፍ ለምን አቃተው?

$
0
0

በዓለሙ ግርማ

በሚኒስተሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 152/2000 የኢትዮጵያ የሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲ ተቋቁሟል፡፡ ይህ ኤጀንሲ ሲቋቋም ሦስት ዓበይት ዓላማዎች ነበሩት፡፡

  1. የሆርቲካልቸር ምርትና ምርታመነት በተፋጠነ በቀጣይነት እንዲያድግ የማብቃት፣
  2. ዓለም አቀፍ የምግብ ደኅንነት መሥፈርቶችን የሚያሞሉ የሆርቲካልቸር ምርቶችን ለውጪ ገበያ በዓይነትና በብዛት የሚቀርቡበትን ሁኔታ የማመቻቸት፣
  3. ድጋፍ ሰጪ አገልግሎቶችን ያስተባብራል፣ እነዚህን በማቋቋም ደንብ በተሰጠው  ኃላፊነት ዓላማ መሠረት በማድረግ ተጠሪነቱ ለእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ሚኒስቴር ሆኖ የተቋቋመ ኤጀንሲ ነው፡፡

መንግሥት ድህነትን ለመቀነስና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችለውን የምዕተ ዓመቱን የልማት ግብ ለማሳካት በመንግሥት በኩል ግብርና መር ኢንዱስትሪ ልማት ፖሊሲና ስትራቴጂ ተቀርፆ በተግባራዊነቱ የግል ባለሀብቱ በማሳተፍ የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ይገኛል፡፡ ከእዚህም መካከል አንዱና ዋነኛው ወደ ውጭ የሚላኩ የግብርና ምርቶችን በመጠንና በጥራት ማሳደግ የውጭ ምንዛሪ ለማስገኘትና ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር በሰፊው እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ 

የኢትዮጰያ ሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲ በየሚኒስተሮች ምክር ቤት ባወጣው 152/2000 የማቋቋሚያ ደንብ መሠረት ተደራጅቶ የተሰጠውን ሥልጣን፣ እንዲሁም ማከናወን ያለበት ቁልፍ ተግባራት በመለየት ሥራዎችን እንደየባህሪያቸው በአንድ ላይ በማሰባሰብ የሚጠበቀውን ውጤት ለማስመዝገብና ልማቱን ለማፋጠን ከፍተኛ ርብርብ ለማድረግ፣ በሦስት ዋና የሥራ ሒደት በሁለት ደጋፊ የሥራ ሒደቶች እንዲዋቀር ተደርጎ የተቋቋመ ነው፡፡ በኤጀንሲው አደረጃጀት ላይ ተለይተው የወጡ የሥራ ሒደቶች የተገልጋይ ፍላጎት በማሟላት በቀጣይነት ኤጀንሲው የሴክተሩን ልማት ከጊዜ፣ ከወጪ፣ ከጥራትና ከመጠን የሚያስቀምጠውን ትልቅ ግብ (Ambitious Objective) ተደራሽነት እንዲኖረውና አጋዥና የሥራ መስመር እንዲሆን፣ መንግሥት መዋቅር ፈቅዶና በጀት መድቦ ያቋቋመው ኤጀንሲ ተልዕኮውን በመሳት እንዲደግፈው የተቋቋመው ሴክተር  አመራሩ እየተሸመደመደ ልማቱን ሳይደገፍ ኤጀንሲው በቁሙ ራሱን መግደሉን በአደባባይ ይታያል፡፡ ይኼንንም የሴክተሩ ተዋናዮችና አልሚ ባለሀብቶች ይገልጻሉ፡፡

ተቋሙ ሲቋቋም የተሰጠው ተልዕኮና ራዕይ ያለው ቢሆንም፣ ለሙያው ሩቅ በመሆንና ራዕይ በማጣት ምክንያት አንድም ፕሮጀክት ሳይቀርፅና መሠረታዊ የሴክተሩ መረጃና ዳታ ሳይኖረው ምን እንደደገፈ አይታወቅም፡፡ ሴክተሩ ምን እንደሚያስፈልገው፣ ከባለሀብቱ ጋር አስተሳስሮ የአርሶ አደሩን ገቢ በማሳደግ  ተገልጋይ ባለሀብቶች እርካታ አግኝተውና የልማት ሥራዎች ተስፋፍተው በውጭ ገበያ ተወዳዳሪ ሆነው የሚቀርቡበትን ሁኔታ ሳያመቻች፣ የሚጠበቀውን የሥራ ዕድል ሳይፈጥር በአመራሩ ደካማነትና ልፍስፍስነት ራሱ ኤጀንሲው የልማቱ ማነቆ ሆኖ ቆይቷል፡፡

ሀ. የቴክኖሎጂ ድጋፍ የኤጀንሲው ችግር     

  1. የሆርቲካልቸር ምርታማነትና ጥራትን አለመደገፍ

የሆርቲካልቸር የኤክስፖርት ምርት በገበያ ላይ ተወዳዳሪ እንዲሆን ለማስቻል ጊዜ ያፈራውን ቴክኖሎጂ በመጠቀም የቅድመና የድኅረ ምርት አያያዝ ክህሎትን ለማጎልበት፣ ብቃት ያለው ፈጻሚ በመፍጠር በኤጀንሲው በኩል ይህንን ለመደገፍ የሚያስችል አመራር አቅም አልተገነባም፡፡ በተደጋጋሚ ወጣት ሠራተኞች አቅማችን ገንብተን ሴክተሩን እንደግፍ ቢሉ አመራሩ ለሙያው በቁ ባለመሆኑና ግንዛቤው ስለሌለው፣ ምርታማነት ለማሻሻል የሚወሰዱ የአቅም ግንባታና የልማት ቴክኖሎጂ ፖኬጆች የሉም፡፡ ባለሀብቱ እባካችሁ አትምጡብን፣ ሥራ አታስፈቱን፣ የምትጨምሩት እሴት የለም  በማለት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ገልጿል፡፡ ለኤጀንሲው የሚመደበው በጀት ለእኛ እሴት ስለማይጨምር ለህዳሴው ግድብ ቢውል ይሻላል ብለው አስረድተዋል፡፡

በአበባ ልማት ላይ የተሰማሩት የግል ባለሀብቶች በተለይ ኢትዮጵያዊያን ዜግነት ያላቸው የመዳረሻ ገበያዎችን ባህሪና ዝርዝር ፍላጎት ባልገመገመ መንገድ ኢንዱስትሪው ለአገራችን አዲስ እንደመሆኑ መጠን፣ ኤጀንሲው ለመደገፍ የሚያስችል ክህሎት የለውም፡፡ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚባለው በብልሹ አሠራር የተጠላለፈ በመሆኑ ያለሟቸው የአበባ ዝርያዎች የምርታማነትና የጥራት ችግር ብቻ ሳይሆን፣ በገበያ ላይ ያላቸው ተፈላጊነት ዝቅተኛ ስለነበር የተከፈላቸው አነስተኛ ዋጋና የሽያጭ ገቢ በግብርና ልማታቸው ላይ ከፍተኛ ኪሳራ አድርሷል፡፡

በአትክልት፣ በፍራፍሬና በኸርብስ ንዑስ የልማት ዘርፍም ቢሆን ልማቱን የማስፋፋቱ ሥራ በኤጀንሲው በአግባብ ስላልተደገፈ፣ ባለሀብቱ በግል ጥረቱ የሞከረው በጥቂት ሰብሎችና ዝርያዎች ላይ ነው፡፡ የተሻለ ገቢ የሚያስገኙ፣ ምርታማነታቸው ከፍተኛና በዓመቱ ውስጥ ተከታታይ ምርት የሚሰጡ የሰብል ዓይነቶች ኤጀንሲው  የአገሪቱን  የምርምር ተቋማትን ዩኒቨርሲቲዎች በማማከር ለሴክተሩ ግብዓት የሚሆኑት  በመፈተሽ ላይ ኤጀንሲው የተጠናከረ ሥራ እንዲሠራ ባለድርሻ አከላት ባለማስተባበሩና ባለመሥራቱ፣ የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ሚኒስተርም በአግባቡ ሴክተሩን ስላልመራው ለልማቱ ወደኋላ መቅረት ምክንያት ነው፡፡

  1. መልካም አሠራርና ስታንዳርድ አለማVላት

የኮድ ኦፍ ፕራክቲክስ (code of practice) በአበባው ንዑስ የልማት ዘርፍ በሁሉም የሴክተሩ ባለሀብቶች ተወስዶ ባለመተግበሩ፣ በአትክልት ፍራፍሬና ኸርብስ ንዑስ ልማቶች ላይ ኤጀንሲው በባለቤትነት ከሚመለከታቸው የመንግሥት ባለድርሻ ተቋማት ጋር በበቂ ባለመጀመሩ፣ ይህ ሁኔታ በመዳረሻ ገበያዎች ላይ በተለይም በሸማቾች ዘንድ አገራዊ መልካም አሠራርንና ስታንዳርድ (good agricultural practices) የኮድ ኦፍ ፕራክቲስ ትግበራ በሆርቲካልቸር የኤክስፖርት ልማት ላይ በባለቤትነት ከባለድርሻ አካላት ጋር ሠርቶ የአገሪቱን የኤክስፖርት ገጽታ በመገንባት የወደፊቱን የአገሪቱን ኤክስፖርት ዕድገት ምቹ ሁኔታ መፍጠር አልተቻለም፡፡ ጥቂት ኪራይ ሰብሳቢዎችና ደላሎች የኤጀንሲው ትኩረት ኪራይ በሚሰበሰብበት ላይ ብቻ እንዲሆን አቅጣጫውን ሲያስቱት ቆይተዋል፡፡ የኤጀንሲውም ዕቅድ ከወረቀት ፎርማት ውጪ አልዘለለም፡፡ የሚገመገመውም ካለፈው ዓመት አፈጻጸም ውድቀቱ ጋር በማነፃፀር ነው፡፡ ለዚህም ነው በመጀመርያው ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን እንደርስበታለን ያለውን 1.4 ቢሊዮን ዶላር በምክር ቤቱ የፀደቀ ዕቅድ አፈጻጸም ለፓርላማው ወደ 500 ሚሊዮን ቀነሶ፣ እሱንም ሳያሳካ የቀረው ተጠያቂነት ባለመኖሩ ምክር ቤቱ ያፀደቀውን በማን ሥልጣን እንደተከለሰ አይታወቅም፡፡

  1. የግብዓት አቅርቦት ችግር

ለሆርቲካልቸር ኤክስፖርት የተዘጋጁ አገራዊ ፓኬጂንግና ስታንዳርዶች ኤጀንሲው ከባለድርሻ አካላት ጋር መሥራት ባለመሞከሩ፣ አገራዊ ፋብሪካዎች እንዲያመርቱ በማድረግ ውጭ ምንዛሪ ማዳን ባለመሞከሩ፣ ተጀምረው የነበሩ የካርቶን ፋብሪካዎች ባለመበረታታቸው፣ አንዳንድ የሴክተሩ ኪራይ ሰብሳቢዎችና ደላሎች  የአገር ውስጡ ምርት  እንዳይበረታታ አሻጥር ፈጽመዋል፡፡ የአገር ውስጥ ባለሀብት በኤጀንሲው ተደግፎ የፓኬጂንግ ሥራ ለመሥራት ኪራይ ሰብሳቢዎችና ደላሎች ከፍተኛ እንቅፋት ሲሆኑ፣ አመራሩ ይህን ለመከላከል ምንም አላደረገም፡፡

የማዳበሪያና የኬሚካል አቅርቦት ዋጋን ሊያረጋጉ የሚችሉ ንብረትነታቸው የመንግሥት የሆነ የባለድርሻ አካላት ጋር በጥናት የተደገፈ ሥራ ኤጀንሲው አልሠራም፡፡ በዚህም ዘርፍ ኪራይ ሰብሳቢዎችና ደላሎች ጊዜው ያለፈበት ፀረ ተባይ መድኃኒት ወደ አገር ውስጥ እንዲገባና በየሱቁ እንዲሸጡ ሲያደርጉ ኤጀንሲው ለሴክተሩ ያደረገው እንቅስቃሴ የለም፡፡ ባለፉት ዓመታት ልማትን በመደገፍ በሚል በአገር ላይ የተደረጉ ብልሹ አሠራሮች ተጠያቂነት ሊኖር ይገባል፡፡ የፌደራል ፖሊስና ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ  በተጠናከረ መንገድ ለልማታችን እንቅፋት የሆኑ አደገኛ አከሄዶችን ተገቢ ምርመራ በማድረግ አስተማሪ ዕርምጃ ሊወስዱ ይገባል፡፡ ይህ ሳይደረግ ኤጀንሲውን ከሰፋፊ እርሻ ኢንቨስትመንት ኤጀንሲ ጋር ለመቀላቀል የሚደረገው ሩጫ የደላላውና የኪራይ ሰብሳቢው ሰንሰለት የት ድረስ እንደሆነ እንዳይታወቅ የሚደረግ ስለሆነ መቆም አለበት፡፡  

ኤጀንሲው ከምርምር ተቋማትና ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር ትስስር ባለመፍጠሩ ለወቅቱ ገበያ የሚሆኑ የአበባና አትክልት ፍራፍሬ ዝርያዎች በአገር ውስጥ አልተገኙም፡፡ በአገር ውስጥ ዝርያ ማውጣት የሚችል ድርጀት አለመፈጠሩ የኤጀንሲው ድክመት በመሆኑ፣ በሴክተሩ ዕድገት ላይ ተፅዕኖ በመፍጠር በቀጣይ በአገር ውስጥ የቴክኖሎጂ ሽግግር አቅም ግንባታ በዘርፉ የሥራ ዕድል እንዳይፈጠር ኤጀንሲው ተልዕኮውን አልተወጣም፡፡

  1. የሎጂስቲክስ መሠረተ ልማት ችግር

እዚህ ላይ የሚያሳዝነው እኛ ኢትዮጵያዊያን ስለሆንን ሌላ አገር የለንም፡፡ ከውጭ ዜጎች ጋር በመሆን የኢትዮጵያ አየር መንገድ መወዳደር ስለማይፈልግ የውጭ አየር መንገድ እንዳይገባ እየተደረገ የሴክተሩ ፈተና ሆኗል በማለት አመራሩን ከመኮነን፣ በጥናት የተደገፈ አዲስ ሐሳብ ካለ አማራጭ ማቅረብ ይገባል፡፡ ሁሉም ለአንድ አገር እስከሠራ ድረስ የጠላት አገር አየር መንገድ ይመስል ስም ማጥፋት ተገብ አይደለም፡፡ አየር መንገዱ የግለሰብ አይደለም የአገር ሀብት ነው፡፡ ኤጀንሲውም ለአየር መንገዱ ዕድገት ማሰብ ነበረበት፡፡ ይህን ስንል እነዚህ ሰዎች ሌላ አገር አላቸው ወይ ብለው የውጭ ዜጎች ምን ያህል ይታዘቡናል?

ለአየር መንገዱ ሠራተኞች በኤጀንሲው በኩል ሥልጠና ቢሰጥ፣ ሠራተኞቹ ምን ያህል ለኤክስፖርት ሥራው ውጤታማ በሆኑ ነበር? ኤጀንሲው የማይመለከተውን ትቶ ለሴክተሩ የሚበጅ ቢሠራ የተሻለ ይሆናል፡፡

አሁን በመገንባት ላይ ባሉ የክልል ኤርፖርቶች የሆርቲካቸር ልማት ዕምቅ አቅም ያለው አካባቢ መሆኑን አረጋግጦ ዘመናዊ የማቀዝቀዣ ክፍል እንዲገነቡ በማማከር፣ የተጠናው አሉባልታ ሳይሆን ሀቅ ይዞ ለልማት ጉልበት ቢፈጥር  ኤጀንሲው ውጤታማ በሆነ፡፡ እንዳሁኑ  ለልማቱ እንቅፋት ማነቆ አይሆንም ነበር፡፡

  1. የአነስተኛ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ሆነው እንዲሠሩ አለማድረግ

 በጎረቤታችን ኬንያ በአውትግሮዎሮች ትስስር ለአርሶ አደሩ ከፍተኛ የገቢ ምንጭ የተፈጠረለት ነው የአገራችን አርሶ አደሮች ኤጀንሲው ምንም ዓይነት ሥራ በዚህ ዘርፍ ባለመሥራቱ አልተጠቀሙም፡፡ ከባለድርሻ አካላት ጋር ክፍተቱን ለመሙላት ከዘርፉ ባለሙያዎች ጋር ዓውደ ጥናት በማዘጋጀት በጉዳዩ ላይ ምክክር አድርጎ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ የሚሆኑበት፣ ሠፋፊ የሥራ ዕድሎች የሚፈጠሩበት፣ የተማረ አርሶ አደርሮች የሚፈጠሩበት ምቹ ሁኔታ መፍጠር ሲገባው፣ ኤጀንሲው የኪራይ ሰብሳቢና የደላሎች መፈንጫ ሆኖ ቆይቷል፡፡

 ደሃው አርሶ አደር ለኪራይ ሰብሳቢነት ምቹ ሁኔታ አልፈጠረም፣ ለኪራይ ሰብሳቢ የሚሆን ጥሪት የለውም፡፡ ሩጫው አርሶ አደሩን ከደላሎች ጋር ሆኖ አፈናቅሎ የመሬት ካሳ አስጨምርልሀለሁ በማለት ገንዘቡን መቀማት ነው፡፡ መሬቱን ለልማት ሲለቅ ተጠቃሚ እንዲሆን ተግባራዊ የማሳመን ሥራ ባለመሠራቱ አርሶ አደሩ እንዲከፋ ከማድረግ የዘለለ ከፌደራል መንግሥት እስከ ክልል መሥሪያ ቤት በተዘረጋ ኔትወርክ የኪራይ ሰብሳቢና የደላላ ትስስር አርሶ አደሩ ሲሰቃይ ቆይቷል፡፡ ኤጀንሲው ፍትሐዊ ሥራ እንዲሠራ፣ የሰፊው አርሶ አደር ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ፣ የሥራ ዕድል እንዲሰፋ ጥረት አላደረገም፡፡ ሞኝ ዘፈኑ አንድ ነው እንዲሉ ሁሌ የኪራይ ሰብሳቢዎች  ምንጭ የመሬት ጥያቄ ነው፡፡

አንድም ቀን ሥራው ታስቦበት አነስተኛ ገበሬዎች በኤክስፖርት ገበያ ተጠቃሚ እንዲሆኑ አልተደረገም፡፡ ለሆርቲካልቸር ምርት ግብዓት የሚሆን የሎጅስቲክስ አቅርቦት ለምሳሌ እንደ ጎረቤታችን ኬንያ ለአነስተኛ አርሶ አደሮች የማቀዝቀዣ የየቴክኖሎጂ የገበያ ድጋፍ የሚመቻችበትን ሁኔታ አጥንቶ ለመንግሥት አቅርቦ ተጠቃሚ የሚያደርግ ዕቅድ እንኳን የለውም፡፡ እርሶ አደሩ ልማቱን በጥርጣሬ ቢመለከተውና ቢያጠፋውም አይገርምም፡፡ ምክንያቱም ከልማቱ ተጠቃሚ መሆኑ አልተረጋገጠም፡፡ እንዲገነዘብም የሴክተሩ ባለቤት ነኝ የሚለው አካል አላሳየውም፡፡ 

  1. የግብይት አድማስ እንዲሠፋ ምንም አለመሠራቱ

የሆርቲካልቸር ምርት በተለይ ከአበባ አቅርቦት ውስጥ እስከ 80 በመቶ አንድ አገር ላይ ብቻ (ሆላንድ) በማተኮሩ፣ ይህንንም በጨረታ ማዕከሉ የሚካሄድ ግብይት ኮምፒተራይዝድ በመሆኑ በተጠና መልኩ የኤክስፖርተሩን የገበያ ሽያጭ የሚስጥር ቁጥር ከባለሀብቱ በመውሰድ የሻጩን ገቢ መከታተል ሲቻል፣ ለግል ጥቅም መሞዳሞድ ትቶ የአገርን ጥቅም ማስቀደም የኤጀንሰው ተልዕኮ ነው፡፡

ኤጀንሲው ከዘንግ ወደ ኪሎ መቀየሩ አገር መጉዳቱ እየታወቀ ቢሆንም፣ አሁን ያለው ሁኔታ በጥናት መመለስ ሲገባ ይህን ያነሳ በኤጀንሲ አመራር ሲወገዝ ይታያል፡፡ አመራሩ አንድ ያልገባው ማንም ዜጋ በአገሩ ጉዳይ ያገባዋል መንግሥት የተጭበረበረበት ጉዳይ የአገር ጥቅም የነካ በመሆኑ፣ የአገሪቱ ዓቃቤ ሕግና የፌደራል ፖሊስ  በዚህ ጉዳይ ጥብቅ ምርመራ ሊያከሂዱበት ይገባል፡፡ ማንም ኃላፊ ሆነ ከፍተኛ አመራር ሊጠየቅበት ይገባል፡፡ ይህም ማለት በአገሪቱ ቆላማ አካባቢ አበባው ውኃ የመያዝ አቅሙ ትንሽ ነው፡፡ በደጋው አካባቢ ውኃ የመያዝ አቅሙ ከፍያለ በመሆኑ፣ አብዛኛው የአበባ ልማት ያለው በአገሪቱ ስምጥ ሸለቆ ሞቃታማ አካባቢ ነው፡፡ ይህም ከኪሎ ይልቅ በቁጥር ቢለካ የበለጠ ገቢ ለአገር እንደሚያስገባ፣ በተለይ ኢትዮጵያዊ ዜግነት ያላቸው የዘርፉ ባለሀብቶች ይገልጻሉ፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ ለገበያ የሚቀርቡ ምርቶች የኮንስሊዴሽንና የተጨማሪ እሴት ሥራዎች ባካተተ መንገድ እንዲዘጋጁ ኤጀንሲው ምንም ዓይነት ሥራ አለመሥራቱ ለሴክተሩ ዕድገት አለመኖር  አሰተዋፅኦው  የጎላ ነው፡፡

የገበያ መዳረሻ ለማስፋት ምንም ዓይነት ጥናት አልተካሄደም፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚደርስባቸው መዳረሻዎች የአባባ ወይም የአትክልትና ፍራፍሬ ገበያ ፍላጎት በመቃኝት ለመለየት ምንም ዓይነት ጥናት አልተደረገም፡፡ ቢታሰብበት ኖሮ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ለሱም ገበያ ነውና በጋራ ማጥናት በተቻለ ነበር፡፡ ኤጀንሲው የባለድርሻ አካላትን አሰተባብሮ መሥራት አቅሙም ሆነ ክህሎቱ የለውም፡፡ ለዕቅዱ መውደቅ  ሌላው ሚስጥሩ የአመራሩ ክህሎት ችግር ነው፡፡

በኤጀንሲው ከፍተኛ አመራር ከአገር ውጭ በሚደረጉ ኢግዚቢሽኖች ለገበያ ማስፋፍያ ሥራ ምክንያት ጉዞ ቢደረግም፣ ከአመራሩ የአቅም ውስንነት ከአበል ለቀማ የዘለለ ውጤት ሳይታይ የተጠናም ጥናት ሆነ ሰነድ የለም በውጭ ገበያ የማስተዋወቅ ሥራ መሥራት የሚገባቸው የሕዝብ ግኑኝነት ሠራተኞች እንዳይሄዱ ስለሚደረግ ለባለሙያዎቹ የአቅም ግንባታ አልተደረገም፡፡

  1. ክህሎት ያዳበረ ተቋምና የሰው ኃይል እንዲፈጠር አለመሠራቱ

በሆርቲካልቸር ኤክስፖርት ልማትስ ከእርሻ ጀምሮ እስከ ገበያ መዳረሻ ድረስ በየእርከኑ ያለውን አሠራር ጠንቅቆ የሚያውቅ አመራርና ፈጻሚ ተግባራዊ ችሎታና ብቃት ያለው ተቋምና ባለሙያ እንዲፈጠር ኤጀንሲው ምንም ዓይነት ጥረት አላደረገም፡፡ ከምርምር ተቋማትና ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር ለመሥራት ሙከራ አልተደረገም፡፡ አንድ የሆርቲካልቸር የተግባር ማሠልጠኛ ለመገንባት ጥረት ቢደረግም፣ የተፈቀደውን በጀት ኪራይ ሰብሳቢዎች ተቀራመቱት፡፡ ይህም ጉዳይ በአዋጅ በተሰጠው ሥልጣን ፌዴራል ፖሊስና ዓቃቤ ሕግ ጉዳዩን እንዲመረምሩትና ኪራይ ሰብሳቢዎችን ተጠያቂ እንደሚያደርጉ ይጠበቃል፡፡

የሚያሳዝነው ሴክተሩ እሴት መጨመር አልቻለም፡፡ አዲስ ዘመን ጋዜጣ በአንድ ወቅት ኢኮኖሚ ዓምድ ሥር በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውሎ ላይ በ2006 ዓ.ም. እንደዘገበው፣ ዕቅዱ በአካፋ አፈጻጸም በማንኪያ መሆኑን ዘግቧል፡፡ በለሀብቱ ሥራ አታስፈቱን፣ አትምጡብን ሲል እሴት የሚጨምር ኤጀንሲ ለመመሥረት መጠናት ያለበት ይዘውት በወደቁ አመራሮች ሳይሆን ዝርዝር ችግሮቹ በገለልተኛ ምሁራን ተጠንቶና ክፍተቱ ምን እንደሆነ ታውቆ ነው፡፡ ተጠያቂው ማነው ተብሎ መፍትሔ ሊፈለግበት ይገባል፡፡ ይህ ባይሆን አመራሩ እንዳይታወቅ የሚፈልገው የሚደበቅ ሒደት በባለቤቱ ሕዝብ ፊት ሊጋለጥ ይገባል፡፡

በድጋፍ ስም የተደረጉ ፍትሐዊ ያልሆኑ ድጋፎች፣ በእነዚህ ሽፋን የተፈጸሙ ኪራይ ሰብሳቢነቶች አልሚ ባለሀብቶችና መንግሥት ሊያገኝ የሚገባውን የታክስ ጥቅም አስቀርተዋል፡፡ በሚመለከታቸው ተቋማት አስፈላጊው ምርመራ ሊደረግና ለሌሎች ተቋማትም አስተማሪ የሚሆን ዕርምጃ ሊወሰድ ይገባል፡፡ ይህ ሳይፈጸምና በተገቢው መንገድ ሳይገመገም፣ ተቋሙ ችግሩን ሳይለይ ኪራይ ሰብሳቢዎችን በመሸፈን በእርሻና ተፈጥሮ  ሀብት ሚኒስቴር ሥር ካለው የኢንቨስትመንት ኤጀንሲ ጋር ለመቀላቀል መሮጥ መገታት አለበት፡፡ በዚህም መልካም አሰተዳደርን ለማስፈን፣ የኪራይ ሰብሳቢዎችን ተጠያቂነት ለማረጋገጥ፣ የአገራችን ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ከኪራይ ሰብሳቢዎች ነፃ መሆኑን ለማረጋገጥ  ለሚደረገው ትግል አስተማሪ ዕርምጃ መንግሥት  ይውሰድ፡፡ ለሌሎች ተቋማት ማሳያ ዕርምጃ ከአስፈጻሚው አካል ይጠበቃል፡፡

በአገራችን የአበባ ልማት ዘርፍ ከተሠማሩ ልማታዊው ባለሀብትና ኪራይ ሰብሳቢው መለየት አለበት፡፡ በቅርቡ በተደረገ የተሳሳተ ዕርምጃ ከመንግሥት ዕውቅና ውጪ በመንደር ደላላ አማካይነት ከአርሶ አደሩ መሬት በኪራይ ወስደው ከአርሶ አደሩ ጋር መግባባት ያቃታቸው ስምንት እርሻዎች ዕዳቸውን (የእርሻ መሬት ካሳ) መንግሥት መክፈሉ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህን ያህል ገንዘብ መንግሥት ካወጣ ለምን ከእርሻ ኮሌጆች ለወጡ የእርሶ አደር ልጆች መንግሥት አደራጅቶ አላበደረም? ትክክለኛ ድጋፍ እያደረግኩ ነው የሚለው ኤጀንሲ የቴክኖሎጂና የገበያ ድጋፍ አላደረገም? ወይስ አንዳንድ ኪራይ ሰብሳቢዎች በፈጠሩት ተፅዕኖ መንግሥትን በማሳሳት ከኪራይ ሰብሳቢ ባለሀብቶች ጋር ተሞዳሞዱበት፡፡ ይህ ድጎማ በልማታዊ ባለሀብቶች ተቃውሞ ደርሶበታል፡፡  የኢትዮጵያ ሆርቲካቸር አልሚዎችና ላኪዎች ማኅበር አገራዊ አመለካከት ሊፈተሸ ይገባል፡፡ ለመሆኑ ለጉልበት ሠራተኞችና ለአርሶ አደሩ ልጆች ምን ያህል ክፍያ ይከፍላል? ከጎረቤት አገር ክፍያ ጋር ምን ይመስላል? አባላቱ ማኅበራዊ ኃላፊነት እንዲወጡ ጥረት እያረገ ነው? ወይስ አንፃራዊ ነው? ወይስ እንደ ኮሜዲ ድራማ በሕዝብ ላይ እየተወነ ነው? ሴክተሩ ባለቤት ይኑረው፡፡

ከአዘጋጁ፡-ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው alemu2008gmail.com ማግኘት ይቻላል፡፡

 

 
 

 

 

    

 

 

Standard (Image)

የአዲስ አበባ የግል ትምህርት ቤቶች የሚያበረክቷቸው ጥቅሞች ለምን ተዘነጉ?

$
0
0

    በያሬድ ኃይለ መስቀል

ሰሞኑን በሸገር 102.1 እና በ97.1 ኤፍ ኤም ሬዲዮኖች ላይ የግል ትምህርት ቤቶችን በተመለከተ የተደረጉ ውይይቶችን አዳምጫለሁ። ውይይቶቹ መልካም ናቸው። 

ይሁንና ዋነኛውን ጥያቄ ለውይይት ባለመቅረቡ በመሠረታዊ ችግሩ ላይ ውይይት አልተካሄደም።  ይህም ጥያቄ ወላጆች ለምን የመንግሥት ትምህርት ቤቶችን ትተው ልጆቻቸውን በግል ትምህርት ቤቶች ያስተምራሉ የሚለው ነው፡፡

ይህ ጥያቄ ቢጠየቅ ኖሮ የተዘረዘሩት የግል ትምህርት ቤቶች  ችግሮች  መንስዔዎቻቸው ምን እንደሆነ በቀላሉ ለመረዳት በተቻለ ነበር።

የግል ትምህርት ቤቶች ችግር የለባቸውም ወይም ከበርካታው ሕዝብ ገቢ ጋር ሲመዘን ውድ አይደለም ለማለት አይደልም። ዋጋም ሆነ ጥራት ካለው አቅርቦትና አማራጮች ጋር ነው የሚመዘነው። ውይይቱ ለምን ወላጆች የመንግሥትን ትምህርት ቤቶች ጠሉ ከማለት ይልቅ፣ የግል ትምህርት ቤቶችን ወደመኮነን ያዘነበለ ነበር። 

ከዚህም አልፎ የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ  ባለሥልጣናትም በተከኩራራ መንፈስ ስለዘጉዋቸው ትምህርት ቤቶች ሲዘርዝሩ የታዘብኩት የግል ትምህርት ቤቶች ለኢኮኖሚውም በብዙ ቢሊዮን ብር በጅት ለመንግሥት እየደጎሙ፣ የተሻለ የትምህርት ሥርዓት እንዲኖር እያደረጉ ስላለው ጥቅም በደንብ እንዳልተገነዘቡ መረዳት ይቻላል። 

በትምህርት ሚኒስቴር መረጃ መሠረት 498 የመንግሥት ትምህርት ቤቶች በአዲስ አበባ ሲኖሩ፣ 1,728 የግል ትምህርት ቤቶች አሉ። ይህ እንግዲህ ከ20 ዓመታት በፊት  ጥቂት ከነበሩት የግል ትምህርት ቤቶች ተነስተው 1,728 ደርሰዋል። በአዲስ አበባ ከ900,000 ሺሕ በላይ ተማሪዎች አሉ። ከእነዚህ ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ልጆች የሚማሩት በግል ትምህርት ቤቶች ነው።

ይህ ደግሞ የግል ትምህርት ቤቶች ትልቁን ሸክም ከመንግሥት ተረክበው በብዙ ቢሊዮን ብር በጀት እያዳኑለት ነው። 

የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ እንዳይመዘግቡ አዝዣለሁ ካላቸው ትምህርት ቤቶች መካከል አንዳንዶቹን አውቃለሁ። እነዚህ ትምህርት ቤቶች በርካታ ወላጆች ልጆቻቸውን ለማስገባት ብዙ የሚደክሙባቸው፣ ልጆቻቸው የትምህርት ቤቶቹን የመግቢያ ፈተና እንዲያልፋ ምን ያህል እንደሚደክሙ አውቃለሁ። ከእነዚህ ውስጥ የጊብሰን አካዳሚን ለምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል።

እነዚህ እንዲዘጉ አዘናል ያሉዋቸው ትምህርት ቤቶች የጥራት ችግር ስላለባቸው ነው የሚለውን ብዙ ወላጅ ለመቀበል ይከብደዋል። 

የግል ትምህርት ቤቶችን የመንግሥት ካሪኩለምና የመንግሥት መጻሕፍት በግድ ተከተሉ ማለቱም ስህተት ነው። ብዙ ወላጅ ከመንግሥት ካሪኩልም ውጪ የግል ትምህርት ቤቶች የሚሰጡዋቸውን ተጨማሪ ትምህርቶች በመፈለግ ነው ወደ ግል ትምህርት ቤቶች የሚልኩት። 

ዛሬ ወላጆችን ለምን የግል ትምህርት ቤቶች ልጆቻችሁን ታስገባላችሁ ተብለው የቃለ መጠይቅ ዳሰሳ ቢደረግ የሚከተሉትን ዋና ዋና ምላሾች የሚሰጡ ይመስለኛል።

በመንግሥት ትምህርት ቤቶች የሚሰጠው ትምህርት ጥራቱ ወርዷል፣ ለልጆቻችን በግል ክትትል አይደረግም፣ ልጆቻችን ለሚገጥማቸው ዓለም አቀፋዊ ፋክክር ብቁ አያደርጋቸውም፣ ቋንቋ በራሱ ግብ ባይሆንም ትልቅ የዕውቀትና የሐሳብ መገልገያ መሣሪያ ነው። የመንግሥት ትምህርት ቤቶች ቋንቋን ማስተማር ቀርቶ በልኩ ማንበብና መጻፍንም በውሉ አያስተምሩም፣ ካሪኩለሙም ጊዜ ያለፈበት ነው፣ መጻሕፍቱም ለእኔ ልጅ መማርያ በሚል መንፈስ ሳይሆን ለሰፊው ሕዝብ ልጅ ‹‹ተደራሽነት›› ተብለው በግብር ይውጣ የተዘጋጁ በመሆናቸው፣ ከቃላት ግድፈት ጀምሮ እስከ ‹‹ራስ ዳሸን›› ግድፈት ይዘው ስለሚታተሙ ነው፣ የማሰብ ችሎታን ከማዳበር ይልቅ በቃል ጥናት ላይ የቆሙ ናቸው የሚሉ ይመስለኛል። 

ይህ እምነት ባለበት ሁኔታ የትምህርት ቢሮ ኃላፊዎች እኛ ትክክል ነን ከሚሉ ረጋ ብለው ከግሉ ትምህርት ቤቶች ጥንካሬ ቢማሩ፣ ካልሆነም ቢኮርጁ የመንግሥት ትምህርት ቤቶችን ተመራጭነትን ሊጨምሩ በቻሉ ነበር። ለዚህ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነው። 

ከግል ባንኮች በፊት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ብር ያስቀመጠ  ሰው ከዘጠኝ ሰዓት በኋላ ገንዘቡን ማውጣት አይችልም ነበር። ዘጠኝ ከሩብ የደረሰ ባንክ ተዘግቷል፣ ብር ቆጠራ ላይ ናቸው ተብሎ ነበር የሚመለሰው። የግል ባንኮች ተከፍተው እስከ ምሽቱ አንድ ሰዓት ድረስ ሲያስተናግዱ በኤቲኤም (ATM) እና በኮምፒዩተር  ኔትወርክ  ተገልጋይ ሲያበራክቱ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዘጠኝ ሰዓቱ ብር ቆጠራ አልተከበረም ብሎ የግል ባንክ ዕድገትን አላደናቀፈም። ይልቁንም የግል ባንኮች ያስተዋወቁዋቸውን አሠራሮችና ቴክኖሎጂዎች በመተግበር ፈጣን ዕድገት ለማምጣት ሠራ። ውጤቱም እየታየ ነው። በግል ባንክ የሚሰጥ አገልግሎቶች ሁሉ በንግድ ባንክ አሉ። ይህ ፉክክር ለባንኮች ዕድገት ምክንያት ሆኗል። 

የግል ትምህርት ቤቶች በወላጅ ተመራጭ ያደረጉዋቸው ብዙ ነገሮች አሉ። የትምህርት ቢሮ ኃላፊዎች ከማማ ላይ ሆነው ትልቅ ዱላ ይዘው የፖሊስ ሥራ ላይ ከሚያጠፉ፣ ከማማው ወርደው በጣት ይቆጠሩ የነበሩት የግል ትምህርት ቤቶች ለምን ዛሬ ወደ 1,500 ትምህርት ቤቶች መድረስ ቻሉ ብለው ቢጠይቁ፣ አማካሪ ቀጥረው ቢያስጠኑ፣ ቃለ መጠይቅና የዳሰሳ ጥናት ቢያደርጉ ጠቃሚ ትምህርት መማር በቻሉ ነበር።

ባለፋት አሠርት ዓመታት በርካታ የግል ትምህርት ቤቶች ተከፍተዋል። በ2007 ዓ.ም. በወጣ መረጃ 1,671 ትምህርት ቤቶች በአዲስ አበባ ብቻ ነበሩ። በአዲስ አበባ ወደ 900,000 ተማሪዎች አሉ። ከእነዚህ ተማሪዎች ከግማሽ በላይ የሚሆኑት በግል ትምህርት ቤቶች ይማራሉ።

የዚህ ጥቅም ደግሞ ለእነዚህ ሁሉ ተማሪዎች መንግሥት ትምህርት ቤቶች ገንብቶ፣ አስተማሪ ቀጥሮ፣ የማስተማሪያ መሣሪያዎች አቅርቦ ማስተማር ግዴታው ነበረ። በተጨማሪ እዚህ አገር ወደ 2.6 ሚሊዮን የሚደርሱ ልጆች በየዓመቱ ይወለዳሉ። ለእነዚህ ሁሉ ትምህርትን ማዳረስ ግዴታው ነው። ይህ ቢያንስ ቢያንስ 52,000 አዳዲስ ክፍሎች በዓመት መገንባት አለበት። ይህ ለአንደኛ ክፍል ተማሪዎች ብቻ ነው። ይህም በአንድ ክፍል ውስጥ 50 ልጆች ቢማሩ ብለን ካሰላነው ነው። በአደጉት አገሮች አንድ አስተማሪ ለእያንዳንዱ ተማሪ ትኩረት ሰጥቶ ክትትል እንዲያደርግ በክፍል ውስጥ ከ30 ተማሪዎች በላይ አይመደብም።

ስለዚህ በክፍል 50 ተማሪ ብለን ካሰብን 52,000 የመማሪያ ክፍሎች ለአንደኛ ክፍል ተማሪዎች ብቻ መገንባት አለባቸው። በተጨማሪም 52,000 መምህራን ለአንደኛ ክፍል መቅጠር አለበት። የአንድ አስተማሪን ደመወዝ፣ ጡረታና ጥቅማ ጥቅሞችን አስበን በ2,500 ብር ብለን ብናሰላ  ለአንደኛ ክፍል አስተማሪዎች ብቻ መንግሥት 130 ሚሊዮን ብር በወር ወይም 1.56 ቢሊዮን ብር በዓመት ያስፈልገዋል። 

የኢትዮጵያ የ2008 ዓ.ም. ጠቅላላ የትምህርት የዓመት በጀት 38.9 ቢሊዮን ብር ነበር። ከላይ የተጠቀሰው 1.56 ቢሊዮን ብር የአምናውን በጀት አራት በመቶ ነው። አራት በመቶ ለአንደኛ ክፍል አስተማሪ ብቻ ከዋለ ለትምህርት ቤት ግንባታ፣ ለመማሪያ ግብዓትና ሥልጠና ሲጨመር ብዙ ቢሊዮን ይደርሳል።

የግል ትምህርት ቤቶች ባይኖሩ ኖሮ የመንግሥት በጀት የግድ ማደግ ነበረበት ወይም አገልግሎቱን መቀነስ ግድ ይሆን ነበር።

ግብር (ታክስ) ከፋዩ ቤተሰብ ግን ግብር በከፈልኩበት ትምህርት ቤት ውስጥ ጥራት ያለው ትምህርት አይሰጥም፣ ልጆቻችን በአገርም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ሊያደርጋቸው አይችልም  ብለው ባያምኑ ተጨማሪ ወጪ ከፍለው የግል ትምህርት ቤቶች አያስገቡም ነበር። 

ለዚህ ነው በአዲስ አበባ ብቻ 1,671 የግል ትምህርት ቤቶች ሊኖሩ የቻሉት።  ለጊዜው የግል ትምህርት ቤቶች በጀት ምን ያህል እንደሆነ መረጃ በእጄ ባይኖርም፣ የግል ትምህርት ቤቶች ለተማሪ  በወር 300 ብር ያወጣሉ ብለን ብናሰላ ወደ 1.5 ቢሊዮን ብር የሚገመት የመንግሥትን ወጪ እየሸፈኑ ነው። 

ይህ ማለት ለመንግሥት ከሚከፍሉት የትርፍ ግብር፣ የሠራተኛ ደመወዝ ግብርና የመገልገያ ዕቃዎች ቫት ክፍያን ሳይጨምር መንግሥት በዓመት ከ1.5 ቢሊዮን ብር በላይ ለአዲስ  አበባ ተማሪዎች መመደብ ነበረበት። ይህ ማለት የግል ትምህርት ቤቶች ለመንግሥት የዚህን ያህል ቀጥተኛ ድጎማ እያደረጉ ናቸው።

በዚህ ላይ ለ1,500 ትምህርት ቤቶች መገንቢያ፣ ለመምህራን ደመወዝ፣ ለአስተዳደርና ለትምህርት መገልገያዎች አቅርቦት በዓመት ያወጣ የነበረውን ከደመርን ደግሞ የግል ትምህርት ቤቶች ብዙ ቢሊዮን ብር አስተዋጽኦ የሚያደርጉ  ይመስለኛል።

የግል ትምህርት ቤቶች አስተዋጽኦ በኢኮኖሚው ላይ ዝርዝር ጥናት የሚጠይቅና ለድኅረ ምረቃ የኢኮኖሚክስ ተማሪዎች ጥሩ የመመረቂያ ጥናት ሊሆን ይችላል።

አንዳንድ የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ባለሥልጣናት ቃለ መጠይቆችን ሳዳምጥ ግን ትልቅ የግንዛቤ ችግር እንዳለባቸው ይታያል። ከሥልጣን ማማ ላይ ሆኖ ቁልቁል እያዩ ዘጋነው፣ ከለከልነው፣ ማስጠንቀቂያ ሰጠነው ሲሉ ነው የሚሰሙት።

መገንዘብ ያልቻሉትና ሊረዱት የከበዳቸው ነገር መንግሥት በየዓመቱ ከሃምሳ ሺሕ በላይ ክፍሎችን እያዘጋጀ ትምህርት ቤቶችን መክፈት አቅም የለውምም፣ አይኖረውም። የግል፣ የኮሙዩኒቲ፣ የሃይማኖት፣ የበጎ አድራጎት ትምህርት ቤቶች እንዲስፋፉና ሽክሙን እንዲጋሩለት ማግባባትና ማሳመን እንጂ፣ መጥረቢያውን ይዞ መመንጠሩ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚና አቅም ካለመረዳት የመጣ ነው።

ይህ በበርካታ ቢሊዮን ብር የሚገመት ሸክም ከመንግሥት ትከሻ ላይ ያነሳን የኢኮኖሚ ዘርፍ ማዳከሙ ትክክል አይደለም። ይልቁንም መረዳት ያለበት የኢኮኖሚ ክፍል ነው።

ከላይ እንዳየነው የኢትዮጵያ ሕዝብ ትምህርት ቤት ለማሠሪያና ለሌሎች ማኅበራዊ መገልገያዎች ግብር (ቀረጥ) ይከፍላል፡፡ በእዚህም ገንዘብ  አስተማሪ፣ አስተዳዳሪ፣ ሚኒስቴር ቀጥሮ በመሠረታቸው ትምህርት ቤቶች ውስጥ በነፃ ልጆቹን ከማስተማር ይልቅ ለምን በጣም ውድ በሆኑ፣ ተቸግሮ ለተጨማሪ ወጪ ተዳርጎ  በግል ትምህርት ቤት ውስጥ ለማስተማር መረጠ የሚለውን ጥያቄ የትምህርት ቢሮ ኃላፊዎች ቢመልሱ፣ ለተነሱት ችግሮች ሁሉ መፍትሔው ግልጽ ብሎ ይታይ ነበር። 

አባቶቻችን ‹‹የራሷ እያረረባት...›› የሚሉት አባባል አለ። በአዲስ አበባ ብቻ ከ1,671 የግል ትምህርት ቤቶች በ2007 ዓ.ም. ነበሩ። ዘንድሮ በተደረገው ቆጠራ ቁጥራቸው ቀንሷል፡፡ ይህም የትምህርት ቢሮዎች ስላላደሱላቸው ወይም ጠንካራ ፉክክር ከገበያው ስላስወጣቸው ይሆናል። 

ደግሞ ደጋግሞ መጠየቅ ያለበት ሁላችንንም ያስተማረ፣  በርካታ ምሁራንን ያፈራ፣ በበለፀጉት አገሮች ሳይቀር ሄደን ተወዳዳሪ እንድንሆን ያስቻለን የመንግሥት ትምህርት ቤትና ካሪኩለም ለምን ወላጆች ጠሉት ብለን ብንጠይቅ ምናልባትም  ብቃት በሌላቸው ባለሙያዎች በመመራቱ፣ ከጥራት ይልቅ ለፖለቲካ መጠቀሚያ የሚውል የተማሪ ቁጥርን እንደ ግብ በማድረጉ፣ የትምህርት ጥራት ወረደ የሚባል ይመስለኛል። 

በርካታ ወላጆች የመንግሥት ትምህርት ቤቶች ለልጆቻቸን በቂ አይደሉም፣ ልጆቻቸው ወደፊት ለሚገጥሙዋቸው ፉክክሮች ለማዘጋጀት ብቁ አይደሉም ብሎ በማመናቸው ምክንያት፣ ልጆቻቸውን ይዘው ወደ ግል ትምህርት ቤት መሰደድ መረጡ።  ወደው ሳይሆን የልጆቻቸውን ተስፋ ከጅምሩ ላለማጨለም ሲሉ ነው። 

ከፖሊሲ አውጪ መሪዎች ጀምሮ እስከ አስፈጻሚው የትምህርት ሚኒስቴር ባለሥልጣናት ድረስ ‹‹ጥራት ሳይሆን ተደራሽነት ነው›› በሚል ፍልስፍና ታጥረው የትምህርት ጥራት ወደቀ። በትውልድ ላይ ቤተ ሙከራ ሲካሄድ ያየ ሁሉ ልጆቹን ለማዳን እግሬ አውጭኝ አለ።

‹‹ተደራሽነትና ጥራት›› የተነጣጠሉና በአንድ ላይ መሄድ አይችሉም የሚለው ጽንሰ ሐሳብ ከየት እንደተቀዳ አላውቅም። ጥራት ማለት ችግር የሌለበትና የተገልጋዩን ፍላጎትን የሚያሟላ ወይንም ከተገልጋዩ ፍላጎት በላይ ሆኖ የሚገኝ ማለት ነው። “Meeting and Exceeding Customer Expectations” ወይም “Fitness for Intended use” ለምሳሌ “iPhone 1” እና “iPhone 7” አንድ አይደሉም። 

ይህ ማለት ግን የመጀመሪያው “iPhone” ከነበሩት ሁሉ ስልኮች በጣም የበለጠ ነበር። ይህም የኖክያ (Nokia, Motorola etc) ከነበረው ተገልጋይ ፍላጎት ከፍ ብሎ በመገኘቱ ተመራጭና የጥራት ተምሳሌት ሆነ።  “iPhone 7” በዚያ ዘመን ቢታወቅ ኖሮ “iPhone 1” መሳቅያ በሆነ ነበር።

የኢትዮጵያ ትምህርት ‹‹ወደቀ›› ሲባል ከነበረውም ወረደ ማለት ነው። በተለይም ነባርና ክግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ባስቆጠሩ የአዲስ አበባን ትምህርት ቤቶች ማለት ነው። 

አትዮጵያ ዘመናዊ ትምህርት ከጀመረች 100 ዓመታት አለፉ። እኛ በመምህራን ማሠልጠኛ ምሩቃን መምህራን ነው የተማርነው፡፡ አስተማሪዎቻችን 8ኛ እና 10ኛ ክፍል ያጠናቀቁ ነበሩ፡፡ ዛሬ ዲፕሎማ፣ ዲግሪ፣ ማስተርስ ባላቸው መምህራን የተሞላ ነው፡፡ ቲቪ፣ ኢንተርኔት ባለበት ዘመን የመንግሥት ትምህርት ቤቶች በቅጡ ማንበብና መጻፍ የማይችሉ ተማሪዎች የሚያፈሩት ‹‹በተደራሽነት›› ምክንያት ነው ማለት፣ የአመራሩን ስንፍና ለመሸፍን የሚደረደር ምክንያት ነው።  

ትናንት የቄስ ትምህርት ቤቶች ይወጡት የነበሩት ማንበብና መጻፍ፣ 38.9 ቢሊዮን ብር በጅት የተመደበላቸው የመንግሥት ትምህርት ቤቶች መተግበር እየተሳናቸው ነው የሚል ግንዛቤ ላይ ስለተደረሰ ነው። 

ችግርን ከመጋፈጥ ይልቅ በካድሬ ቋንቋ ‹‹ተደራሽነት›› ማመካኛ ሆነ። እያንዳንዱ ልጅ ለቤተሰቡ ብርቅዬ ነው፣ መተኪያ የለውም። ግድ የለም ይህ ቤተ ሙከራ በልጄ ላይ ይካሄድና ውጤቱን ልይ አይልም? 

ስለዚህ አማራጭ በማጣት ቤተሰቦች ልጆቻቸውን  ይዘው እግሬ አውጪኝ አሉ፣ የግል ትምህርት ቤቶችን አጨናነቁ፡፡ የቻለ ውድ ዋጋ ከፍሎ፣ ያልቻለም ደግሞ ሆዱን አስሮ የልጆቹ ተስፋ ከጅምሩ እንዳይጨልም ወደ ግል ትምህርት ቤቶች ተሰደደ፡፡ ይህም  በኤፍኤም ሬድዮኖች ላይ የተነሱት የግል ትምህርት ቤቶች ችግሮች ተጋለጡ። ውድ ናቸው፣ ትክክል። በመንግሥት መጽሐፍ አያስተምሩም። ለምን ያስተምሩ? ቤተሰብ የተሻለ ነገር ፍለጋ አይደለም እንዴ በግል ትምህርት ቤት የሚያስተምረው? ውጤታማ ናቸው? አዎ። መንግሥት ራሱ ከግል ትምህርት ቤት ወደ ዩኒቨርሲቲ የመግቢያ ነጥብ ከመንግሥት ትምህርት ቤቶች በላይ ያደረገው የመንግሥት ትምህርት ቤቶችን ችግር ስለተረዳ ነው። 

በአዲስ አበባ ብቻ 1,671 የግል ትምህርት ቤቶች ቢኖሩም ፍላጎት ከአቅርቦት ጋር አልተጣጣመም፡፡ ወላጆች ለትምህርት ያልደረሱ ልጆቻቸውን አስተማሪ ቀጥረው የግል ትምህርት ቤቶችን የመግቢያ ፈተና እንዲያልፉ ማስጠናት፣ በዕውቅናና በአማላጅ ጭምር ሲለማመጡ ነው የሚታየት።

የአዲስ አበባ የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዲላሞ ኦቴሮ ልጃቸውን በግል ትምህርት ቤት እንደሚያስተምሩ በFM 97.1 ላይ ገልጸዋል።  ይህ ደግሞ አስገርሞኛል። ጋዜጠኛው አቅም ቢኖረው ለምን ብሎ መጠየቅ ነበረበት። ለዚህ ሁሉ የዳረገንን ችግር መልስ በሰጡን ነበር። ይኼም ባለሥልጣኑን ጨምሮ በርካታ ሕዝብ የመንግሥት ትምህርት ቤቶች ልጆችን ብቁ ማድረግ አይችልም የሚለው ግንዛቤ ማስረጃ ነው።

ቶኒ ብሌር የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚንስትር ከሚኖሩበት አካባቢ አርቀው በውጤታማነቱ በሚታወቅና (በማይከፈልበት) የሕዝብ ትምህርት ቤት ልጃቸውን በማስገባታቸው ምን ያህል ወቀሳ እንደደረሰባቸው ትዝ ይለኛል።

ሁሉም ጋዜጦችና ፖለቲከኞች የተስማሙበት ቶኒ ብሌር የሚመራው ትምህርት ቤቶች ለልጁ በቂ ካልሆኑ እንዴት ለእኛ ልጆች ብቁ ይሆናሉ። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ኃላፊነት ሁሉንም ትምህርት ቤቶች  ለሁሉም ልጆች ብቁ ማድረግ አይደለምን የሚሉ ነበሩ። ይህ ለልጁ ትምህርት ቤት መረጣ ግብዝነት ነው የሚል ትችትና ተጠያቂነት ነው። ቶኒ ብሌር የሌበር ፓርቲ መሪ ሆነው በግል ትምህርት ቤት ቢሆን ልጃቸውን የሚያስተምሩት ትልቅ ተቃውሞ በተቀሰቀሰ ነበር። ለሕዝብ፣ ለሠራተኛው፣ ለግራ ዘመም፣ ለአብዮታዊ ዲሞክራት ነኝ ለሚል ትውልድ ደግሞ የትልቅ ግብዝነት ባህሪው መገለጫ ሐውልት ነው።

የኢትዮጵያ ግን የተለየ ነው። የትምህርት ቢሮዎቹ ኃላፊዎች እንኳን ሳይቀር በሚመሩት ትምህርት ቤቶች እምነት የላቸውም። ለዚህም ነው ትምህርት የወደቀው።

እ.ኤ.አ. በ1965 የተመረጠው የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ሐሮድ ዊልሰን ለትምህርት ሚኒስቴር ያጨውን ሮይ ጄኪንስን ጠርቶ ለትምህርት ሚኒስትርነት ሲሾመው፣ ሮይ ጄኪንስ ‘ይቅርታ እኔ ልጆቼን በግል ትምህርት ቤቶች እያስተማርኩ ስለሆነ ለዚህ ኃላፊነት ብቁ አይደለሁም’ ማለቱ እስካሁን ይጠቀሳል። በዴሞክራሲ አገሮች ፖለቲከኞች በሚመሩትና በሚሰብኩት የፐብሊክ ሰርቪስ የማይመጥናቸው ከሆነ፣ ከፖለቲካ ውጪ በርካታ ሙያ መምረጥ አለባቸው የሚል ያልተጻፈ ሕግ አለ። ለዚህም ነው ቶኒ ብሌር ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው፣ ባለቤታቸው ደግሞ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሚቆሙ የሕግ ጠበቃ ሆነው በአገሪቱ ውድ ትምህርት ቤት ማስተማር ሲችሉ፣ የብሌርና ሼሪ ብሌር ልጆች ወደ መንግሥት ትምህርት ቤት የተላኩት። 

የአገራችን የግል ትምህርት ቤቶች ውድ ናቸው፣ ብዙም ችግር አለባቸው። ግን አማራጬ ደግሞ የባሰ ሆነ። ይህ ደግሞ ለብዙ ቤተሰብ ውድድር ውስጥ የማይገባ  ፈተና ነው።

የመንግሥት ፖሊሲ በፈጠራቸው ችግርች ምክንያት  ከተፈጠሩ የግል ትምህርት ቤቶች ትርፍ ተካፋይ ብቻ ሳይሆን፣ ለእነዚህ ሁሉ የግል ትምህርት ቤት ተማሪዎች ትምህርት ቤት ሠርቶ፣ አስተማሪ መድቦ፣ ቾክና መጽሐፍ ለማቅረቢያ ይውል የነበረውን በቢሊዮን የሚቆጠር በጀት ያድናል። በዚህም ሸክሙን ያቃለለትን የግል ትምህርት ቤቶች ሲያመሰግን አይታይም።

ለዚህም ነው ጥያቄው ለምን የመንግሥት ትምህርት ቤቶች ተመራጭ አልሆኑም ወደሚለው መመለስ አለበት። ከዚያም የመንግሥት ትምህርት ቤቶች ከግል ትምህርት ቤት ምን መማር ይገባቸዋል መባል አለበት።

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የዋይ ኤች ኤም የማማክር ሥራ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው YarHM@aol.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

Betty የግብፅ ከዘመነ የቅኝ ግዛት መስፋፋት ወደ ዘመነ ዓባይ ፍርኃት መሸጋገር

$
0
0

ኢትዮጵያ ረጅም ታሪክ ያላት አገር ነች፡፡ ዘወትር እንደምንሰማውና በተለያዩ ድርሳናት ተጽፎ እንደምናገኘው 3,000 ዓመታትን ያስቆጠረች የዕድሜ ባለፀጋ ነች፡፡ በዚህ የዕድሜ ዘመኗ ብዙ የታሪክ ሁነቶችን አስተናግዳና ተሻግራ ዛሬ ላይ ደርሳለች፡፡ በብዙ የትውልድ ቅብብሎሽ እዚህ ላይ የደረሰችው አገራችን ብዙ ፈተናዎችንና ጋሬጣዎችንም ተሻግራለች፡፡ እንደ አገር ከተመሠረተች ጀምሮ እስከ 20ኛው ክፍለ ዘመን መገባደጃ ድረስ በየአካባቢው ይነሱ የነበሩ የጐሣ መሪዎችና ገዥዎች ከሌሎች አካባቢ መሪዎች ጋር ያደርጉት ከነበረው የእርስ በርስ ጦርነት ባሻገር፣ የውጭ ኃይሎች በተደጋጋሚ ጊዜ ለመውረር ሙከራ ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ ከእነዚህ የውጭ ኃይሎች መካከል አንዷ ግብፅ ነች፡፡

ግብፅ ኢኮኖሚዋ በዓባይ ወንዝ የተመሠረተና በሲናይ በረሃ ታጅባ ህልውናዋን የምትመራ አገር ነች፡፡ በዘመነ ቅኝ ግዛት መስፋፋት ጊዜ የራሷን ግዛት ለማስፋፋት ሙከራዎችን ያደረገች አፍሪካዊት አገርም ነች፡፡ ከስዊዝ ቦይ መከፈት ማግሥት ጀምሮ ኢኮኖሚዋን በንግድና በቴምር ምርት እያፈረጠመች የመጣችው የዓረብ ሊግ አባሏ አገር ግብፅ፣ አሁን ከዓረብ አገሮች የተሻለ ኢኮኖሚ መፍጠር ችላለች፡፡ ግብፅን ከአመድ ያነሳት እየተባለ በሚጠራው ንጉሷ ኬዲቭ እስማኤል አማካይነት ብዙ ዘመናትንና የታሪክ ገድላትን አሳልፋ እዚህ ላይ የደረሰችው ግብፅ የግዛት መስፋፋት ስታስብ ቅድሚያ የመጣላት የኢትዮጵያ ጉዳይ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ በወቅቱ ብዙ ፈተናዎች የተጋረጡባትና የተረጋጋች አገር እንዳልሆነች በመገንዘብ ግብፅ ፊቷን ወደ ኢትዮጵያ አዙራለች፡፡

የኢትዮጵያ ንጉሥ ካሣ ኃይሉ (በንግሥና ስማቸው ዳግማዊ ቴዎድሮስ) ዘመናዊ ኢትዮጵያን ለመገንባት ሲታትሩ በነበረበት ወቅት ትልቅ ፈተና ከሆኑባቸው መካከል አንዱ የግብፅ ጉዳይ ነበር፡፡ የሞሐመድ ዓሊ ጦር ከካሣ ጋር ተዋግቶ ድል ሲሆን ግብፅ ሠራዊቷን በጋላባትና በመተማ አድርጋ ኢትዮጵያን የመውጋትና የማተራመስ ስትራቴጂ ቀይሳ ጦሯን ሰብቃ፣ ጋሻዋን መዝዛ ወደ ኢትዮጵያ አቀናች፡፡ በወቅቱ ኢትዮጵያ ውስጥ ከውጭው አደጋ ይልቅ ውስጣዊ የሥልጣን ትግል ይበልጥ ክብደት የሚሰጠው ስለነበር የግብፅን ሠራዊት ለመመከት አስቸጋሪ ሆኖ ነበር፡፡ ግብፅ ያኔ እንደ አሁኑ የዓባይ ጉዳይ ሳይሆን የሚያሳስባት የቅኝ ግዛት ማስፋፋት ጉዳይ ነበር፡፡ በቀይ ባህር በኩል ያላትን ኃያልነትና ተሰሚነት ከፍ ማድረግ፡፡ በተለይ ይህ ሥጋት በከፍተኛ ሁኔታ ሊያሳስባት የቻለው ዳግማዊ ቴዎድሮስ በ1855 ‹‹የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት›› ተብለው ዘውድ ከደፉ በኋላ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ በአካባቢው የሚኖራትን ኃያልነትና ተሰሚነት በመፍራት የታቀደ ዘመቻና ወረራ ነበር፡፡ በዚህም ከኢትዮጵያው ንጉሥ አፄ ቴዎድሮስ ጋር ተፋልመው ከፍተኛ ኪሳራ ደርሶባቸዋል፡፡

ግብፅ ከኢትዮጵያ ጦር ጋር ባካሄደችው ዘመቻ ከፍተኛ ኪሳራ እንደደረሰባትና በድል ልታጠናቅቅ እንደማትችል ስታውቅ ከንጉሡ በታቃራኒ የቆሙ የአካባቢው መሪዎችን መደገፍና ማስታጠቅ ጀመረች፡፡ ኢትዮጵያን እርስ በርስ የማተራመስ ስትራቴጂ የጠነሰሰችው እንግዲህ ከዚህ ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡

በዮሐንስ 4ኛ ዘመነ መንግሥት ጊዜም በኢትዮጵያ ላይ ቀጥተኛ ጦርነት አውጃለች፡፡ በዳግማዊ ቴዎድሮስ ጊዜ የተከተለችው ፖሊሲና ስትራቴጂ አዋጭ እንዳልሆነ ስታወቅ ራሷን ገለል አድርጋ የቆየችው ግብፅ በዮሐንስ 4ኛ ጊዜም ሌላ ጦርነት ከፍታለች፡፡ እስከዚህ ዘመን ድረስ ግብፅ ዓባይን ፈጣሪዋ ለሷ ብቻ ብሎ የፈጠረው ስጦታ አድርጋ በመውሰድ በዚህ ላይ የይገባኛል ጥያቄ ይነሳል ከሚል ፍርኃት ሳይሆን፣ አሁንም የግዛት ማስፋፋት ከነበራት ጉጉት የመነጨ ነበር፡፡ ለውጭ ጠላት መቼውንም እጅ ሰጥቶ የማያውቀው የኢትዮጵያ ጦር ግን በሁለት የጦር አውድማዎች ላይ የግብፅን ወታደር አመድ አደረገው፡፡ በ1875 በጉንደትና በ1876 በጉራ የጦር አውድማዎች ላይ፡፡

በታሪክ ግብፅና ኢትዮጵያ ይህን የመሰለ መስተጋብር ፈጥረው አልፈዋል፡፡ የጠቡና የግጭቱ መንስዔ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ግብፅ ነበረች፡፡   

የስዊዝ ካናል መከፈት ያስፈነጠዛቸው ኬዲቭ እስማኤል በምሥራቅ አፍሪካ የሚኖራቸውን ኃያልነት በህልማቸው ብቻ እንዳዩት አረፉ፡፡

የግብፅና የኢትዮጵያ ግንኙነት በዚህ ሁኔታ ከተቋጨ በኋላ እንደገና የሚያገረሸው ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ነው፡፡ በብዙ ምሁራን ዘንድ የኢትዮጵያ ሦስቱ አዕማድ ተብለው የሚጠሩ ጉዳዮች ማለትም ተፈጥሮ፣ ሃይማኖትና ታሪክ ተስማምተው ከሚኖሩባት አገር ውስጥ ተፈጥሮአዊ ስጦታችን የሆነውን ዓባይ ባነሳን ጊዜ የተፈጠረው እሰጥ አገባ ነው፡፡ ይህም ግብፅ ‹‹ከዘመነ የቅኝ ግዛት መስፋፋት ወደ ዘመነ ዓባይ ፍርኃት የተሸጋገረችበት ዘመን ነው›› ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡

ምንም እንኳ ግብፅ በዙሪዋ የሲናይ በረሃ የከበባትና ካለ ዓባይ ሌላ ህልውና እንደሌላት ቢታመንም፣ ‹‹ብቻዬን ልጠቀም›› የሚለው አመለካከቷና ፍላጐቷ በኢትዮጵያ አገራችን እንደተሻረ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ የሁለቱ አገሮች ሌላኛው የታሪክ ገጽታም የሚጀምረው ከዚሁ ነው፡፡ ግብፅ የነበራትን በሰሜኑ የአገራችን ክፍል የቅኝ ግዛት የማስፋፋት ፖሊሲ ሽራ በሰላም መኖር ከጀመረች ከብዙ ዓመታት በኋላ ያገረሸች አገር ሆናለች፡፡ የዓባይ ጉዳይ ሲነሳ የራስ ምታቷ ይጨምራል፡፡ የደም ፍላቷ ያይላል፡፡ ለዚህም ማሳያ ሊሆን የሚችለው ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ኢትዮጵያ ዓባይን ለመገደብ በተንቀሳቀሰችበት ወቅት አገራችንን ለማተራመስ ለኤርትራ ታደርገው በነበረው የደኅንነትና የወታደራዊ ሎጀስቲክስ ድጋፎች ታይቷል፡፡ ይህ ድጋፍ ግን ጐልቶ የወጣው ኤርትራ ከኢትዮጵያ ለመገንጠል ታደርገው በነበረው እንቅስቃሴ ጊዜ ነው፡፡

በእነ ዑስማን ሳልህ ሳቤ አማካይነት ግብፅ ኤርትራን እንደ ዶሮ ጫጩት ፈልፍላ ካሳደገች በኋላ ራሷን አፍሪካዊት ሲንጋፖር ለማድረግ ያቀደችው ዕቅድ አልተሳካም፡፡

ሻዕብያ ውስጥ ያደፈጠው የግብፅ የደኅንነት ቡድን ከኤርትራው ድሉ በኋላ ለሁለተኛና ለመጨረሻ ጊዜ ኢትዮጵያን የማተራመሱ አጀንዳ ኦሮሚያ ውስጥ የተወለደውና ራሱን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ብሎ የሚጠራውን ቡድን በማስታጠቅና በመደገፍ ነው የጀመረችው፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነን የሙርሲ መንግሥት ራሱን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ብሎ የሚጠራውን ቡድን መደገፍና ማስታጠቅ አንደኛው መፍትሔ እንደሆነ፣ በብሔራዊ ቴሌቪዥናቸው ለሕዝባቸው ያስተላለፉትን መልዕክት መውሰድ ይቻላል፡፡ እንግዲህ በዚህ ጊዜ የተደራጀው ኃይል ነው ዛሬም መቀመጫውን ግብፅ አድርጐ ኢትዮጵያን ለማፈራረስ ሌት ከቀን የሚሠራው፡፡

ምንም እንኳ ኢትዮጵያ የብዙ ብሔር ብሔረሰቦች መኖሪያ አገር ብትሆንም፣ ተቻችሎ የመኖርና የመፈቃቀር ባህላችን ዓለም ያወቀው ፀሐይ የሞቀው ጉዳይ ነው፡፡ በያኔው ዘመን እንኳ ውድ አባቶቻችን ለውጭ ጠላት አገራቸውን አሳልፈው አልሰጡም፡፡ ሚስጥራቶቿንም አላባከኑም፡፡ የውስጣቸውን ችግር በራሳቸው ነበር የሚፈቱት፡፡ ይህንን ነው ከአያትና ከቅድመ አያቶቻችን የተማርነው፡፡ ይህንን ነው ከአያትና ቅድመ አያቶቻችን የወረስነው፡፡ ይህንን ነው ከአያትና ቅድመ አያቶቻችን የቀሰምነው፡፡

በአሁኑ ጊዜ ግን እየታየ ያለው ጉዳይ የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ዕድሉን ቢያገኙ የዓባይን ግድብ በአንድ ቀን አፍርሰው ከሚያድሩ አገሮች ጋር መደራደር፣ እከከኝ ልከክህ ማለት፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የፖለቲካ ሥልጣን እንድይዝ እጄም፣ እግሬም፣ ዓይኔም ሁነኝ፡፡ ላንተ ደግሞ የዓባይን ግድብ አፍርሼ ከሥጋት እገላግልሃለሁ የሚል ድርድር፡፡ በበኩሌ ‹‹የከሸፈ ትውልድ›› እንዳንባል ግን መጠንቀቁ አይከፋም እላለሁ፡፡

በእርግጥ በዘመነ ግሎባላይዜሽን ሁሉም ነገር በእጅ በደጅ በሆነበት ጊዜ አገሮች የደረሱበትን ደረጃ አይተን የራሳችንን አገር ኢኮኖሚና የዴሞክራሲ ከፍታ ስንመለከት ብዙ ጥያቄ የሚያስነሱ ጉዳዮች አሉ፡፡ ሥር የሰደደ ሙስና፣ በሥልጣን መባለግ፣ ኢ- ፍትሐዊ አሠራሮችና መድሎዎች፣ የሥራ ፈጠራ ዕድሎች ማነስ፣ የአሠራር ውስንነት፣ የአመራር ቁርጠኝነትና የአቅም ማነስ፣ ወዘተ. ችግሮች እዚህም እዚያም እየታዩ ነው፡፡ እነዚህን ችግሮች ደግሞ መንግሥት ‹‹ችግሬ ናቸው፣ አብረን እንፍታቸው›› ብሎ ባመነበትና በአደባባይ እየተናገረ ባለበት ወቅት የአገርን ደኅንነት አደጋ ላይ ሊጥል በሚችል ሁኔታ የአገር ውስጥ ተቃዋሚ ነን ባዮች ከውጭ አገር መንግሥት ጋር፣ ያውም በዓይነ ቁራኛ ከምታየን አገር ጋር ወዳጅነት መመሥረት የአባቶቻችንን ቃል መሻር ነው የሚሆነው፡፡ ለብዙ ሺሕ ዓመታት ማንነቷን ጠብቃ ዜጎቿ ተፈቃቅረውና ተቻችለው በኖሩባት አገር እንደ ሩዋንዳው የዘር ጭፍጨፋ እንዲከሰት የሚታትሩ  ትውልደ ኢትዮጵያውያን እዚህም እዚያም እየታዩ ነው፡፡

ግብፅም አንዴ ሞቅ አንዴ ለቀቅ ስታደርግ የነበረውን ኢትዮጵያን የማተራመስና መንግሥት አልባ የማድረግ ስትራቴጂ አሁንም እንደቀጠለችበት መረዳት ይቻላል፡፡ ምንም እንኳ በአሁኑ ጊዜ ግብፅ፣ ሱዳንና ኢትዮጵያ በዓባይ ግድብ ላይ ጥናት የሚያደርግ ቡድን አቋቁመው በተፋሰስ አገሮቹ ላይ የህዳሴው ግድብ የሚያሳድረውን ተፅዕኖ እያስጠኑ ቢሆንም፣ ከመድረክ በስተጀርባ ምን እየተከናወነ እንደሆነና ወደፊትስ ምን ሊከናወን እንደሚችል በቀላሉ መረዳት እንችላለን፡፡

የህዳሴው ግድብ ኢትዮጵያዊያን አሻራ ያረፈበት የማዕዘን ድንጋይ ነው፡፡ የተለያዩ ሐሳቦች እያነሳን ብንሞግትም፣ ውይይቶች ብናደርግም፣ ክርክራችን ቢጦፍም ዓባይን ግን ለድርድር ልናቀርበው የማይገባ አሻራችን መሆን አለበት፡፡ በዓባይ ጉዳይ ከሚሞግቱን አገሮች ጎን ተሠልፈን ጥቅማችንን ለርካሽ የፖለቲካ ሥልጣን ስንል አሳልፈን አንስጥ፡፡ ያኔ የአባቶቻችንን ቃል ጠበቅን ማለት ነው፡፡ ያኔ ‹‹እኛ እኮ ኢትዮጵያውያን ነን›› ብለን አፋችን ሞልተን መናገር እንችላለን ማለት ነው፡፡

ከአዘጋጁ፡-ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው Zemetenagnelove@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

መሠረታዊ የሐሳብ ገበያችን እንዳይፈርስ

$
0
0

ኢትዮጵያ ከራስ አሉላ አባ ነጋ እስከ ራስ ጎበና ዳጬ፣ ከፊታአውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ ዲነግዴ እስከ ፊታውራሪ ገበየሁ፣ ከራስ መኮንን እስከ አሚር አብዱላሂ፣ ከደጃዝማች ባልቻ ሳፎ እስከ ራስ መንገሻ ዮሐንስ፣ ወዘተ. ጀብዱ የሠሩ፣ ፍቅርንና አንድነትን ሰብከው ያለፉ ልጆች ባለቤት ነች፡፡ ኢትዮጵያዊነት የተገነባው በእነዚህ ዓይነት ግለሰቦችና አገር ወዳድ ሰዎች ነው፡፡ ዛሬ ኢትዮጵያ በፅኑ ዓለት ላይ የቆመች አገር ሆናለች፡፡ በቀላሉ የሚፈርስ ማንነት የላትም፡፡ ወደ ነፈሰበት የማትነፍስ፣ ወደ ተዛመመበት የማታጋድል ከብረት በጠጠረ ምሰሶ ላይ የቆመች አገር ነች፡፡፡ ፍቅር ሲሰበክባት የኖረች፣ አብሮ የመኖር ሚስጥር የተገለጠባት አገር፡፡

እዚህ ላይ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበሩት አብርሃም ሊንከን በአንድ ወቅት የተናገሩትን ብጠቅስ ከላይ ያሰፈርኩትን ሐሳብ የበለጠ ያብራራዋል ብዬ እገምታለሁ፡፡ ‹‹ለማንም ጥላቻንና ጥልን ሳናሳይ፣ ለሁሉም ፍቅርንና በጎነትን እንግለጽ… (“With malic to ward none, with charity for all”) የሚለውን ንግራቸውና ምክራቸው ‹‹ከተራራው የጌታ እየሱስ ስብከት ቀጥሎ የሰው ልጅ ያደረገው ትልቅ ንግግርና ምክር›› እየተባለ በአሜሪካውያን ዘንድ እስከ ዛሬ ድረስ ይሞካሻል፡፡ ዛሬ አሜሪካ ለደረሰችበት የዕድገት ደረጃ ለመድረስ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ይታመናል፡፡ በመሪያቸው ስብከት የተማረኩት አሜሪካውያን ጥልንና ፍርኃትን አስወግደው በፍቅርና በአንድነት ገመድ የተሳሰሩ ሕዝቦች ሆነዋል፡፡

ትናንትና የእኛ አያትና ቅድመ አያቶቻችን በፍቅር በመኖራቸው የአክሱምን ሐውልት አነፁ፡፡ የላሊበላን አብያተ ክርስቲያናት ከአንድ የድንጋይ ቋጥኝ ፈለፈሉ፡፡ የፋሲልን ግንብ አቆሙ፡፡ የጀጎልን ግንብ ለታሪክ አኖሩ፡፡ የሼክ ሁሴን ዓሊ መስጊድን አስረከቡ፡፡ ጠላትን በመጣበት እግሩ አባረሩ፡፡

ይህ ባልሆነበት ዘመን ደግሞ በአገራችን የዚህ ተቃራኒ ጉዳይ ተፈጥሮ አልፏል፡፡ ታዋቂው ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ የነበሩት ሙሉጌታ ሉሌ ‹‹ሰው ስንፈልግ ባጀን››› በሚለው መጽሐፋቸው እንደጠቀሱት፣ ፍቅርና ሰላም ባልተሰበከበት በደርግ ዘመን በተለይም በ1969 ዓ.ም. የዚያድ ባሬ ጦር ኢትዮጵያን እንደወረረና በኦጋዴን ልዩ ልዩ ሥፍራዎች በጋላዲ፣ በጅጅጋ፣ በቀብሪ ደሐር፣ ወዘተ በፀሐይና በንፋስ ስትንገላታ ቀለሟ እየተለወጠ የነበረውን፣ ዳሩ ግን የኢትዮጵያችንን ክብርና ነፃነት የምትገልጸውን ሰንደቅ ዓላማ እያወረዱና እያቃጠሉ የተስፋፊነት ምልክት የሆነውን የሶማሊያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክን ባለአምስት ኮከብ ሰንደቅ ዓላማ በዚህች አገር አውለብልበዋል፡፡  ምንም እንኳን ይኼ ድርጊት ረጅም ጊዜ የቆየ ባይሆንም፡፡

ፍቅር ከሌለ ትርፉ ሊሆን የሚችለው ይህ ነው፡፡ የደርግ መንግሥት የሕዝቡን ዴሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብት በመንፈጉ ዜጎች እንደ ንብ መንጋ በአንዴ ጠላትን ለመውጋት አልዘመቱም፡፡ ዘመቻውም የነበረው በግዳጅ ነበር፡፡ ዜጎችም ለተለያዩ አደጋዎች ተጋልጠዋል፣ ታስረዋል፣ ተጨፍጭፈዋል፡፡ የሚሊዮኖች ደም ፈስሷል፡፡ እናት የወለደችውን ልጅ አካለ መጠን ደርሶ የማየት ዕድል አልነበራትም፡፡ እናቶቻችን አንብተዋል፡፡

ይኼ ሁሉ ዘግናኝና አሰቃቂ ድርጊት የተከሰተው መንግሥት ይከተለው የነበረው የአስተዳደር ሥርዓት ፍፁም አምባገነን በመሆኑና ሰብዓዊ መብቶች የተረገጡበት ጊዜ ስለነበር ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ወጣቶች ፈቅደው ሳይሆን ተገደው ወደ ጦር አውድማ ተግዘዋል፡፡ ይህ ያለ ሕዝቡ ፍላጎት ይካሄድ የነበረው ግዳጅ ደግሞ ፍፃሜው ምን እንደሆነ በታሪክ አይተናል፡፡ በወቅቱ በዜጎች መካከል መቃቃርና በዓይነ ቁራኛ መተያየት ነበር፡፡ ወንድም ወንድሙን ገድሏል፡፡ በአንድነት ተቀናጅተን ጠላትን ሳይሆን የራሳችንን ዜጋ ገድለናል፡፡ ይህ የማይፋቅ ቀይ ስህተት ሆኖ በኢትዮጵያ ታሪክ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በወቅቱ ፍቅር አልተሰበከም፡፡ አንድነት አልታወጀም፡፡ ከአገራዊ ጉዳይ ይልቅ የጥቅመኝነትና የሥልጣን ፍላጎቶች ጎልተው ወጡ፡፡ የኅብረተሰቡን ችግር ለማዳመጥ ጆሮ የነበረው መሪ አልነበረም፡፡ በዚህና በሌሎች ጉዳዮች ምክንያት ተቃውሞዎች በየአቅጣጫው መታየት ጀመሩ፡፡ ተቃውሞውን ወደ አንድነትና የተቀናጀ ትግል ያመጣውና ኢትዮጵያን ከአምባገነኑ ሥርዓት ለማላቀቅ ቆርጦ የተነሳው ግን ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕወሓት) እየተባለ የሚጠራው ድርጅት ነበር፡፡

ይህንን ግፍና መከራ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስወገድ ቆርጦ የተነሳው ሕወሓት ከሌሎች ድርጅቶች ጋር ግንባር በመፍጠር ኢሕአዴግ ተብሎ የደርግን ግባተ መሬት አሳካ፡፡ ለአሥራ ሰባት ዓመታት የተጨቆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ አዲስ ጮራ ማየት ጀመረ፡፡ አዲስ አየር ተነፈሰ፡፡ ዜጎች በሠላም ወጥተው በሰላም መግባት ጀመሩ፡፡ የዜጎች ዴሞክራሲዊ እና ሰብዓዊ መብቶች ተረጋገጡ፡፡ የፌዴራሊዝም ሥርዓቱ ባጎናጸፈው ድል ብሔር ብሔረሰቦች በቋንቋቸው የመናገርና የፈለጉትን ሃይማኖት የመከተል መብቶች ተረጋገጡላቸው፡፡ በዚህም የተነሳ ጭቆናን መሸከም የማይችል ሞጋች ኅብረተሰብ፣ መጠነ ሰፊ የተማረና አምራች ኃይል ተፈጠረ፡፡

የጥንቱ ትውልድ አክሱምንና ላሊበላን እንዳቆመ ሁሉ ዛሬም ዓባይ በሕዝቡ ሙሉ ድጋፍ እንዲገደብ እየተንቀሳቀሰ በመሆኑ ኢሕአዴግን ይበል የሚያሰኝ ሥራ ነው፡፡ የገጠሩን አርሶ አደር ተጠቃሚ በማድረግና የእርሻውን ክፍለ ኢኮኖሚ በማዘመን ወደ ኢንዱስትሪ ለመሸጋገር የሚደረገው ጥረት በጣም የሚበረታታ ነው፡፡

ይኼ በእንዲህ እንዳለ ኢሕአዴግ በ25 ዓመታት የሥልጣን ዘመኑ ብዙ ያልሠራቸው የቤት ሥራዎች እንዳሉት ግን መካድ አይቻልም፡፡ ዛሬ ላይ የሕዝብ ጥያቄ ሆነው በየአካባቢውና በየአደባባዩ የምንሰማቸው ጉዳዮች ኢሕአዴግ ያላሳካቸው ተብለው በራሱ ልሳን ሳይቀር የሚነሱት ጉዳዮች ዛሬ ለአገራችን ትልቅ ፈተና ሆነዋል፡፡ እነዚህን ጉዳዮች እዚህ ላይ መጥቀሱ አንባቢያንን ማሰልቸት ሊሆንብኝ ይችላል ብዬ በመገመቴ አልፌዋለሁ፡፡ በእነዚህ ጉዳዮች የተነሳ ዛሬ ዛሬ በአገራችን ውስጥ ተቃውሞዎችና ጥያቄዎች እየተነሱ ነው፡፡ እነዚህ ቅሬታዎችና ጥያቄዎች ከውስጣዊ ሹክሹክታ አልፈው ወደ አደባባይ መውጣት ጀምረዋል፡፡ ፒተር በርገርና ሪቻርድ ጆን ኒሃውስ የተባሉ ሁለት የፖለቲካ ምሁራን ‹‹To Empower People››  በሚለው መጽሐፋቸው ‹‹የሕዝብ ሥልጣን ሲመነምንና ማዕከላዊ ሥልጣን ሲያብጥ መሠረታዊ የሐሳብ ገበያው ይፈርሳል፡፡ በመጨረሻም ሕዝብ ጥያቄውን አንግቦ አደባባይ ይሠለፋል፤›› ይላሉ፡፡

በአገራችን ውስጥ አሁን ላይ እየሆነ ያለው እንግዲህ ይህ ነው፡፡ የመንግሥት ሥልጣን ማበጥ እየታየ ነው (በእነሱ አጠራር ኪራይ ሰብሳቢ አመራር ተፈጥሯል)፡፡ ሕዝቡም ከሹክሹክታና  ከአሉባልታ አልፎ ጥያቄውን ወደ አደባባይ ይዞ ወጥቷል፡፡ እንግዲህ ጨዋታው እዚህ ላይ ነው፡፡ ኢሕአዴግ የሕዝቡን ጥያቄ ለመመለስ መስዋዕትነት የከፈለበት ወቅት ከተሻረና ከችግርና ከኢዴሞክራሲያዊ አሠራሮች ራሱን ማሻሻል ካልቻለ ውጤቱ የዜሮ ድምር ጨዋታ ይሆናል፡፡ መንግሥት በአሁኑ ጊዜ የሕዝብን ጥያቄ በአፋጣኝ የመመለስ ውስንነት እየታየበት ነው፡፡ በዚህም የተነሳ እንደ ባለሙያዎቹ ገለጻ የሐሳብ ገበያው ፈርሶ ለአገርም ለዜጋም አደጋ የሆነ ጉዳዮች ብቅብቅ ማለት ጀምረዋል፡፡ መንግሥት የሐሳብ ልዩነትን ሙሉ በሙሉ እንደ ተፈጥሯዊና የዴሞክራሲ ሥርዓት መገንቢያ ሁነኛ መሣሪያ አድርጎ መውሰድ አልቻለም፡፡

በአገሪቱ የሚታዩ አንዳንድ ግለሰቦችና ቡድኖች በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እያሳዩዋቸው ያሉ ተገቢ ያልሆኑ ሥነ ምግባሮችን በፍቅር ተቀብሎ በፍቅር ማሸነፍ አልቻለም፡፡ እንዲያውም ልማታዊ፣ ጠባብ፣ ትምክህተኛ፣ አክራሪ፣ ወዘተ እያለ የማግለልና ነገሩን የባሰ እያጋነነው ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለመሪውም ሆነ ለአገር ትልቅ ኪሳራ አለው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ዕርምጃ በአሜሪካ ታሪክ ሳይቀር የከፋ ጉዳት አስከትሎ አልፏል፡፡ በጆማካርቲ (ሪፕብሊካን) ዘመን ዜጎችን በኮሙኒስትነት በመጠርጠርና በአሜሪካ ጥቅም ተፃራሪነት፣ በብሔራዊ ስሜት ጉድለት በመወንጀል መጎተትና እስር ቤት ውስጥ ማጎር የተለመደ ነበር፡፡ ይኼ ድርጊት በአሜሪካ ታሪክ ክፉኛ መስዋትነት አስከፍሏል፡፡ የአሜሪካ ሕዝብና መንግሥትም ከንዲህ ዓይነት አስከፊ ድርጊቶችና ዕርምጃዎች ትልቅ ትምህርት ወስዷል፡፡

የእኛም አገር በአሁኑ ወቅት ሙሉ በሙሉ ባይባልም በዚህ ስሜት ውስጥ ነው ያለችው፡፡ እነዚህ የተለያዩ ምድብና ስያሜ የምንሰጣቸው ዜጎችም ሆኑ ቡድኖች ምንም እንኳን ድርጊታቸው ለአገር በጎና ጥሩ ነው ባይባልም፣ ከዚህ ድርጊታቸው እንዲወጡ ፍቅር በመስጠትና በማቅረብ ማሸነፍ አለብን፡፡ መንግሥት የአገሪቱን የፖለቲካ ምኅዳር በማስፋት ጥልን ሊያሰፉ የሚችሉ ፍረጃዎችንና ምድቦችን መተው አለበት፡፡ ትውልድ ያልፋል፣ ታሪክ ግን አያልፍም፡፡ በዚህ በማያልፍ ታሪክ ደግሞ የማይፋቅ ታሪክ ሠርቶ ማለፍ ጀግንነትና ከዚህ ትውልድና መንግሥት የሚጠበቅ ጉዳይ ነው፡፡ ውስብስብ የፖለቲካ ችግር ያለበትን ዓባይ እንደደፈርን ሁሉ ልዩነቶች በነፃነት እንዲስተናገዱ ቁርጠኛ መሆን አለብን፡፡ በተለይ መንግሥት በዚህ ላይ ትልቅ ሥራ ሊሠራ ይገባዋል፡፡  

አገራችን አሁን ካለችበት የፖለቲካ አዙሪት ልትወጣ የምትችለው የመንግሥት ቁርጠኛ አቋም ሲረጋገጥ ብቻ ነው፡፡ ኢሕአዴግ ጠያቂ ትውልድ እንዳፈራ ሁሉ የቀረፀው ፖሊሲና ስትራቴጂም ፍሬ ማፍራት አለበት፡፡ የአገሪቱ ሕገ መንግሥት በፈቀደው ደረጃ ዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶቻቸው እንዲከበር ከፍተኛ ሥራ መሥራት አለበት፡፡ ያኔ ልዩነቶች ይጠባሉ፡፡ ብሔራዊ መግባባቶች ይፈጠራሉ፡፡ ኢትዮጵያም ወደቀደመ ስመ ገናናነቷ ትመለሳለች፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው zemetenagnelove@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡     

Standard (Image)

አዋጁን ቀጣይነት ያለው የሰላምና የዴሞክራሲ ግንባታ መሠረት እናድርገው

$
0
0

በአበበ ተክለሃይማኖት (ሜጀር ጄኔራል)

ባለፉት 25 ዓመታት ኢትዮጵያ ሰላም ባጣው በምሥራቅ አፍሪካ የሰላም ተምሳሌት ሆና የራሷን ሰላም አረጋግጣ ለሌሎች የምትደርስ አገር ሆናለች፡፡ እሰዬው፡፡ ይህ ሰላም የመላው የኢትዮጵያ ሕዝቦች ትግል ውጤት ነው፡፡ የተሟላ ዴሞክራሲያዊ ሕገ መንግሥት አፅድቀው መተግበር በመጀመራቸው ነው፡፡ የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦችንና የግለሰብ መብቶችን አጣምሮ በተሟላ ሁኔታ የሚያረጋግጥ ሕገ መንግሥት በከፊልም ቢሆን መተግበር ሲጀምሩ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትን በማምጣት ድህነትን በተነፃፃሪ ፍጥነት በመቅረፍ ዴሞክራሲያዊ የአገር ግንባታ ተያያዙ፡፡

ሕገ መንግሥቱን ተግባራዊ ለማድረግ ባደረጉት ያልተቆጠበ ጥረት ሰላም ማረጋገጥ ሲጀምሩ፣ በአንፃሩ ደግሞ ሕገ መንግሥቱ ሲሸረሸር በተለያየ ደረጃ የሚገለጽ የሰላም ማጣት ሁኔታ እየታየ ነው፡፡ በሰላም ላይ አደጋ ሊከሰት የቻለበት አንዱ ምክንያት የዴሞክራሲ እጥረት፣ የተጠያቂነት መጥፋት፣ የሕግ የበላይነት መዳከም፣ ሥልጣንን ለግል ጥቅም ማዋል፣ የሙስና መስፋፋት ወይም የፍትሕ ማጣት ተብሎ ሊገለጽ ይችላል፡፡ ሌላው የሁሉም ድክመትና ድምር ጥፋት ያመጣው ነው ሊል ይችላል፡፡ በአጠቃላይ ግን ሕገ መንግሥታችንን መተግበር ሰላም እንዳመጣ  ሁሉ፣ ሲሸረሸርም ለሰላም ማጣት ዋነኛ ምክንያት ይሆናል፡፡

ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ባለመከበራቸው፣ ሕገ መንግሥታዊ ተቋማት ሥርዓቱ ያስቀመጠላቸውን ግዴታ መወጣት ባለመቻላቸው፣ ሰላም፣ ፈጣንና ቀልጣፋ ማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት በመረጋገጡ እየተፈጠሩ ካሉት ማኅበራዊ ኃይሎች ፍላጎት ጋር ተጣጥሞ መሄድ ያልቻለው ፖለቲካዊ ሥርዓት ወደኋላ በመጎተቱ ምክንያት መረጋጋት እየታጣ ሄዷል፡፡ አዲሱ ትውልድ ለሚያነሳው ጥያቄ አሮጌው አመራር የሚመጥን መልስና ፖለቲካዊ መፍትሔ ማቅረብ ባለመቻሉ ቅራኔ ተፈጥሯል፡፡

በውስጥ ችግሮቻችን ምክንያት ሁከቱ ተፈጠረ፡፡ ፅንፈኛ ኃይሎች ከውጭ ጠላቶቻችን ጋር ተባብረው የሕዝቦችን ተቃውሞ ወዳልሆነ አቅጣጫና ወደ አመፅ ቀየሩት፡፡ በርካታ የሰው ሕይወት ጠፋ፣ ንብረት ወደመ፣ የልማት ተቋማት ጋዩ፣ ጠላቶቻችን ጊዜያችን አሁን ነው ብለው አቀጣጠሉት፡፡ ሁከት ቀጠለ፡፡ ለ25 ዓመታት የተገነቡት ተቋማት የተነሱትን ፖለቲካዊ ጥያቄዎች በአግባቡ መመለስ ባለመቻላቸውና በሰላማዊ መንገድ ማካሄድ ስላልቻልንና ስለተሸነፍን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሥር እንገኛለን፡፡ ይኼ ሽንፈት ነው፡፡ ከዚህ ሽንፈት እንዴት እንወጣለን የሚለው መፍትሔ ከሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚጠበቅ ነው፡፡ 

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በአማርኛው፣ በእንግሊዝኛው “article 93, Declaration of state of emergency” በጉዳዩ ላይ የተጻፉ ጽሑፎች እንደሚያሳዩት ሁለቱ አገላለጾች በተለይ ‹‹አስቸኳይ ጊዜ›› እና “emergency” የሚሉት ቃላት መስማማታቸውን ለባለሙያዎች በመተው፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ/ደንብ ዓይነት፣ ተፈጥሮ፣ ዓላማና ውጤቱ ላይ አስተያየት መስጠት ተገቢ ይመስለኛል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ (emergency) ዓይነቶች

በሁለት መሠረታዊ ዓይነቶች ከፋፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ በማኅበራዊና በኢኮኖሚያዊ፣ በፖለቲካዊና በወታደራዊ ክስተቶች ምክንያት የሚታወጁ ደንቦች/አዋጆች፡፡

ማኅበረ ኢኮኖሚ ስንል በተፈጥሮ ወይም ሰው ሠራሽ አደጋ ምክንያት በዋናነት በማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ላይ የሚደርስ ቀውስ ነው፡፡ ከፍተኛ የሆነ የመሬት መንቀጥቀጥ፣ ጎርፍና ማዕበል፣ ከፍተኛ ድርቅ ወይም በሽታ ወይም ኢኮኖሚያዊ አለመረጋጋት የሚፈጥሩዋቸውን ቀውሶች በአጭር ጊዜ ለመፍታት የሚደነገጉ አዋጆች ናቸው፡፡ ይህን ቀውስ ለመታደግ የአገሪቱን የሰውና ተፈጥሯዊ ሀብት ለማንቀሳቀስ ያለምንም እክልና ጊዜ የማይወስድ መፍትሔ ለማምጣት ሲያስፈልግ፣ ዴሞክራሲያዊ መብቶችን በማገድና በተወሰነ ደረጃ ኃይል መጠቀምን የሚያሳዩ ክስተቶች ናቸው፡፡

ሁለተኛው ፖለቲካዊና ወታደራዊ የሚባል ሆኖ ኃይልን በኃይል የመመከት ባህርይ ሲሆን፣ ዋናው ፖለቲካዊና ወታደራዊ ኃይል የሚለው እንደ ሁኔታው ደረጃው የሚለያይ ነው፡፡ ዋናው ኃይል መፍትሔ ሆኖ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴዎች የሚጠይቁ፣ ሌሎች ደግሞ ዋናው ፖለቲካዊ ሆኖ በኃይል የሚታጀቡ ናቸው፡፡ የአገር መወረር ፖለቲካዊ አንድምታ እንኳን ቢኖረውምና ዲፕሎማቲክ ሥራዎች ቢኖሩትም፣ ዋናው መፍትሔው ወታደራዊ ነው፡፡ መፈንቅለ መንግሥት በተመሳሳይ ሊታይ ይችላል፡፡

የውስጥ አመፅ ወይም የእርስ በርስ ጦርነት ግን ወታደራዊ ገጽታና የግጭት መልክ ቢኖረውም ቁምነገሩ ግን ፖለቲካዊ ነው፡፡ መነሻውም መፍትሔውም ፖለቲካዊ ነው፡፡ በሕዝቦችና በመንግሥት መካከል የሚኖረው የመብትና ግዴታ በተሟላ መንገድ አለማሟላት ነው፡፡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመንም ሆነ በደርግ ጊዜ የነበረው የአገሪቱ ቀውስ ሕዝቦች የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብታችንን ይረጋገጥልን የሚል ሲሆን፣ ገዢዎች ደግሞ እነዚህን መብት ለጠየቀ መልሳቸው ኃይል በመሆኑ የእርስ በርስ ጦርነት ተጧጡፎ ባለመብቶቹ አሸንፈዋል፡፡

በ2008 ዓ.ም. የተከሰተው ሁከትም የዴሞክራሲ፣ የፍትሕና የእኩልነት ጥያቄ መነሻ የፈጠረው እንቅስቃሴ ነው፡፡ ገዢውን ፓርቲ በየደረጃው በሰላማዊ መንገድ መታገል እየጠበበ በመምጣቱ፣ የመንግሥት ተቋማት ለሚነሱት ጥያቄዎች የሚመጥን መፍትሔ መውሰድ ባለመቻላቸውና የወጣቶች ችኩልነትና ግልፍተኝነት ተጨምሮበት በፅንፈኞችና በውጭ ጠላት ኃይሎች ቆስቋሽነት የተካሄደ ነው፡፡ መነሻው ፖለቲካዊ ሆነ በሁከት የተደራጀ ሁከት ለማቀዝቀዝ ኃይል በሚያስፈልገው ቢሆንም ዋናው መፍትሔ ግን አሁንም ፖለቲካዊ ነው፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተፈጥሮ

በዴሞክራሲያዊ ሥርዓቶች በ‹‹ብሔራዊ ደኅንነትና በሕዝቦች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መካከል ቀጣይነት ያለው ቅራኔ (tension) መኖሩ የግድ ነው፡፡ የአመፅ ቀውሶች እነዚህን መሠረታዊ የሆኑ መብቶች የሚፃረሩ በመሆናቸው ሥርዓቱ ራሱን ለመከላከል ግድ ይለዋል፡፡ ሕገ መንግሥቱን ራሱን ከማጥፋት ለመከላከል መደራጀት አለበት፡፡ የሕገ መንግሥታችን አንቀጽ 93 ራሱን በኃይል ከሚንዱት ለመጠበቅ ማለትም ዴሞክራሲያዊ ያልሆነ አንቀጽ ግን ዴሞክራሲያዊ የሆነን ሕገ መንግሥት ለመከላከል የተደራጀ ነው፡፡ የሕዝቦችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ለመጠበቅ ለአጭርና ለተወሰነ ጊዜ ቢሆንም፣ ዴሞክራሲያዊ መብቶችን በጠቅላላ የተወሰኑ ሰብዓዊ መብቶችን በተወሰነ ደረጃ ይነፍጋል፡፡ ምን ዓይነት ምፀት ነው?

 አምባገነን በሆኑ ሥርዓቶች ግን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሁኔታዎ ሁልጊዜም የሚኖሩና ስታንዳርድ ተደርገው የሚወሰዱ ናቸው፡፡ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን በማያረጋገጥ አገር የአስቸኳይ ጊዜ ሁኔታ ሁልጊዜ እንዳለ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ መንግሥት ተቃውሞን ውጤታማ በሆነ መንገድ በመከላከል አምባገነን ሥርዓቱን የመጠበቅ እንጂ፣ የሕዝቦችን መብቶች ማረጋገጥ ደንታ ስለሌለው ሁልጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንደሚኖር ታሳቢ ሊደረግ ይችላል፡፡

ሰብዓዊ መብቶች የሚረጋገጡት ዴሞክራሲያዊ መብቶች ሲረጋገጡ ብቻ ነው፡፡ ሕዝቦች ሰብዓዊ መብቶቻቸውን የሚያስጠብቁት ዲሞክራሲያዊ መብቶችን መሠረት አድርገው በሚያደርጉት ትግል ነው፡፡ ከመንግሥት የሚሰጥ ስጦታ (መና) ከሆነ ግን ዘላቂነት የሌለውና አባታዊ (Paternalistic) ነው የሚሆነው፡፡ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ ሥርዓት በሕገ መንግሥትና በሕገ መንግሥት መንፈስ የወጣ አዋጅ እስከሆነ ድረስ ልክ፣ ‹‹ልጅህ ራሱን ለመግደል ሲከጅል እንዳይሞት ሽጉጡን ለመንጠቅ እጁን በጥይት መምታት ያህል ነው›› ክፉኛ ይቆስላል፣ ያሳምመዋል፡፡ ከሁኔታው ጋር የሚሄድ ዝግጅት ካልተደረገ ደግሞ ደሙ እየፈሰሰ ሊሞት ይችላል፡፡ ወይም ደግሞ እጁን ለመምታት ተብሎ ልቡን ወይም ራሱን ከተመታ ሊሞትም ይችላል፡፡ በተመሳሳይ መንገድ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሕዝቦች መብትንና ሥርዓቱን ለመጠበቅ ተብሎ የሚያቆስልና የሚያሳምም ከሆነና ዝግጅት ካልተደረገ፣ ወይም የተወሰደው ዕርምጃ ተመጣጣኝ ካልሆነ የሕዝቦችን መብት መጠበቅና ሥርዓቱን መታደግ መሆኑ ቀርቶ ‹‹የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች›› እንደሚባለው ሊሆን ይችላል፡፡ ፀረ ዴሞክራሲ ሊያገነግን ይችላል፡፡ አዋጁ ያለውን ሁኔታ ለማረጋጋት የግድ በሚል ነው፡፡ ሰላማዊና ሕጋዊ በሆነ መንገድ ችግሮቻችንን ለመፍታት ስላልቻልን የመጣ አስፈላጊ ግን የሽንፈት መንገድ ነው፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ታሳቢ ዓላማዎች

አዋጁ ወላፈንን ያዳፍናል እንጂ እሳቱን ሊያጠፋ አይችልም፡፡ ችግሩና መፍትሔው ፖለቲካዊ ነው ማለታችን የተፈጠረው ሁከት የእሳቱ ወላፈን መሆኑን በመገንዘብና ረመጡ የሚጠፋው ወይም እንዳይቀጣጠል የሚያደርገው ሕገ መንግሥቱን ተግባራዊ ማድረግ መሆኑን በማመን ነው፡፡ አዋጁ የእሳቱ ወላፈን እንዳይፋጅ በመከላከል ዓላማና መሠረታዊ የሆኑ ችግሮች የሚፈቱበት የተመቻቸ ሁኔታ መፍጠር እንጂ፣ ከዚያ በላይ የሚቆም ዓላማ ሊኖረው አይችልም፡፡ ጊዜያዊ መፍትሔ ስለሆነም፣

  1. የሁከቱ ዋና ተዋናይ የሆነው ወጣት ዓመፅ ማስነሳቱ ወይም መሳተፉ ወይም ደግሞ መደገፉ ስህተት መሆኑን የሚያምንበት ሒደት መሆን ይኖርበታል፡፡ በፅንፈኞችና በወራሪዎች ላይ አይቀጡ ቅጣት የሚያስፈልግ ቢሆንም ምናልባት 99 በመቶ የሚሆነውን ወጣት በሚመለከት መቅጣት ሳይሆን ማስተማር፣ በተደረገው ተመጣጣኝ ዕርምጃ ተማምኖ ጥያቄዎች ፍትሐዊና ሕገ መንግሥታዊ ቢሆንም አካሄዱ ግን ስህተት እንደነበረ አምኖ አዋጁ ሲነሳ እፎይ ብሎ፣ ሕዝቦችንና መንግሥትን አመስግኖ ወደ ልማቱ የሚዘጋጅበት ሁኔታ መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ አብዛኛው ወጣት ጥቃት ደርሶብኛል ካለ ግን መሠረታዊ ቅሬታና ቂም ይዞ ስለሚወጣ አዋጁ ዓላማውን አላሳካም ማለት ነው፡፡
  2. በብሔሮችና ብሔረሰቦች እየታየ ያለው መጠራጠር የሚቀንስ ካልሆነም ባለበት የሚገታ መሆን አለበት፡፡

አዋጁ ‹‹መጣልን›› የሚሉ እንደሚኖሩ ሁሉ ‹‹መጣብን›› የሚሉ እንዳይኖሩ ከመጀመሪያው ግምት ውስጥ አስገብቶ እንደየአካባቢው ሁኔታ እጅግ በጣም ብዙው ሕዝብ መጣልን እንዲል መደረግ ይኖርበታል፡፡ እነዚያ መጣልን የሚሉ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅን ያላግባብ መጠቀሚያ እንዳያደርጉት መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡

እንደየአካባቢው ሁኔታ ብሔር/ብሔረሰቦች ልዩ ሚና እንዲኖራቸው ማድረግ ተገቢ ይመስለኛል፡፡

  1. አዋጁና አተገባበሩ ማዕከላዊነት ያለው በመሆኑ ከፌዴራል ሥርዓቱ ጋር ግጭት አለው፡፡ ልክ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱን በዴሞክራሲያዊ ባልሆነ መንገድ ለመታደግ የሚደረግ ሙከራ ያለው ዓይነት ግጭት ነው፡፡ የአዋጁ ዓላማ ሰላም ከማስፈን ጎን ለጎን ብሔር ብሔረሰቦችንና ሕዝቦችን የሚወክሉ ክልሎችና ልዩ ዞኖች ሥልጣንና ግዴታ በመጠበቅ ፌዴራላዊ ሥርዓቱ ተጠናክሮ እንዲወጣ ማድረግ ይገባል፡፡

ምንም እንኳን ሕገ መንግሥቱ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አዋጁን ተከትሎ ከአባላቱና ከሕግ ባለሙያዎች መርጦ የሚመድባቸው ሰባት አባላት ያሉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም መርማሪ ቦርድ ያቋቁማል የሚል ቢሆንም፣ መፍትሔውን በዘላቂነት ለማምጣት ችግሩ የተከሰተባቸው ቦታዎች ላይ ያሉ ሕዝቦች ዋነኛ የችግሩ የመፍትሔ አካላት ተደርገው ሊወሰዱ ይገባል፡፡ የተፈጠረውን ቀውስ ለመፍታት ከምክር ቤቱና ከሕግ ባለሙያዎች ከሚመረጡት ሰባት አባላት በተጨማሪ፣ ችግሩ በተፈጠረባቸው አካባቢዎች የሚገኙ የሕዝብ ተወካዮችና የክልል ምክር ቤት አባላት፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ እናቶች፣ ወጣቶችና በሕዝቡ ዘንድ አመኔታና ከበሬታ ያላቸው ከልዩ ልዩ ሙያዎች የተውጣጡ ግለሰቦች የችግሩ አፈታት በውስጡ ቂምን ያረገዘ እንዳይሆን ከፍተኛ አስተዋፅኦ ከማድረጉም በላይ፣ በሕዝቦች መካከል ያለውን ግንኙነት በማጠናከር ፌዴራላዊ ሥርዓቱ ዋስትና እንዲያገኝ የላቀ ሚና ይጫወታሉ፡፡

ኪራይ ሰብሳቢነትና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ

አውቶክራቲክ (ዴሞክራሲያዊ ያልሆነ አካሄድ) የግድ ቢልም ከረዥም ጊዜ አንፃር በሚገባ ካልታየ አደገኛ ሊሆን ይችላል፡፡ ኪራይ ሰብሳቢዎች አውቶክራቲክ አካሄድን ይወዱታል፡፡ መሸሸጊያቸው ነውና፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ አውቶክራቲክ አካሄድ ኪራይ ሰብሳቢነት እንዲሰፋ፣ ጥልቀት እንዲኖረውና ቀጣይነት እንዲለብስ የተመቻቸ ሁኔታ ይፈጥራል፡፡ ይመጋገባሉ፡፡

ስለዚህ በመንግሥት ደረጃ የሚደረገው የፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ትግል የተለየና ጥልቀት ያለው መሆኑን ተገንዝቦ መታገል ያስፈልጋል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አስፈላጊ ቢሆንም የፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ትግሉ በከፍተኛ ደረጃ ሊያኮላሸው ይችላል፡፡

መንግሥት ኪራይ ሰብሳቢነት ተጠናውቶኛልና እታገለዋለሁ ብሎ ዝግጅት በጀመረበት በዚህ ጊዜ ሁኔታው አስገድዶት አስቸኳይ ጊዜ ታዋጀ፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነት እንኳንስ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ውስጥ ይቅርና የተሟላ ዴሞክራሲያዊ ምኅዳር ባለበት እንኳን ተግዳሮቶቹ ከፍተኛ ነው፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነት ማሸነፍ የሚቻለው ዴሞክራሲያዊ ምኅዳሩ በማስፋት ነው፡፡ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ዴሞክራሲያዊ መብቶች ይነፍጋል፡፡ ስለዚህ በዚህ ሁኔታ ኪራይ ሰብሳቢነትን በተሟላ ሁኔታ መታገል አይቻልም፡፡ ኪራይ ሰብሳቢዎች እንዲያሸንፉ የተመቻቸ ሁኔታ ይፈጥራልና፡፡

የመንግሥት ሥልጣን ለግል መጠቀሚያነት በሽታ እስከ ቀበሌ (ሚሊሻ) ድረስ የሚዘልቅ ነው፡፡ ኪራይ ሰብሳቢዎች ጊዜያችን አሁን ነው ብለው የግል ጥቅማቸውን ለማሳካት ከማናቸውም በላይ ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ቂም በቀል፣ ዛቻ፣ ወዘተ መሣሪያቸው ይሆናል፡፡ ሕዝቡ ተበድያለሁ ብሎ እንዳይናገር አይቀጡ ቅጣት ሊያወርዱበት ይከጅላሉ፡፡ በዚህም ምክንያት በሕዝቡ ውስጥ የኪራይ ሰብሳቢነት አማራጭ እየሰፋ ይሄዳል፡፡

በአጠቃላይ መንግሥት ኪራይ ሰብሳቢነት ዋናው ችግሬ ብሎ ባወጀበት ወቅት፣ ሁከት ተፈጥሮ ኢትዮጵያ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መተዳደርም የፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ትግሉን እጅግ የሚያወሳስብና የሚያራዝመው መሆንን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ከላይ ጀምሮ በየደረጃው  እስከ ቀበሌ (ሚሊሻ) ድረስ የራሳቸው ፍላጎት ያላቸው ኪራይ ሰብሳቢዎች የተሻለ ጊዜ መጥቶልናል በማለት ዳንኪራ ሊመቱ ይችላሉና፡፡

በአስቸኳይ ጊዜ ወቅት የሲቪል/ፖለቲካዊ ቁጥጥር ወሳኝነት

ባደጉት አገሮች ቀውስ ቢኖርም ባይኖርም ሲቪል/ፖለቲካዊ ቁጥጥር ለዴሞክራሲ ሥርዓቱ አለኝታ ነው፡፡ በማደግ ላይ ላሉ አገሮች ግን ወሳኝ ነው፡፡ ሕገ መንግሥታዊ ተቋማቱ ገና ያልተደላደሉ በመሆናቸው፣ የሕዝቡ ንቃተ ህሊና ያልዳበረና ድርጅቶች ደካማ ስለሆኑ ራሱን መከላከል አይችልም፡፡

በአጠቃላይ ሲታይ በአስቸኳይ ጊዜ ወቅት የሥልጣን ክፍፍሉ የሚዳከምበት፣ ሥራ አስፈጻሚው የመሪነት ሚና ስለሚወሰድ ሌሎቹ የመንግሥት አካላት ጥግ የመያዝ ዝንባሌ ይታይባቸዋል፡፡ ሆኖም የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት የተወካዮች ምክር ቤት በአንቀጽ 93 መሠረት ሥራ አስፈጻሚው የደነገገውን አዋጅ በመሻር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ በዚህ አንቀጽ በንዑስ አንቀጾች 5 እና 6 መሠረት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም መርማሪ ቦርድ በማቋቋም ሒደቱን የሚከታተልበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ ምክር ቤቱ አዋጁ በማፅደቅ/በመሻር፣ ብቃትና ማንነታቸውን ያረጋገጡ አባላት ለመርማሪ ቦርድ በመመደብ ቀጣይነት ያለው ድጋፍና ክትትል በማድረግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከሚፈለገው በላይ እንዳይቀጥል በመወሰን ለሕገ መንግሥቱ፣ ለህሊናውና ለሕዝቡ ብቻ እንዲያገለግል በልዩ ሁኔታ ልዩ ዕድል ያገኘ ይመስለኛል፡፡

በቀውስ ወቅት መደናገጥ፣ ፍራቻ፣ ጥላቻና ስሜታዊነት ሊጎለብቱ ቢችሉም ዋናው ችግር ግን ሕዝቡና መሪዎቹ አገሪቱ እየገጠማት ያለውን ቀውስ በትክክል መገምገማቸው ላይ ነው፡፡ ወይ ቀውሱን አሳንሰው ያዩትና የበለጠ እንዲሰፋና አደገኛ እንዲሆን ያደርጉታል፡፡ አልያም ቀውሱን በጣም አጋንነው በመገምገም አውቶክራቲክ አካሄድ እንዲጠነክርና ጊዜውም እንዲራዘም በማድረግ የሚያመረቅዝ አደጋ ሊፈጥሩ ይችላሉ፡፡ እያንዳንዱ አላስፈላጊ የአዋጁ ቀን ደም የምናነባበት ስለሚሆንና መሠረታዊ ችግሩም የሚያመረቅዝ በመሆኑ፣ በተቻለ መጠን የአዋጁን ጊዜ ማሳጠሩ እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በሚዛናዊነት እየገመገሙ ፈጣን የማስተካከል ዕርምጃ ይጠበቃል፡፡

ለቀውሱ ምክንያት ፖለቲካዊ ነው፡፡ መሠረታዊ መፍትሔውም ፖለቲካዊ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የሚኒስትሮች ምክር ቤት ወይም እሱ የወከለው ኮማንድ ፖስት ከማናቸውም ጊዜ በላይ ፖለቲካዊ ቁጥጥሩ መጎልበት አለበት፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ያላግባብ ተግባራዊ ቢደረግ ጥፋቱ ከፍተኛ ስለሚሆን፡፡  

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የቀድሞ የኢሕአዴግ ታጋይና የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ የነበሩ ሲሆን፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡ 

Standard (Image)

የኢኮኖሚ ልማትንና የገበያ ኢኮኖሚን የማምታታት ጦስ

$
0
0

በጌታቸው አስፋው

ሙያዊ ቃላት ዕለት በለት እንደ ዋዛ ሲነገሩና ጥናትና ምርምር ሲደረግባቸው የተለያየ መረዳትና ትርጉም ይሰጣሉ፡፡ ይኼንን ጽሑፍ ለማቅረብ የፈለግሁት ኢሕአዴግና ተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች፣ ሌሎችንም የኅብረተሰብ ክፍሎች ጨምረው ስለሕዝባዊው አመፅና ሁከት መነሾና መፍትሔ በጥናትና ምርምር አስደግፈው በምሁራን በቀረቡላቸው ጽሑፎች አማካይነት ከአካሄዱት ውይይት ተነስቼ ነው፡፡ በጥቅሉ ስመለከተው የውይይት አቅራቢዎቹን፣ ጠያቂዎቹንና አስተያየት ሰጪዎችን ሐሳቦች ደምሬ ቀንሼ አባዝቼ አካፍዬ በሒሳብ ስሌት ያገኘሁት ውጤት አንድ ቁጥር ሆኖብኛል፡፡

በዝርዝር ስመለከትም ውይይቱ ሁለት ነገሮችን በአዕምሮዬ ጫረብኝ አንዱ የሕዝቡን አመፅ የራሳቸው ለማድረግና የየራሳቸውን ታሪክና ጥንካሬ የውይይቱ ማዕከላዊ ነጥብ ማድረጋቸው ነው፡፡ ሁለተኛው በፖለቲካው፣ በልማቱ፣ በማኅበራዊው መስክ እያሉ ሲከራከሩ ስሰማ ከሠላሳ ዓመት በፊት በአስመራ ዩኒቨርሲቲ ስለልማት ሳስተምር፣ ከልማት ጠበብት አንብቤ የቀሰምኩት ሙያዊ ዕውቀትና የእነርሱ መከራከሪያ አልጣጣም ብሎኝ ነው፡፡ በልማት ጠበብት ትምህርት ልማት የሰው ልጅ ሁለንተናዊ ለውጥ ሲሆን፣ ፖለቲከኞቹ ግን ልማት ብለው የሚያወሩት ስለኢኮኖሚ ልማት ብቻ ነበር፡፡

ኢሕአዴጎች በፖለቲካውና በማኅበራዊ አገልግሎቱ አንዳንድ ድክመቶች ቢታዩብንም፣ በልማቱ ግን ማንም የማይክደው የተዋጣለት ስኬት አስመዝግበናል አሉ፡፡ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችም እየተቅለሰለሱም ቢሆን ይኼንን አምነው ተቀብለዋል፡፡ የልማት ጠበብት የልማት ትርጉም ይኼንን አይቀበልም፡፡ ምክንያቱም ልማት ፖለቲካዊም፣ ኢኮኖሚያዊም፣ ማኅበራዊም፣ መንፈሳዊም ሁለንተናዊ ጉዳይ ነውና ነው፡፡

ከዚህም በላይ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጥ የኢኮኖሚ ልማትና የገበያ ኢኮኖሚ በመምታታቱ ቀውስ ይመጣል ብዬ ለአንድ ዓመት ተኩል ያህል በሪፖርተር ጋዜጣ በተከታታይ የጻፍኩትና ያልኩት ሆኖ አየሁ፡፡ ያልኩት በመሆኑ ተደስቼ ሳይሆን መቅሰፍቱ ወደፊትም ብቅ ጥልቅ እያለ የልጆቻችንን ሕይወት እንዳይቀጥፍ ሌላ የማስጠንቀቂያ ደወል ለመደወል፣ ዛሬም እንደገና በሙያዬ መነጽር አይቼ ካልተጠነቀቅንና መንገዳችንን ካልቀየርን አደጋ ያጋጥመናል ብሎ ለመጻፍ በድጋሚ ሞራል አግኝቼአለሁ፡፡

መንግሥትንም ደመወዝ ሳይከፍላቸው እንዳይሳሳት ከሚያርሙት የሙያ ሰዎች በነፃ የሚያገኘውን መድኃኒት ችላ ብሎ ደመወዝ ከሚከፍላቸው ሙያተኛ ባለሟሎቹ በሽታን ከሚሸምት፣ የአመፅ ጭላንጭል በታየ ቁጥር እየደጋገመ ቆርጬ እጥለዋለሁ የሚለው በሽታ ይበልጥ ወደ ሰውነቱ እየተሰራጨ ጧት ማታ ለሕዝብ በመሀላ ቃል ከመግባት ይልቅ መድኃኒቱን ወስዶ ቢድን ይሻለዋል ለማለትም ነው፡፡

ልማትና የኢኮኖሚ ልማት ምንና ምን ናቸው?

ገና እ.ኤ.አ ከ1950ዎቹና ከ1960ዎቹ ጀምሮ ሲሞን ኩዝኔትስን፣ ጉናር ሚርዳልንና ሌሎችም የልማት ጠበብቶች ልማትን በሰፊው ትርጉምና በጠባቡ ትርጉም ለይተው ያስተምሩ ነበር፡፡ በሰፊው ትርጉም የሰው ልማት ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ሁለንተናዊ ለውጥ ማለት ሲሆን፣ ከአራትና ከአምስት መገለጫዎቹ አንዱ ሰው በአምሳሉ ለተፈጠረው ለሌላ ፍጡር ሰው አቀንቃኝና አጎብዳጅ ሆኖ ከመኖር ይልቅ፣ በውስጡ በራስ መተማመን ሊኖረው ይገባል ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ የልማት ጠበብቶች አውራውና የኖቬል ተሸላሚው አማርተያ ሴንም ልማትን ሲተረጉሙ፣ ሰው ሕጋዊ የሆነን ማንኛውም ነገር በራሱ ለመሥራት አቅምና ነፃነት ማግኘቱ ነው፡፡ ሁለቱም ትርጉማቸው ተመሳሳይ ሆኖ በግለሰብ ላይ የሚታይ ራስን የመቻል ሁለንተናዊ ለውጥ ነው፡፡

ከምዕተ ዓመታት በፊት ለአሜሪካኖች ብልፅግና የፕሮቴስታንት እምነት አስተዋጽኦ እንዳደረገ ይገመታል፡፡ ምክንያቱም ዕምነቱ አንድ ፈጣሪህን ብቻ አምልክ እንጂ በአምሳያህ ለተፈጠረ ሌላ ሰው እንዳንተው ፍጡር ነውና አትስገድ አትንበርከክ ይላልና ነው፡፡ ዛሬም ድረስ የአሜሪካ ፕሬዚዳንትና አንድ የፅዳት ሠራተኛ አብረው ሻይ ቢጠጡ አንዱ ሌላውን አይንቀውም፣ አይፈራውምም፡፡ ሁለቱም በሰውነታቸውም በሥራቸውም ይከባበራሉ፡፡

እኛ ጋ የቀበሌና የወረዳ ሊቃነመናብርት እንኳ ይኼንን አያደርጉም፡፡ በዩኒቨርሲቲዎቻችንማ ባለ ማስትሬቱ ለባለ ዶክትሬቱ ሻይ ቤት ውስጥ ተነስቶ ወንበሩን ካልሰጠው ያኮርፈዋል አሉ፡፡ ይኼ ሰው ታዲያ ለምቷል ሊባል ይችላል? እኔማ ባለማስተርስ፣ ባለዶክትሬት ብዬ አልጠራቸውም፡፡ ግራዝማች፣ ቀኛዝማች ነው የምላቸው፡፡ አይበቃቸውም? ምን ለውጥ አምጥተዋል?? ዛሬ በኢትዮጵያ ድህነት እየከበዳቸውም ራሳቸውን ለአምሳያቸው ሰው ከመስገድ ነፃ ያወጡ፣ ከአንድ አምላካቸው በቀር ለሌላ የማይሰግዱና የማይንበረከኩ እየበዙ ነው፡፡ ምድሪቱም በእነርሱ ትባረክ ይሆናል፡፡

‹‹እሳቸው እንዳሉት…..›› ብሎ ዜና የሚያቀርብ ጋዜጠኛ አልለማም፡፡ የሌላ ሰው አቀንቃኝ ነውና፡፡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎቹን ለማስመረቅ መክፈቻ ንግግር የሚያዘጋጅ የዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት የንግግሩን ግማሽ መንግሥትን ለማሞካሸት ከተጠቀመ አልለማም፣ ለሌላ አጎብዳጅ ነውና፡፡ መሳቅ ሳያስፈልገው አለቃውን በሳቅ ለማጀብ የሚስቅ ሰው አልለማም፣ አለቃ አምላኪ ነውና፡፡ ባለሥልጣንን የሚፈራና ለባለሥልጣን የሚሰግድ ሰው አልለማም፣ የራሱን አቅም አያውቅምና፡፡ ኢትዮጵያዊ ያውም የገጠሩ ኢትዮጵያዊ ከእነኚህ ዓይነቶች ያለመልማት ምልክቶች ራሱን ነፃ ለማውጣት ነው አሻፈረኝ ያለው፣ የደማው፣ የቆሰለውና የሞተው፡፡

ወደ ዴሞክራሲያዊ ውክልናው ሳንሄድ በፊት ሳትወከሉ የተወከላችሁ እስኪ ወካዩ በልማት ትርጉም ራሱን ፈልጎ እንዲያገኝ ፍቀዱለት፡፡ ዴሞክራሲያዊ ውክልና የሚያስፈልገውኮ ለአስተዳደር ቅልጥፍና እንጂ ሰው በራሱ ላይ ምድራዊ ንጉሥ የመሾም ሱስ ይዞት አይደለም፡፡ ሕዝብ መገዛት ይፈልግ አይፈልግ ሳታውቁ እኔን ይወደኛል፣ እኔ ልወከልና ልግዛ ብላችሁ ባትጣሉና ባትነታረኩ ጥሩ ነው፡፡ ለመምረጥ ገና ከሌላም ከራሱም ጋር ይታገላል፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ ሁለንተናዊ ልማት ከተገዢነትና የበታችነት ስሜት ከመሰማት ያድነኛል ብሎ ለሁለንተናዊ ልማት ነው የደማው፣ የቆሰለውና የሞተው፡፡ ሙሴ ወደ ግብፅ ፈርኦን ሄዶ የእስራኤል ሕዝብ ለአምላኩ ይሰግድ ዘንድ ነፃ ልቀቀው ይልሃል ኃያሉ እግዚአብሔር አለ፡፡ ፈርኦንን ሥልጣን አጋራኝ አላለም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብም እንደ ሙሴ ነፃ እንዲወጣ የሚታገልለት የሙሴን ልቦና የተሸከመ የሁለንተናዊ ልማት ተሟጋች እንጂ የሚፈልገው ፈርኦኖች ለማቀያየር አይደለም፡፡

በጌዴኦ ሕዝብ ለሕዝብ የተፋጀው ያነቃውና ያስተማረው የፖለቲካ ሰው ስላልነበረ ነው፡፡ በየመሸታ ቤቱ ማንቼ፣ አርሴ ስትሉና ወዝወዝ በሉ ስትባሉ ከርማችሁ የፖለቲካ ድርጅቶች የጋራ ምክር ቤት ስብሰባ ስትጠሩ ሱፍና ከራባታችሁን አጥልቃችሁ፣ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ የምትሉ ፖለቲከኞች ከስብሰባው በፊት አንብቡ፣ ዕወቁ፣ ጻፉ፡፡ ያላነበበ፣ ያላወቀ፣ ያልጻፈና የማያዛልቅ ፀሎት ለቅስፈት ነው፡፡ ሰው ብዙ ከማንበብና ከማወቅ የተነሳ ከራሱ ቀና ያልሆነ አስተሳሰብም ነፃ መውጣት አለበት፡፡

ሌላው ስለልማት በጠባብ ትርጉሙ የልማት ጠበብት ያስተማሩት ስለኢኮኖሚ ልማት ነው፡፡ የኢኮኖሚ ልማት ከቀላል ዓይነት የማምረት ዘዴ ወደ ከባድና ውስብስብ የማምረት ዘዴ ለመሸጋገር በትምህርት፣ በጤና ጥበቃ፣ በመሠረተ ልማቶችና በማኅበራዊ አገልግሎቶች የመንግሥት አቅርቦት ሰውን የማብቃት እገዛ ሰው በግል ጥረቱ ኑሮውን የሚያሸንፍበት አጋዥ ሁኔታ መፍጠር ነው፡፡ የኢኮኖሚ ልማት ለታዳጊ አገር ሰው የኑሮ ዘዴ የመጀመርያው ምዕራፍ ሲሆን፣ ውድድራዊ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሁለተኛው ምዕራፍ ነው፡፡ አንደኛው ምዕራፍ ለሁለተኛው ምዕራፍ መንገድ ጠራጊ ብቻ ነው፡፡

‹‹ፈረስ ያደርሳል እንጂ አይዋጋም›› እንደሚባለው የኢኮኖሚ ልማት ሰውን የማብቃት ሥራ ነው እንጂ የመጨረሻ ግብ አይደለም፡፡ ሠርተው ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን የሚመግቡ፣ የሚያለብሱና የሚያስጠልሉ ግለሰቦች ከኢኮኖሚ ልማት ቀጥሎ  በነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ተወዳድሮ የሚያሸንፉበት፣ የሚሸናነፉበትና ሊያሸንፉ ወደሚችሉበት ሥራቸውን መቀየር የሚችሉበት የውድድር ሕግና ሥርዓት ተዘርግቶ ማየት ይፈልጋሉ፡፡ ይኼ ካልሆነ የኢኮኖሚ ልማቱ የውጊያውን ሥርዓት ሳይዘረጋ ድንበር ላይ ስንቅና ትጥቅ ሰጥቶ ወታደር እንደሚያከማች የጦር መሪ ነው፡፡ ጠላትን መምታት ካልቻሉ ወታደሮቹ በጊዜ ብዛትና በመሠላቸት መሪውን ራሱን ይመቱታል፡፡ ኢሕአዴግ በኢኮኖሚ ልማት ፍልስፍናው የገጠመውም ይኼ ነው፡፡

የኢሕአዴግ ኢኮኖሚ ልማት ሰውን በማብቃት እገዛው ላይ የሚያቆም ነው፡፡ ቀጥሎ ባለው የኑሮ ዘዴ ምዕራፍ ሁለት ሰዎች በውድድር ከማግኘት ይልቅ በኢኮኖሚ ልማቱ ሒደትና ወቅት በሽሚያ ታግለው ያሸነፉ ጥቂቶች፣ ሁሉንም ለራሳቸው አግበስብሰው ሠርቶ ከማሠራትም ይልቅ ተቀምጠው ለመብላት ስለወሰኑ ሕዝቦች በውድድር ሊከፋፈሉ የሚችሉት ሀብት ጠፋ፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ አመፁና ሁከቱ የበይ ተመልካች የሆኑት ብዙኃኑ በኢኮኖሚ ልማቱ ሒደት እኛ ጋ ያልደረሰውን ሀብት ተሻምተው ከወሰዱት በጉልበታችን ነጥቀን እንወስዳለን ነው፡፡

ኢሕአዴግ የተባበሩትን ብቻ ለመጥቀም አስቦም ይሁን ወይም በችሎታ ማነስ ምክንያቱን በውል ባላውቅም፣ በኢኮኖሚ ልማቱ ሰዎችን ወደ ውድድር ሜዳው ቢያደርስም የውድድሩ ሕግና ሥርዓት የሆነው የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሚናውን እንዲጫወት አላደረገም፡፡ አልሚዎቹና ተባባሪዎቻቸው ድርሻ ድርሻዎቻቸውን ይዘው ለሚዎቹ ባዶ እጃቸውን ቀሩ፡፡ በውድድር የሚከፋፈል ሀብት በጥቂቶች ታንቆ ተያዘ፡፡ የአመፁ ዋና ኢኮኖሚያዊ ምክንያት ይኼ ነው፡፡

ኬኩን በጋራ አተልቀን እንደሚገባን እንከፋፈለዋለን የሶሻሊዝም መርህ የኢኮኖሚ ልማት፣ ከካፒታሊዝም ውድድራዊ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ጋር አልዋሀድ ብሎ ለግለሰቦች ከገበያ ውድድር ይልቅ ሽሚያን የሀብት ማፍሪያ መሣሪያ አደረገ፡፡  የኢኮኖሚ ልማትና የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ካልተመጣጠኑና ካልተመጋገቡ ይኼ ሽሚያ የሰው ቁጥር በጨመረ ቁጥር የሚጨምር እንጂ የሚቀንስ አይደለም፡፡ ጊዜ አልፎ ጊዜ ሲተካ ሕዝብ በዝቶ መሬት ስትጠብም ሁኔታው ይባባሳል እንጂ አይቀንስም፡፡

የኢኮኖሚ ልማት ለሰዎች የግል ብልፅግና ጥረት እንደ መንገድ ጠራጊ ምዕራፍ በአብዛኛው በጋራ የሚታሰብና በጋራ የሚሠራ መንግሥታዊ የደቦ ሥራ ሲሆን፣ ግቡን ካልመታ በቡድኑ ውስጥ የታቀፉ መንግሥታዊ ሥልጣን የተቆጣጠሩና እነርሱን የተጠጉ ጥቂት አባላቱንና ተሽሎክላኪ ባለሀብቶችን ብቻ ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው፡፡

በዚህም የኢኮኖሚ ልማት መሠረታዊ  ፍልስፍናው በግል ምርታማነትና በግል ትርፍ ላይ ከተመሠረተውና ግለሰብን ማዕከል ከሚያደርገው ውድድራዊ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሥርዓት ጋር በፍልስፍናም በአካሄድም ይለያል፡፡ በውድድራዊ ነፃ ገበያ መርህ ራሱንና ቤተሰቡን የመቀለብ፣ የማልበስና የማስጠለል ግዴታና ኃላፊነት የግለሰቡ ነው፡፡ ውድድር በሽሚያ ሲተካ ብዙዎቹ ግለሰቦች ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ለመቀለብ፣ ለማልበስና ለማስጠለል አቅም ሲያጡ ወደ አመፅ ይገባሉ፡፡

‹‹ፈርሳ እንደ አዲስ የተገነባች ከተማ›› በመባል የተደነቀችውና የኢኮኖሚ ልማት ውጤት ታይቶባታል በተባለችው በአዲስ አበባ ሕንፃዎችና መንገዶች ግንባታ ጉልበቱን ያፈሰሰው ወጣቱ ነው፡፡ በግንባታው ወቅት የተከፈለው የጉልበቱ ዋጋ በምግብ፣ በልብስ፣ በመጠለያና በመዝናኛ ወዲያው አልቋል የማታ የማታ የተሠራውን ሕንፃም ሆነ መንገድ ይዘው የቀሩት ግን ባለሀብቱና መንግሥት ብቻ ናቸው፡፡ ወጣቱ ባዶ እጁንና ባዶ እግሩን ይዞ ቀረ፡፡ ጥቂት ገንዘብ የቆጠቡትም ሆቴል ቤቶችን፣ ቡቲኮችን፣ የውበት ሳሎኖችን፣ የድለላ ሥራዎችን የመሳሰሉ ጥቃቅን አገልግሎቶችን በመስጠት ይተዳደራሉ፡፡ የኢኮኖሚ ልማት በግንባታ ላይ ብቻ ሲያተኩርና መንግሥት መሪ ሲሆን ውጤቱ ይኼው ነው፡፡ መንግሥት ሲፈረጥም የኢኮኖሚው አንቀሳቃሽ ሞተር ግለሰብ ይኮላሻል፡፡

ስለዚህም የወጣቱ በተቀጣሪነት ሥራ ማግኘት ተጠቃሚነት በግንባታ ወቅት ብቻ ነበር፡፡ የግል ሕንፃ ከግንባታ በኋላ ለባለንብረቶቹ የኪራይ ገቢ አምጥቷል፡፡ የመንግሥት መንገድ ግንባታም ለተጠቃሚዎች ጥቅም ሰጥቷል፡፡ ለወጣቱ ቋሚ የሥራ ዕድል ግን አልፈጠረም፡፡ የኢኮኖሚ ልማት ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ካልተሸጋገረ ልማታዊ መንግሥት ወደ የጨነገፈ መንግሥት (Failed State) ይቀየራል፡፡

በገበያ ኢኮኖሚ የግላዊና የብሔራዊ ኢኮኖሚው መስተጋብር

ለወትሮው እነ የዓለም የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ ነበሩ የኢኮኖሚያችን ዕድገት ምስክሮች፡፡ ዛሬ እኛ እንመስክርላቸው ወይም እንጠይቃቸው፡፡ የኢኮኖሚ ዕድገት ከማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋት ጋር ተስተካክሎ ተረጋግጧል ሲሉን ከረሙ፡፡ ለመሆኑ የእነርሱ ማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋት ምንድነው? የውጭ ምንዛሪ እጥረቱ ነው? የዋጋ ንረቱ ነው? በመሬት ሽሚያ ለሁከት የዳረገውን የወጣቱን ሥራ አጥነት ነው የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋት ሲሉ የከረሙት፡፡

ስለአዲሶቹ ለጥንታውያን ኢኮኖሚስቶች (New Classical Economists) እና ስለ አዲሶቹ ለኬንሳውያን ኢኮኖሚስቶች (New Keynessian Economists) የግል ኢኮኖሚው መሠረታውያን ለብሔራዊ ኢኮኖሚው (Microeconomic Foundations of the Macroeconomy) ጽንሰ ሐሳቦችን እንደ ውኃ የጠጡት የዓለም የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ ባለሙያዎች፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የግል ኢኮኖሚ መሠረታውያን ፈጽሞ እንደሌሉ አያውቁም ነበር ብሎ ማሰብ ይከብዳል፡፡ ደግሞ ለድሃ አገር ብለው ስለሚንቁን አያስፈልጋቸውም ብለው ደምድመው ይሆናል፡፡ ከዚህ ሌላ ምንም ምክንያት ሊኖር አይችልም፡፡ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሥርዓት ልዩ ልዩ ገበያዎች የሆኑት የሠራተኛ፣ የመሬት፣ የካፒታልና የምርት ነፃ ገበያዎች ሳይኖሩ የገበያ ውድድር ባልነበረበት ሁኔታ፣ ስለምን ዓይነት የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋት ነበር ሲያወሩና ሲመክሩ ሲመሰክሩ የኖሩት? ወጣት ልጆቻችን ለኑሮ ዋስትና የመሬት ሽሚያ ላይ እስከሚወድቁ ድረስ በአሳሳች ምስክርነታቸው ዕድገታችሁ ያስቀናል ሲሉን ኖሩ፡፡ ዛሬስ ምን ሊሉን ይሆን?

ለእኔ እንደ አገር በቀል ኢኮኖሚስት የሚሰማኝና በብዙ ጽሑፎቼም እንዳስገነዘብኩት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የግል ኢኮኖሚው መሠረታውያን ለብሔራዊ ኢኮኖሚው እጅግ በጣም ደካማና ያስተናገድነው አመፅና ሁከትም ዋና መንዔዎች ናቸው፡፡ ይኼንን እምነቴን በልዩ ልዩ መንገዶች ባለፉት ሁለት ዓመታት አስተጋብቼአለሁ፡፡ ከዚህ በፊት በሪፖርተር ባቀረብኳቸው በርካታ ጽሑፎቼ የኢኮኖሚ ልማት እንደ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ አጋዥ መሣሪያ  እንጂ፣ እንደ ምትክ ወይም የመጨረሻ ግብ ተደርጎ መቆጠር እንደሌለበት አሳስቤአለሁ፡፡ አሁንም አሳስባለሁ፡፡ የኢኮኖሚ ልማት ለሰው ሥራን በማቅለል በቅልጥፍና እንዲሠራ ያግዘዋል እንጂ፣ እያንዳንዱን ሰው ከነቤተሰቡ አይመግብም፣ አያለብስም፣ መጠለያ አይሰጥም፣ መዝናኛም አይሆንም፡፡

ሰው ሠርቶ ራሱንና ቤተሰቡን ለመመገብ፣ ለማልበስ፣ ለማስጠለልና ለመዝናናት በነፃ ገበያ ውስጥ ተወዳድሮ ኑሮን ማሸነፍ ይጠበቅበታል፡፡ ለዚህም በነፃ ገበያ ሥርዓት ውስጥ የነፃ ገበያ መሠረታውያንን መለማመድ ከሌሎች ጋር መወዳደር፣ ማሸነፍና መሸነፍን መቀበል ከተሸነፈበት ወጥቶ ወደ የሚያሸንፈው መቀየር እንጂ፣ ገበያው አልተሳሳተም ማለት መቻል አለበት፡፡ አዲሱ ትውልድ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ መሠረታውያንን እንዲለማመድ ሳይሆን፣ በተፈጥሮ ያገኘሁትን መሬት ከሌላ አካባቢ የሚመጡ እንዳይጋሩኝ በሚል አደገኛ የሽሚያ አመለካከት እየተቀረፀ ነው፡፡ ዛሬ ብሔረሰብን ማዕከል አድርጎ የተጀመረ ይኼ መሬት የእኔ ብቻ ነው የሀብት ሽሚያ ነገ መንደርን ማዕከል አድርጎ ከነገወዲያ ቤተሰብን ማዕከል አድርጎ፣ ከዚያም ሲያልፍ ግለሰብን ማዕከል አድርጎ ይነሳል፡፡

ወጣቱን ትውልድ የሚያሳትፍ በውድድር ላይ የተመሠረተ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን  እንደገና እንደ አዲስ የሚገነባ ሥርዓት መሠረት ካልተጣለ በቀር፣ መንግሥት ጥቂቶች አልምተው ይቀልቡህ በሚል ፍልስፍናው ከቀጠለ የኢኮኖሚ ልማት ወደ ላይ ተሰቅሎ ሰማይ ቢነካም፣ ሀብት እንደ ዝናብ ከሰማይ ቢፈስም፣ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች በሙሉ ለመልማታችን ምስክርነት ቢጠሩምና ምለው ተገዝተው ቢመሰክሩም ቀውሱ፣ አመፁና ሁከቱ በሌላ ጊዜ ተመልሶ ለመምጣት ተላለፈ እንጂ አልተወገደም፡፡ በተለይም ደግሞ የቡድን መብትን የሚያቀነቅነው ፌዴራላዊ ሥርዓት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን አስመልክቶ በተነሳው ሁከት ላይ ነዳጅ አርከፍክፎ የአቀጣጣይነት ሚና ተጫወተ፡፡ መሬት የብሔራዊ መንግሥቱ ይሁን የክልል መንግሥታት፣ የአካባቢ መንግሥታት ይሁን ወይስ በቡድን የተደራጁ ወጣቶች መለየት እስከሚያቅት ድረስ ግራ አጋብቷል፡፡ ወደኋላ ተመልሰን እንደ ጥንት አባቶቻችን ‹‹በሚስትና በርስት ቀልድ የለም›› እያልን ነው፡፡ ኢትዮጵያዊ በገዛ አገሩ ለኑሮ ከክልል ወደ ክልል ሲሄድ የውጭ ኢንቨስተር ወይም ስደተኛ መጣ ሊባል ነው፣ ፓስፖርት መግቢያና መውጫ ቪዛም ሊያስፈልገው ነው፡፡

በ21ኛው ክፍለ ዘመን ሰው መሬት ለመያዝና ገበሬ ለመሆን የሚፈልገው ሌላ ዘመናዊ የኑሮ አማራጭ ሲያጣ ብቻ ነው፡፡ እንዳይሰደድ ዓለም አቀፍ ኬላዎች የተዘጉበት ወጣት መሰደድ ካልቻልኩ በክልሌ መሬቴ ላይ ከሰፈረው የሌላ ክልል ስደተኛና ኢንቨስተር ነጥቄ እወስዳለሁ አለ፡፡ ምን ይሁን ልሰደድ ብሎ አይኑ እያየ ባህር በላው፡፡ ዓይኑ እያየ የሰው አገር አሸዋ በላው፡፡ አሁን ደግሞ ዓይኑ እያየ የአገሩ ምድር ትዋጠው እንዴ? ለብሔራዊ ኢኮኖሚው የግል ኢኮኖሚው መሠረት መሆን ካልቻለ ብሔራዊ ኢኮኖሚው ከውጭ በሚገኝ ብድር የልማት ሥራና የውጭ ኢንቬስተሮች መጥተው በሚሠሩት የኢኮኖሚ ሥራ፣ ምን ያህል ቢምዘገዘግ ሸንበቆ አደገ አደገ ሲሉት ይሆናል፡፡ ሳይጠነክር የተመዘዘ ጎብጦ ቁልቁል ያድጋል፡፡

ስለግላዊ ኢኮኖሚና ብሔራዊ ኢኮኖሚ መስተጋብርና ትስስር መጽሐፍ ከማሳተምም ባሻገር፣ በሪፖርተር ተሟገት ዓምድ በርካታ ጽሑፎችን ለንባብ አቅርቤአለሁ፡፡ የሚሰማ አንብቦ ከባለሙያ ይሰማል፣ ይማራል፣ የማይሰማ እንደ ሰሞኑ ከመከራ በመከራ ይሰማል ይማራል፡፡ ከመከራም በመከራ አልሰማ ካለ ችግሩ የባሰ ይሆናል፡፡ በሃያ አምስት ዓመታት ውስጥ አንዱ ቢሊየነር ሌላው ያጣ የነጣ ድሃ የሆኑት በሽሚያ እንጂ በውድድር እንዳልሆነ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ መሠረታውያን በኢኮኖሚው ውስጥ አለመስረፅን ጠቅሼ፣ በጽንሰ ሐሳብም በመረጃም አስደግፌ አብራርቼአለሁ፣ አበክሬ አስጠንቅቄአለሁ፡፡ ግላዊና ብሔራዊ ኢኮኖሚያችን በሚል ርዕስ በ2007 ዓ.ም. ካሳተምኩት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ሁኔታ ባሻገር ይኼ ቀን እንዳይመጣ በሪፖርተር የ2007 ዓ.ም. ግማሽ ዓመትና የ2008 ዓ.ም. ሙሉ ዓመትን በአሥራ ስምንት ወራት ውስጥ አሥራ ሦስት የማስጠንቀቂያ ጽሑፎች በማቅረብ ተሟግቼአለሁ፡፡

የኢትዮጵያ መሪዎቿና ምሁሮቿ እንዳያስተውሉ የዘፈን፣ የስፖርት ወሬ፣ የተረት ተረት፣ ልብ ወለድና ወዝወዝ በሉ መናፍስት እንደ ፈርኦን ልባቸውን ቢያደነድኑትም፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት በሪፖርተር ላይ ስለኢኮኖሚው ከተናገርኳቸው ነገሮች አንዱም መሬት ጠብ አላለም፡፡

‹‹ሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ››

መንግሥት የአመፁ ምክንያት የወጣቱ በኑሮው ሁኔታ አለመርካት መሆኑን አውቆ ፀቡን ለማብረድ ለወጣቱ ሥራ ፈጠራ አሥር ቢሊዮን ብር ጥሪት አዘጋጅቼአለሁ ብሏል፡፡ ለወጣቱ ሥራ ፈጠራ ሲባል የተያዘውን ገንዘብ አስፈላጊነት ባምንም ስለውጤታማነቱ ያለኝን ጥርጣሬ ከመግለጽ ግን ወደ ኋላ አልልም፡፡ ጥርጣሬን በማሳየት ሳልወሰንም ጥሪቱን ከመያዝ ጎን ለጎን መታሰብ የሚገባቸውን ጉዳዮች አንድ ሁለት ብዬ አነሳለሁ፡፡ አንደኛ የተያዘው ገንዘብ  ወጣቱ በአካባቢው ባሉ ሌሎች አገሮች ጉልበቱን ሽጦ በሁለትና በሦስት ዓመት ውስጥ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ብር የሚኒባስ ታክሲ መግዣ ገንዘብ ይዞ መምጣት፣ በአገር ውስጥ ሠርቶ ከማደግ ይበልጥ እንደሚጠቅመው በተረዳበት ዘመን መሆኑ ወጣቱን ምን ያህል ሊያማልለው እንደሚችል ጥርጣሬ አለኝ፡፡ ለመነሻ ካፒታል የተበደረውን ለደላላ ከፍሎ ፈትለክ የማይልበት ምክንያት የለውም፡፡ 

በሁለተኛ ደረጃ ባዶ እጁን ከዩኒቨርሲቲ የተመረቀ ወጣት ለሥራ ፈጠራ ሃምሳ ሺሕ ብር ወይም መቶ ሺሕ ብር ብድር ከባንክ ቢያገኝ አሁን ባለው የገበያ ዋጋና የኑሮ ውድነት፣ ከወላጆቹና ከቤተሰቡ ትከሻ ወርዶ ምን በልቶ፣ ምን ጠጥቶ፣ ምን ለብሶ፣ የት አድሮ ነው የተበደረውን ገንዘብ ለኢንቨስትመንትና አዲስ ሥራ ፈጠራ የሚያውለው? ኢንቨስትመንትና ኢንተርፕረኑርሺፕ ከመሠረታዊ ፍጆታ መሟላት በኋላ ይመጣሉ እንጂ አይቀድሙም፡፡ በሦስተኛ ደረጃ ገንዘቡ ወደ ገበያችን ውስጥ ገብቶ የገንዘብ አቅርቦትን በማብዛት ሸቀጦችን ከማናርና ኑሮን የባሰ ከማክበድ በቀር ለወጣቱ ዘላቂ የኑሮ መሠረት የሚሆን ቋሚ ሥራ ይፈጥራል ብሎ ማሰብ ይከብዳል፡፡ ለነገሩ ቋሚ ሥራ የሚባል ነገር አገሪቱን ከከዳት ድፍን ሃያ አምስት ዓመት ሞልቷል፡፡ የያዙትን ሥራ ለዓመት ሁለት ዓመት ይዘው የሚቆዩ የከተማ ወጣቶች ስንቶች ናቸው? ሁሉም ነገር ‹አየር ባየር› ነው፡፡

በአራተኛ ደረጃ ኢንተርፕረኑር የመክሰር ሥጋትን ደፍሮ ገንዘቡን በመዋዕለ ንዋይ መልክ የሚያፈስ ያፈሰሰው ገንዘብም እንዳያከስረው ጥንቃቄ የሚያደርግ ሰው ነው፡፡ ቢከስር የማይጠየቅበትን የባንክ ገንዘብ ወስዶ የሚሠራ ሰው የትኛውን የመክሰር ሥጋትን ደፍሮ ነው ኢንተርፕረኑር ሊባል የሚችለው? አበዳሪ ባንኮችም በኪሳራ ሥጋት ምንም የሚያሳስባቸው ነገር የለም ገንዘቡ ቢከስር በኢትዮጵያ ሕዝብ ስም የተበላሸ ብድር ተብሎ ይያዛል በቃ፣ ጉዳዩ ይኼው ነው፡፡ በአምስተኛ ደረጃ ወጣቱ የሚያመርተው ምርት ምንድነው? ምርቱን የሚገዛው ሸማችስ ማን ነው? ሸማች ለመፍጠር የሸማቹን ገቢ ማሳደግ ቢያስፈልግ ሸማቹ ባደገው ገቢው የውጭ ምርት ከመሸመት ይልቅ፣ የወጣቶቹን ምርት እንዲሸምት ምን ማድረግ ይቻላል? ከኤክስፖርት ተኮር ፖሊሲዋ ጋር አገሪቱ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ ምርት ለመተካት ምን አድርጋለች? ቻይና እየከለከለቻት ይሆን እንዴ? ያጠራጥራል፡፡ የቀድሞው ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንዱስትሪዎች ሥራ ፈጠራ ሄዶ ሄዶ በየመንገድ ዳሩና በጠባብ ኪዮስኮች በጀበና ቡና ማፍላት ብርቅ ሥራ ተደመደመ፡፡ ቀጣዩ ሥራ ፈጠራና አጓጊ ኢንተርፕረኑርሺፕ በየመንገድ ዳሩ ጠላ ጠመቃ ሊሆን ይችላል፡፡

ኢንተርፕረኑርሺፕና ኢኮኖሚክስ

ኢንተርፕረኑርሺፕ ቁልፍ የኢኮኖሚክስ ቃል ቢሆንም፣ ከሥራ ፈጠራና ከኢንዱስትሪ ዕድገት ጋር ተገናዝቦ ብዙ የመባሉን ያህል ከኢኮኖሚክስ ጋር በተዛመደ ግን ምንም አልተባለም፡፡ ብዙ ሰዎች ዳር ዳሩን ይረግጣሉ እንጂ ኢኮኖሚክስን ይፈሩታል፡፡ ቁጥርን የሚወዱት የኪሳቸውን ብር ለመቁጠር ብቻ ስለሆነ ኢኮኖሚክስ ውስጥ ያለውን ቁጥር እንደ ጦር ነው የሚፈሩት፡፡ ኢንተርፕረኑር ካፒታል ገዝቶ፣ መሬት ተከራይቶ፣ ሠራተኛ ቀጥሮ፣ አደራጅቶና አቀናብሮ ይዞ ለመቆየትም ኃላፊነትን ወስዶ የኪሳራ ሥጋትን በመድፈር ሥራ የሚጀምር፣ የሚመራና የድርጅቱ ህልውናም በእርሱ ጥረት ላይ የሚመረኮዝ ነው፡፡ ከአራቱ የምርት ግብረ ኃይሎች (Factors of Production) አንዱ የሆነ ለአገልግሎቱ ክፍያ መደበኛ ትርፍ የሚያገኝ ሰው ወይም ባለድርጅት ነው፡፡ የኪሣራ ሥጋት ስላለበት ኢንተርፕረኑር እንደማይከስር በጥናት ሳያረጋግጥና ሳያምን በመላምት ብቻ ሌሎቹን የምርት ግብረ ኃይሎች አያደራጅም፣ የንግድ ሥራም አይጀምርም፣ ቢሆንም ሁሌም ጥናቱና ግምቱ ትክክል ይሆናል ማለት ስላልሆነ ለሚወስደው የኪሳራ ሥጋት ድፍረት ክፍያ ትርፍ ያገኛል፡፡

የሸማቾችን ፍላጎት እርግጠኛ ሆኖ መተንበይ በማይቻልበት ሁኔታ ለሚመረተው ዕቃ ገበያ መኖር አለመኖር በመረጃ ሳይረጋገጥ፣ ሌሎች ተመሳሳይ ምርት የሚያመርቱ ድርጅቶች ብዛትና የምርታቸው መጠን በማይታወቅበት ሁኔታ፣ በማይታወቁ የአደጋ አጋጣሚዎች ውስጥ ደፍሮ በተስፋ ግምት (Expectation) ሀብቱንና ጊዜውን በምርት ተግባር ላይ ያውላል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የእሳት አደጋዎች፣ የመሰረቅ አደጋዎች፣ የምርት መበላሸት፣ ወዘተ የመሳሰሉ የአደጋ አጋጣሚዎችም አሉ፡፡ የእሳት አደጋዎች፣ የመሰረቅ፣ የምርት መበላሸት፣ ወዘተ የመሳሰሉት አደጋዎች የመድን ዋስትና በመግባት ከኪሳራ ሊዳን ሲቻል ድርጅቱ የገበያውን ሁኔታ ባለማወቅ ወይም የተሳሳተ ግምት በመገመት ለሚደርስበት ኪሣራ ግን ዋስትና ሊሰጠው የሚችል የመድን ድርጅት አይኖርም፡፡

ስለዚህም ነው አንድ ኢንተርፕረኑር የማይተነበዩና የመድን ዋስትና ሊገባላቸው የማይችሉ የመክሰር ሥጋቶችን ደፍሮ ሀብቱን፣ ዕውቀቱን ጉልበቱንና ጊዜውን በአንድ በመረጠውና ተስፋ ባደረገው የሥራ ዓይነት ስላዋለ ነው፣ የሥጋት መካሻ የማምረት ተሳትፎ ክፍያ ዋጋ መደበኛ ትርፍ (Normal Profit) የሚያገኘው፡፡ ለዚህም የመንግሥት ፖሊሲን በገበያ ኢኮኖሚ ላይ ተፅዕኖ አጥንቶ የወደፊቱን ስለሚተነብይ ነው ኢኮኖሚክስ በከፊል የተስፋዊ ግምት ጥናት ጥበብ ነው የሚባለው፡፡ ኢንተርፕረኑር ከገቢው ላይ ለመሬት የኪራይ ወጪ፣ ለካፒታል የወለድ ወጪ ለሠራተኛ የደመወዝ ወጪ ከከፈለ በኋላ የሚተርፈው የራሱ ሥጋትን በመቋቋሙ የሚያገኘው መደበኛ ትርፍ ነው፡፡ ይኼ መደበኛ ትርፍም ከሥራ ሥራ ይለያያል፣ ከቴክኖሎጂ ጋርም ይቀያየራል፡፡

ኢንተርፕረኑር ለኪሣራ ሥጋት ከሚገኝ መደበኛ ትርፍ በላይ የሞኖፖል ትርፍም ያገኛል፡፡ እነዚህ የኢንተርፕረኑር መደበኛ ትርፍና የሞኖፖል ትርፍ መጠኖችን መለየትና ማወቅ፣ ከወጪና ከገቢ ዓይነቶች ጋር ማነፃፀር የኢኮኖሚክስ ጥናት መስክ ነው፡፡ ሞኖፖላዊ ትርፍ ለሥጋት ከሚያስፈልገው ትርፍ በላይ የሚገኝ ትርፍ ሲሆን፣ በቂ ውድድር በዘርፉ ውስጥ ባለመኖሩ ምክንያት በዘርፉ ውስጥ ያሉ ድርጅቶች አቅርቦትን በመቀነስና ዋጋ በማናር ሸማቾችን በዝብዘው ከሚገባቸው በላይ የሚያገኙት ትርፍ ነው፡፡ የሞኖፖሊ ድርጅቶች አቅም የሚፈጥረውም መንግሥት የመሬትና የካፒታል አከፋፋይ ሲሆን ነው፡፡ 

ይኼ የሞኖፖል ትርፍ ባለፉት ዓመታት እንደ ስኬት ተቆጥሮ በተቋቋምኩ በጥቂት ወራት ውስጥ ሚሊየነር ሆንኩ፣ በአሥር ሺሕ ብር ካፒታል ተነስቼ በዓመቱ አሥር ሚሊዮን ካፒታል አስመዘገብኩ እየተባለ ፕሮፓጋንዳ ሲነዛበትና ወጣቶችን ወደ ሥራ ለማስገባት ማማለያ ማስታወቂያ ሆኖ ቆየ፡፡ ጋዜጠኞች ሲጨፍሩና ሲያስጨፍሩ  ሲደልቁና ሲያስደልቁ ኖሩ፡፡ የሬድዮና ቴሌቪዥን መገናኛ ብዙኃን ፕሮግራሞች በሚሊዮኖች የሚለካ ትርፍ በሚያስቆጥሩ ሥራ ፈጣሪዎች ሪፖርት ተጥለቀለቁ፡፡ በአካፋ ካልተዛቀ ትርፍ ተገኘ አይባልም፡፡  ከዚያ በታች ማትረፍ ወደ ሥራ የሚጋብዝ አልሆን አለ፡፡ በመቶ ብሮች ይሠራ የነበረ ደላላ እንኳ በሚሊዮኖች ካልሆነ ሺዎችን የናቀበት ዘመን መጣ፡፡  በአንድ በኩል የሚበላ፣ የሚለበስና የሚታደርበት ጠፍቶ በጭንቅ እየኖሩ አቅመ ደካማ እናት አባት ጫንቃ ላይ ተቀምጠው በሌላ በኩል በአጭር ጊዜ ሚሊዮኖች ካላተረፉ ሥራን መናቅ የኢኮኖሚያችን እንቆቅልሽ ሆነ፡፡ ለነገሩ የኑሮ መክበዱ ራሱ ነው ሚሊዮኖች ካልተተረፈ ኑሮን ተስፋ አስቆራጭና ስደትን አስመራጭ ያደረገው፡፡ ሚሊዮን ትርፍ ፍለጋ ሲዞሩ ሚሊዮን ትርፍ ፈላጊ ያጋጥማል፡፡ ገበያዎቻችን ሚሊዮን ፈላጊዎች የሚተራመሱባቸው ሆነዋል፡፡ ሚሊዮን የሰበሰቡ ሚሊዮን ይዘራሉ፣ ሚሊዮን ያጭዳሉ፣ ሚሊዮኖችም ሚሊየነሮችን እያዩ ይናደዳሉ፣ ለአመፅም ይሰናዳሉ፡፡

ስለዚህም ተስፋ እንዲለመልም ኑሮ መቅለል አለበት ኑሮ እስከሚቀልም የኢኮኖሚው ዕድገት መገታት አለበት፡፡ ያለሚሊዮኖች የማንረካ ሰዎች አሥሮችም፣ መቶዎችም፣ ሺሕዎችም ገንዘብ መሆናቸውን ጠንቅቀን እስከምንገነዘብ በምናገኘው የላባችን ዋጋ እስከምንረካ ድረስ ኑሯችን ሊቀል ይገባዋል፡፡ ኑሯችን እንዲቀልልንም የአሥሮች፣ የመቶዎችና የሺዎች ብሮች የመግዛት አቅም ወደ ነበረበት ባይመለስም መጠጋት አለበት፡፡ ወደር የሌለው ትርፍ ፍለጋ በገበያዎች አለመጥራት፣ በሸማቹና በአምራቹ አላዋቂ መሆንና በአቅራቢው የበላይነት መያዝ ምክንያት የዋጋ አወሳሰን ሥርዓት በፍላጎትና አቅርቦት መጣጣም መስተጋብር  አለመሆን ምክንያቶች የመጣ ነው፡፡ ይኼ ሁኔታ ነው በአገራችን ለብሔራዊ ኢኮኖሚው የተመጣጠነ ዕድገት አጋዥ ማዕዘን ሊሆኑ የሚችሉት የግል ኢኮኖሚው መሠረታውያን አለመኖርን የሚያረጋግጠው፡፡ ይኼ ሁኔታም ነው በጊዜ ብዛት አመርቅዞ አመፅና ሁከት የሚፈጥረው፡፡

ይኼንን ደግሞ ያበረታታው መንግሥት ራሱ ነው፡፡ ኢንተርፕረኑር በአጭር ጊዜ ሚሊዮኖችን አትርፎ ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ ተሸጋግሮ ለመንግሥትም ለኢኮኖሚ ልማት የሚውል የድርሻውን ግብር ማስገባት ይጠበቅበታል ብሎ ሰበከ፣ ለፈፈ፡፡ ከነጋዴው ወስዶ ብዙ ግብር ሰብሳቢዎችን ቀጠረ፡፡ የኋላ ኋላ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ መሠረታዊ ጽንሰ ሐሳብና ቁልፍ ቃል የሆነው የኢንተርፕረኑርሺፕ መሬትና ካፒታልን እየቆነጠረ በሚሰጠው መንግሥታዊ የሕዝብ ሀብት አስተዳደርና በሶሻሊስት ሀብት ይዞታ ሥርዓት ውስጥ እንዴት እንደሚሠራ ግራ አጋባ፡፡ ነጋዴው ከሌለ ግብር ሰብሳቢውም አይኖርም፡፡ ሃያ አምስት ዓመት ሙሉ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን እየገነባን ነው ብለን ገበያዎቻችን ከመጥራት ወደ አለመጥራት፣ ከመደበኛ ትርፍ ወደ የሞኖፖል ትርፍ ተጓዙ፡፡ በምርታማነት ያልተደገፈ ሞኖፖላዊ ትርፍ ሀብታሙን ሲያከብር ድሃውን አደኸየ፡፡ የደኸየውም በአመፅ ሁኔታውን ካልቀለበሰ መኖር እንደማይችል አምኗል፡፡ አመፅን ትናንትም ሞክሯል፣ ዛሬም እየሞከረ ነው ነገም ሊሞክር ይችላል፡፡

ማጠቃለያ

ኢንተርፕረኑሮች ለኪሣራ ሥጋት መካሻ የሚሆን መደበኛ ትርፍ እያገኙ ወደ ማምረት ተግባር እንዲገቡ፣ ገበያዎች ካለመጥራት ወደ መጥራት እንዲጓዙ፣ ሸማቹና አምራቹ አዋቂ ተገበያዮች እንዲሆኑ፣ ዋጋዎች እንዲሰክኑ፣ ለአዳዲስ ድርጅቶች መቋቋሚያና የመነሻ ካፒታልና የመሬት ዋጋ ወጪ እንዲቀንስ፣ የኢኮኖሚው ዓመታዊ ዕድገት ለተወሰነ ጊዜ ዝቅ ማለት አለበት፡፡ ለዚህም ተስማሚ የጥሬ ገንዘብ ፖሊሲ መንደፍ ያስፈልጋል፡፡ ለሁለት አኃዝ የኢኮኖሚ ዕድገትና ለተመሳሳይ መጠን የዋጋ ንረት ሲባል እስከ ዛሬ በየዓመቱ ከሃያ እስከ ሃያ አምስት በመቶ ሲያድግ የቆየው የጥሬ ገንዘብ አቅርቦት (Money Supply) ከምርት ዕድገቱ ይልቅ ለዋጋ ንረቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ስላበረከተ በዓመት በተወሰነ መጠን ብቻ እንዲያድግ በማድረግ የታሰበው ዝቅ ያለ የዕድገትና የዋጋ ንረት ደረጃ ላይ ሊደረስ ይቻላል፡፡

የገንዘብ አቅርቦት መጠኑን ተከትሎ ዝቅ የሚለው የኢኮኖሚው ዕድገት የመንግሥት ፕሮጀክቶችን፣ የግል አምራቾችን፣ ሸማቾችን፣ ምን ያህልና ለምን ያህል ጊዜ እንደሚጎዳና እንደሚጠቅም በጥናት ሊረጋገጥ ይችላል፡፡ ዋናው ነገር እንደ ጥንቸል እየሮጡ ያላዩት ገደል ውስጥ ከመግባት እንደ ኤሊ ተጉዞ ግብ ላይ መድረስ ይሻላል ነው፡፡ የአንድ አገር ኢኮኖሚ ዕድገት ይቀንስ ማለት ቀላል ነገር እንዳልሆነ እገነዘባለሁ፡፡ የአገሪቱ የመካከለኛ ዘመን ዕቅድም አምስት ዓመታት ሙሉ በተከታታይ ባለሁለት አኃዝ ዕድገት ለማስመዝገብ ነው፡፡

በአጭር ጊዜ መካከለኛ ገቢ ለመግባት በህልም ቅቤ የመጠጣት አባዜ ናላችን ዞሮ፣ ድህነቱ ተባብሶ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ቀውስ ውስጥ ከመግባት ነባራዊ እውነቱን እንመልከት፡፡ በመሠረቱ ዕቅድ የሚታቀደው የኢኮኖሚውን ውስጣዊ መስተጋብሮች ነባራዊ ሁኔታን መርምሮ መሆን ቢኖርበትም፣ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዶቹ በኢኮኖሚ ልማት ትርጉማቸው የመንግሥትን መሠረተ ልማት መገንባትና ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ አገልግሎት የመስጠት አቅም መሠረት ያደረጉ እንጂ፣ የኢኮኖሚውን ነባራዊ ሁኔታ ያልመረመሩና ያላገናዘቡ መሆናቸውን ከዚህ ቀደምም በጽሑፎቼ አስገንዝቤአለሁ፡፡ ልማትን፣ የኢኮኖሚ ልማትንና የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን ፍልስፍናዎችና አካሄዶች ለያይተን ካልተገነዘብንና ለሁሉም በቂ ትኩረት ካልሰጠን ረጅም መንገድ አንጓዝም፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው Getachewasfaw240@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

Standard (Image)

አሳታፊ የሆነ ተቋማዊ አሠራር ለአገራዊ ችግሮች መፍቻ

$
0
0

በደጀኔ አሰፋ ዳምጠው

እንደሚታወቀው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገራችን በተከሰተው ከፍተኛ አለመረጋጋት ሳቢያ አገሪቱ ወደ ከፋ አደጋ ከመድረሷ በፊት ሰላም፣ ደኅንነትና መረጋጋትን ማስፈን ተገቢ ነው በሚል ዕሳቤ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል፡፡ አዋጁ ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያት ደግሞ ካለው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር በተለመዱት የሕግ አግባቦችና አተገባበሮች ብቻ አገርን ለማረጋጋት እንደማይቻል በመንግሥት ዘንድ መታሰቡ ነው፡፡ አዋጁም በፓርላማ ፀድቆ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ እነሆ አንድ ወር ገደማ ሆኖታል፡፡

ስለዚህ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ብዙ ተብሏል፡፡ አስተያየቶችም ከተለያየ አቅጣጫ ፈስሰዋል፡፡ ብዙ ሊባል ተፈልጎም ብዙ ሳይባል ቀርቶ ይሆናል፡፡ እንደኔ ዕይታ ይህ አዋጅ አገሬን በሚገባ የሚያረጋጋ፣ ሰላምን የሚያስመልስና ደኅንነትን የሚያረጋግጥ ከሆነ ሰላምና ደኅንነት ለአንድ አገር እጅግ ወሳኝ ነገር በመሆኑ ሊደገፍ የሚችል ነው፡፡ ሆኖም ግን አገር ከተረጋጋና ሰላም ከተመለስ በኋላ አግባብነት ላላቸው የሕዝብ ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ አጥጋቢ መልስ እንዲያገኙ በቂ መድረክ ሊፈጥር ይገባዋል፡፡ ከዚህ አንፃር ከታየ አብዛኛውን አገር ወዳድ ሊያስማማ የሚችል ይሆናል፡፡

የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለመተቸት ሳይሆን፣ መንግሥት አሳታፊ የሆኑ ተቋማዊ አሠራሮችን በሁሉም ረገድ ተግባራዊ እንዲያደርግ ለማሳሳብ ነው፡፡ ቢሆንም ግን እግረ መንገዱን ከአዋጁ ጋር የተያያዙ ጥቂት ነጥቦችን ለውይይት ያነሳል፡፡ ለምሳሌ በአገሪቱ የነበረው አለመረጋጋትና ቀውስ በአንድ ቀን እንዳልተፈጠረ ይታወቃል፡፡ ሁኔታዎችም አደገኛ አዝማሚያ ማሳየትና ለመቆጣጠር ፈታኝ ሊሆኑ እንደሚችሉ አመላካች ነገሮች መታየት ከጀመሩ መሰነባበታቸውን እንኳን የአገርን ሰላምና ደኅንነት ማስጠበቅ ተቀዳሚ ተግባሩ ለሆነው መንግሥት ይቅርና ለማንኛውም ሰው ግልጽ ነበሩ፡፡ ለወደፊት የሚሆን ትምህርትን ከመውሰድ አንፃር በዚህ ወቅት ቆም ተብሎ መጠየቅ ካለባቸው ብዙ ጥያቄዎች ሊኖሩ ቢችሉም ጽሑፉ ሦስቱን ለማንሳት ይሞክራል፡፡ እነኝህም፣

  1. በተወሰኑ አካባቢዎች የሕዝብ ጥያቄዎችና አለመረጋጋቶች በየፊናቸው መታየት በጀመሩበት ወቅት፣ ወቅታዊ መፍትሔዎችን አፈላልጎ ከመተግበር አንፃር የመንግሥት ሚና እንዴት ይታያል?
  2. ነገሮች ከተከሰቱ በኋላ በሒደት ሁኔታዎች ተባብሰውና ወዳልታሰበ አቅጣጫ ፈሰው አላስፈላጊ ጉዳቶችን ከማስከተላቸው በፊት ወይም የደረሰውን ኪሳራ ከመቀነስ አኳያ የመንግሥት ዝግጅትና ድርሻ ምን ሊሆን ይገባው ነበር?
  3. ሁኔታዎች እዚህ ደረጃ (የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ) ከመድረሳቸው በፊት ሕዝብን መሠረት ያደረጉና በተግባር የተፈተኑ አዋጭ ሥልቶችን በመጠቀም ረገድ መንግሥት ድርሻውን በሚገባ ተወጥቶ ነበር የሚያስብሉ ማሳያዎች አሉን? የሚሉት ናቸው፡፡

ምንም እንኳን ለእነዚህ ጥያቄዎች ሁሉም ከራሱ ዕይታ አንፃር እንደ መልስ የሚያቀርበው ነገር እንደሚኖር ባይጠረጠርም ጸሐፊው እንደ ዜጋ የራሱን አተያይ ለማካፈል ይሞክራል፡፡ የመጀመሪያ ነጥብ የሚሆነው ተቋማዊ አሠራሮችን ይመለከታል፡፡ በተለይም የሕዝብ ጥያቄዎችን በሚገባ መቀበልና ማስተናገድ ስለሚችል ወጥ እና ጠንካራ አሳታፊ ተቋማዊ አሠራር፡፡ ጽሑፉ ወደ ዋና ርዕሰ ጉዳዩ ከማለፉ በፊት እንደ መነሻ የሚቀጥለውን የመንደርደሪያ ሐሳብ ያቀርባል፡፡ እንደሚታወቀው የሚሊኒየሙ የልማት ግቦች የተነደፉት እ.ኤ.አ. በ2002 መጀመሪያ ላይ ሲሆን የተጠናቀቀው ደግሞ በ2015 ነው፡፡ ኢትዮጵያ የሚሊኒየሙን የልማት ግቦች ከመቀበልና ከማስፈጸም ጋር በተያያዘ የወጣውን የሚሊኒየም ስምምነት ሰነድ ከፈረሙትና ከተቀበሉት 189 አገሮች አንዷ ስትሆን፣ ግቦቹን ለማስፈጸምም መጠነ ሰፊ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ፣ የዜጎችን ተሳትፎና ልማታዊነትን የሚያረጋግጡ አገራዊ ፖሊሲዎች እንዲነደፉ በማድረግ፣ የሰው ኃይልና ቁሳዊ ካፒታል በማቅረብና በመፈጸም ከስምንቱ የምዕተ ዓመቱ ግቦች ስድስት ያህሉን በማሳካት አመርቂ ውጤት ማስመዝገቧ ይታወቃል፡፡

በተከታይነት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የተነደፈው ደግሞ ዘለቄታዊ የልማት ግቦች (Sustainable Development Goals) ይባላል፡፡ ይህም አሁን ካለንበት እ.ኤ.አ. ከ2016 እስከ 2030 በአጠቃላይ ለሚቀጥሉት 15 ዓመታት የሚተገበሩ ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያላቸው 17 የሚሆኑ የልማት ግቦችን የያዘ ነው፡፡ እ.ኤ.አ. በሴፕቴምበር 2015 በኒውዮርክ በመገኘት ይህንን የስምምነት ሰነድ ከፈረሙትና ከተቀበሉት አገሮች አነዷ ደግሞ ኢትዮጵያ ነች፡፡ ከእነዚህ ሉላዊ (ግሎባል) ግቦች ጋር በተጣጣመ መንገድ ደግሞ አገራችን የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ (1 እና 2) በማለት የሰየመቻቸውን የአምስት ዓመታት የልማት ዕቅዶችን በመንደፍ የመጀመሪያውን አጠናቃ ሁለተኛውን መተግበር ጀምራለች፡፡

ከአገራችን የልማት ዕቅድ ሰነዶች መረዳት የሚቻለው ደግሞ የተተለሙትን ግቦች ለማረጋገጥ ማለትም አገራችን በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊና በፖለቲካዊ ዘርፎች መልካም ስምና ገጽታ እንዲኖራት ተገቢውን ሥልት ነድፎ በፅናት መሥራትን እንደሚጠይቅና ይኸው እንደሚደረግ ነው፡፡ በተለይም የዜጎችን ተሳትፎና ልማታዊነትን ከሚያረጋግጡ ሥልቶች መካከል አንዱ በፊዚካላዊ ሀብቶች ላይ ብቻ ሳይሆን፣ በሰውና በማኅበረሰቡ ተቋማት ላይ አግባብ ያለው አሳታፊ የልማት ዕቅድ ዝግጅት አንዱ ነው፡፡ በመሆኑም አሳታፊ የሆነ የልማት ዕቅድ ዝግጅት የሚጀምረው ኅብረተሰቡ ካለበት ከታች ነው፡፡ የአካባቢው አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች፣ ነጋዴዎች፣ መሬት ያላቸውና የሌላቸው፣ ሥራ ያላቸውና የሌላቸው፣ ኑሮአቸውን በየትኛውም ዓይነት መንገድ የመሠረቱ፣ በየትኛውም ዕድሜ ክልል ያሉ፣ ሁሉንም ፆታዎች ያካተተ፣ ከየትኛውም ሃይማኖት ያሉ የማኀበረሰብ አባላት በሙሉ በዕቅድ ዝግጅት ከመጀመሪያው ጀምሮ መሳተፍ ይኖርባቸዋል፡፡ ምክንያቱም ሥራውን የሚሠሩትና ውጤቱን ይዘው ተጠቃሚ የሚሆኑት እነሱ ስለሆኑ ነው፡፡ በተመሳሳይም ሒደቱ እነዚህ የማኀበረሰብ አካላት በክትትልና ግምገማ ላይ ያላቸውን ድርሻ በውል ያገናዘበና ያሳተፈ ሊሆን ይገባዋል፡፡

የአሳታፊ ዕቅድና በጀት ብጀታ ጽንሰ ሐሳባዊ ትርጉም

አሳታፊ ዕቅድና በጀት ብጀታ የሚለውን ጽንሰ ሐሳብ ከመተንተናችን በፊት፣ ዕቅድ ማለት ምን ማለት እንደሆነ በጥቅሉ እንመልከት:: ማቀድ በአጭሩ ዛሬ ላይ ቆሞ ቀጥሎ መሆን ስለሚገባው ወይም የሚፈለገውን ነገር ሥልታዊ በሆነ መንገድ ማሰብ እንደማለት ነው፡፡ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ከማቀድ ጋር በተያያዘ እንዲህ የሚል አባባል አለ፡፡ “If you fail to plan, you plan to fail” ‹‹ማቀድ ካልቻልክ ለመውደቅ አቅደሃል›› እንደማለት ነው፡፡ ከዚህ አባባል መረዳት የሚቻለው ምንም እንኳን ያቀደ ሁሉ ሙሉ በሙሉ ይሳካለታል ማለት ባይቻልም አለማቀድ ግን የውድቀት ቅድመ ሁናቴ እንደሆነ ነው:: ስለዚህ ‹‹ዕቅድ›› ማለት የስኬት ወይም የውድቀት ቁልፍ ነገር መሆኑን እናስተውላለን::

በአጠቃላይ የማቀድ መሠረታዊ ጠቀሜታዎች ከብዙ በጥቂቱ የሚከተሉትን ያካትታል፡፡ ስለወደፊቱ አስቦ ለሚመጣው ነገር ለመዘጋጀትና ትክክለኛውን አቅጣጫ ለመያዝ፣ ወደፊት ምላሽ ሊሰጣቸው የሚገባቸውን ጉዳዮች ለማወቅና ቅድሚያ ሊሰጣቸው የሚገቡ ጉዳዮችን ለመተንተን፣ አንድ እንዲደረስበት የታለመ ጉዳይ ሊከናወን መቻል አለመቻሉን ለመገመት፣ ራዕይና ግብን ለመለየትና ትልቁን ውጤት ለማስመዝገብ፣ ለትግበራ የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን ለመለየት፣ ምን ያህል እንደሚያስፈልግና የት እንደሚገኙ ለማወቅ፣ እንዴት መሰብሰብ እንዳለብንና በአግባቡ ለመመደብና ለመጠቀም፣ ካሉት የትግበራ አማራጮች መካከል ለመምረጥና አንድን ነገር ለማድረግ ምክንያቱን ለማስቀመጥና የዕቅዱን ትግበራዎች በአግባቡ ለመምራትና በተረጋጋ ሁኔታ እንዲከናወን ማስቻሉ የሚሉት ተጠቃሾች ናቸው፡፡

በተያያዥም አሳታፊ ዕቅድና በጀት ብጀታ በአጭርና በቀላል አገላለጽ ከንድፈ ሐሳቡ ወይም ከጉዳዩ ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ቁርኝት ያለው ግለሰብ፣ በአካል ወይም በውክልና በጉዳዩ ምንነትና የበጀት ምደባ ሒደት ላይ ድምፁን የሚያሰማበትና ብሎም የውሳኔ ሰጭነት ሚናን የሚወጣበት ሥርዓት ነው፡፡ በመሆኑም ዕቅዱን ወይም ፕሮጀክቱን በበላይነት የሚያስተባብሩ አካላትና የሴክተር ባለሙያዎች ከላይኛው ክፍል እስከ ታች ያሉትንና የተገለሉ የማኅበረሰብ አካላትን፣ የልማት ሠራተኞችን፣ በጉዳዩ መሳተፍ የሚፈልጉ ዜጐችን፣ በንቃት ተሳታፊ የሆኑ አካላትንና ሌሎች ተያያዥ ተቋማትን ያሳትፋል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ዕቅዱ በአንድ አልያም በሁለት ግለሰቦች በበላይነት የሚሽከረከር ሳይሆን ማንኛውንም የማኅበረሰብ አካል ያማከለ ሊሆን ይገባል፡፡

አሳታፊ ዕቅድ በሐሳብ ደረጃ ያለው ምሥል ይህ ሲሆን ተግባራዊ እውነታው ግን ከዚህ የተለየ የሚሆንበት ሁኔታ አለ፡፡ ይኸውም ግለሰቦች አንድም ዕቅድ የማዘጋጀቱ ሒደት ከሚፈጥረው የሥራ ጫና ወይም ከሚወስደው ጊዜ አንፃር ፍላጐት ላያሳዩ ይችሉ ይሆናል፡፡ አልያም በዕቅዱ ወይም በዕቅዱ ትግበራ፣ ክትትልና ግምገማ ላይ ግለሰቦች ቀጥተኛ ተሳትፎ እንዲኖራቸው ባለመደረጉ ምክንያት የመገለል ስሜት ሊያዳብሩ ይችላሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ  የተሰወኑ ግለሰቦች የተሻለ ተሰሚነትና ድርሻ አላቸው በሚል ስሜት አንዳንድ ግለሰቦች ለዕቅድ ዝግጅቱም ሆነ ለትግበራው እንግዳ እንደሆኑ የሚቀሩበት ሁኔታ አለ፡፡ እንግዲህ በዚህና በመሰል ሁኔታዎች ነው አሳታፊ እንዲሆን የታስበው የዕቅድ ዝግጅት ከሁሉን አቀፍ ወደ ምንም አቀፍ የሚሸጋገረው፡፡

በዚህ ሁሉ መሀል ልብ ልንለው የሚገባን ቁልፍ ጉዳይ ቢኖር ‹‹አሳታፊ››  የሚለውን ሐሳብ ነው፡፡ አሳታፊ ስንል አንድን የሥራ ክንውን ከመሥራታችን በፊት የሌሎች ግለሰቦችን አስተያየት ማካተት ብቻ ሳይሆን፣ ግለሰቦቹ በሥራው ሒደት ላይ ዓይነተኛ ሚና እንዲኖራቸው የማድረግ ጽንስ ሐሳብ ነው፡፡ እውነተኛ የሆነው የአሳታፊ ሥነ ዘዴ የሚገለጸው የሁሉንም ተሳታፊ አካላት ስሜትና ሐሳብ ያገናዘበ እንደሆነ ነው፡፡ ይህ ማለት ሌሎች በሚያቀርቡት ሐሳብ ዙሪያ የሚደረግ ክርክርና በውይይቱ የሚካተቱና የሚቀሩ ሐሳቦች የሉም ማለት አይደለም፡፡ ይህም ሆኖ የሁሉም አካል ሐሳብና አመለካከት ሊደመጥና መድረክ ሊሰጠው ይገባል፡፡ ምክንያቱም በጉዳዩ ዙሪያ በዘርፉ ያሉ ባለሙያዎች አልያም በጣም የተማሩ ተብለው የሚታሰቡ ሰዎች ብቻ እንደ ውኃ ልክ የሚያስቀምጡት መፍትሔ ባለመኖሩ ነው፡፡ በመሆኑም እያንዳንዱ ታሳታፊ አካል ድርሻውን መወጣትና በሒደቱ ዙሪያ የውሳኔ ሰጭነት ሚናውን መጠቀም ይኖርበታል፡፡

የዜጎችን ተሳትፎ የሚያረጋግጡ አገራዊ የፖሊሲ ማዕቀፎች ዳሰሳ

ኢትዮጵያ ከሰው ሀብት ልማት ጋር በተያያዘ ብዙ የሚባሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሰነዶችና የአፍሪካ ኅብረት ስምምነቶችን ፈርማ የተቀበለች አገር ናት፡፡ የሕጎች ሁሉ የበላይ የሆነው የአገሪቱ ሕገ መንግሥት የአገሪቱ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ያላቸውን የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት እስከመገንጠል ያረጋገጠ ሕገ መንግሥት ነው፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሕጎችን ማውጣትና ተፈጻሚ እንዲሆኑ ማድረግ ሕገ መንግሥታዊ ሥልጣኑ ነው፡፡ የትኛውም ዓይነት አገራዊ ፖሊሲም ይሁን ከበጀት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን የሚያወጣውና የሚያፀድቀው የአገሪቱ ፓርላማ ነው፡፡ እነዚህና ሌሎች ሕገ መንግሥታዊ መብቶች ባሉበትና የዜጎችን ተሳትፎ የሚያረጋግጡና የሁሉም ፍላጎቶች በእኩል የሚስተናገዱባት አንዲት ኢትዮጵያን ለመፍጠር መንግሥት ያላሰለሰ ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ በተሳትፎ ላይ የተመሠረተ ልማታዊነት መንግሥት የነደፈው አገራዊ የልማት ሞዴል ሲሆን፣ የተፋጠነ የሀብት ፈጠራና ክምችት፣ እንዲሁም ኢንዱስትሪ መር የሆነ የልማት ፕሮግራም እንዲኖር ማረጋገጥ የሞዴሉ አንኳር ተልዕኮዎች ናቸው፡፡

የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ሰነዶች በተቀረፁበት ጊዜ ምንም እንኳን የኤስፒአርፒ እና የፓስዴፕ ተሞክሮና ልምዶችን እንደ ግብዓት ቢጠቀምም፣ ሒደቱ አሳታፊነት ባለው ሁኔታ መሠራታቸውና ብዙ ወረዳዎችን ያካተቱ መሆናቸው የተሳካ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ይህ ማለት ግን ሙሉ በሙሉ አሳታፊ ነበር ወይም እንከን አልባ ነበር ለማለት አይደለም፡፡ ምክንያቱም በሒደቱ ውስጥ በተለይም ዕድል የተነፈጋቸውና ለችግር ተጋላጭ የሆኑ የማኅበረሰብ አካላት ያልተካተቱ በመሆናቸውና የበጀት ብጀታው ሒደት አሳታፊነቱን በሚመለከት ገና ብዙ ያልተኬደበት መሆኑ ነው፡፡

በአጠቃላይ ሲታይ ግን ድሆችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፖሊሲዎች በመነደፋቸውና ድህነትን ታሪክ በማድረግ ላይ ያተኮሩ ፈርጀ ብዙ ተግባራት ላይ ወጪ በመደረጉ፣ ድሆች መሠረታዊ አገልግሎቶችን መጠቀም የሚችሉበት ሰፊ ዕድል የፈጠረላቸው ሲሆን፣ በማኅበራዊ ልማት ዘርፍ ለመተግበር በተቀመጡ ውጤት ጠቋሚዎች ትልሞች ላይ ከፍተኛ መሻሻልን አሳይቷል፡፡ መንግሥት የማኅበራዊ ልማትን ለማሻሻል ቁርጠኝነቱን ያሳየ ሲሆን፣ በተለይም መሠረታዊ ማኅበራዊ አገልግሎቶችን ተደራሽ ከማድረግ አንፃር እንቅስቃሴዎችን የአገሪቱን ወረዳዎች መሠረት ባደረገ ሁኔታ ከነብዙ ችግሮቹ በማከናወን ላይ ይገኛል፡፡

ከዚህ የምንረዳው አሳታፊ ዕቅድን ለማከናወንና በአገሪቱ ተግባራዊ ለማድረግ መንግሥት የሄደበትን ርቀትና ይህንን ሒደት የሚደግፍ በአገር ደረጃ እየተተገበረ ያለ የሕግ ማዕቀፍ መኖሩን ነው፡፡ ይህም መንግሥት ምን ያህል በአሳታፊነት ላይ የተመሠረተ ዕቅድ ለማውጣትና የተሻለ ግብን ለመምታት መታቀዱን ያሳያል፡፡ ከዚህ የፖሊሲ ማዕቀፍ የምንረዳው አሳታፊ የልማት ዕቅድ በውስጡ ከሚያቅፋቸው ዋና ዋና ተግባራት መካከል የዜጎችን ፍላጐትና ግብዓቶችን የመለየት ቅድመ ክንውን፣ ምዘና፣ ክትትልና ተያያዥ ግምገማዎችን፣ መዋቅራዊ አደራጀጀቶችን፣ ዕቅድና የዕቅድ አፈጻጸሞችን ያካትታል፡፡

ካለው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር የአሳታፊ ተቋማዊ አሠራር ጠቀሜታና አንድምታ

አሳታፊ የሆነ ተቋማዊ አሠራር ብዙ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ ከዚህ ጽሑፍ ዓላማና አገራችን ካጋጠማት ፈተና ጋር በተያያዘ ጽሑፉ ጥቂት ነጥቦችን ብቻ በዋናነት ይዳስሳል፡፡ ለምሳሌ መንግሥት አሳታፊነትን በመጠቀም ‹‹ጥያቄ አለኝ›› ከሚለው ሕዝብ ጋር በጥልቀት እንዲወያይ ያስችለዋል፡፡ በመወያያየትና በመደማመጥ ደግሞ በጋራ የታመኑባቸውንና ለአብዛኛው ጠቃሚ ይሆናሉ ተብለው የሚነሱ የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ለመተለም ያስችላሉ፡፡ እነዚህን የመፍትሔ አቅጣጫዎች ደግሞ ደረጃ በደረጃ በመተግበር ሁኔታዎችን ለማስተካከል የሚያስችል ምቹ ከባቢን እንዲፈጠር ያግዛል፡፡ ምቹ ከባቢ መፈጠሩ ደግሞ መንግሥት ከሚያስተዳደረው ሕዝብ ጋር የበለጠ እንዲጣበቅ ያስችለዋል፡፡ ሁሉም እንደ ባለድርሻ የራሱን የቤት ሥራ እንዲወስድ ያደርጋል፡፡ ይህም ሁሉም ዜጋ ለአገሪቱ ሰላምና ደኅንነት ዘብ እንዲቆምና የድርሻውን እንዲወጣ ያደርገዋል፡፡ በአንፃሩም ‹‹የአገሪቱን ሰላምና ብልፅግና አይፈልጉም›› ተብለው የተፈረጁ ኃይሎች በአገሪቱ ጉዳይ ጣልቃ መግባት እንዳይችሉ በር ይዘጋል፡፡ ይህ መሆን ከቻለ ደግሞ መንግሥት ሌሎች የልማትና አንገብጋቢ አገራዊ ጉዳዮች ላይ እንዲያተኩር ዕድል ይፈጥርለታል፡፡

ሆኖም ይህ አሳታፊ ተቋማዊ አሠራር በአገራችን በሁሉም ዘንድ ተግባራዊ ነበሩ የሚያስብሉ ሁኔታዎች አልነበሩም፡፡ በእርግጥ ብቅ ጥልቅ የሚሉ፣ በግብር ይውጣ መልክ የሚታዩ፣ ወጥነት (uniformity) የሌላቸው፣ በተወሰኑ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑና በሆነ ጊዜ ብቻ የሚከወኑ አሳታፊ የልማት ዕቅድ ዝግጅቶች ነበሩ፡፡ እነዚህ ተጀምረው የነበሩትም ቢሆን በተወሰኑ አካላት የሚፈጸሙ በመሆናቸው አሳታፊነት የሚባለው ጉዳይ በአስፈጻሚ አካላት ፍላጎት (goodwill) ላይ የተንጠለጠለ እንዲሆን አስገድዶታል፡፡ ከዚህ አንፃር አሳታፊነት በሁለንተናዊ መልኩ እንደ ተቋማዊ አሠራር (Institutionalization) በማስረፅና በሁሉም ረገድ በመተግበር ዙሪያ ጉልህ ክፍተቶች ተስተውለዋል፡፡ ይህም ዜጎች በአገራቸው በሚከናወኑ የልማት እንቅስቃሴዎች ባይተዋር እንዲሆኑና የባለቤትነት ስሜት እንዳይሰማቸው ያደርጋቸዋል፡፡

በሌላ አነጋገር አሳታፊነት እንደ ተቋማዊ አሠራር ቢሰርፅና ቢተገበር ኖሮ፣ በየጊዜው የሚነሱ የትኞቹንም ዓይነት የሕዝብ ጥያቄዎች ከሥር ከሥር በመፍታት ነገሮች እንዳይወሳሰቡ፣ ጥያቄዎችም ቅርፅ አልባ (Amorphous) እንዳይሆኑና ብሎም ወዳልተፈለገ አቅጣጫ እንዳይፈሱ ባደረጉ ነበር፡፡ የሕዝቡ ጥያቄ በሌላ ሦስተኛ ወገን እንዳይነጠቅና ማብሪያና ማጥፊያው ከቤት ውጪ ባልተሰቀለም ነበር፡፡ አሳታፊነት ቅድሚያ ቢሰጠው ኖሮ አገሪቱ ያለፈችበትን አጣብቂኝ ሁኔታ ቢያንስ መቀነስ ያስችሉ ነበር፡፡ ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ! በአንፃሩ መንግሥት የሕዝቡን ተሳትፎ በዘላቂነት ሳያረጋግጥ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ወዲህና ወዲያ ሲል ይስተዋላል፡፡ በነገራችን ላይ ‹‹ተሳታፊነት›› ከ‹‹ተጠቃሚነት›› እንደሚቀድም ልብ ሊባል ይገባዋል፡፡ ለአብነት የቀላል ባቡር መስመር ዝርጋታን በተመለከተ ምንም ውይይት ከሕዝቡ ጋር ሳይካሄድ፣ የባቡሩ ቀለም ምን እንዲሆን ትፈልጋላችሁ የሚል ጥያቄ ለነዋሪዎች መቅረቡ እንደ ትዝብት የሚጠቀስ ሆኖ ይታወሳል፡፡ ብቻ እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩ ተግባራት በመንግሥት ዘንድ በውል ባለመተግበራቸውና በሌሎች ምክንያቶች ሳቢያ ይመስላል አገሪቱ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ (ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን) ትተዳደር ዘንድ የዳረጋት፣ ወይም ላላስፈላጊ ኪሳራዎች ተጋልጣ እንድታልፍ ያደረጋት፡፡ ለምሳሌ ልማቱ የእኔ ነው ብሎ ቢያስብ ኖሮ ሕዝቡ ራሱ የጠፉትን መሠረተ ልማቶችም ሆኑ ፋብሪካዎች… ወዘተ ከጥፋት ይጠብቃቸው ነበር፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት ተከስተው የነበሩ አደገኛ ሁኔታዎችና አለመረጋጋቶች የቀን ተቀን መስተጋብር ሆነው በታዩበት ወቅት፣ በተግባር የተስተዋለው የመንግሥት ድርሻ አናሳ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ አግባብነት አላቸው ተብለው የታመነባቸውን የሕዝብ ጥያቄዎችን ለመፍታት የተወሰዱ ዕርምጃዎች ኢምንትነት (ዝምታውን ጨምሮ)፣ እግር በእግር ተከታትሎ ካለመፍታት ጋር ተያይዞ የታዩ ችግሮች ነበሩ፡፡ ይህንንም ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች በቴሌቪዥን ቀርበው የተናገሩት ክፍተት እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ ስለዚህ የመንግሥት ድርሻ ከዚህ የተለየ ሊሆን ይገባው ነበር ማለት ነው፡፡ አሊያም ለተነሱት ዘርፈ ብዙ ጥያቄዎች አንድ መልክ ብቻ እንዳላቸው በማሰብ ተመሳሳይ የሆነ መልስ ለመስጠት ባልተሞከረም ነበር የሚል ዕይታ አለኝ፡፡ በነገራችን ላይ ከየትኛውም የመፍትሕ ዕርምጃ በፊት ጥያቄዎችን በሚገባ መመርመርና መረዳት የመጀመሪያ ቁልፍ ተግባር ሊሆን ይገባዋል፡፡ ይህም አግባብነት ያላቸው፣ ውጤታማ የሆኑና በሕዝብ ተቀባይነት ያላቸውን የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ለመተለም ይረዳናል፡፡

ካልሆነ ግን ‹‹ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል›› እንደሚሉት ዓይነት ዘለቄታዊነት የሌለው መፍትሔን እንድንወስድ ሊያደርገን ይችላል፡፡ ይህም ‹‹ጉልቻ ቢለዋወጥ…›› እንደሚባለው ዓይነት እውነትና ቅንነት በሌለው መንገድ የፖለቲካ ትርፍን ለማግኘት በሚመስል መልኩ የግለሰቦች የኃላፊነት ቦታ ብቻ በመቀያየር፣ ዘላቂ መፍትሔ ይመጣል የሚልም ሆነ እውነተኛ ለውጥ እንደመጣ ለማሳያነት በቂ ማስረጃ ይሆናል የሚል ግምት የለኝም፡፡ አሁን በጨረፍታ እንዳየነው አገሪቱ በአንድ ዓመት ውስጥ ሁለት ጊዜ የካቢኔ ሚኒስተሮች ሹመትን አከናውናለች፡፡ በእርግጥ ይኼኛው ሹመት የ‹‹አቶ›› ዎችን ቁጥር ከማሳነስ ረገድ አመርቂ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ በዚህ ረገድ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች (በአብዛኛው በዶክተሮችና በፕሮፌሰሮች ከመመራታቸው ጋር ተያይዞ) የሚነሳውን ትችት ከመመከት አንፃር ጠቃሚ ሊሆን ይችላል፡፡ በእርግጥ አሁን የተነሱት ሚኒስትሮች በፖለቲካው ውስጥ የነበራቸውን የሕይወት ልምድም ሆነ ያላቸውን የፖለቲካ ‹‹ኮንስቲቱዌንሲ›› መሠረት ስንመለከት ብዙም እንዳልሆነ ልንገምት እንችላለን፡፡ በመሆኑም መነሳታቸው በፓርቲው ውስጥ ሊፈጥር የሚችለው ውጥረት እምብዛም እንዳልሆነ በማሰብም ሊሆን ይችላል እንደ ጦስ ዶሮ የፓርቲው ቤዛ የተደረጉት፡፡ በአንፃሩ አዳዲሶቹ ሹመኞች የመጡበት ብሔር ሞቅ ተደርጎ የቀረበ መሆኑን ሳስብና ካላቸው ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ልምድ ይልቅ ያቀረቧቸው ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ መተኮሩ ምናልባት ሌላ የፖለቲካ ጨዋታ ይኖረው ይሆን የሚል ሥጋትን ጭሮብኛል፡፡ በዚህ ክንውንም የሕዝቡ ጥያቄ እንደተመለሰ መገመት ለባሰ ስህተት የሚዳርግ ይመስለኛል፡፡ ‹‹ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ…›› እንዲሉ!

ከዚህ ይልቅ ግን ሕዝቡን በጥሞና ማዳመጥና ለሕዝቡ ጥያቄ የሚመጥን መልስ ለመስጠት መዘጋጀትና ቁርጠኝነት ማሳየት እንጂ፣ እንዲህ ዓይነቱ በውል ያልተጤነ ክንውን አንድ ዓመት እንኳን ሊቀጥል እንደሚችል ምንም ዋስትና ያለው አይመስልም፡፡ ካስተዋልነው የሹመት ሥነ ሥርዓት ኩነቶች በመነሳት ማለቴ ነው፡፡ እንደኔ ዕይታ መንግሥት የሕዝብ አባት ነውና በልበ ሰፊነት እየታገሰ፣ ሕዝብ የሚባለውን የአገር ምንነት እያከበረ፣ አገር የሚባለውን ትልቅ ምሥል አርቆ እየተመለከተ (እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል ሳይል)፣ የአገሪቱን ዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን በማክበርና በማስከበር የዜጎችን ደኅንነት መጠበቅ ተቀዳሚ ሥራው ማድረግ ይኖርበታል፡፡

ከላይ እንደተጠቀሰው የሕዝብን ጥያቄዎች (ጥያቄዎቹ በውጭ ኃይሎች የተቀመሩ አሊያም የተሳሳቱ ናቸው ቢባል እንኳን) እንደ ጥያቄ በማክበር ለጥያቄዎቹ ዕውቅና መስጠት፡፡ ከሕዝቡ ጋር በመነጋገገር እንደ ስህተት የሚነቀሱ ጉዳዮችን ማመን፡፡ ለጥያቄዎቹ ተገቢውን ምላሽ ደረጃ በደረጃ እየሰጠና ለማስተካከልም እውነተኛ ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት እንዳለው በማረጋገጥ በዋናነት ከሕዝቡ ጋር ያለውን ግንኙነት ጤናማና ጠንካራ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ ይህን ስል የትኛውም ለውጥ በተረጋጋና በሰከነ መንፈስ ሊሆን ይገባዋል የሚለውን ለማስመር ነው፡፡ በዚህም አገርን ከጥፋት ለመታደግ፣ ተዓማኒነት ያለውን የአሠራርም ሆነ የአመራር ሽግግር (ለውጥ) ዕውን ለማድረግ ይረዳል በሚል ነው፡፡ ካልሆነ ግን ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ›› የሚለው ብሂል እንደ ትንቢት በእኛ ላይ ሲፈጸም ይኖራል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ብሔራዊ የምክክር መድረኮች (National Dialogue Forums) ወይም የምክክር ጉባዔዎች በሚገባ ቢከናወኑ የተሻለ ነው እላለሁ፡፡ በእነዚህም ጉባዔዎች ጉዳዩ የሚመለከታቸው በአገር ውስጥም ከአገር ውጭም ያሉ ሁሉንም ወገኖች ማካተት፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችንም ተሳትፎ ማሳደግና ትርጉም ያለው እንዲሆን ማረጋገጥና በአገሪቱ መፃኢ ዕድል ላይ እንዲመክሩና ብሎም የውሳኔ ሰጭነት ሚና እንዲኖራቸው ማስቻል የማይተካ ሚና ይኖረዋል፡፡ ከዚህ ባሻገር በተለያዩ ምክንያቶች ሳቢያ እስከ ዛሬ ድረስ ከፖለቲካ ምህዋሩ ተገልሎ የቆየውን የሲቪል ማኅበረሰብ ተቋማትን (CSOs) በማቅረብና እንደ አንድ ጠቃሚ ባለድርሻ በመውሰድ፣ በአገሪቱ ጉዳይ ላይ እንዲወስኑ እውነተኛ ተሳትፎአቸውን ማረጋገጥ ይገባል፡፡ በነገራችን ላይ የሲቪል ማኅበረሰብ ተቋማት የሌሉበት የፖለቲካ እንቅስቃሴ ሁልጊዜም ዴሞክራሲያዊነቱ በጥያቄ ምልክት ውስጥ እንደወደቀ ነው፡፡

በተመሳሳይ በየፊናው ለተሰማሩ የአገሪቱ ምሁራን ቦታ በመስጠት ድምፃቸውና ምክረ ሐሳቦቻቸው እንዲሰማ ማስቻል የለውጥ ሒደት ፍሰቱን ይጨምራል፡፡ በመደብ የተደራጁ የሙያ ማኅበራትን (ለምሳሌ የመምህራን፣ የሚዲያ ባለሙያዎች፣ የሕግ ባለሙያዎች፣ የጠበቆች፣ የሕክምና ባለሞያዎች፣ የኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች፣ የደራሲያን፣ የአርቲስቶች፣ ወዘተ…) በሚገባ ማሳተፍ ጠቀሜታው የትየለሌ ነው፡፡  የምርምር ተቋማትንና በቁጥር ምንም ውስን ቢሆኑም ያሉትን ገለልተኛ የሆኑ የፖሊሲ ቲንክ ታንኮች ፖለቲካዊ ሚና እንዲጫወቱ ማስቻል የሒደቱን አመክንዮ ያረጋግጣል፡፡ ወጤቱም በሁሉም ዘንድ ተቀባይነት እንዲኖረውም ያግዛል፡፡ የእምነት ተቋማትም ነፃ በሆነ አሠራር ከእምነት ልጆቻቸው ጋር በመወያየት የሚያፈልቁትን ምክረ ሐሳብ በውል ማዳመጥና ማጤን ያስፈልጋል፡፡

ወጣቱ፣ ሴቱ፣ አዛውንቱ፣ የንግዱ ማኅበረሰቡ፣ አገር በቀል የማኅበረሰብ ተቋማት፣ ሕፃናትን፣ አካል ጉዳተኞችን፣ የጎዳና ወጣቶችን፣ ፆታዊ ተዳዳሪዎችንና ሌሎች የተለያዩ የማኅበረሰብ አካላትን የሚወክሉ ማኅበራትን በሚመለከታቸው ጉዳዮች ማሳተፍና ብሎም በዚህ ጽሑፍ ያልተገለጹ ሌሎች አደረጃጀቶችና ወገኖች ተሳትፎአቸውን ማሳደግና ድምፃቸው በሚገባ መሰማቱን ማረጋገጥ የለውጥ/ሽግግር ሒደቱን ያሳልጣል፡፡ ዋጋውንም ከፍ ያደርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም መንግሥት አፅንዖት በመስጠት ምላሽ እንዲያገኙ መጣር ያለበት በሠልፍ (በቡድን) ለሚቀርቡ ጥያቄዎች ብቻ ሳይሆን በግለሰብ ደረጃ ለሚመጡ አቤቱታዎችም ሊሆን ይገባዋል፡፡ በየትኛውም ተቋም ለመገልገል የሚመጡ ግለሰቦችን እንደ ትልቅ ባለጉዳይና የአገሪቱ ባለድርሻ በመመልከት እንደሚገባ መቀበልና ማስተናገድ መንግሥት ለዜጎቹ ያለውን የክብር ቦታ የሚያመላክት በመሆኑ፣ ዜጎች በመንግሥት ላይ የሚኖራቸውን አመለካከት የተሻለ እንዲሆን ያደርጋል፡፡ ሕዝብ ማለት የግለሰቦች ድምር እንደሆነ ልብ ይሏል፡፡

እዚህ ላይ  ከምሠራው ሥራ ጋር በተያያዘ አንድ ነገር ለአብነት ማንሳት እወዳለሁ፡፡ አሁን ባለንበት የበጀት ዓመት መንግሥት ለአገሪቱ ወጣት ‹‹የተሻለ›› የሚባል በጀት (አሥር ቢሊዮን ብር ተንቀሳቃሽ ፈንድ) በመመደብ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና የኢኮኖሚ ደረጃውን ለማሻሻል መታቀዱ ይታወቃል፡፡ ይህም በወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ተግባራዊ እንደሚሆን ተገልጿል፡፡ በእርግጥ ሚኒስትሩ ለአንድ ዓመት ገና ቢሮውን እየለመዱ ባሉበት ወቅት በዚህኛው ሹም ሽር ቢሻሩም፣ የዚህ አዲስ ተቋም መደራጀት ወጣት ላይ ተገቢውን ኢንቨስትመንት ለማድረግና አበክሮ ለመሥራት በመንግሥት ዘንድ የተያዘውን አቅጣጫና ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ተገልጿል፡፡ እንዲህ ዓይነት ጅምሮች ደግም ሊመሠገኑና በጣም ሊበረታቱ ይገባቸዋል፡፡ ሆኖም ግን ይህንን በጀት በተመሳሳይ ጉዳይ ላይ ብቻ ማፍሰስ የወጣቱ ችግር አንድ ዓይነት መልክ እንዳለው ብቻ ታስቧል ወደሚል መላ ምት ይወስደናል፡፡ ይህ ደግሞ ስህተት ነው፡፡

በእርግጥ የአገራችን አብዛኛው ወጣት የኢኮኖሚ ችግር ሊኖርበት እንደሚችል ዕሙን ቢሆንም ችግሩ ግን ኢኮኖሚያዊ ብቻ ነው ማለት አይደለም፡፡ ዘርፈ ብዙ ችግሮች አሉበት፡፡ እነዚህን አንገብጋቢ ተግዳሮቶችን በውል ለመተንተን ደግሞ ሁሉም ወጣት በያለበት አደረጃጀት ድምፁ ሊሰማለት ይገባል፡፡ ፍላጎቱ ምን እንደሆነ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ከዚያም የተሻለ የሚባልና የወጣቱን ትክክለኛ ፍላጎት መሠረት ያደረገ ዕቅድ ማውጣት ያስችላል፡፡ የተመደበውን በጀት በተመለከተ እንዴት መውረድ እንዳለበትም ሆነ አጠቃቀሙን በሚመለከት አዋጭ የሚባሉ የአተገባበርና የበጀቲንግ ሥልቶችን ለመንደፍ ያግዛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ወጣቱ ያለበትን ችግር ብቻ ሳይሆን ያለውንም ዕምቅ ኃይል እንዲገነዘብና እንዴት መጠቀም እንዳለበት ለማበረታታት መንገድ ከፋች ይሆናል፡፡ በዚህ ረገድ ወጣት ላይ የሚሠሩ የሲቪክ ማኅበራት ሚና ቀላል አይሆንም፡፡ ስለዚህም የሲቪክ ማኅበራትን ተሳትፎ ማበረታታትና ተቀራርቦ ለመሥራት የሚያስችሉ መድረኮችን መፍጠር ከመንግሥትም ሆነ ከማኅበራቱ ይጠበቃል፡፡

ምንም እንኳን ከላይ በተጠቃቀሱት ጉዳዮች ዙሪያ የጠለቀ ትንታኔ ማቅረብ ባልችልም፣ እንደ አንድ አገር ወዳድ ሰው ሳስበው ግን ባለፉት ጊዜያት መንግሥት በብዙ ጉዳዮች ዙሪያ በቂ ዝግጅት እንዳልነበረው ይሰማኛል፡፡ ስለዚህም የተነሱትን ጉዳዮች ዕውን ለማድረግ (ክፍተትን ለመሙላት) መንግሥት የቱንም ዓይነት መስዋዕትነት እንዲከፍል ሊያስገድደው ቢችልም፣ የሕዝብን ጥያቄ ለመመለስ ግን ከየትኛውም ጊዜ በላይ ፖለቲካዊ ዝግጁነትና የአመራሩ ቁርጠኝነት ይፈለጋል፡፡ ወጣም ወረደ ግን እነዚህና መሰል የተስተዋሉ ክፍተቶች እንደ ትምህርት ቢወሰዱና ተቋማዊ አሠራሮች በሚገባ ተግባራዊ ቢሆኑ፣ እንደ ሌሎች የሠለጠኑ አገሮችና መንግሥታት ችግሮቻችንን በመነጋገር ለመፍታትና አላስፈላጊ አገራዊ ጉዳቶችን ለመቀነስ ይረዱናል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ቸር እንሰንብት!

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dejene_assefa@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

 

Standard (Image)

የመልካም አስተዳደር ዕጦትና የሕግ የበላይነት ጥሰት በቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማኅበር

$
0
0

በመፍትሔ አፈላላጊ ስብስብ

ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽንና ከካፍ በፊት በጀግኖች አባቶቻችን የተመሠረተው አንጋፋ ክለባችን፣ ከዕድሜ ጠገብነቱና ካለው ወርቃማ የሰው ኃይል ብዛት ጋር ሲገመገም በቅርብ ከተቋቋሙ ወጣት ክለቦች በአደረጃጀትና በመልካም አስተዳደር ብዙ ተበልጦ ይገኛል፡፡

የተዋደቁለትና የተደፉለት መሥራች አባላቱ ቀና ብለው ሊያዩ ቢችሉ ኖሮ ልባቸው በሐዘን በተሰበረ ነበር፡፡ ክለቡ በየመርሐ ግብሩ ዋንጫ ቢሰበስብም ዛሬም እንደ ትናንቱ በዳረጎት እየተደጎመ መጓዙ የተጣለበት ግዴታ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ እንደ ዕድሜ ጠገብነቱ በፋይናንስ አቋሙ በራሱ ገቢ መተዳደር ሲገባው በግለሰቦች መልካም ፈቃድ ላይ ተንጠልጥሎ እንዲኖር በመገደዱ፣ ከእነዚህ ግለሰቦች በኋላ ከመፍረስ ሊታደጉት የሚችሉ በፍቅሩ ያበዱ ቁርጠኛ አባላቱ ብቻ ናቸው፡፡ ዛሬ ላይ ቆመን ግራና ቀኝ ብናስተውል የኢትዮጵያ ቡና፣ የደደቢት፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ የወልዲያ ከነማ ክለቦች ራሳቸውን በራሳቸው ገቢ ችለው እንዲገኙ ለማስቻል አኩሪና ደስ የሚያሰኝ ተግባራትን ደረጀ በደረጃ እየገነቡ ይገኛሉ፡፡

ግንቦት 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ቦርዱ ከሕገ ደንብ ውጪ የቀጠረው ኦዲተር እንኳን ሳይቀር ያለው ተንቀሳቃሽ ገንዘብ  315,000.00 ብር (ሦስት መቶ አሥራ አምስት ሺሕ ብር) እንደሆነ በአደባባይ ሲገለጽ፣ የአባላት መሰብሰቢያና መገናኛ ክለባቸው ከሳሪ ሆኗል ተብሎ ለውጭ ግለሰብ በኪራይ ሲሰጥና መሰብሰቢያ አጥተን በሜዳ ላይ ስንጣል ይኼ የአገር ቅርስ ክለባችን በአደገኛ የህልውና ጥያቄ ላይ ስለመገኘቱ የማይጠረጥር አባል ካለ አባል ነው ለማለት አያስችልም፡፡ ትናንት የተቋቋመው ወጣቱ ወላይታ ዲቻ ክለብ እንኳን 35,000 ከፋይና ተመዝጋቢ አባላት አፈራ ሲባል በ80 ዓመታችን 850 የማይደርሱ አባላት ምልዓተ ጉባዔ (50 በመቶ) ናቸው ስንባል የማያስደነግጠን አባላት ካለን ቆም ብለን በጥልቅ ልናስብ ይገባል፡፡

ከላይ የሚስተዋለው አሳሳቢ ሁኔታ ለምን ተከሰተ? ቢባል በአጭሩ ብልሹ አሠራር የፈጠራቸው በክለቡ የመልካም አስተዳደር ዕጦትና የሕግ የበላይነት መጣስ ዓይነተኛና ቁልፍ ክስተቶች ናቸው፡፡ ከመልካም አስተዳደርና ከሕግ የበላይነት መጣሶች እጅግ ጥቂቱን ለአብነት ለመጥቀስ ያህል በየዓመቱ መጠራት የነበረበት ጠቅላላ ጉባዔ ለአራት ተከታታይ ዓመታት አለመጠራት፣ ቦርዱ የሥልጣን ዘመኑ ካለፈ ከሁለት ዓመት ተኩል በላይ ቢሆንም ራሱን ከሕግ በላይ አድርጎ በሥልጣን ማቆየቱ፣ በየዓመቱ አባላት ዓመታዊ ዕቅድና የሒሳብ ሪፖርት ሰምተው በጠቅላላ ጉባዔ ማፅደቅና ውሳኔ መስጠት አለመቻላቸው፣ የክለቡን ኦዲተር የመሾም፣ የሥልጣን ጊዜ የመወሰን፣ አበል የመወሰን ሥልጣን የጠቅላላ ጉባዔው አባላት የሥልጣን ኃላፊነት ቢሆንም፣ በፕሬዚዳንቱና በቦርዱ ይኼ ሕግ ተጥሶ በራሳቸው ፈቃድ ኦዲተር መሾማቸው፣ ክለቡን ከ18 የማያንሱ ስፖንሰሮች ላለፉት 16 ዓመታት በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ቢለግሱትም ገንዘቡን ለማን እንደተሰጠ፣ ምን ያህል እንደተሰጠ፣ ምን ላይ እንደዋለ ከአባላት መደበቁ፣ ቦርዱ ክለቡ ራሱን በራሱ ገቢ እንዲተዳደር እንዲያደርግ ሕገ ደንቡ ቢደነገግም ተግባራዊ አለማድረጉ፣ የአሠልጣኞችና የተጨዋቾች ግዢና ክፍያ ለአባላት ድብቅ ሚስጥር መደረጉ፣ አባላት ዕምነት አጥተውበት በጠቅላላ ጉባዔ የተባረረ ሥራ አስኪያጅ ከሦስት ዓመት በኋላ እንዲመለስ መደረጉ፣ ክቡር ዶ/ር ሼክ መሐመድ አል አሙዲ ለስታዲየም ግንባታ 70 ሚሊዮን ብር ለፕሬዚዳንቱ ቢሰጡም የሜዳው አፈር ተቆፍሮ ከ12 ዓመት በላይ ተገትሮ መገኘቱ ዓይነተኛዎቹ ናቸው፡፡

በእዚህ አጭር ማብራሪያ በሙሉ ሊዘረዘሩ በማይችሉ አያሌ ምክንያቶች የክለቡ ህልውና በአደጋ ላይ መሆኑን በመገንዘባችን፣ ስድስት ነባር የክለቡ አባላት ቦርዱ እንዲያነጋግረን ብንጠይቅም ሰሚ በማጣታችን ሕገ መንግሥታችን በአጎናፀፈን የመጻፍና የመናገር መብት ተጠቅመን በተለያዩ ሚዲያዎች በክለቡ ያለውን የመልካም አስተዳደር ዕጦት ለማሳወቅ ተገደድን፡፡ አልፎ ተርፎም ከ160 በላይ አባላት በክለቡ ዙሪያ የተከሰቱትን ችግሮች ለመቅረፍ የሚያስችሉ አጀንዳዎች ቀርፀን ቦርዱ ለስብሰባ አቅርቦ እንዲያወያየን ጠይቀን፣ ጉዳዩንም ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አሳወቅን፡፡ በክለባችን የተንሠራፋውን ብልሹ አሠራርና መልካም አስተዳደር ዕጦት በመቅረፍ ክለባችን ዘመናዊ አደረጃጀት፣ አወቃቀርና ሲስተም ተላብሶ በራሱ ገቢ የሚተዳደር ክለብ እንዲሆን ለማድረግ አሁንም እየታገልን እንገኛለን፡፡

የክለባችን ፕሬዚዳንት አቶ አብነት ገብረ መስቀል ይኼንን የአባላት ጥያቄ ላለመቀበል ወስነው ተደፈርኩ በሚያስመስል ሁኔታ ኢትዮጵያ ጨዋነትን ድባቅ በመታ ቋንቋ በብሥራት 101.1 ሬድዮ ጣቢያ በግንቦት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. ዘለፋ፣ ስድብና ማንቋሸሽ ፈጽመውብናል፡፡ የተጠቀሙበትን ቋንቋ ከአንድ ታላቅ ክለብ መሪ የማይጠበቅ አሳፋሪ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ ምንም እንኳን እርሳቸውም ሆኑ የቦርዱ አባላት የሥልጣን ዘመናቸው ቢያልፍም ራሳቸውን በሥልጣን ሰይመው አቆይተዋል፡፡ እንዲሁም ፕሬዚዳንቱ በግንቦት 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ስብሰባ ጠርተው ሲዘልፉን ውለዋል፡፡ የእነዚህንም አስገራሚ ትዕይንት በዕለቱ የብዙ ሚዲያ ጋዜጠኞች በስብሰባው ተገኝተው ምስክር ሆነው ተመልክተውታል፣ አይተውም ዘግበውታል፡፡፡ በመሠረቱ የሥልጣን ዘመኑ ያለፈበት ፕሬዚዳንት ይኼንን ስብሰባ የመጥራትም ሆነ የመምራት ሕጋዊነት የለውም፡፡ ሌላው አስገራሚው ነገር ፕሬዚዳንቱ በዚሁ ስብሰባ ላይ ራሳቸውን ከአባላትና ከሕግ በላይ በማስቀመጥ፣ ‹‹እኔ ኢንተርናሽናል ነኝ፣ ዩሮ አለኝ፣ ምንም ልታመጡ አትችሉም፤›› በማለት በስብሰባው ላይ በድፍረት መናገራቸው ነው፡፡ ፕሬዚዳንቱ በተደጋጋሚ ላደረሱብን ስድብና ዘለፋ ይቅርታ እንዲጠይቁን ብንጠይቃቸውም ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ ከውስጣችንም አራቱን በማገዳቸው እግዱን እንዲያነሱ በጽሑፍ ብንጠይቃቸውም እንቢታን በመምረጣቸው ማንም ሰው ከሕግ በላይ ስላልሆነ ሕገ መንግሥታዊ መብታችንን ለማስከበር ሳንወድ በግድ ጉዳዩን ለሕግ አቅርበናል፡፡

በቅርቡም በክለቡ ውስጥ የተከሰተውን አምባገነንነትንና የመልካም አስተዳደር ዕጦት ለማስወገድ ጉዳዩን ለሕግ ለማቅረብ በዝግጅት ላይ እንገኛለን፡፡ በክለቡ ውስጥ የተከሰተውን የሕግ ጥሰትና የመልካም አስተዳደር ዕጦት በተመለከተ ላለፉት ስምንት ወራት ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፣ ለወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር፣ ለኢትዮጵያ እንባ ጠባቂ ተቋም ውሳኔ እንዲሰጡበት አመልክተን ጉዳዩን በመከታተል ላይ እንገኛለን፡፡ ሁኔዎችንም በግልባጭ ውሳኔ እንዲሰጡበት አመልክተን ጉዳዩን በመከታተል ላይ እንገኛለን፡፡ ሁኔታዎችንም በግልባጭ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በተደጋጋሚ አሳውቀናል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ አቶ አብነት ገብረ መስቀል ላደረሱብን ስድብና ማዋረድ ብሥራት 101.1 ሬድዮ ጣቢያ ተባባሪ ሆኖ በመገኘቱ ይቅርታ እንዲጠይቀን ፣በበኩላችንም ለተከበሩ የክለቡ አባላት ፕሬዚዳንቱ በእኛ ላይ ያቀረቡት መሠረተ ቢስ የሐሰት ውንጀላን ለማስተባበል በተላለፈው ፕሮግራም ላይ የበኩላችንን እንድናሰማ ብንጠይቅም ዝምታን በመምረጡ፣ ጉዳዩን ለኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ባለሥልጣን ከነካሴቱ አቅርበን አቤቱታችንን መርምሮ ሬድዮ ጣቢያው ጥያቄያችንን እንዲያስተናገድ ትዕዛዝ ቢሰጥም፣ ሬድዮ ጣቢያው ምክንያቶችን በመደርደር ተግባራዊ ባያደርግም ሕግ የበላይ ነውና ዕውን መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡

በመጨረሻም በእኛ በኩል መላው የክለቡ አባላትና ደጋፊዎች እንዲያውቁልን አጥብቀን የምናሳስበው፣

1ኛ በክለባችን ተንሠራፍቶ የሚገኘውን የሕግ ጥሰትና የመልካም አስተዳደር ዕጦት ለማስወገድና የክለባችን ህልውና ለማስጠበቅ በምናደርገው ሕጋዊ ትግል በሬዲዮ ፕሮግራሙም ሆነ በሌሎች የሕግ መድረኮች ክለቡን የሚጎዱ ሁኔታዎች ቢከሰቱ፣ ተጠያቂው ራሱን ከሕግ በላይ ያደረገው ፕሬዚዳንቱና ቦርዱ ብቻ እንደሚሆኑ፣

2ኛ የክለቡ የዓመታት ገቢና ወጪ በውጭ ኦዲተር ተመርምሮ እውነቱ እንዲወጣ እንደምንታገል፣  

3ኛ የሥልጣን ዘመናቸው ያለፋባቸው የቦርድ አባላትና ፕሬዚዳንቱ ሕገ ደንባችንን በጣሰ መንገድ ራሳቸውን በሥልጣን ላይ መሰየማቸው ተቀባይነት እንደሌለው ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፣ ለወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር አቤቱታችንን በተደጋጋሚ ያሳወቅን እንደመሆኑ ግቡን እስኪመታ እንደምንታገል፣

4ኛ የክለባችን ባለቤትና ዋናው የሥልጣን አካል አባላትና ጠቅላላ ጉባዔ ስለሆኑ፣ ጉዳዩ የሚመለከተው አካል ጠቅላላ ጉባዔ ጠርቶ በመምራት አባላት በክለቡ ችግሮች ዙሪያ ሐሳባቸውን በነፃነት አንሸራሽረው መፍትሔ እንዲሰጡበት በኢትዮጵያ ፉትቦል ፌዴሬሽን እስከ ካፍና ፊፋ ድረስ ለተፈጻሚነቱ እንደምንታገል፣

5ኛ በሚጠራውና በገለልተኛ አካል በሚመራው ስብሰባ ምርጫ አስፈጻሚ ተሰይሞ በሕገ ደንቡ መሠረት ሠርተው የሚያሠሩ፣ የክለቡን ሕገ ደንብ የሚያከብሩ የቦርድ አባላት ምርጫ እንዲካሄድ፣ ክለባችን ዘመናዊ አደረጃጀት ኖሮት ራሱን በራሱ ገቢ የሚያስተዳደር ክለብ እንዲሆን የበኩላችንን ጥረትና ትግል እያደረግን ስለሆነ፣ አባላትም ችግሮችን በጥሞና መርምረው የመፍትሔ አካል እንዲሆኑ ጥሪያችንን በትህትና እናስተላልፋለን፡፡

ግለሰቦች ያልፋሉ! ክለባችን ለዘለዓለም ተከብሮ ይኖራል!

የመፍትሔ አፈላላጊ ስብስብ

  1. ተስፋዬ ነጋሽ                      4. አንተነህ ፈለቀ
  2. ታደሰ መሸሻ                       5. ሥዩም ተፈሪ
  3. ዳንኤል ካሣ                        6. ማሙዬ ነጋ

ከአዘጋጁ፡ጽሑፉ የጸሐፊዎቹን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

Standard (Image)

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችን ይመለከታል?

$
0
0

በደጀኔ አሰፋ ዳምጠው

እንደምን ሰንብታችኋል? በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ይህን መጣጥፍ እንድጭር ገፊ ምክንያት የሆነኝ በጥቅምት 12 ቀን 2009 ዓ.ም በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ የወጣ የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት ማስታወቂያን መመልከቴ ነው፡፡ በእርግጥ ይህን ጽሑፍ ካዘጋጀሁ በኋላ ማስታወቂያው በሪፖርተር ጋዜጣም እንደወጣ አስተውያለሁ፡፡ ማስታወቂያው “ዲቪ 2018”ን ይመለከታል፡፡ በትልቁ! ከትልቅነቱ የተነሳም ስንት ፎንት እንደሆነ እንኳን ለመገመት ይከብዳል፡፡ የፊደላቱ መተለቅ ወይም መጥቆር (መወፈር) ደግሞ በሥነ ጽሑፍ ዓይን ሲታይ ለዚያ ጉዳይ የተሰጠውን አፅንኦት የሚገልጽ ይመስለኛል፡፡ ዲቪ የሚለው ምህፃረ ቃል ‘ዳይቨርሲቲ ቪዛ’ ማለትና የአሜሪካ አገር እንደሆነ ሲወራ ሰምቻለሁ፡፡ እስከማውቀው ድረስ ደግሞ የኢትዮጵያ ፖስታ የመንግሥት እንደነበረ ነው፡፡ የተለወጠ ነገር እንዳለ አላውቅም፡፡ ደግሞም አይመስለኝም፡፡ ይህንን የምለው በማስታወቂያው ውስጥ የተገለጹትን ፍሬ ነገሮች በመመዘን እንጂ “ዲቪ 2018”ን ለምን አስተዋወቀ በማለት አይደለም፡፡ ፍሬ ጉዳዮቹ ከትዝብቴ ጋር እነሆ፡፡

“ዲቪ 2018 በኢትዮጵያ ፖስታ ድርጅት ለአንድ ወር ብቻ” ይላል፡፡ በነፃ የሚሰጥ ይመስል! ለዚያውም የእኛው ፖስታ ድርጅት ከአሜሪካ መንግሥት ጋር በሼር የዲቪ ዕድልን ፈጥሮ የሚያስተዋውቅ ይመስላል፡፡ ከዚያም “ዲቪ 2018 ከመስከረም 24 እስከ… ስለሆነ በመላው አገሪቱ በሚገኙ የአገልግሎት መስጪያ ጣቢያዎች አገልግሎቱን ማግኘት የምትችሉ መሆኑን እየገለጸ፣ ተሳታፊ እንድትሆኑ በአክብሮት ተጋብዛችኋል፤“ ይላል፡፡ እስቲ ያሳያችሁ የዲቪ 2018ን ዕድል የአሜሪካ መንግሥትና ሕዝብ እንጂ የኢትዮጵያ ፖስታ ድርጅት ያዘጋጀው ዕድል እንዳልሆነ እየታወቀ አፉን ሞልቶ “ተሳታፊ እንድትሆኑ በአክብሮት ይጋብዛል’’ ሲል የልጁ ሠርግ አሊያም የልጁ ልደት ይመስል “…ማን በሠረገው ማን ይጋብዛል’’ አያስብልም? ለነገሩ አሁን አሁን የምናየው ነገር እኮ “…እከሌ ሊያገባ እከሌ ገገባ…“ ወይም “…የምጣዱ ሳለ የእንቅቡ ተንጣጣ…“ ዓይነት የሚመስል ከሆነ እኮ ሰነባብቷል! በማያገባን መግባት፣ የሰውን ጩኸት መቀማት፣ የሌላ ሰው ጉዳይን ማራገብ፣ ከባለቤቱ/ባለጉዳዩ በላይ ማቀንቀንን እንደ የሕይወታችን ፍልስፍና ስንከተል የጣድነው የራሳችን ዋና ጉዳይ እያረረ ተቸገርን ለማለት ነው፡፡

ወረድ ብሎ ደግሞ በትልቁ “ያስታውሱ“ ይለናል፡፡ የረሳችሁ እንደሆነ ወዮላችሁ! እንደ ማለት፡፡ ከዚያም በጣም አበክሮ “የዲቪ ፎርም የሚቆየው ለአንድ ወር ጊዜ ብቻ በመሆኑ በአስቸኳይ ፎርሙን በመሙላት ይላኩልን፤ …“ ይላል፡፡“ ጥድፊያው! ይህ አባባሉ ደግሞ አንድ ከአገር ስለመሰደድ አስቦ ለማያውቅ ዜጋ (እኔን ጨምሮ) በሕይወቱ በጣም አስፈላጊ የሆነ ነገር እያለፈው እንደሆነ እንዲሰማው ሊያደርግ የሚችል ሲሆን፣ በሌላ ጎኑ ደግሞ አገሪቱ ላይ በጣም መጥፎ አደጋ ስላለ “ከዚህ ለማምለጥ ዲቪ 2018”ን አሪፍ አጋጣሚ እንደሆነ የሚጠቁም ያስመስለዋል፡፡ ይባስ ብሎ “...እኛ በኢንተርኔት እናስተላልፋለን’’ ይላል፡፡  በእርግጥ እንደሚታወቀው በአገሪቱ ላይ ያንዣበበውን አደጋ ከማስቀረት አንፃር መንግሥት የማኅበራዊ ድረ ገጾችና ሞባይል ዳታን ላልተወሰነ ጊዜ ዘግቷል፡፡ በዚህ ውሳኔ ደግሞ አይደለም ተጠቃሚው ማኅበረሰብ መንግሥት ራሱ ደስተኛ እንዳልሆነ ይገመታል፡፡ አንገብጋቢ የአገር ጉዳይ ስለሆነበት እንጂ፡፡ ታዲያ ይህንን ደስ የማይል ሁኔታ እንደገና በማስታወቂያ መልክ ለማስታወስ ይሆን? ወይስ እናንተ ኢንተርኔት ቢቋረጥባችሁም እኛ ግን እንጠቀማለን ብሎ “እንቁልልጬ” ለማለትና ለማብሸቅ? አልገባኝም፡፡ በመጨረሻም በማስታወቂያው ግርጌ “መልካም ዕድል!’’ ይላል፡፡ ይህን ሲል በዚህ አገር መኖር መጥፎ ስለሆነ ‘ለጫማው በኋላ ይታሰባል ዋናው ማምለጡ ነው’ ለማለት ይሆን? ይህም አልገባኝም፡፡

ምንም እንኳን አብዛኞቻችን አሜሪካ ስለሚባለው አማላይ አገር፣ ብዙ ዕድሎች ስላሉበት አገር፣ ያደገና የበለፀገ አገር የምናውቅ አሊያም በስማ በለው የሰማን ወይም ለማየት የጓጓን ልንሆን እንችላለን፡፡ በአንፃሩ የእኛ አገር ድህነት ለማንም ግልጽ ነው፡፡ የሥራ ዕድሎች ጠባብ የሆኑባት፣ ኢፍትሐዊነት በሀብት ክፍፍልም ሆነ በብዙ ረገድ የሚታይባት፣ ሙስና፣ የመልካም አስተዳደር ዕጦት፣ የመረጃ እጥረት፣ የዋናተኛ እጥረት፣... ብቻ እንደ ኩዋሻኮር ብዙ ዕጦትና እጥረት ያሉባት አገር እንደሆነች ይታወቃል፡፡ እነዚህንና ሌሎች ተግዳሮቶችን ለመቅረፍም እንደ አገር ብዙ ሠርተናል፣ ተጨባጭ ለውጦችም ተመዝግበዋል፣ ብዙም ይቀረናል፡፡ ይህንንም ሕዝቡ ያውቃል፣ መንግሥትም ያምናል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ጽሑፉ በዋናነት የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት የመንግሥት መሥሪያ ቤት ሆኖ ሳለ ከአገር እንድንሰደድ ለምን ያበረታታል የሚለውን ለመጠየቅና እንዲህ ዓይነቱ የስደት መልዕክት በመንግሥት አፍ ሲራገብ “የአፋጣኝ ጊዜ የስደት አዋጅ’’ አይመስልምን? የሚለውን ለመጠቆም ይፈልጋል፡፡

በእርግጥ በድህነትና መሰል አገራዊ ችግሮች (Pushing Factors) እና በውጭ ባሉ ሳቢ ምክንያቶች (Pulling Factors) ሳቢያ ብዙ ወገኖቻችን እንደተሰደዱ እናውቃለን፡፡ በስደትም የብዙ ዜጎቻችን ሕይወት ጠፍቷል፣ ጉልበታቸው ተበዝብዟል፣ ሰብዕናቸው ተዋርዷል፣ ለአካላዊና ለአዕምሯዊ ጉዳት ተዳርገዋል፡፡ መንግሥትም ስደትን (በተለይ ሕገወጥ ስደትን) እንደ ዋና አሳሳቢ ችግር ግንዛቤ ውስጥ አስገብቶ ዘርፈ ብዙ ምላሾችን ለመስጠት እየጣረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ለዚህም ነው በማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት የሚመራና ሴቶችና ሕፃናት ሚኒስቴርን፣ የፌደራል ፖሊስን፣ የፍትሕ አካላትንና ሌሎች የሚመለከታቸው ተቋማትን ያካተተ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው፡፡ በመሆኑም መንግሥት ከኅብረተሰቡ ጋር በመተባበር ሕገወጥ ደላሎችን አሳዶ በመያዝ ለሕግ ያቀርባል፡፡ ውስን ቢሆኑም የሥራ ዕድሎችን ለመፍጠር ይሞክራል፤ በስደት አስከፊነት ዙሪያ የዜጎችን ንቃተ ህሊና የማሳደግ ሥራዎችን ያከናውናል… ወዘተ፡፡ በአንፃሩ በሕጋዊ ይሁን ሕገወጥ መንገድ ከአገር የተሰደዱ ዳያስፖራዎች ወደ አገራቸው እንዲገቡና (ከቻሉ) እንዲያለሙ ካልሆነ ግን በነፃነት መኖር እንደሚችሉ እያበረታታ ይገኛል፡፡  

ይህ በእንዲህ እንዳለ የፖስታ ድርጅቱ እንዲህ ዓይነቱን ማስታወቂያ ለመሥራት የተነሳሳው በምን ምክንያት ሊሆን ይችላል የሚለውን ለመመለስ የተለያዩ መላ ምቶችን መዳሰስ ተገቢ ይመስላል፡፡ ቀዳሚ መላ ምት የሚሆነው ድርጅቱ ይህን ማስታወቂያ ሲሠራ በእንዲህ ዓይነት መንገድ ሊታይ ይችላል ብሎ ስላልገመተ ይሆናል የሚል ነው፡፡ ይህ መላ ምት ትክክል ነው ካልን ደግሞ በማስታወቂያ ዙሪያ በሚሠሩ የዘርፉ ምሁራን ዘንድ እንደ ተራ ስህተት የሚታይ አይሆንም፡፡ ምክንያቱም ማስታወቂያ (Promotion/Advertisement) እንደ አንድ ሳይንሳዊ የሙያ ዘርፍ የራሱ የሆኑ አሠራሮች፣ ሥልቶችና ሥነ ምግባሮች ያሉት በመሆኑ አንድ ማስታወቂያ ሲሠራ በጥናት የተደገፈ፣ ከብዙ አቅጣጫ የተመዘነና ነባራዊ ሁኔታዎችን ያገናዘበ… ወዘተ ሊሆን ይገባዋል ከሚሉት መርሆች አንፃር ማለት ነው፡፡ ይህም ያስፈለገበት ምክንያት ደግሞ ምንም እንኳን በማስታወቂያው ማስተላለፍ የተፈለገው ጉዳይ (ከሠራው አንፃር) ጠቃሚ ሊሆን ቢችልም፣ በሌላ መልክ ሊተረጎም አሊያም ያልታቀደበትን አሉታዊ መልዕክት ሊያስተላልፍ የሚችልበት አጋጣሚ በመኖሩ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የፖስታ ድርጅቱ ከተጠያቂነት የሚድን አይመስልም፡፡

ሌላኛው መላ ምት በወቅቱ ካለው የአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ አንፃር መንግሥት ፌስቡክና መሰል ማኅበራዊ ድረ ገጾችን መዝጋቱን ተከትሎ የኢትዮ ቴሌኮም ገቢ ከመቀነሱ ጋር ተያይዞ የሚነሳው ነጥብ ነው፡፡ ሆኖም ግን በዚህ መልኩ የመንግሥት ገቢን ለማሳደግ በሚል ከሆነ ገቢን ማሳደግ ከዜጎች ሕይወት የሚቀድም አይሆንም፡፡ በመንግሥትም ደረጃ እንዲህ ይታሰባል ብዬ ጭራሽ አልገምትም፡፡ ከሆነ ግን ማስታወቂያው በእንዲህ ዓይነት መልኩ ሊሠራ አይገባም ነበር እላለሁ፡፡ አንዳንዶቻችን ደግሞ ይኼኛው የዲቪ ማስታወቂያ ስለአሜሪካ ስለሆነ “ስደት”ን አይመለከትም ወይም “ስደት” የሚባለው ጉዳይ ለዓረብ አገር ብቻ ነው የሚል እሳቤ ሊኖረን ይችላል፡፡ በእርግጥ “ሕጋዊ” ስደት አለ፡፡ “ሕገወጥ” ስደት አለ፡፡ እዚህ ላይ ግን “ሕጋዊ” ወይም “ሕገወጥ” ስደት ስንል ከአገር የሚወጣበት ሁኔታ በሕጋዊ ወይስ በሕገወጥ መንገድ የሚለውን ለመጠቆም እንጂ፣ በሕጋዊም ይሁን በሕገወጥ መንገድ የሚደረግ ስደት ሁሉም ስደት ነው፡፡ እንኳንስ ዜግነትን ጭምር የሚያስቀይረው በዲቪ የሚደረገው ስደት፡፡ አለቀ!

ገሚሶቻችን ደግሞ የእኛ ፖስታ አገልግሎት የዲቪ ማስታወቂያውን የሠራው እንደ ህንድ ባሉ አገሮች የሚከናወን የአዕምሮ ፍልሰት (Braindrain) ተብሎ የሚታወቀውን ፍልሰት እንጂ ተራ ስደትን ለማበረታታት አይደለም እንል ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን የአዕምሮ ፍልሰትም ቢሆን ስደት እንጂ ሌላ ስም የለውም፡፡ የእኛ ዜጎች ወደ አሜሪካ የሚሄዱት በዚህኛው ምክንያት ነው ተብሎ ከታመነ ደግሞ፣ በዚህ ጊዜ የእኛ አገር ዘርፈ ብዙ እውቀቶችን፣ ብዙ አዋቂዎችን፣ ተመራማሪዎችንና የቴክኖሎጂ ሽግግሮችን… እየፈለገች ያለችበት ሁኔታ ስላለ ከሌሎች ይልቅ የተማሩ ሰዎች ፍልሰትን እጅግ አጥብቃ ትቃወማለች እንጂ ታበረታታለች የሚል እምነት የለኝም፡፡ በዚህ አግባብ ከታየ የአዕምሮ ፍልሰት የሚባለው መከራከሪያ ነጥብም አዋጭ አይሆንም ማለት ነው፡፡ በአጠቃላይ ወደ ዓረብ አገር (በአውሮፕላን፣ በባህር፣ በኮንቴይነር፣ በእግር…) መሄድ ስሙ ስደት ከሆነ ወደ አሜሪካ (በአውሮፕላን፣ በሱዳን፣ በኬንያ፣ በደቡብ አፍሪካ፣…) የሚደረግ ጉዞ ከስደት ውጪ ሌላ ስያሜ ሊኖረው አይችልም፡፡ በሱዳን፣ በኬንያ፣… ስል ግን ከላይ እንደተጠቀሱት የመጓጓዣ ዓይነቶች እንዳልሆኑ ይታወቅልኝ፡፡

“ስደት” በሚባለው ጽንሰ ሐሳብ ዙሪያ አንድ ሌላ መከራከሪያ ነጥብ ሊነሳ ይችላል፡፡ ይህም “ስደት” የሚባለው ኩነት በደሃ አገሮችም ሆነ በበለፀጉ አገሮች ከጥንት ጀምሮ የነበረ፣ አሁንም ያለና ወደፊትም የሚኖር ዓለም አቀፋዊ መስተጋብር መሆኑ ነው፡፡ በመሆኑም የእኛ አገር ዜጎች ቢሰደዱ ምን ነውር አለው የሚል ተጠይቅ ሊያስነሳ ይችላል፡፡ ከዚህ አንፃር ከታየ የእኛ አገር ዜጎች መሰደዳቸው ምንም ነውር ላይኖረው ይችላል፡፡ ሆኖም ግን አገራችን ካሏት ዋና ዋና ሀብቶችና የወደፊት የዕድገት ዓምዶች መካከል በዋናነት ሊጠቀስ የሚችለው የሰው ሀብቷ ነው፡፡ በተለይም ከአገሪቱ አጠቃላይ ሕዝብ ብዛት ከ40 እስከ 45 በመቶ የሚሆነውን ቁጥር የሚይዘው የአገሪቱ ወጣት ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል፡፡ በዚህ አግባብም ይመስላል መንግሥት በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የወጣቱን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ደረጃ ለማሻሻልና ወጣቱ የልማት ተዋናይ እንዲሆን የሚያስችሉ የመፍትሔ ዕርምጃዎችን እየወሰደ ያለው፡፡ ለምሳሌ በድኅረ ምርጫ 2007 በተደረገው የሚኒስትር መሥሪያ ቤቶች አወቃቀር ከሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር ተገንጥሎ “ወጣቶች እና ስፖርት“ የተሰኘ ተቋም ከጠፋበት ተመልሶ እንደ አዲስ መዋቀሩን ልብ ይሏል፡፡ ይህም በወጣቶች ዙሪያ ተገቢውን ኢንቨስትመንት ለማድረግና አበክሮ ለመሥራት በመንግሥት ዘንድ የተያዘውን አቅጣጫና ቁርጠኝነት የሚያሳይ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ የዚህ ተቋም መደራጀትም በአገሪቱ ያለውን ሰፊ የወጣት ቁጥር ተደራሽ ለማድረግም ሆነ ዘርፈ ብዙ ተግዳሮቶቹን ለመቅረፍ የሚጫወተው ሚና ቀላል አይሆንም፡፡ ይህ ውሳኔም በብዙ የወጣት አደረጃጀቶች፣ የወጣት ሲቪክ ማኅበራትና በጎ አድራጎት ድርጅቶች ዘንድ “ወጣቶች በቂ ትኩረት ያገኛሉ” የሚል ተስፋን ከመጫሩም በላይ ለመንግሥትም አድናቆትን አትርፎለታል፡፡ የወጣቱ መሻት ተሳክቶ ማየት ውስጤ ነው!

አሁን ባለንበት የበጀት ዓመት ደግሞ በዚህ ችግር (ስደት) ዓይነተኛ ገፈት ቀማሽ ለሆነው የአገሪቱ ወጣት “የተሻለ“ የሚባል በጀት (10 ቢሊዮን ብር) በመመደብ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና የኢኮኖሚ ደረጃውን ለማሻሻል መታቀዱ ይታወቃል፡፡ ምንም እንኳን በዚህ በጀት ሁሉንም የወጣት ጉዳዮች ይመልሳል የሚል እምነት በመንግሥትም ዘንድ ባይኖርም እንደ መልካም ጅማሮ ግን ይበል፣ እሰይ የሚያስብል ነው፡፡ እነዚህ ጅምሮች የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ከተፈለገ ደግሞ ከየትኛውም ዕርምጃ በፊት የጉዳዩ ባለቤት የሆነውን ወጣትም ሆነ በየደረጃው ካሉ የወጣት አደረጃጀቶች፣ ሲቪክ ማኅበራትና በጎ አድራጎት ድርጅቶች ጋር መምከር ፋይዳው አያጠያይቅም፡፡ በዚህም ወጣቱ የእኔ የሚለው ዕቅድ እንዲኖረውና የባለቤትነት ስሜት እንዲፈጠርበት ከማድረጉም በላይ፣ የበጀት ሥርዓቱም ግልጽና ተጠያቂነት ያለው እንዲሆን ያግዛል፡፡ በሒደቱም ሁሉም አካል ተሳታፊ ስለሚሆን የወጣውን የጋራ ዕቅድ የመሳካት ዕድል ከፍ ያደርገዋል፡፡ ስለዚህ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴርም ሆነ ሌሎች ተቋማት ሊያገለግሉዋቸው የቆሙላቸውን የማኅበረሰብ ክፍሎችና የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላት በዕቅድና በጀት ዝግጅት፣ በትግበራ፣ በክትትልና ግምገማ ሒደቶች በማሳተፍና የውሳኔ ሰጪነት ሚናቸውን በማሳደግ የበለጠ ውጤታማ እንደሚሆኑ (እግረ መንገዴን) ለማመልከት ነው፡፡ ካልሆነ ግን “እኔ አውቅልሃለሁ” በሚል እሳቤ የሚወጡ ዕቅዶች ማጣፊያ ያጠራቸው መዘዞችን ወልደው ምን ዓይነት የችግር ብፌ እንዳስነሱብን ማስታወስ አያሻኝም፡፡ 

ብቻ ወደ ተነሳንበት ዋና ጉዳይ እንመለስ፡፡ ስደት! መንግሥት ስደትንም ለመቀነስ ይረዳ ዘንድ ነው “ወጣቱ በአገሩ ሠርቶ፣ በአገሩ መለወጥ ይችላል”፣ “ከሠራን መለወጥ እንችላለን” በሚሉ መፈክሮች አገራዊ ንቅናቄን ለመፍጠር እየሞከረ ያለው፡፡ በዚህ ርብርብም ዓለም አቀፍ ተቋማትም ሆኑ ለጋሽ አገሮች ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር ለመሥራት ቁርጠኝነታቸውን እየገለጹ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ ከጥቂት ወራት በፊት በአገራችን ለሚገኙ ስደተኞች ሥራ ፈጠራና ተያያዥ ጉዳዮች ማከናወኛ የሚሆን ከአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ በአውሮፓ ኅብረት የተለገሰውን 500 ሚሊዮን ዶላር መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ብቻ ከላይ በተዘረዘሩት አመክንዮችና በተጨባጭ ካለው የአገሪቱ ሁኔታ መረዳት የሚቻለው አገራችን እንደ አገር፣ እንደ ሕዝብ፣ እንደ መንግሥት በዚህ ጊዜ ስደትን በተለይም የወጣቱን ፍልሰት ማበረታታት እንደሌለብን ይመስለኛል፡፡ ሆኖም ግን ይህ ሁሉ ጥረትና ቁርጠኝነት ባለበት ሁኔታ ፖስታ ድርጅት የዲቪ 2018ን ማስታወቂያ በተጋነነ ወይም ስደትን በሚያበረታታ መልክ መሥራቱ አንደምታው ብዙ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን የዚህ መጣጥፍ ዓላማ የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅትን በሕገወጥ ደላላነትም ሆነ በሕጋዊ አስኮብላይነት ለማስፈረጅ ወይም ደግሞ ዲቪን ለመቃወም ሳይሆን፣ በተቋማት ዘንድ የሚታዩ ክፍተቶችን፣ ጠቃሚ ያልሆኑ አመለካከቶችንና የታዳጊውን ወጣት ትውልድ የማያንፁ አካሄዶች ልብ እንዲባሉ ለመጠቆም ነው፡፡

ለምሳሌ ይህ የተጠቀስው የፖስታ ድርጅቱ ማስታወቂያ በተገቢ ትኩረትና በውል ታስቦበት የተሠራ እንዳልሆነ መገመት አይከብድም፡፡ በእርግጥ እንዲህ ዓይነት ማስታወቂያዎች፣ ከመልዕክታቸው አንፃር በግሉ ሴክተርም ይስተዋላሉ፡፡ ይህ ደግሞ እንደ ተቋማዊ ቸልተኝነት (Institutional Recklessness) ተደርጎ ብቻ የሚወሰድ ሳይሆን፣ በተቋማቶቻቸን መካከል አለመናበብ እንዳለ በተወሰነ ደረጃ አመላካች ነው፡፡ ይህንን የኢትዮጵያ ፖስታን ማስታወቂያ የፌደራል ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ፣ ወጣቶችና ስፖርት ወይም ሴቶችና ሕፃናት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች ቢመለከቱት ምን ዓይነት ግብረ መልስ ሊሰጡት ይችላሉ የሚለውን ሳስብ በጣም ከባድ ሊሆን እንደሚችል አልጠራጠርም፡፡ ስደትን ለመዋጋትና ወጣቱን በአገሩ ለማብቃት የበኩላቸውን ጥረት እያደረጉ ያሉ ሌሎች መንግሥታዊ ድርጅቶች፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ተቋማትና የወጣት ማኅበራትም ቢሆኑ ደስተኛ አይሆኑም፡፡ ስለዚህ እንዲህ ዓይነት ስህተቶች እንደ ተራ ግድፈት ሳይታለፉ ትምህርት ቢወሰድባቸው ጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ ምክንያቱም አለመናበብ ካለ በየተቋማቶቻችን የምናወጣቸውን ዕቅዶች በተገቢው መልኩ ፈጽመን ተጨባጭ ለውጥ እንዳናመጣ ጋሬጣ ከመሆን አልፎ፣ አንዱ የሚሠራውን ሌላኛው የሚያፈርስበትን አጋጣሚ ሊፈጥር ይችላል፡፡ ጥረታችንንም …ጠብ ሲል ስደፍን… እንደሚባለው ዓይነት ያደርግብናል፡፡ በመሆኑም በሁሉም ረገድ “መናበብ” የጊዜው ጥያቄ (Demand) ይመስላል፡፡

ብቻ በአገራችን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ ሆኖ በዋናነት ደግሞ “ተጠርጣሪ” ወይም “ችግር ሊፈጥሩ ይችላሉ” ተብለው የሚታሰቡ አካላት ላይ አተኩሮ እየሠራ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ግን አዋጁ/አስፈጻሚው ከዚህ በዘለለ እንዲህ በውል ሳይታሰብበት እንደተለቀቀው የ“ዲቪ 2018” ዓይነት ማስታወቂያ (የግድ ማስታወቂያ መሆን አይጠበቀበትም፤ ስለዚህኛው ድርጅት ብቻም አይደለም) የወጣቱን ልብ የሚያሸፍት፣ በአገር ሠርቶ መለወጥ እንደማይቻል የሚያስተጋባ፣ በአገር ውስጥ ጉዳይ ጨለምተኛ እንድንሆን የሚጋብዝ፣ ውጭ ናፋቂ እንድንሆን የሚያበረታታ፣ አሊያም በራስ መተማመናችንን የሚገዳደር አመለካከትም ሆነ አተገባበርን የሚያራምዱ ተቋማትን ሃይ እንዲልልን እንጠይቃለን፡፡ ተቋማትም እርስ በርስ እንዲናበቡና አሳታፊ እንዲሆኑ ተገቢውን አቅጣጫ እንዲሰጥልን እንሻለን፡፡ ይህም በአንድም ይሁን በሌላ መንገድ አዋጁ የወጣበትን ግብ ለማሳካት ይረዳልና ነው፡፡

ቸር እንሰንብት!

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dejene_assefa@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

Standard (Image)

የፍትሕ ሥርዓቱ በሕግ ብቻ እንዲመራ ለህሊናችን ታማኝ እንሁን!

$
0
0

በኤፍሬም አፈረ

በቅርቡ በሪፖርተር ጋዜጣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሰብዓዊ መብት ማዕከል የሰብዓዊ መብት መምህርና ተመራማሪ አቶ ጌታሁን ካሳ ‹‹የፍትሕ ሥርዓቱ አመኔታ ያተረፈ ሕዝብ የሚቀበለውና በሕግ ብቻ የሚመራ መሆን አለበት›› በሚል ርዕስ ለሪፖርተር ጋዜጣ የሰጡትን ቃለ ምልልስን ሚያዝያ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. በወንጀል ጉዳዮች የፍትሐዊ ዳኝነት መመዘኛዎች (Fair Trial Standards) በፌዴራል ፍርድ ቤቶች ተግባራዊ ዕይታ አስመልክቶ የቀረበው የጥናታዊ ጽሑፉን ዓውደ ጥናት ዝርዝር በመመልከት ከተጨባጭ የጉዳዩ ክስተት ማሳያ የተካሄደውን ይኼንን የማዳበሪያ ጽሑፍ ከቃለ መጠይቁ ዋና ዋና ሐሳቦችን በመውሰድ ለማዘጋጀት ተሞክሯል፡፡

ጊዜው ጥቅምት 30 ቀን 2008 ዓ.ም. በመዲናችን በአንድ የመንግሥት የልማት ድርጅት ተቋም የተፈጠረ ክስተት ነው፡፡ ይኼም የተቋሙ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ በክፍሉ ሥር የሚገኘውን የስብሰባ አዳራሽ አለመዘጋቱን ሲረዳ በሰርቪስ ቤቱ ከደረሰ በኋላ የቅርብ አለቃውን በማሳወቅ፣ ወደ ድርጅቱ ከምሽቱ 1፡40 ሰዓት በመመለስ ለመዝጋት ይመለሳል፡፡ በወቅቱ ሥራ ላይ ያልነበረ ቢሆንም ያለሥራ በምድረ ግቢው የነበረ ሌላ ሠራተኛ ግቢው ውስጥ የገባ ሠራተኛ አለ ብሎ በቦታው ላይ ለነበሩ ሠራተኞች ይናገራል፡፡ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያው አዳራሹን ዘግቶ ሲመለስ ምን ታደርጋለህ? በማለት ባለሙያውን ከኋላ ተከትሎ ለመደብደብ ከመሞከር ውጪ በወቅቱ እንዳችም የተናገረው አልነበረም፡፡ ባለሙያው በሥነ ሥርዓት በጥበቃ ሠራተኞች ተፈትሾ መውጣቱንና ወደ ቤቱ መሄዱን በወቅቱ የተመለከትነው ትዝብት ነበር፡፡

ሆኖም በወቅቱ ኃላፊነቱን ሊወጣ የመጣን ባለሙያ ተግባር ወደ ሌላ አቅጣጫ በመቀየር ያለሥራ በድርጅቱ እስከ ምሽቱ 1፡40 ሰዓት ተገኝቷል የሚል መረጃን ብቻ መሠረት በማድረግና በመቀበል የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ ዕርምጃ ይወስዳል፡፡ ያ ሠራተኛ ባለሙያውን የንብረት ክፍሉን በር ሲነካ ተመልክቻለሁ በማለቱ ብቻ ከሥራውና ከደመወዝ እንዲታገድ፣ በአካባቢው ባለው ፖሊስ ጣቢያም በሐሰት ለቀናት እንዲታሰርና ከተቻለም እንዲፈረድበት ከፍተኛ ጥረት ተደርጎ ነበር፡፡ በባለሙያው ላይ በሰውም ሆነ በአሻራ ማስረጃ ተብሎ ሊቆጠር የሚችል ነገር ባለመገኘቱ ከቀናት በኋላ የተፈታ ሲሆን፣ በባለሙያው ላይ ተፅዕኖ አሳድሮ የነበረው ሥራ አስኪያጅ በከተማ አስተዳደሩ ውሳኔ ከአንድ ሳምንት በኋላ ከሥራ እንዲሰናበት ተደርጓል፡፡ ከዚህም ባሻገር በዚሁ ወር በኃላፊው ላይ ይስተዋሉ በነበሩ የሙስና ብልሹ አሠራሮች ሳቢያ ከቀናት በኋላ በቁጥጥር ሥር ውሎ ጉዳዩ በመታየት ላይ ይገኛል፡፡ በድርጅቱ ስም የተከሰሰው የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ ግን ከፀረ ሙስና ኮሚሽን በተሰጠው ጊዜያዊ ከለላ ወደ ሥራ ተመልሶ በድርጅቱ አጠቃላይ ሠራተኞች የተቋሙን የመልካም አስተዳደር ችግር ሊያጣራ ይችላል ተብሎ ይመረጣል፡፡ ባለሙያው ከኮሚቴ አባላት ጋር በመሆን የተቋሙ ሥራ አስኪያጅ እንዲሁም ባለሙያውን ለማሳሰር ምክንያት የሆነው ግለሰብ የተፈጸሙ የተለያዩ የብልሹ አሠራር ችግሮችን በተጨባጭ በመለየት የተለያዩ ግኝቶችን በማቅረብ ለከተማ አስተዳደር ኃላፊዎች ቀርቦ፣ ለተቋሙ በአዲስ ሁኔታ የተመደበው ሥራ አስኪያጅ የተለያዩ የማስተካከያ ውሳኔዎችን እንዲወስን አቅም ፈጥሯል፡፡

በሌላ በኩል ኅዳር 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ጉዳዩን አስመልክቶ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያው ለሥራ ወደ ድርጅቱ ኃላፊነቱን ለመወጣት ስሄድ የድብደባ ሙከራ ሊፈጸምብኝ ተሞክሯል ብሎ ሪፖርት ለማድረግ ፖሊስ ጣቢያ ቢገኝም፣ በወቅቱ የነበረው  የጣቢያው ዓቃቤ ሕግ፣ የፖሊስ ጣቢያው መርማሪ፣ የፖሊስ ጣቢያው ኃላፊና የከሳሽ ድርጅት ኃላፊዎች የተለያዩ ጫናዎችን በማድረግ በወቅቱ ክስ እንዳይመሠረት ያደርጋሉ፡፡ በዕለቱ ከጠዋቱ ጀምሮ በቦታው የተገኘው የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያው ‹‹የድብድባ ሙከራ ተፈጽሞብኛል ሊታይልኝ ይገባል፤›› በሚል ጥያቄ ቢያቀርብም ሰሚ ሳያገኝ ይቆያል፡፡

በቀጥታም ፖሊስ በተቋሙ በቦታው የነበሩ ምስክሮችን ቃል ይቀበላል፣ ተነካ የተባለውን የንብረት ክፍል በር አሻራም ያስነሳል፡፡ ሆኖም ከመነሻው በቦታው የነበሩ እማኞች የተቋሙ ኃላፊ የፈለጉትንና ከሳሽ ነኝ ያለውን ግለሰብ ለማስደሰት ሳይሆን ለህሊናቸው ቃላቸውን ቢሰጡም፣ የእነሱን ቃል ችላ በማለት የአሻራ ውጤት እስኪመጣ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያውን የጣቢያ ዋስትና ይከለክላሉ፡፡ ፍርድ ቤት በማግሥቱ ከሳሽ ፖሊስ ሆኖ ለዳኛ ያቀርባሉ፡፡ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያው፣ ‹‹ጉዳዩ ቂም በቀል እንደሆነ ከመነሻው ጠቋሚ ነኝ፤›› ያለው ግለሰብ በተጨባጭ የተለያዩ የኪራይ ሰብሳቢነት ችግሮቹን ስላቀረበበት፣ እንደ ተቋም የሚታዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በግልጽ ስለሚታገል የተፈጸመበት ድርጊት መሆኑን አብዛኛው ሠራተኛ የሚያውቀውና ፀሐይ የሞቀው ሀቅ በመሆኑ፣ ሠራተኛው በድርጊቱ ተገርሞ የፍትሕ አካላትን ሥራ ይመለከት ነበር፡፡

ከሳሽ ፖሊስ፣ ዋስትና ከልካይም ፖሊስ በሆነበትና የጊዜ ቀጠሮ በማግሥቱ የጠየቀው ፖሊስ ለሰባት ቀን የአሻራ ውጤትና አሳማኝ ማስረጃ ሊያመጣ ባለመቻሉ ጉዳዩን ሲከታተሉ የነበሩት ዳኛ በዋስትና የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያው እንዲፈታ ያደርጋሉ፡፡ በቂ ወንጀል ማቋቋም የሚያስችል መረጃ ያልነበረው የጣቢያ ዓቃቤ ሕግ ፋይሉን ለመዝጋት የሚጠቅመውን የሽፋን አንቀጽ በመጥቀስ በ42/1/ሀ ይዘጋል፡፡ ይኼም ከመነሻው ለሕግ ውግንና ባለመቆሙ ምክንያታዊ ያልሆነ ክስና አዋጁን ሽፋን በማድረግ የተጠቀመበት በመሆኑ የተዘጋ ቢሆንም፣ ባለሙያው በስም ማጥፋት የሐሰት ክስ መነሻ የሆነው ሠራተኛ እንዲከሰስለት ጥያቄ ቢያቀርብም፣ ለመክሰስ በቂ የሆኑ ማስረጃዎች ዓቃቤ ሕግ ቢቀርብለትም፣ ክስ ከመመሥረት ይልቅ ከወንጀል ሕጉ አንቀጽ 613 መሠረት ጉዳት ለማድረስ የተፈጸመ ነው ለማለት አይቻልም ተባለ፡፡ ማንም ሰው ወንጀል ሲፈጽም ዝም ብሎ ማየት ስለሌለበት ጥቆማ መስጠት እንደሚችል የወ/መ/ስ/ ሕጋችን ይደነግጋል፡፡ የተሰጠ ጥቆማ ሐሰት ከሆነ መወንጀል እንደሚያስጠይቅ የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 446 እንደሚያስቀምጥ ቢያትትም በሐሰት መወንጀል የተጠየቀ ሰው ደግሞ በስም ማጥፋት ወንጀል እንደማይጠየቅ ከወንጀል ሕጉ አንቀጽ 613/5/ ተቀምጧል፡፡ ይሁንና ሌሎችንም ምክንያቶችን በመስጠት ተገቢው ሕጋዊ ኃላፊነትን ለመወጣት ያልፈለገው በየደረጃው የሚገኝ ዓቃቤ ሕግ ድርጊት የሚገርም ሳይሆን፣ በአገራችን ስም ማጥፋት የሁልጊዜ ተግባር በመሆኑ ተገቢውን ትኩረት ሳይሰጡ ቀርቷል፡፡

ክብር ለዴሞክራሲ ተቋማት በተለይም ለፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ይሁንና በሥልጣናቸው የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያውን ለማሳሰር ሲታትሩ የነበሩት የተቋሙ ኃላፊ፣ በሙስናና ብልሹ አሠራር ተጠርጥረው ለእስር ባይዳረጉ ኖሮ ይኼ ታሪክ በእዚህ ሁኔታ ሊወጣ ባልቻለም ነበር ‹‹ንጉሥ አይከሰስ ሰማይ አይታረስ››  ሳይሆን ‹‹እውነት አይክሰስህ›› ማለት ይቀላል፡፡

በተቋም የመልካም አስተዳደር ችግር ሲኖር መከሰስ የሚገባው የማይከሰስበት፣ ሊያስከስስ የማይችል ድርጊትና ሁኔታ ግን ሥልጣንን ያላግባብ በመጠቀም የሚፈጸምበት ሁኔታ እንዳለ ጉልህና ተጨባጭ መገለጫ መሆኑን በእርግጠኛነት ማስቀመጥ ይቻላል፡፡

በተመሳሳይ በመዲናችን ከአቃቂ ቃሊቲ ወደ አዲስ አበባ ሊገባ የነበረና የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት የምርት ሱፐርቫይዘር ‹‹በሰነድ ተረክቦት ሆኖም የገባበት አልታወቅም›› በሚል ሲድበሰበስ የነበረውና ለፖሊስ ‹‹ክስ ለመመሥረት የይርጋ ጊዜ አልፎታል፤›› ሲል የነበረውና ‹‹በሕገወጥ ሁኔታ ታርዶ የተያዘው የ800 ኪሎ ግራም የአሳማ ሥጋ መዲናቸንን ቢያነጋግርም፣ የተቋሙ አመራርና የሕግ ክፍል ተጠርጣሪውን በሥነ ሥርዓት ዕርምጃ በደመወዝ ቅጣት ያለፈው ቢሆንም፣ ችግሩ ከሥነ ሥርዓት ዕርምጃ ያለፈ የሰው ልጅ ሕይወትን አደጋ ላይ ሊጥል የሚችል ነው፤›› በማለት የፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ባደረገው ማጣራት አስታውቋል ለመጥፋቱ ምክንያት የሆነውንና ለሕዝብ ግንኙነቱ የሐሰት መታሰር ምክንያት የሆነው ሠራተኛ በዚሁ ዓመት በቁጥጥር ሥር ውሎ የተፈታ ቢሆንም፣ ጉዳዩ በፍርድ ቤት እየታየ ይገኛል፡፡ በእነዚህም ‹‹አርቀህ አትቆፍር የሚገባበትን አይታውቅም›› እንዲሉ የተቋሙ ማኔጂንግ ዳይሬክተርና ይኸው ግለሰብ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ ይገኛል፡፡

በእነዚህም በዘርፉ የምርምር ሥራቸውን ያቀረቡት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሰብዓዊ መብት ማዕከል፣ የሰብዓዊ መብት መምህርና ተመራማሪ እንደጠቆሙትም የወንጀል ክሶችና የዳኞች የውሳኔ ነፃነት ሰፊ በሆነባቸው ቦታዎች ዳኞች፣ ዓቃቤያን ሕግና ፖሊስን ከተከሳሽ ይበልጥ ያዳምጣሉ፣ ዋስትና መፍቀድ ሲገባው ይከለክላሉ፣ ምርመራው ባለቀ ምንም ተጨማሪ ጊዜ በማያስፈልገው ጉዳይ ላይ ጊዜ ቀጠሮ ይፈቅዳሉ፡፡ በተመሳሳይም ‹‹የስም ማጥፋት ተፈጽሞብኛል ሕጉን በእኩል ደረጃ ሊያስፈጽሙልኝ ይገባል፤›› ብሎ ተበዳይ ሲያቀርብ ከጣቢያ ጀምሮ ያለ ዓቃቤ ሕግ የዘጋውን፣ በየደረጃው ይኼንኑ ከማፅናት ውጪ ምንም ፋይዳ ሳይገኝ በዘርፉ የመጨረሻው አካል ድረስ ቢሄዱም ስም ማጥፋት ባህላችን ነው፣ ከባድ ስርቆት ግን ከባድ ነው በማለት በንፅፅር የፍርድ ግዜ ርዝማኔ በማስቀመጥ እንደ ቀላል ያዩታል፡፡ ይኼንን ነው ‹‹ክስተቱ አልፎ አልፎ የሚታዩ አንዳንዴ የሚያጋጥሙ ብሎ ማለፍ መቅረት እንዲሁም ተጠያቂነት ሊበጅለት ይገባል፤›› ብሎ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሰብዓዊ መብት ማዕከል የሰብዓዊ መብት መምህርና ተመራማሪ አቶ ጌታሁን ካሳ የሚያስቀምጡት፡፡ በመሆኑም የፍትሕ ሥርዓቱ አመኔታ ያተረፈ፣ ሕዝብ የሚቀበለው፣ በሕግ ብቻ የሚመራ መሆን አለበት የሚባለውም ለዚህ ነው፡፡ እናም ዋስትና በመከልከል የሚደርስ የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ እንደ ንፁህ የመቆጠር መብት መጣስና ተገቢ ምላሾች የማይገኙባቸው ሁኔታዎችን በወቅቱ በመፈተሽ በ42/1(ሀ) ስም መዝጋት ብቻ ፍትሕን ማረጋገጥ አይደለም፡፡ ከእዚህ ጋር የሚስተዋሉ የመብት ጥሰቶችን፣ የኪራይ ሰብሳቢነት ተግባራትና ሥልጣንን ያላግባብ የመጠቀም አዝማሚያዎች ከወዲሁ ሊፈተሹ ይገባል፡፡ በቂም በቀል የተጎዱ ዜጎችን እንታደጋቸው፡፡ በጥልቅ ተሃድሶ የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትና ብልሹ አሠራርን ለማስወገድ ከሕግና ከሞራል ተፃራሪ ተግባራትን ባለመፈጸም ለሙያችንና ለህሊናችን  ታማኝ እንሁን፡፡      

ከአዘጋጁ፡-ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን ኢሜይል አድራሻቸው Samuelfrea@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡  

Standard (Image)

በጥልቀት መታደስ እስከ ምን ድረስ?

$
0
0

በዘመኑ ተናኘ

1977 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ታሪክ የክፉ ጊዜ እየተባለ ይጠራል፡፡ ወቅቱ የሰሜን ኢትዮጵያ ሕዝብ በከፍተኛ ደረጃ ለረሃብና ለስደት የተዳረገበት ነው፡፡ ይህ ጊዜም በኢትዮጵያ ታሪክ ‹‹አሰቃቂው ረሃብ›› እየተባለ ይጠራል፡፡ በዚህ ወቅት በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ለሞት የተዳረጉበት ነው፡፡ ዜጎች የሚመገቡት፣ እንስሳት የሚግጡትና የሚጠጡት አጥተው በየሜዳውና በየጫካው ቀርተዋል፡፡ ይህ ክስተት በተፈጠረበት ጊዜ የወቅቱ የአገሪቱ አስተዳደር በኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ጡንቻዎቹ የፈረጠሙና የዳበሩ ስላልነበሩ ለችግሩ አፋጣኝ መፍትሔ ሳይሰጠው ቀርቷል፡፡ በዜጎቻችንም ላይ የከፋ ጉዳት አስከትሎ አልፏል፡፡

ይህ ችግር ከተከሰተ ከብዙ ዓመታት በኋላ በ2008 ዓ.ም. ዳግመኛ የከፋ ድርቅ በአገራችን ተከሰተ፡፡ በእርግጥ ከዚህ ቀደምም ቢሆን እንደዚህ ጊዜው የከፋ ባይባልም፣ አልፎ አልፎ በአገራችን አካባቢዎች ተከስቶ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ባለፈው ዓመት ተከስቶ የነበረውን ድርቅ መንግሥትና ሕዝብ የከፋ ጉዳት ሳያደርስ በብዙ ቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ በመመደብና ወጪ በማድረግ ዜጎቻችንን ከሞት መታደግ ተችሏል፡፡ ይህም ጊዜ ኢሕአዴግ የተፈተነበት እንደሆነ በርካታ ባለሙያዎች ሲናገሩ ይደመጣል፡፡

ይህ ተፈጥሮአዊ ክስተት ካስከተለው ችግር ባሻገር ኢሕአዴግ ባለፈው ዓመት በሰው ሠራሽ ችግሮችም ተፈትኗል፡፡ ዋነኛው የጽሑፌ ጭብጥ አድርጌ ለመጻፍና ለመተንተን የምፈልገው ጉዳይም በ2008 ዓ.ም. ኢሕአዴግ ስለተፈተነባቸው ችግሮችና በቅርብ ጊዜም ከእነዚህ ችግሮች ለመውጣት እንደ መፍትሔ አድርጎ እየተንቀሳቀሰበት ስላለው የጥልቅ ተሃድሶ እንቅስቃሴ ላይ አስተያየቴን ለማስፈር ነው፡፡

በአዲስ አበባ ዙሪያ ካሉ የኦሮሚያ ክልል ከተሞችና ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ ከተቀሰቀሰው የሕዝብ ተቃውሞና ጥያቄ እስከ ወልቃይት፣ እንዲሁም ከአማራ ክልሏ መዲና ባህር ዳር እስከ ደቡብ ክልል በአንዳንድ አካባቢዎች በተነሱ ሕዝባዊ ተቃውሞች ኢሕአዴግ በኃይለኛው ተፈትኗል፡፡

ይህ ችግር በአገራችን ውስጥ ከፍተኛ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮችን አስከትሎም አልፏል፡፡ የችግሩ መንስዔ ተደርጐ የሚወሰደው ደግሞ የመንግሥት ኢፍትሐዊ አሠራር፣ ሥር የሰደደ ሙስናና የወጣቱ የሥራ ዕድል ፈጠራ ውስንነት እንደሆነ መንግሥት ያመነው ፀሐይ የሞቀው ጉዳይ ነው፡፡ የእነዚህ ችግሮች ከጊዜ ወደ ጊዜ መስፋፋትና ውስብስብነታቸው እያደረ መጨመር የሕዝብ ቁጣና ጥያቄ በየአካባቢው እንዲነሳ ምክንያት ሆኗል፡፡ ይህ ችግር በሚሊዮን የሚቆጠር ንብረት እንዲወድም ከማድረግ ባሻገር ሊተካ የማይችለውን የሰው ልጅ ሕይወትም ቀጥፎ አልፏል፡፡ የአገራችን ስምና ታሪክም ተሸርሽሯል፡፡ ‹‹የቱሪስት መዳረሻ›› እየተባለች ትጠራ የነበረች ዛሬ ከዚህ ኪሎ ሜትር በላይ እንዳትሄዱ እየተባለ ለውጭ አገር ዜጎች የሚሰበክባት አገር ሆናለች (ምንም እንኳ በቅርቡ ይህ ክልከላ ቢነሳም)፡፡ በዚህም የተነሳ አገራችን ከቱሪዝም ታገኝ የነበረው ገቢ በአሁኑ ወቅት በ35 በመቶ እንደቀነሰ አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የአገሪቱ ኢኮኖሚም በከፍተኛ መጠን ተጎድቷል፡፡ አንዳንድ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች እንደሚሉት ባለፈው ጊዜ ተከስቶ በነበረው ሕዝባዊ ተቃውሞ ብቻ አገራችን በሁለት ዓመት ሊተካ የማይችል ኢኮኖሚ አጥታለች፡፡

ባለፈው ጊዜ ለሕዝብ ጥያቄ አፋጣኝ መፍትሔ ባለመሰጠቱ የተነሳ ችግሮች ከጊዜ ወደ ጊዜ መሠረታቸው እየሰፋና ውስብስብ እየሆኑ መጥተዋል፡፡ የሚፈልገውን ያላገኘ ሕዝብም ጥያቄዎቹን ይዞ ወደ አደባባይ ወጥቷል፡፡

መንግሥትም ንብረትና የሰው ልጅ ሕይወት ከጠፋና ከወደመ በኋላ መፍትሔ ለመስጠት መንቀሳቀስ ጀምራል፡፡ ‹‹ጥልቅ የተሃድሶ እንቅስቃሴ›› በሚል መፈክር ችግሬን እቀርፋለሁ ብሎ ለሕዝቡ ምሎና ተገዝቶ ወደ እንቅስቃሴ ገብቷል፡፡   

መንግሥት ለችግሮቹ አፋጣኝ መፍትሔ ለመስጠት ተግባራዊ እንቅስቃሴ ማድረግ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን የተለያዩ ለውጦችንና ተሃድሶዎችን አካሂዷል፡፡ ለሕዝብ ጥያቄ በአፋጣኝ መልስ ለመስጠት ውስንነት የነበረበትን ከፍተኛ የአመራር አካላት እንደገና የማዋቀርና ችሎታንና የሕዝብ ወገንተኝነትን መሠረት በማድረግ ሹም ሽር አካሂዷል፡፡

ኢሕአዴግ በጥልቅ ተሃድሶ ዘመቻው ወቅት ከወሰዳቸው ዕርምጃዎች መካከል ባለፈው ጊዜ የኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅች (ኦሕዴድ) ያደረገውን የአመራር ለውጥ መውሰድ ይቻላል፡፡ ከዚህ ቀደም የኦሮሚያን ክልል ይመሩና ያስተዳድሩ የነበሩ ከፍተኛ አመራሮች የሕዝብ ወገንተኝነት ባላቸው የአመራር አካላት ተተክተዋል ተብሏል፡፡ የክልሉ ሕዝብ በተደጋጋሚ ጊዜ ያነሳቸው የነበሩ ጥያቄዎችን በአፋጣኝ ለመመለስ አዲሱ የክልሉ አመራር የጥልቅ ተሃድሶ እንቅስቃሴውን ጀምሯል፡፡ ከከፍተኛ አመራር እስከ ዝቅተኛ አመራር ድረስ የሥልጣን ሹም ሽር በማድረግ ሕዝቡ የሚጠይቃቸውን የማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች ለመመለስ የክልሉ አዲሱ አመራር በሙሉ አቅሙ እየተንቀሳቀሰ መሆኑም ተሰምቷል፡፡ በዚህም የተነሳ አንዳንድ የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚገልጹት የኢሕአዴግ በጥልቀት መታደስ ማሳያ ከሆኑ ዋነኛ ጉዳዮች መካከል አንዱ በክልሉ የተካሄደው የሥልጣን ሹም ሽር እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ለዚህም ምሥጋና ተችሮታል፡፡

ኢሕአዴግ ከዚህ አለፍ ሲልም በ2009 ዓ.ም. የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲከፈት ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ በምክር ቤቱ ተገኝተው የ2009 ዓ.ም. የመንግሥት የትኩረት ነጥቦችን የዘረዘሩበት፣ በሌላ ጊዜ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ለትኩረት ነጥቦች ማብራርያና ከምክር ቤቱ አባላት ለሚያነሱ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት በተገኙበት ወቅት ያደረጉት የካቢኔያቸው ሹም ሽር ይበል ያሰኘ ጉዳይ ነበር፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በወቅቱ የመንግሥታቸውን በጥልቅ የመታደስ ስኬት እውን ለማድረግ የካቢኔ ሹም ሽር ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ እንደተገኘ ለምክር ቤቱ አባላት አብራርተዋል፡፡ በዚህም የተነሳ ኢሕአዴግ ይታማበት ከነበረው ለካቢኔነት የሚያበቃው በፖለቲካ ወገንተኝነት ሳይሆን፣ መሪዎች ባላቸው የሕዝብ ወገንተኝነትና የትምህርት ደረጃ ላይ ብቻ በመመርኮዝ አመራር የሚሆኑበትን መንገድ ቀይሷል፡፡ በዚህም ዘዴ በመጠቀም በትምህርታቸው የገፉና የሕዝብ ወገንተኛ ናቸው የተባሉ አመራሮችን ሾሟል፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክም የጦር መሣሪያ ይዘው ሳይሆን ብዕር ጨበጠው ያሳለፉ አካላት የሚኒስትሮች ምክር ቤትን ተቀላቅለዋል ብለን አፋችንን ሞልተን መናገር እንችላለን፡፡ ይህ ደግሞ በጥልቅ የመታደስ ጉዞ አንዱና ዋነኛው ማሳያ ነው፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢሕአዴግ አሁንም በጥልቅ ተሃድሶ ጉዞው ያልፈታቸውና የሕዝብ ቅሬታ ሆነው የዘለቁ ጉዳዮች እዚህም እዚያም ከመሰማት አልቦዘኑም፡፡ ከነዚህ መካከል አሁንም ድረስ በብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) እና በሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕወሓት) የአመራር አካላት ላይ ግልጽና የሚታይ የሥልጣን ሹም ሽር አለማድረጉን በመጥቀስ፡፡ የሕዝብን ብሶት ያባባሱና ለሕዝብ ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ ያልሰጡ ከፍተኛ አመራሮች አሁንም በሁለቱም ክልሎች  የተለያዩ አመራሮች ውስጥ እንዳሉ በማብራራት፡፡

በእርግጥ የሁለቱ ክልሎች የአመራር አካላትና የሚዲያ ሰዎች ሰሞኑን በተለያዩ ሚዲያዎች እንደሚገልጹት ከሆነ፣ የየክልሎቻቸው ከፍተኛ አመራር በጥልቅ የመታደስ እንቅስቃሴ ውስጥ እንዳሉና በተወሰኑ የአመራር አካላት ላይም ዕርምጃ እየተወሰደ እንደሆነ ይደመጣል፡፡ የብዙዎች አስተያየት ግን ለምን የተወሰዱ ዕርምጃዎች በግልጽ ለሕዝብ ይፋ አይሆኑም? የሚል ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ኢሕአዴግ አሁንም ከማድበስበስ አባዜው አልተላቀቀም የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡

በ1960ዎቹ ውስጥ ዝነኛና ተወዳጅ የነበረው ጋዜጠኛ ጀምስ ዊልሰን በአንድ ወቅት ለኢንኪዋየር መጽሔት ባቀረበው ዘገባ፣ ‹‹ማንም መንግሥት የሕዝብ የችግር ምንጭ የሆነን ጉዳይ አድበስብሶ ባለፈ ቁጥር የባሰ ችግር ያስከትላል፤›› ይላል፡፡ ይህንን ጉዳይ ዘርዘር አድርጎ ሲያቀርበው፣ ‹‹ችግርን ካድበሰበስነው ከሀቅ ይልቅ በተስፋ እንድንኖር ያደርገናል፡፡ ይህ ተስፋ ሲያልቅና ሲሟጠጥ ደግሞ እንደ ብርሃን ወለል ብሎ የሚታየው ሀቅ የችግር ሥር መሠረት ይሆናል፡፡ ሲበዛ ሲበረክት ደግሞ ጎስቋላው ክፍል መንቀሳቀሱ አይቀርም፡፡ የበገሌ አመለካከት (Relative Deprivation) እየዘቀጠ መሄድ ሊገታ የማይችል ኃይል ይፈጥራል፡፡ በሌላ መንገድ ሲገለጥ የጎስቋሎች አመፅ፣ የድህነት በባሰ ድህነት መከሰት፣ የአብዮት ተስፋ መፋፋት (A revolution of rising expectation) መሆኑ በሒደት ከፍ ይልና የአብዮትን ምድጃ የሚቆሰቁስ ይሆናል፤›› ይላል፡፡ በአገራችን ከወራት በፊት ተከስቶ የነበረው ሁኔታም ይህንን መሰል አብዮት የተከተለ ነው፡፡

ሥራ አጥነት የአብዮቱን ምድጃ ቆስቁሷል፡፡ የመንግሥት የአመራር አካላት እጀ ረጅምነትና ሙሰኛነት አብዮቱን አፋፍሟል፡፡ ጀምስ ዊልስን እንደገለጸው ʻአደባብሰው ቢያርሱ በዓረም ይመለሱʼ ነውና ነገሩ አሁንም ኢሕአዴግ በጥልቅ የተሃድሶ ጉዞው ማድበስበስን ትቶ በኦሮሚያ ክልልና በፌዴራል መንግሥት የወሰደውን ዓይነት ዕርምጃ በትግራይ፣ በአማራ እንዲሁም ደበቡብ ክልሎች መውሰድ አለበት፡፡ የተወሰደ ዕርምጃ ካለም ለሕዝቡ ይፋ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡  ወይም ደግሞ በጥልቅ መታደስ ጊዜ ዕድሳት የማያስፈልጋቸው አመራሮችና ክልሎች ካሉ ለሕዝቡ ይፋ መሆን አለበት፡፡ በዚህ ወቅት መታደስ የማያስፈልግበት ምክንያትም አብሮ በተብራራ ሁኔታ መገለጽ አለበት፡፡

በእኔ አመለካከት ግን በፌዴራሉ ከፍተኛ የመንግሥት አመራር አካላትና በኦሮሚያ ክልል የተደረገው በጥልቅ የመታደስ ጉዞ በዘጠኙ ክልሎችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደር አካላትም መደረግ አለበት፡፡ ይህ ከሆነ የአብዮቱን ምድጃ የሚቆሰቁሱ አካላት አርፈው ይተኛሉ፡፡ እጃቸውንም ለሰላም ይዘረጋሉ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው Zemenutenagn09@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡   

Standard (Image)

እኛስ እነ ማንን እንመስላለን?

$
0
0

በጌታቸው አስፋው

ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ ልማት ጉዞ የተጓዘችበትን ርቀት ቆም ብላ የምታጤንበት፣ እነ ማንን እንደምትመስል መስተዋት የምትመለከትበት፣ በኢኮኖሚ ልማት ደም ሥሯ ውስጥ የሚዘዋወረው ደም ምን ዓይነት እንደሆነ የምትመረምርበትና ዛሬ ያለችበትን ሁኔታ ለማወቅ ከሌሎች መሰል አገሮች ጋር መመሳሰሏንና መለያየቷን ገምግማ ቀጣይ መንገዷን መቃኘት እንዳለባት የሰሞኑ ግርግር ራሱ ያስገድዳታል፡፡

በልማታዊ መንግሥት ጉዞ የተራመዱትን አገሮች በስኬታቸው መጠን ልክ በጣም የተሳካላቸውና በመጠኑ የተሳካላቸው ወይም ያልተሳካላቸው፣ ካለመሳካትም አልፎ በዕዳ የተዘፈቁ ብሎ በየፈርጁ መከፋፈል ይቻላል፡፡

ስለልማታዊ መንግሥት አስተሳሰብ ብዙ ታዳጊ አገሮች እንደ አዲስ ግኝት አጋነው ቢናገሩም፣ የልማት ኢኮኖሚስቶች ግን ከ1950ዎቹና ከ1960ዎቹ የልማት አስተሳሰቦች ብዙ የተለየ ነገር የለውም ይላሉ፡፡ የልማታዊ መንግሥት አስተሳሰብ ቀደም ካሉት እንደ ጉናር ሚርዳል፣ ፖል ባራን፣ ሮዘንስቴን ሮዳን፣ ሲሞን ኩዝኔትስ፣ ሮስቶው፣ ሳሙኤል ሀንቲንግተን የልማት ኢኮኖሚክስ አመለካከት አይለይም ይላሉ፡፡

ታዳጊ አገሮች ከቅኝ ግዛት ከተላቀቁበትና የራሳቸውን ዕጣ ፋንታ ራሳቸው ወሳኝ ከሆኑበት ከ1950ዎቹና 1960ዎቹ ጀምሮ የራሳቸው ምሁራንም ሆኑ ምዕራባውያን በምን ዓይነት የዕድገትና የልማት ጎዳና ቢጓዙ፣ እንደ ሀብታም አገሮች ሊበለፅጉ እንደሚችሉ ብዙ ጽንሰ ሐሳቦችን አፍልቀዋል፡፡

የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማ ታዳጊ አገሮች በምን ዓይነት የኢኮኖሚ ልማት ጽንሰ ሐሳቦች እንዳለፉና በኢኮኖሚ ልማት ጉዟቸው እርስ በርሳቸው የሚመሳሰሉ ወይም የተለያዩ አካሄዶች እንደ ነበሯቸው፣ የሚመሳሰሉበት ሁኔታዎች ካሉ ኢትዮጵያ እነ ማንን እንደምትመስል ለመመልከት ነው፡፡

የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ ኢኮኖሚ ልማት

ቅኝ ተገዢ ታዳጊ አገሮች ነፃ ከወጡበት ጊዜ አንስቶ ሰፍኖ የቆየው የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ (Modernization Theory) የኢኮኖሚ ልማት አመለካከት ታዳጊ አገሮች፣ ያደጉ አገሮች ባደጉበት ዘመናዊ መንገድ ተጉዘው ለማደግ ‹‹የአቦ ሰጥ›› ዕድል አግኝተዋል የሚል ነው፡፡ ዘመናዊ ማለትም የአኗኗር ዘይቤን ለዘመናዊነት ፀር ከሆኑት የታዳጊ አገሮች ልማዳዊ፣ ባህላዊ፣ ማኅበራዊ፣ ሃይማኖታዊ ሁኔታዎች ቀይሮ ኑሮን ከበለፀጉት አገሮች የዕድገት ደረጃና የጊዜው ኑሮ ሁኔታ ዓይነት ጋር ማመሳሰል ነው፡፡

ይኼ ጽንሰ ሐሳብ ከከተሜነት ኢንዱስትሪያላዊነትና ከትምህርት መስፋፋት ጋርም ይመሳሰላል፡፡ ዘመናዊነት ሲጨምር በቤተሰብና በማኀበረሰብ ከመታወቅ ይልቅ በራስ ወይም በግለሰብነት መታወቅ ዋናው የማንነት መገለጫ ይሆናል፡፡ ከቡድን መብትና ግዴታዎች የግለሰብ መብትና ግዴታዎች ይቀድማሉ፡፡ ለሕዝብ የሚታገሉ የፖለቲካ ሰዎችም አስተሳሰባቸው ዘመናዊ ከሆነ በቤተሰብና በብሔረሰብ ቡድን ሰውን ከሰው አይለያዩም አይከፋፍሉም፡፡ በቤተሰብና በብሔረሰብ ማንነት መታወቅ ለቤተሰብና ለብሔረሰብ መብት መታገል ኋላቀር አስተሳሰብ ይሆናል፡፡

የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ ኢኮኖሚ ልማት አቀንቃኞች የኢንዱስትሪ እመርታ፣ የመገናኛ ብዙኃን መስፋፋት፣ የበለፀጉት አገሮች የክህሎት ሐሳቦች፣ በአብሮ መኖር ሒደት አማካይነት ወደ ታዳጊ አገሮች መስረፅ የታዳጊ አገሮችን ልማዳዊና ባህላዊ ኢኮኖሚ ስለሚያዘምን፣ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ ሽግግር የምርት አደረጃጀታቸው እንዲሁም የሸቀጥ ፍላጎትና አቅርቦት በበለፀጉት አገሮች ዕድገትና ብልፅግና ጎዳና መልክ ይገራል የሚል ሐሳብ ነበራቸው፡፡

የጥገኝነት ጽንሰ ሐሳብ ኢኮኖሚ ልማት

የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ አቀንቃኞችን በመቃወም የኢንዱስትሪ አብዮት የተካሄደበትን የአውሮፓን ወግና ልማድና የአሜሪካንን ዕድገት ጎዳና መቅዳትና መከተል እንደ የዘመናዊነት ምልክት መታየቱን ባለመደገፍ፣ ታዳጊ አገሮችም የራሳቸውን ልማድና ባህል ቢያዳብሩ ‹‹የምዕራቡን ዓለም ‘ሳይቀዱ’ የሰው ‘ሳይገለብጡ’›› በራሳቸው መንገድ ሊዘምኑ ይችሉ ነበር የሚል አመለካከትም ከታዳጊ አገሮች ምሁራን መጥቶ ነበር፡፡

የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ ኢኮኖሚ ልማት አስተሳሰብን በመቀናቀን ከተነሱት ጽንሰ ሐሳቦች መካከል አንዱና ዋናው፣ በ1950 ዓ.ም. ብቅ ያለው የጥገኝነት ጽንሰ ሐሳብ (Dependency Theory) አመለካከት ትርጉም የሚከተለው ነው፡፡

እንደ የጥገኝነት ጽንሰ ሐሳብ ታዳጊ አገሮች በበለፀጉት አገሮች ካፒታል፣ ቴክኖሎጂ፣ ሙያና የንግድ ሥርዓት እየተጠቀሙ አብሮ መኖራቸውና ያላቻ ጋብቻ መፍጠራቸው፣ የራሳቸውን ዕውቀትና የአመራረት ዘይቤ እንዳያዳብሩ በበለፀጉት አገሮች ምርት ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ አድርጎ ጎድቷቸዋል፡፡ የኢኮኖሚ ልማታቸውን ከማፋጠን ይልቅ አቀጭጮታል፡፡ ጥሬ ሀብት ከታዳጊ ቅኝ ተገዢ ዳር አገር ወደ ቅኝ ገዢ መሀል አገር ፈልሷል፡፡

የጥገኝነት ጽንሰ ሐሳብ ያላደጉ አገሮች የበለፀጉ አገሮች የቀድሞ ድህነት ዘመን ግልባጮች ሳይሆኑ የራሳቸው ወግ፣ ልማድ፣ ባህልና ህልውና የነበራቸው ነገር ግን ቀድመው ከዘመኑት ጋር በአብሮ መኖር ውስጥ ደካማ የሆኑና የተጎዱ በመሆናቸው፣ ይኼንን ሁኔታ ሊቀለብሱ ይገባል በማለት ያስተምራል፡፡

ከ1960 ዓ.ም. በኋላ ሜክሲኮን፣ ብራዚልን የመሳሰሉ የላቲን አሜሪካ አገሮችና ደቡብ ኮሪያን፣ ታይዋንን የመሳሰሉ የእስያ አገሮች ኢምፖርትን በአገር ውስጥ ምርት በመተካትና የበለፀጉ አገሮችን ኤክስፖርት ገበያዎች ሰብረው በመግባት፣ በቅይጥ የንግድ ስትራቴጂ አማካይነት ከጥገኝነት የሚያድን የልማት መንገድ ተከትለዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በጊዜው የካፒታሊስት አገሮችና የሶሻሊስት አገሮች ተቃራኒ ጎራ በመፍጠር ታዳጊ አገሮችን ወዳጅና የንግድ ሸሪክ ለማድረግ ብዙ ጥረው ነበር፡፡ ታዳጊ አገሮችም የገለልተኝነት አቋም ከመያዝም ባሻገር የነዳጅ ዋጋ እስከወደቀበት እስከ 1970 ዓ.ም. ድረስ፣ በነዳጅ አምራች አገሮች ጡንቻ አማካይነት ብዝበዛ የሌለበት አዲስ ዓይነት የሰሜንና የደቡብ ግንኙነት ለመፍጠርና በዓለም ዙሪያ አዲስ ፍትሐዊነት የሰፈነበት የኢኮኖሚ ሥርዓት (New Economic Order) ለመዘርጋት ተፍጨርጭረውም ነበር፡፡

በአሁኑ የግሎባላይዜሽን ዘመንም ሉዓላዊ ልማታዊ መንግሥታትና ዓለም አቀፍ ሥርዓት አብረው ተቻችለው የመኖራቸው ሁኔታ እያከራከረ ነው፡፡ የመንግሥታቱ ውስጣዊ ሉዓላዊ የልማት አስተዳደርና የግሎባላይዜሽን ዓለም አቀፍ የነፃ ገበያ ሥርዓት ግንኙነት የወቅቱ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚ እንቆቅልሽ ነው፡፡ የእንቆቅልሹ ፍቺም በሦስት ፈርጆች ተከፍሎ ይታያል፡፡

አንዱ መንግሥታት በጊዜ ብዛት ይከስማሉ ሲል ሁለተኛው መንግሥታት ምንም ቢሆን በግሎባላይዜሽን አይተኩም፣ ሉዓላዊነታቸውን ጠብቀው ይኖራሉ የሚል ነው፡፡ ሦስተኛውና መካከለኛ አቋም የሚይዘው ልማታዊ መንግሥታት የግሎባላይዜሽንን ፍላጎት የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን ሥርዓት ከፖሊሲያቸው ጋር አጣጥመው በውስጣቸው ያሰርፃሉ የሚል ነው፡፡

በዚህም መሠረት እንደ ታይላንድ፣ ታይዋን፣ ማሌዥያ፣ ደቡብ ኮሪያና ቬትናም ባሉ ልማታዊ መንግሥታት አገር መንግሥት ሕዝቡን ከግሎባላይዜሽን ዘመን ድንበር ዘለል ኩባንያዎች ምዝበራ ለመከላከል፣ ድንበር ዘለል ኩባንያዎች የአገር ውስጥን የደመወዝ አከፋፈልና የሥራ ከባቢ ሁኔታ ጠብቀው ግብር ከፍለው ከትርፋቸው ከፊሉን በአገር ውስጥ ተጠቅመው እንዲሠሩ አስገድደዋል፡፡ የአገር ውስጥ ጥሬ ዕቃ እንዲጠቀሙና የአገር ውስጥ ሠራተኞችን በዓለም አቀፍ የሠራተኛ ዋጋ እንዲቀጥሩም አድርገዋል፡፡

ሁለት ዓይነት የካፒታሊስት ሥርዓት መንግሥታዊ ቅርፅ

ከ1970 ዓ.ም. መጨረሻ ጀምሮ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬጋን፣ የእንግሊዟ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርጋሬት ታቸርና የጀርመኑ ቻንስለር ሄልሙት ኮል የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሥርዓት እንደገና እንዲያንሰራራ ባደረጉት ሙግት፣ የታዳጊ አገሮች ብዝበዛ የሌለበት አዲስና ፍትሐዊ የሰሜንና የደቡብ የኢኮኖሚ ግንኙነት ሥርዓት የመፍጠር ጥረትና ህልም መከነ፡፡

የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሥርዓትም በሁለት አቅጣጫዎች ተከፈለ፡፡ አንዱ ጃፓን እንደ ቁንጮ ምሳሌ ተደርጋ የምትጠቀስበት የልማታዊ መንግሥት (Developmental State) ካፒታሊስት ሥርዓት ሲሆን፣ ሌላው አሜሪካ እንደ ቁንጮ ምሳሌ ተደርጋ የምትጠቀስበት የኒዮሊበራል ቁጥጥራዊ (Regulatory) ነፃ ገበያ ካፒታሊስት ሥርዓት ነው፡፡

የዓለም ባንክ፣ የዓለም የገንዘብ ድርጅት፣ የዓለም የንግድ ድርጅትና ምዕራባውያን አገሮች በጋራ ሆነውም ዓለምን በነፃ ገበያ ኢኮኖሚ መስመር ለማስጓዝና በኢኮኖሚው ውስጥ የመንግሥትን ሚና ለመቀነስ የዋሽንግተን መግባቢያ ስምምነትን ተፈራርመው ተንቀሳቀሱ፡፡ በመዋቅር ማሻሻያ (Structural Adjustment) ፕሮግራም ስም ወደ ኢትዮጵያ ጎራ ብለውም በ1980ዎቹና በ1990ዎቹ ዓመታት ከመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በርካታ ሠራተኞች አፈናቅለዋል፡፡

የልማታዊ መንግሥት ጽንሰ ሐሳብ 

የልማታዊ መንግሥትን ጽንሰ ሐሳብ ከላይ ከተጠቀሱት ሁለት የዘመናዊነትና የጥገኝነት የኢኮኖሚ ልማት ጽንሰ ሐሳቦች ጋር የሚያመሳስላቸው፣ በልማታዊ መንግሥት መርህ በሚጓዙ አገሮች ሁለቱ ጽንሰ ሐሳቦች ጎን ለጎን በጣምራነት አብረው ስለሚኖሩ ነው፡፡ ከዚህም በላይ የዚህ ዘመን ልማታዊ መንግሥታት ከኒዮሊበራሊዝም ግሎባላይዜሽን ጋርም አብረው እየኖሩ ነው፡፡

በአንድ በኩል ጀማሪ የልማታዊ መንግሥት አገሮች ለበለፀጉ አገሮች በጥሬ ዕቃ አቅራቢነትና ከበለፀጉ አገሮች ዘመናዊ የኢንዱስትሪ ሸቀጦችን በመሸመት የበለፀጉ አገሮች ዘመናዊ ሥልጣኔ ተቋዳሽ በመሆን አብረው ሲኖሩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ የኢንዱስትሪ ምርት ለማምረት በበለፀጉት አገሮች ካፒታል፣ ቴክኖሎጂና ሙያ ላይ ስለሚሞረከዙ ዕድገታቸውና ልማታቸው በበለፀጉት አገሮች ላይ ጥገኛ ነው፡፡

ጃፓን ራሷ ሳትቀር የለማችው ራሷን ሆና ሳይሆን የበለፀጉ አገሮችን ወግና ልማድ ተውሳና አዳብራ እንደሆነ ታምኖ፣ የበለፀጉ አገሮችን ወግና ልማድ ተቀብሎ አብሮ ለመኖር የመፈለግ ዘመናዊነትና የበለፀጉ አገሮችን ካፒታል ቴክኖሎጂና ሙያ የዕድገት መሠረት ማድረግ የጥገኝነት ጽንሰ ሐሳቦች ቅልቅል ሥርዓት ነው፡፡ ስለዚህም የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብና የጥገኝነት ጽንሰ ሐሳብ ሁለት የልማታዊ መንግሥት አውታሮች ናቸው፡፡

ከመላው ዓለም በየጊዜው በርካታ አገሮች የልማታዊ መንግሥት አካሄድን መርጠው የተቀላቀሉ ቢሆንም፣ የላቀ ዕውቅና ተሰጥቷቸው ስማቸው ዘወትር በኢኮኖሚ ነክ ጽሑፎች የሚጠቀሰው ከምሥራቅና ከደቡብ ምሥራቅ እስያ አገሮች ውስጥ ጃፓን፣ ቻይና፣ ሲንጋፖር፣ ህንድ፣ ታይላንድ፣ ታይዋን፣ ቬትናም፣ ማሌዥያ፣ ደቡብ ኮሪያ፣ ፊሊፒንስና ኢንዶኔዥያ ይጠቀሳሉ፡፡ ከላቲን አሜሪካ ቺሊ፣ ኮስታሪካ ሲሆኑ ከአፍሪካም ሞሪሽየስና ቦትስዋና ናቸው፡፡

ለሰላሳ ዓመታት ያህል የዋሽንግተን መግባቢያ ስምምነት የኒዮሊበራሊዝም ፖሊሲን ሲተገብሩ ከቆዩ በኋላ በርካታ የላቲን አሜሪካ አገሮችም የልማታዊ መንግሥት ፖለቲካል ኢኮኖሚ ፍልስፍናን ተከትለው፣ በከተሞች ከኢኮኖሚ ልማት መገለልን ለማስቀረት የሥራ ፈጠራ ችሎታ ኖሯቸው ካፒታል ላጡ ወጣቶች በቀላል ወለድ ብድር ማመቻቸት ጀምረው ነበር፡፡ ሆኖም ግን ለምርቶቻቸው ፈላጊ ገበያ በማጣት ምክንያት ወደ መካከለኛ አምራች ድርጅት ሳይሸጋገሩና እንደ ልማታዊ መንግሥት ስኬታማ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡

ከአፍሪካ ሩዋንዳ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ኢትዮጵያ፣ ታንዛንያ፣ ኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ወዘተም እንደ ዕጩ ወይም በመንገድ ላይ ያሉ የልማታዊ መንግሥት አገሮች ተብለው ይጠቀሳሉ፡፡

ልማታዊ መንግሥት የኢንዱስትሪ ዕድገት ፖሊሲ በማርቀቅና አፈጻጸሙን በቢሮክራቶች ክትትል በመምራት በኢኮኖሚው ዕድገት ውስጥ ቀጥተኛ ተሳትፎ ያደርጋል፡፡ የረጅም ጊዜ ብሔራዊ ግብ አቅደው የሚንቀሳቀሱት ቢሮክራቶች የፖለቲካ ተመራጮች ስላልሆኑ፣ የሕዝብ ድምፅ ለማግኘትና ለአጭር ጊዜ የግልና ብሔራዊ ጥቅም ሲሉ በአሠሪውም ሆነ በሠራተኞች ማኅበራት ፖለቲካዊ ተፅዕኖ ሥር ስለማይወድቁ ለረጅም ጊዜ ብሔራዊ ጥቅምና ለአገር ብልፅግና እንደሚሠሩ ይታመናል፡፡ 

ልማታዊ መንግሥት ጠንካራ ሲቪል ሰርቪስ በመፍጠር፣ ለኢንቨስተር ተስማሚ ሁኔታዎች በማመቻቸት፣ የአነስተኛ ንግድ ማኅበረሰብ ልማትን በመደገፍ፣ መንግሥታዊ የልማት ድርጅቶችን ውጤታማ በማድረግ የኢኮኖሚ ልማቱን  ይመራል፡፡ ለዚህም መንግሥት ሥልታዊ፣ ተቋማዊና ቴክኒካዊ አቅም ሊኖረው ይገባል፡፡

ሥልታዊ አቅም ማለት ብሔራዊ አጀንዳ ለመቅረፅና ለመምራት መቻል ኅብረተሰቡ በብሔራዊ አጀንዳው አተገባበር እንዲሳተፍ ማድረግና ማኅበራዊ ሀብት ለዚህ አጀንዳ አፈጻጸም እንዲውል ማድረግ ናቸው፡፡ ልማታዊ መንግሥት የመንግሥት ክፍለ ኢኮኖሚን፣ የንግዱን ማኅበረሰብ፣ የሠራተኛውን ክፍልና የሲቪክ ማኅበረሰቡን አጋር በማድረግ ለዚህ የጋራ አጀንዳ ማስተሳሰር አለበት፡፡

ያለ አጋር ድርጅቶች ተሳትፎ ልማት አይታሰብም፡፡ ግልጽ፣ የሚለካና በጊዜ ገደብ የታጠረ የልማት ግብ ይዞ ተግባራዊ ለማድረግ ከተፈለገ ግብረ ገብ ያለው ትውልድ ለመፍጠር ከሃይማኖት ተቋማት ጋር አብሮ መሥራትን፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ከሠራተኛ ማኅበራትና ከንግዱ ማኅበረሰብ ጋር አብሮ መሥራትን ይጠይቃል፡፡

ልማታዊ መንግሥት ግቡን ለማስፈጸም ጠንካራና ታማኝ ሲቪል ሰርቪስ ያለበት ተቋማዊ አቅም የሚያስፈልገው፣ በመንግሥታዊ አካል እርከኖች ሁሉ ቀልጣፋና ውጤታማ መዋቅርና ሥርዓት ስለሚያስፈልገው ነው፡፡

ቴክኒካዊ አቅም የሚያስፈልገውም ሰፋፊ ግቦችን ወደ ፕሮግራሞችና ፕሮጀክቶች መንዝሮ ማስፈጸም ስላለበት ነው፡፡ ቴክኒካዊ አቅም ፕሮግራሞችን የማቀድና አፈጻጸማቸውን የመከታተል አቅምንም ይጠይቃል፡፡ እነኚህ ሁሉ ክንዋኔዎችም በቂና የተማረ የሰው ኃይል ይፈልጋሉ፡፡

ከዚህ በላይ የተገለጹትን የልማታዊ መንግሥት ቅድመ ሁኔታዎች ለማሟላት ልማታዊ መንግሥት የሚከተሉት ባህሪያት ሊኖሩት ይገባል፡፡

  • ሕጋዊ ዕውቅና ያገኘ ጠንካራ ማዕከላዊ መንግሥት፣
  • ብርቱና ቁርጠኛ ፍላጎት፣
  • ችሎታና ብቃት ያለው የባለሙያ ቢሮክራሲ፣
  • በግሉ ኢኮኖሚ ከትርፍ ይልቅ የሚገባ ድርሻ ላይ ማትኮር፣
  • የአገር ውስጥ አምራቾችን ከውጭ ከሚገቡ ሸቀጦች መከላከል፣
  • በወጪ ንግድ ላይ ያተኮረ ፖሊሲ፣
  • የውጭ ቴክኖጂ ሽግግርን መሻት፣
  • ሰፊ የመሠረተ ልማት ግንባታ፣
  • የቁጠባና ሥልታዊ ብድር አሰጣጥ ተቋማትን ማበረታታት፣
  • የመንግሥት፣ የሠራተኛውና የአሠሪው አጋርነት፣
  • የግሉ ኢኮኖሚ ለብሔራዊ ጥቅም እንዲቆም መግራት፣
  • ሁሉንም ኅብረተሰብ አካታች ልማት ናቸው፡፡

ፖለቲካዊ ኢኮኖሚ

አንዳንድ የኢኮኖሚ ልማት ጠቢባን የዘመናዊነት መገለጫ የሆኑት ኢንዱስትራላዊነት ከተሜነትና መማር የመሳሰሉ የኢኮኖሚ ልማት ጉዳዮች ከቡድን ይልቅ በግለሰብ ደረጃ የሚገለጹ ስለሆኑ፣ ከዴሞክራሲና ከፖለቲካዊ ጉዳዮች መቅደም እንዳለባቸው ያስገነዝባሉ፡፡

በዚህ የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ የኢኮኖሚ ልማት አመለካከት ፖለቲካን ከኢኮኖሚ የሚያስቀድሙ ሰዎች ያላወቀ፣ ያልተረዳ፣ በቤተሰብና በጎሳ አመለካከት ስሜታዊ የሆነና በጠባብ የዘረኝነት ፍቅር የታወረ፣ በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊ፣ በፖለቲካና በመንፈሳዊ ጥቅል ሕይወቱ ያልለማ፣ ከራሱ ኋላ ቀር አስተሳሰብም ነፃ ያልወጣ፣ በባለማወቅ ዕውቀቱ ለገዢነት ውክልና እንዲመርጣቸው ዴሞክራሲ እንዲቀድም የሚፈልጉ ናቸው፡፡

በደርግ ዘመን አሥራ ሰባት ዓመታት ከካፒታሊዝም አልፎ ሶሻሊስት ፍልስፍና ውስጥ ገብቶ በሠርቶ አደር ጋዜጣ የእነ ማርክስንና የእነ ሮዛ ሉክዘምበርግን ዓለም አቀፋዊ የወዛደር ኅብረትን ሲያነብ ሲሰማና ሲጠመቅ የኖረን ሕዝብ ወደ ኋላ በመጎተት፣ በመንደር ልጅነት አሰባስበው ሥልጣን በአቋራጭ ለመያዝ የቸኮሉ ሰዎች ፖለቲካን ከዳቦ ያስቀድማሉ፡፡

ሕዝቡ በሥራ ማጣት፣ በዋጋ ግሽበት፣ ፍትሐዊ ባልሆነ የሀብትና የገቢ ክፍፍል፣ ነጋዴው በውጭ ምንዛሪ እጦት እየተሰቃዩ ባሉበት ጊዜ የኢኮኖሚ ጉዳይ ወደ ጎን እየተገፋ፣ የፖለቲካ ትግል ያውም በብሔር የተከፋፈለ የዴሞክራሲ ጥያቄ ዋናው የአገሪቱ ጉዳይ ተደርጎ ይነገራል፡፡

ጭቁን ሕዝቦችን በብሔር ከፋፍለው ‹‹ይኼኛው የምታገልለት የብሔሬ ተወላጅ ነው፣ ያኛው የምታገለው የሌላ ብሔር ተወላጅ ነው፤›› ብለው የሚከፋፍሉ ፖለቲከኞች፣ የኩባን ትግል አብሮ መርቶ ፊደል ካስትሮ ሥልጣን እንደያዙ ሁለተኛውን የሥልጣን እርከን የፕላን ሚኒስትርነትን ሹመት ቢሰጡት ትግሌ ለዓለም ጭቁኖች ሁሉ ነው ብሎ ቦሊቪያ ሄዶ መንግሥት ለመጣል ሲታገል ተይዞ ከተገደለውና በ1960ዎቹ ተማሪዎች አብዝተው ከዘመሩለት የአርጄንቲና ተወላጅ ቼ ጉቬራ ዓላማ ጋር የሚጋጩ ናቸው፡፡

‹‹ስለብሔሬ ሰው እንጂ ስለሌላው ሰው አያገባኝም›› የሚል ጠባብ ፖለቲከኛነት ገብጋባነት ስለሆነ፣ በግለሰብ ብልፅግና የሚያምነውን የ1950ዎቹን የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ የኢኮኖሚ ልማት አመለካከት አይወክልም፡፡ ድክመቶቹ ሁሉ እንዳሉ ሆኖ የግሎባላይዜሽን ዘመንን ብልፅግና በገበያ ኃይሎች አማካይነት ለሠራ ሰው ሁሉ በእኩልነትና በውድድር ይዳረሳል:: በግለሰብ ልፋትና የላብ ዋጋ ላይ ያነጣጠረ ዓለም አቀፋዊ የኢኮኖሚ ዕድገትና የልማት ጽንሰ ሐሳብ አመለካከትንም አያንፀባርቅም፡፡

ኢኮኖሚስቶች እንደሚሉት አንድ ሰው ለፖለቲካ ሥልጣን ድምፅ ሲሰጥ ‹‹ሰውየውን ሳይሆን ዳቦውን ነው የመረጠው››፡፡ ዘመናዊና ሀቀኛ ፖለቲከኞችም ከራሳቸው ይልቅ ለሰው አሳቢ ሆነው ሕዝብ ‹‹ሰውን ሳይሆን ዳቦውን›› እንዲመርጥ የሚመክሩ ናቸው፡፡ ስለሆነም በዴሞክራሲ ስም ለመወከልና ፓርላማ ለመግባት ከመሽቀዳደም በፊት፣ ሕዝቡ ማንን ለምን እንደሚመርጥ ለሰው ብሎ ሳይሆን ለራሱ ሲል እንዲመርጥ ማስተማር፣ መጻፍ፣ መናገር፣ ሕዝብም የሚለውን መስማትና መማር ያስፈልጋቸዋል፡፡ ይኼን የሚያደርጉ ሰዎች ከእነርሱ ሥልጣን መያዝና ከእኔ በላይ ሰው የት አለ አስተሳሰብ የሕዝብን ብልፅግና የሚያስቀድሙ ናቸው፡፡

የልማታዊ መንግሥት ዓለም አቀፋዊ ስኬትን የመረመሩ የኢኮኖሚ ልማት ጠቢባን እንደ ምሳሌ ሲያነሱም ታይዋንና ደቡብ ኮሪያ በዘመናዊነት ከበለፀጉ በኋላ፣ ዴሞክራሲን በቀላሉ ሲገነቡ ከብልፅግና በፊት ዴሞክራሲን ለመገንባት የፈለጉት ፊሊፒንስ፣ ባንግላዴሽ፣ ካምቦዲያ፣ ታይላንድ፣ ኢንዶኔዥያ፣ ህንድ በዴሞክራሲያዊውም በልማቱም ሁለገብ ስኬት ትርጉም የፈለጉትን ያህል አልሆነላቸውም ይላሉ፡፡

ጽንሰ ሐሳብና እውነታ

በፍጥነት ከበለፀጉት የቀድሞ ታዳጊ አገሮች መካከል ቻይናንና ደቡብ ኮሪያን የመሳሰሉ የምሥራቅ እስያ አገሮች፣ ታይዋንን ሲንጋፖርን የመሳሰሉ የደቡብ ምሥራቅ እስያ አገሮች፣ በነዳጅ ሀብታም የሆኑ የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮችና አንዳንድ የላቲን አሜሪካ አገሮች ይጠቀሳሉ፡፡

እነዚህ አገሮች ምንም እንኳ የበለፀጉ አገሮች ወደ አገሮቻቸው የፋብሪካ ምርት ኤክስፖርት እንዳያደርጉ እክሎች ቢፈጥሩባቸውም፣ የኤክስፖርት ምርቶቻቸውን በጥንቃቄ በመምረጥ የበለፀጉ አገሮች ኤክስፖርት ገበያ ሰብረው በመግባት የተዋጣላቸው ልማታዊ መንግሥታት ሆነዋል፡፡

በቅድሚያ ሆንግ ኮንግ፣ ደቡብ ኮሪያ፣ ሲንጋፖርና ታይዋን አራቱ ነብሮች ቀጥሎም ኢንዶኔዥያ፣ ማሌዥያና ታይዋን ኢምፖርትን በመተካትና ገበያ ሰብሮ በመግባት በኤክስፖርት ቅይጥ የንግድ ፖሊሲያቸው ዕድገታቸውን አፋጥነዋል፡፡ ከአፍሪካም ሞሪሽየስ የኢንዱስትሪ ዕድገቷን በማፋጠንና ቦትስዋና ያላትን የተፈጥሮና የማዕድን ሀብት ክምችት በአግባቡ በመጠቀም ምክንያት የተሳካላቸው ልማታዊ መንግሥታት ተብለዋል፡፡

ቻይናም በድርጊቷ አሜሪካን ኡኡ እስክትል ድረስ ብታበሳጫትም በዓለም አቀፍ ንግድ ስምምነት የተከለከሉትን ታሪፍና ኮታ ሳትጠቀም ምንዛሪዋን በማርከስ (Currency Undervaluation) ሥልቷ ብቻ፣ በአገሯ ውስጥ ኢምፖርትን ውድ በማድረግና በውጭ አገር ኤክስፖርቷን ርካሽ አድርጋለች፡፡ ኢምፖርትን በመተካት በኢንዱስትሪያላይዜሽን ወደ ውስጥ መመልከትና የገለልተኝነት ወይም ኤክስፖርት ተኮር የወጪ ንግድ ፖሊሲዎቿ የተዋጣላት የልማታዊ መንግሥት ተምሳሌት ሆናለች፡፡ በዚህም የገበያ ኢኮኖሚንም የኢኮኖሚ ልማትንም ፖሊሲዎች አጣምራ አስኬዳለች፡፡

አሜሪካ አፀፋዊ ዕርምጃ እንዳትወስድ ምንዛሪዋ ከብዙ አገሮች ምንዛሪ ጋር በዋጋ የተቆራኘ ስለሆነ ቀውስ ያመጣል ብላ ስላመነች አልቻለችም እንጂ፣ ከቻይና ጋር የምንዛሪ ማርከስ ጦርነት ውስጥ ይገቡ ነበር፡፡

በድህነት ከሚታወቁት የልማታዊ መንግሥታት መካከል ከፍተኛ የሕዝብ ብዛት ያላቸውና ሁከት ያልተለያቸው ባንግላዴሽና ፓኪስታን በተወሰነ ደረጃ ህንድ፣ እንዲሁም ኮትዲቯርን፣ ማላዊን፣ ኬንያን፣ ዛምቢያን፣ ዚምባብዌን በመሳሰሉት በዘርና በጎሳ ፖለቲካ ምክንያት ያልዘለቁ ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገሮች ይገኙባቸዋል፡፡

ኢትዮጵያስ ከየትኛው ጎራ ትመደብ ይሆን? የትኞቹን ልማታዊ መንግሥታት ትመስላለች? ከልማታዊ መንግሥት ቅድመ ሁኔታ ባህሪያትስ የትኞቹን ታሟላለች? የትኞቹ ይጎድሏታል? ዓይነ ጥላችንን ገፍፈን ሳይመሽ በጊዜ እንመልከት፡፡ ‹‹ገበያ ሲያመልጥና ራስ ሲመለጥ አያስታውቅም›› እንዲሉ፡፡

መደምደሚያ

ባህልና ታሪክ በልማታዊ መንግሥት አፈጣጠር ላይ ተፅዕኖ አላቸውን? የምሥራቅ እስያ ልማታዊ መንግሥታት ተሞክሮ ወደ ሌሎች አገሮች ሊሸጋገርና በሌሎች አገሮች ሊገለበጥስ ይችላልን? የሚሉ ጥያቄዎች በልማታዊ መንግሥት ተመራማሪዎች ይነሳሉ፡፡ እኛም የዘመናዊነትና የጥገኝነት ቀደምት የኢኮኖሚ ልማት ጽንሰ ሐሳቦች ከልማታዊ መንግሥት ፖሊሲ ጋር እንዴት ይገናዘባሉ? የቀድሞዎቹ ጽንሰ ሐሳቦች በኢኮኖሚ ልማት ፖሊሲው ላይ ተፅዕኖ አሳድረዋልን? ብለን ስለራሳችን ሁኔታ መጠየቅ እንችላለን፡፡

ዛሬ በምናያት ኢትዮጵያ የ1950ዎቹና የ1960ዎቹ የዘመናዊነትና የጥገኝነት ጽንሰ ሐሳቦች ጎልተው ይታያሉን? የዘመናዊነቱና የጥገኝነቱ ሁኔታ የሚታየው እንደ ሸማችነት ነው? ወይስ እንደ አምራችነት? ብለን ራሳችንንም መጠየቅ እንችላለን፡፡ መነሻችን ላይ ማንን እንመስል ነበር? ዛሬ ማንን እንመስላለን? ከዛሬ ተነስተን ነገን ስናይ ማንን ልንመስል እንችላለን?

በኤክስፖርት ምርት የምዕራባውያንን ገበያ ሰብረው የገቡትን ደቡብ ኮሪያን፣ ታይዋንን፣ ታይላንድን፣ ሲንጋፖርን፣ ቻይናን ወይስ የሕዝባቸው ብዛትና የእርስ በርስ ሽኩቻ የኢኮኖሚያቸውን ዕድገት ያነቀውን ባንግላዴሽን፣ ፓኪስታንን፣ ህንድን? የእኛ የወጣቶች የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንዱስትሪዎች ሥራ ፈጠራ ፓኬጅ ከላቲን አሜሪካ አገሮች  ከተሞች የኢኮኖሚ ልማት ፕሮግራም ጋር እንዴት ይነፃፀራል? ይመሳሰላል? ወይስ ይለያያል?

እነ ማንን እንደምንመስል፣ ከነማን እንደምንለይ፣ ፍርዱን ለአንባቢያን ትቼ በዘመናዊነትና በጥገኝነት ጽንሰ ሐሳቦች የኢኮኖሚ ልማት መነጽሮች ከተጨባጭ ነባራዊ ሁኔታ ተነስቼ ስለእኛ የምለው የሚከተለውን ነው፡፡

እንደ ሸማች በዘመናዊነት ከፈረንጅ ሰልቫጅ ጨርቅ ለባሽ የአዲስ አበባ ባለመኪና አንስቶ እስከ እንስሳትና ሰዎች አብረው በሚኖሩበት ሣር ክዳን የገጠር ቤት ሳይቀር የሳተላይት ቴሌቪዥን ተጠቃሚ ሆነን በበለፀጉት አገሮች የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ ኢኮኖሚ ልማት ውስጥ የተዘፈቅን ነን፡፡

እንደ አምራች ግን ለጥቃቅን የቤት ውስጥ የፍጆታ ቁሳቁሶችና አነስተኛ ማምረቻ መሣሪያዎች እንኳን በበለፀጉት የነፃ ገበያ ካፒታሊስት አገሮች ኢኮኖሚ ላይ ጥገኛ እንደሆንን ነው፡፡ ይኼ እንደ ሸማች የመዘመንና እንደ አምራች የጥገኝነት ክፍተት ሰዓት ቆጥሮ እንደሚፈነዳ ፈንጂ ነው፡፡ እኛም ፈንጂው ላይ ተቀምጠን የሚፈነዳበትን ጊዜ የምንጠብቅ እንመስላለን፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው getachewasfaw240@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

Standard (Image)

የዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫን ማሸነፍ ከአፍሪካ ቀንድና ከኢትዮጵያ ግንኙነት አንፃር

$
0
0

በሉሉ ድሪባ

በቅርቡ ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነው በመመረጣቸው ለበርካታ አገሮችና መሪዎች ጥያቄ ፈጥሯል። በብዙዎች ዘንድ የዶናልድ ትራምፕ መመረጥ ያልተጠበቀ ከመሆኑም ባሻገር፣ የፕሬዚዳንቱ የውጭ ፖሊሲ ከዚህ በፊት ከነበሩት የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ለየት ያለና አወዛጋቢ ነው። የትራምፕ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ የሚያጠንጥነው ቅድሚያ ለአሜሪካ በሚለው ላይ ነው፡፡ ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ  ከዓለም ዙሪያ ወደ አሜሪካ የሚደረገውን ስደትን መቆጣጠር፣ አሜሪካ ከሌሎች አገሮች ጋር የሚኖራትን የንግድ እንቅስቃሴ መቀየር፣ የዓለም አየር ንብረትን በተመለከተ የተለየ አቋም መያዝና ለታዳጊ አገሮች የሚደረጉ ሰብዓዊ ዕርዳታዎችን መቀነስ ወይም መከልከል የሚሉት በግንባር የሚጠቀሱ ናቸው። እንዲሁም ዓለም አቀፋዊ የሊብራል ሥርዓትን በመቃወም አምባገነናዊ መሪዎችን ለምሳሌም ለሩሲያ መሪ ለፑቲን በይፋ አድናቆቱን በመግለጽ ቀደም ሲል የአሜሪካ ወዳጅና አጋር ከሆኑት አገሮች ጋር ያለው ግንኙነት እንደሚለወጥ እየገለጸ ይገኛል።

እንዲሁም ከሙስሊሙ ዓለም ጋር ያለው ግንኙነትና አክራሪነትን ለመዋጋት የሚከተሉት ስትራቴጂ ግልጽነት ካለመኖሩም በተጨማሪ፣ ከታዳጊ አገሮች ለአብነትም ከአፍሪካ አገሮች ጋር የሚኖረው የአሜሪካ ወዳጅነትና ሰብዓዊ ዕርዳታ ጋር ተያይዞ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ሲያነሱዋቸው የነበሩ ጉዳዮች ከዚህ በፊት ያልተለመዱ ከመሆናቸው የተነሳ በዓለም ማኅበረሰብ ዘንድ ጥያቄ ጭረዋል። በተለይም በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ዶናልድ ትራምፕ ለአፍሪካ አገሮች ምን ዓይነት ፖሊሲ እንደሚኖራቸው ሰፋ ባለ መልኩ ባይገልጹም፣ ስለአኅጉሩ ጥቂት ከተባሉት መካከል ዋነኛው የአፍሪካ መሪዎች ለሕዝቦቻቸው መልካም አስተዳደር ስለሌላቸው እንደገና 100 ዓመታት በቅኝ ግዛት መተዳደር አለባቸው በማለት በትዊተር ገጻቸው ላይ ያሰፈራት ይገኝበታል።

በመሆኑም የብዙዎቹ ጥያቄ በቅርቡ የተመረጡት የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ያደረጉዋቸው ንግግሮችን ተግባራዊ ያደርጋሉ? ወይስ አያደርጉም? የሚለው ነው። ይህንን ጥያቄ ለመመለስ ሁለት አተያዮችን ማየት ያስፈልጋል። የመጀመሪያው የዶናልድ ትራምፕ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ቀጣይነት ያለው፣ የቆየና በግለሰቡ እምነት ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ተግባራዊ ሊሆን እንደሚችል ነው። በሌላ በኩል ደግሞ የግለሰቡ ልምድ ማነስ፣ የአሜሪካን የውጭ ግንኙነቶች ውስብስበነት ጠንቅቆ ያለማወቅና የአገሪቱን ጥቅሞች ለይቶ ከማስከበር አኳያ ፕሬዚዳንቱ አሁን ያላቸው ግንዛቤ የተዛባ በመሆኑ፣ ወደፊት ከውጭ ጉዳይ ባለሙያዎች ጋር በመወያየት መሥራት እንደሚችሉ ይገልጻሉ።

ስለሆነም አሁን መታየት ያለበት በቅስቀሳ ወቅት ፕሬዚዳንቱ ያደረጓቸው ንግግሮች ሳይሆኑ አሜሪካ ከሌሎች አገሮች ጋር በምታደርገው ግንኙነት ብሔራዊ ጥቅሞችን ማዕከል ማድረግ አለባቸው። ማለትም የፕሬዚዳንቱ አመለካከትና እምነቶች በአገሪቷ ውጭ ግንኙነቶች ላይ ያለው ተፅዕኖ የማይካድ ቢሆንም፣ የአገሪቱን ጥቅም በተሻለ ሁኔታ ተገንዝቦ ውሳኔ ይሰጣሉ በማለት የሚሾሙዋቸው የካቢኔው አባላትና አማካሪዎችም የላቀ ድርሻ ይኖራቸዋል። ከዚህ በመነሳት አሜሪካ ከአፍሪካ ቀንድ ጋር የሚኖራት ግንኙነት የሚወሰነው ፕሬዚዳንቱ በምርጫ ወቅት ያደረጓቸው ቅስቀሳዎችን ብቻ ሳይሆን፣ የአሜሪካ መሠረታዊ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዎችንና በቀጣናው አገሪቷ ያላት ጥቅሞችን ባማከለ መንገድ የፕሬዚዳንቱንና የሌሎች ሹማምንቶች አመለካከቶችንና እምነቶችን፣ እንዲሁም በዘርፉ ላይ የቆዩ ሙያተኞችንና አማካሪዎችን አስታውሰው ግንዛቤ ውስጥ ማስገባት መቻል አለባቸው።

የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላምም ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እ.ኤ.አ. የ2016 የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ማሸነፍ፣ አሜሪካ ከአፍሪካ ቀንድ ብሎም ከኢትዮጵያ ጋር የሚኖራትን የግንኙነት ሁኔታዎች በመዳሰስ ምን ዓይነት ለውጦች ሊኖሩ እንደሚችሉ ለመገመት ነው። በዚህ መሠረት ይህ ሪፖርት ሦስት ክፍሎችን የያዘ ሲሆን፣ የመጀመሪያው አሜሪካ ከአፍሪካ ቀንድ ጋር ያላትን የቆዩ የግንኙነት ታሪኮችን መዳሰስና አገሪቷ ወደፊትም በቀጣናው የሚኖራት ብሔራዊ ጥቅሞችን መተንተን፣ በሁለተኛው ክፍል አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት ጥቅሞችንና ተግዳሮቶችን መዳሰስ፣ በሦስተኛ ክፍል ደግሞ ለአዲሱ ፕሬዚዳንትም ሆነ ለሌሎች ሹማምንት አፍሪካ ቀንድ ብሎም ኢትዮጵያ ለአሜሪካ ምን ዓይነት ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ እንደሚኖራት በመተንተን የተለያዩ ትዕይንቶች (Scenarios) ማሳየት ነው።

  • በአፍሪካ ቀንድ ያላት ፍላጎት

አፍሪካ ቀንድ ለአሜሪካ ስትራቴጂካዊ ቀጣና ነው፡፡ ምክንያቱ የቀጣናው ጂኦግራፊያዊ መገኛ በአንድ በኩል በነዳጅ ከበለፀገው የመካከለኛ ምሥራቅ አገሮች ባለው ቅርበት ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የአፍሪካ ቀንድ ሦስት አኅጉሮች ማለትም እስያ፣ አውሮፓና አፍሪካን የሚያገናኝ ቁልፍ ቦታ ነው።  ከጥንት ጀምሮ የተለያዩ ኃያላን አገሮች ቀጣናውን ለመቆጣጠር ፉክክር በማድረግ ቆይተዋል። በአሁኑ ወቅትም በአፍሪካ ቀንድ ፍላጎት ካላቸው አገሮች መካከል በዋናነት የባሕረ ሰላጤው ዓረብ አገሮች፣ ግብፅ፣ የአውሮፓ ኅብረት፣ ቻይናና ህንድ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱ ናቸው። ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በኋላ ለአሜሪካ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ካላቸው አካባቢዎች አንዱ አፍሪካ ቀንድ ሲሆን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህም ለአገሪቷ የቀጣናው አስፈላጊነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል። ለአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ አስፈላጊነት በአንድ በኩል ቀጣናው ከመካከለኛ ምሥራቅ ጋር ያለው ጂኦ-ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ሃይማኖታዊ ትስስሮች ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ አሜሪካ ከሌሎች አፍሪካ አገሮች ጋር የጠበቀ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ግንኙነት ለማድረግ አፍሪካ ቀንድን መቆጣጠር ይኖርባታል። ከሁሉም በላይ ደግሞ እ.ኤ.አ. በ1998 የአሜሪካ ኤምባሲዎች በምሥራቅ አፍሪካ ጥቃት ከደረሰባቸው በኋላ፣ እንዲሁም እ.ኤ.አ. በ2001 ‹‹የ9/11›› ጥቃት ተከትሎ አሜሪካ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት ከምታደርገው እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ፣ ቀጣናው ሽብርተኝነትን ለመዋጋት ትኩረት ውስጥ እንዲገባ አድርጎታል። አፍሪካ ቀንድ ለአሸባሪዎች መጠለያና ለእስልምና አክራሪነት ተጋላጭ ሥፍራ ነው። ለዚህም አመላካች የሚሆነው አብዛኛው የቀጣናው ማኅበረሰብ የእስልምና ተከታዮች መሆናቸውና ቀጣናው የእስልምና አክራሪነት ማፍለቂያ ከሆኑ ከመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ጋር ማኅበራዊ ትስስር ያላቸው መሆኑ ነው። ለምሳሌም አልቃይዳ በአካባቢው ሲያደርግ የነበረው እንቅስቃሴና በአሁኑ ወቅትም የአልሸባብ አሸባሪ ቡድን እንቅስቃሴ ቀጣናው ምን ያህል ለእስልምና አክራሪነትና ለሽብርተኝነት ተጋላጭ እንደሆነ ያሳያል። ስለሆነም ያለፉት የአሜሪካ መሪዎች ክሊንተን፣ ቡሽና ተሰናባቹ ኦባማም አሜሪካ በቀጣናው ያላትን ፍላጎት ለማስከበር ከሞላ ጎደል ተመሳሳይ ፖሊሲዎች ይከተሉ ነበር።

በቀጣናው የአሜሪካ ዋና ተልዕኮ በጥቅሞቿና በወዳጆቿ ላይ ጥቃት እንዳይደርስ በማድረግ፣ በአካባቢው የሚገኙ ዓለም አቀፋዊ የሽብር ቡድኖችና የባህር ላይ ዘራፊዎችን እንቅስቃሴዎች መግታት፣ መደምሰስና የቡድኖቹን ትስስርና ግንኙነቶችን መበጣጠስ ላይ ያተኮረ ስትራቴጂካዊ እንቅስቃሴዎችን ታደርጋለች። ይህንን ዓላማዋን ከግብ ለማድረስ አሜሪካ ከአፍሪካ ቀንድ ዋነኞቹ ወዳጆቹዋ ከሆኑት ከጂቡቲና ከኢትዮጵያ ጋር በአጋርነት ስትሠራ ቆይታለች። ለዚህም እ.ኤ.አ በ2002 ዓ.ም. በጂቡቲ ወታደራዊ የጦር ሠፈር ወይም ጣቢያ በማቋቋም ጠንካራ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ትገኛለች። በተመሳሳይ ሁኔታ ከኢትዮጵያ ጋርም በአጋርነት የአካባቢው ደኅንነት ለመጠበቅ ይሠራሉ።

አዲሱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንትም ቢሆኑ የአፍሪካ ቀንድ ጂኦ-ፖለቲካዊና ስትራቴጂካዊ ጥቅሞችን ያገናዘበ ፖሊሲ ይከተላሉ የሚል ግምት አለ። ምክንያቱም የቀጣናው ስትራቴጂካዊ ጥቅም ለአሜሪካ የላቀ በመሆኑ፣ ይህንን ጥቅም ለማስከበር ቀደም ሲል እንደነበረው የተለያዩ ስትራቴጂካዊ ዕርምጃዎችን መከተል ይኖርባቸዋል። ዶናልድ ትራምፕ ምን ዓይነት ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በአፍሪካ ቀንድ ሊኖራቸው እንደሚችል ከማየት በፊት፣ ቀደም ሲል የአሜሪካ መሪዎች በቀጣናው ጥቅሞቻቸውን ለማስከበር ሲከተሉዋቸው የነበሩ ስትራቴጂዎችን ማየት ተገቢ ነው።

ቀዝቃዛው ጦርነት ካከተመ በኋላ አሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ ያላትን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ሦስት የተለያዩ ስትራቴጂዎችን ስትከተል እንደነበረች ውድዋርድ የተባለው አጥኚ ገልጿል። የመጀመሪያው ሙሉ በሙሉ በወታደራዊ ጣልቃ ገብነት በቀጣናው ያላትን ጥቅም ማስጠበቅ ሲሆን፣ ይህንን ለማድረግ እንደ ሽፋን ሆኖ የሚያገለግል አስከፊ ሰብዓዊ ቀውስ ለመከላከል የሚል ነው። ለአብነትም እ.ኤ.አ 1992-93 በሶማሊያ ውስጥ የአሜሪካ ጣልቃ ገብነት የሚገለጸው በሰብዓዊ ቀውስ አማካይነት ነው። በዕርምጃው ምንም እንኳን የሰው ሕይወት ተርፏል ቢባልም፣ አፈጻጸሙ በተለያዩ ሥልቶችና ታክቲኮች ከተቀረው የዓለም ማኅበረሰብ ጋር በደንብ ያልታቀደና ያልተደራጀ ኦፕሬሽን ነበረ፡፡ ለአሜሪካ ፖሊሲም ሆነ መሬት ላይ ያለው እውነታ ለሶማሊያ ማኅበረሰብ ያልተጠበቀና ያልተፈለገ ውጤት አስከትሏል። እ.ኤ.አ. በ1998 በምሥራቅ አፍሪካ የሚገኙ ኤምባሲዎቿ በአልቃይዳ ጥቃት ከደረሰባቸው በኋላ በደኅንነት ምክንያት አሜሪካ በቀጣናው የኃይል ዕርምጃ ተጠቅማ የሰብዓዊ ቀውስ የመከላከል ፖሊሲዋን አቋርጣለች። በአጠቃላይ በ1990ዎቹ አሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ የነበራት የወታደራዊ ዕርምጃ ፖሊሲ እንደተጠበቀው ስኬታማ ሊሆን አልቻለም።

አሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ ስትጠቀም የነበረው ሁለተኛው ስትራቴጂ ፀረ አሜሪካ የሆነን መንግሥት ማወክ (Destabilization) ሲሆን፣ ይህንን ሥልት ስትጠቀም በቀጣናው ባሉ ተቃዋሚ ኃይሎችና ጎረቤት አገሮች አማካይነት አንዱ በሌላው ላይ እንዲነሳ በማድረግ ነው። ለምሳሌም በ1990ዎቹ አጋማሽ የሱዳን መንግሥት ለእስልምና አክራሪዎች የሚሰጠውን ሽፋን ለማስቆም የአሜሪካ መንግሥት እንደ ስትራቴጂ የተጠቀመው በቀጣናው ያሉ አጋር አገሮችን በመጠቀም ለሱዳን ተቃዋሚዎች ድጋፍ መስጠት ነው። ይህንን ስትራቴጂ በመጠቀም በወቅቱም የአሜሪካ መንግሥት ለእስልምና አክራሪነት ሽፋን ሲሰጥ የነበረውን የሱዳን መንግሥት ከሥልጣን እንዲወገድ ቢያደርግም፣ እ.ኤ.አ ከ1998 እስከ 2000 በኢትዮጵያና በኤርትራ ድንበር የተቀሰቀሰው ግጭት የፀረ አሜሪካ መንግሥትን ማወክ ስትራቴጂ ውጤታማ እንዳይሆን ምክንያት ሆኗል።

ሌላኛው ስትራቴጂ ማዕቀቦችን መጣል ነው፡፡ አሜሪካ የምትጥላቸው እነዚህ ማዕቀቦች ከአሁን ይልቅ በፊት ውጤታማ እንደነበሩ ይገለጻል። ደቡብ አፍሪካውያን በአፓርታይድ ሥርዓት ሥር በነበሩበት ጊዜ፣ በ1990ዎች የኢራቅን መንግሥት ለማዳከም፣ እንዲሁም በሊቢያ ላይ የተደረጉ ማዕቀቦች ውጤታማ ነበሩ። በመጀመሪያዎቹ 1990ዎች አሜሪካ ዓለም አቀፋዊ ማዕቀቦች በሱዳን ላይ እንዲጣሉ ብዙ ጉትጎታ ካደረጉት አገሮች የመሪነት ሚና ቢኖራትም፣ እሷ እንደፈለገችው የመላው ዓለም ሕዝብን ድጋፍ ማግኘት ባለመቻልዋ ውጤታማ ሊሆን አልቻለም። በወቅቱ በሱዳን ላይ የሚጣሉ ማዕቀቦችን ካወገዙት አገሮች መካከል አንዷ ግብፅ ነበረች፡፡ ምክንያቱም ዕርምጃው በቀጥታ በራሷ ብሔራዊ ጥቅም ላይ አሉታዊ ጎን ስለነበረው ነው። በተመሳሳይ ሁኔታ እ.ኤ.አ. በ2004 ዓ.ም. በዳርፉር ጉዳይ ላይ የተለያዩ ማዕቀቦችን በሱዳን ላይ እንዲጣል የአሜሪካ መንግሥት ቢፈልግም፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት አባል የሆኑት ሩሲያና ቻይና ማዕቀቦቹ እንዳይጣሉ በማድረግ ሊያጡ የሚችሉትን የራሳቸውን ጥቅም መከላከል ችለዋል።  በወቅቱም በተመድ ውሳኔ ቅሬታ የነበራት አሜሪካ ራሷ በሱዳን ላይ ማዕቀቦችን የጣለች ሲሆን፣ የዳርፉር ቀውስ ከቀጠለ ወደፊትም በርካታ ማዕቀቦችን እንደምትጥል ገልጻ ነበር። አሜሪካ በሱዳን ላይ የጣለቻቸው ማዕቀቦች በዋናነት ዕርዳታና ኢንቨስትመንት ማቋረጥ፣ ትልልቆቹ ዓለም አቀፍ ተቋማት በአገሪቱ ውስጥ ያላቸውን ሚና መቀነስና የመሳሰሉት ነበሩ። አሜሪካ በሱዳን ላይ የጣለቻቸው ማዕቀቦች ሱዳንን ክፉኛ ሊጎዱዋት የሚችሉ ቢሆንም፣ የነዳጅ ሀብቷን ለማልማት ከእስያ አገሮች ድጋፍ ማግኘት በመቻልዋ በተወሰነ ደረጃ ማዕቀቦቹን መቋቋም ችላለች።

አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት ፋይዳዎችና ተግዳሮቶች  

ኢትዮጵያና አሜሪካ የቆየ የሁለትዮሽ ግንኙነት ያላቸው ናቸው ግንኙነታቸውም ቀስ በቀስ እያደገ ሲመጣ ሁለቱም አገሮች በአፍሪካ ቀንድ አካባቢያዊ ደኅንነትና ንግድ ላይ የተመሠረተ የትብብር ግንኙነታቸውን ይበልጥ አጠናክረዋል። የኢትዮጵያ ጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ ሲታይ አገሪቷ በምሥራቅ አፍሪካ ከሚገኙት ባርካታ አገሮች ማለትም ከሱዳን፣ ከኤርትራ፣ ከሶማሊያ፣ ከጂቡቲና ከኬንያ ጋር የምትዋሰን ስለሆነች፣ እንዲሁም በአካባቢው የቆየ ታሪክ ስላላት ለአሜሪካ ልዩ የሆኑ ስትራቴጂካዊ ጠቃሜታዎች አሉዋት።

ከ1970ዎቹ ጀምሮ የአሜሪካ ኢኮኖሚ መዳከሙንና የዋጋ ንረቱን እያባባሰ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ፣ በወቅቱ ሥልጣን ላይ የነበራት የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ኒክሰን ችግሮቹን ለመቅረፍ የኒክሰን ዶክትሪንና ʻዴታንትʼ በሚል እንደገና አዲስ የውጭ ፖሊሲ ቀርፀዋል። የፖሊሲው ዋና ዓላማ የነበረው አሜሪካ በቀጥታ በሌሎች አገሮች የምታደርገውን ወታደራዊ ተሳትፎ መቀነስ እንዳለበት የሚያሳይ ቢሆንም፣ ለተመረጡ ወዳጅ አገሮች በቂ የመሣሪያና ሌሎች ድጋፎችን መስጠት እንዳለባት ይገልጻል። በወቅቱም የኢትዮጵያ መንግሥት የአሜሪካን ዓለም አቀፋዊ አጀንዳ ባይረዳውም ከአፍሪካ ቀንድ አገሮች ኢትዮጵያ በኒክሰን ዶክትሪን ውስጥ የተካተተች አገር ነበረች። በመሆኑም እ.ኤ.አ. በ1953 አሜሪካና ኢትዮጵያ 25 የመከላከያ ስምምነቶች ባደረጉት መሠረት፣ በስምምነቱ ኢትዮጵያ በቀጣናው ለአሜሪካ ወዳጅነት ቁልፍ አገር እንደሆነች ተገልጿል። ስምምነቱ አሜሪካ ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ድጋፍና ወታደራዊ ሥልጠና ማድረግ እንዳለባት ሲገልጽ፣ ኢትዮጵያ ደግሞ በበኩሏ ለአሜሪካ ወታደራዊ ጣቢያ ለመስጠት በመስማማት ለመጀመሪያ ጊዜ ቃኘው የተባለው የአሜሪካ ወታደራዊ ጣቢያ እንዲመሠረት ምክንያት ሆኗል። 

አሜሪካ በፖሊሲዋ ኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ አጋርዋ መሆንዋ ብትገልጽም፣ ከጊዜ በኋላ ግን ኢትዮጵያ ለአሜሪካ የነበራትን አስፈላጊነት በተለያዩ ምክንያቶች ሊቀንስ ችሏል። ለዚህም እንደ ምክንያትነት ከተገለጹት መካከል የመጀመሪያው የሳተላይት ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ከመሻሻሉ ጋር ተያይዞ የቃኘው ወታደራዊ ጣቢያ አስፈላጊነት መቀነሱና አሜሪካ ከቃኘው የተሻለ የወታደራዊ ጣቢያ በህንድ ውቅያኖስ የዲያጎ ጋርሺያ ደሴት ላይ ማግኘቷ ነው። ሌላው ምክንያት አሜሪካ በወቅቱ ኢትዮጵያ ማስተካከል እንዳለበት የገለጸችው አገራዊ ጉዳዮችን ማለትም ዘመናዊ ሕግ ሥርዓት መዘርጋት፣ ለኤርትራ መብቶች መስጠት፣ ሥልጣን ወደታች ማውረድ ወይም የሥልጣን ክፍፍል ማድረግ አለመቻሏ እንደ ምክንያት ተጠቅሷል።

በአፄ ኃይለ ሥላሴ ጊዜ አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር የነበራት ፖሊሲ ሙሉ በሙሉ ባትለውጥም፣ ደርግ ሥልጣን ከያዘ በኋላ የሁለቱም አገሮች ግንኙነት እየሻከረ መጥቷል። ይህ ወቅት ቀዝቃዛው የዓለም ጦርነት እንደመሆኑ መጠን፣ የአፍሪካ ቀንድ አገሮች ከመቼውም ጊዜ በላይ ስትራቴጂካዊ ሥፍራ ከመሆኑ የተነሳ ሩሲያና አሜሪካ ቀጣናውን ለመቆጣጠር ፉክክር ውስጥ የገቡበት ጊዜ ነበር። በወቅቱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተር ወደ ሥልጣን ሲመጡ አሜሪካ ከሌሎች አገሮች ጋር የሚኖራት ፖሊሲ  ከሰብዓዊ መብት ማክበር ጋር በመያያዙ፣ እንዲሁም የግራ ዘመም ፖለቲካ አቀንቃኝ የነበረው የደርግ መንግሥት ከአሜሪካ ወታደራዊ ድጋፍ ማግኘት ባለመቻሉ ግንኙነቱን ወደ ሩሲያ ቀይሮታል።  ከዚህ ጋር ተያይዞም አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር የነበራትን ግንኙነት በማቋረጥ ከ1969 እስከ 1970 ዓ.ም. ድረስ በኦጋዴን ጦርነት ለሶማሊያ ወታደራዊ ድጋፍ አድርጋለች። ይሁን እንጂ ከቀዝቃዛው ጦርነት ማብቃት በኋላ አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት በአዲስ መልክ ተጀምሯል።

በዶናልድ ትራምፕ የሥልጣን ዘመን አሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ ሊኖራት የሚችል ፖሊሲ

ሀ. ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት ቀዳሚ ትኩረት ብለው የለዩዋቸው ጉዳዮችን መሠረት በማድረግ የአሜሪካ ጥቅሞች ሲገመገሙ

45ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡት ዶናልድ ትራምፕ በአፍሪካ ቀንድ ምን ዓይነት ፖሊሲ አቅጣጫ ሊከተሉ እንደሚችሉ ለማወቅ የመጀመሪያው ተግባር፣ አዲሱ ፕሬዚዳንት በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ያላቸውን በደንብ መመልከት ነው።  ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ምንም እንኳን የአፍሪካ ቀንድ ፖሊሲው ምን እንደሚመስል በግልጽ ባያስቀምጥም፣ አጠቃላይ የውጭ ፖሊሲውን በመመልከት ምን ዓይነት ሊሆን እንደሚችል ግን መገመት ይቻላል። ፕሬዚዳንቱ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት የተናገራቸው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አቅጣጫዎች ተግባራዊ የሚያደርግ ከሆነ የአፍሪካ ቀንድ ፖሊሲው በዋናነት የአካባቢው ደኅንነት፣ ሽብርተኝነትን መዋጋት፣ የገንዘብና ሰብዓዊ ድጋፍ ፖሊሲው፣ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ ከኦባማና ከቡሽ አስተዳደር የተለየ አቅጣጫ ሊይዙ እንደሚችሉ የተለያዩ ተንታኞች ግምታቸውን አስቀምጠዋል።

ለ. የደኅንነትሥጋትና ሽብርተኝነትን የመዋጋት ፖሊሲና ስትራቴጂ

ምሥራቅ አፍሪካ በተለይም የአፍሪካ ቀንድ ቀጣና በአሜሪካ የውጭ ፖሊሲ ትኩረት እንዲያገኝ ካደረጉት መካከል አንዱ የቀጣናው ደኅንነት ሁኔታ ነው። አፍሪካ ቀንድ ምናልባትም ከመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ቀጥሎ በጦርነትና በግጭቶች እንዲታወቅ ካደረጉት ምክንያቶች መካከል አንዱ የአክራሪነትና የሽብርተኝነት ችግር ነው። በምሥራቅ አፍሪካ የእስልምና መንግሥት አቋቁማለሁ በማለት እንቅስቃሴ ሲያደርጉ የነበሩ ቡድኖች በተለይም አልሸባብ፣ ከአልቃይዳ ጋር በመሆን በኬንያና በታንዛኒያ በሚገኙ የአሜሪካ ኤምባሲዎች ጥቃት ማድረሱን ተከትሎ፣ እንዲሁም ከ9/11 የሽብር ጥቃት በኋላ አሜሪካ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት ከመቼውም በላይ ጠንካራ አቋምና ፍላጎት እንዲኖራት አድርጓል።

በመሆኑም የቡሽ አስተዳደርም ሆነ የኦባማ አስተዳደር አፍሪካ ቀንድን በተመለከተ የውጭ ፖሊሲዎቻቸው በዋናነት ሽብርተኝነትን በመዋጋት ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን ማድረግ ነው። ትንሽ ልዩነቶች ቢኖሩም ሁለቱም መሪዎች በቀጣናው ሽብርተኝነተን ለመዋጋት ከሞላ ጎደል ተመሳሳይ ስትራቴጂዎችን ይጠቀሙ ነበር። በቀጣናው ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የቡሽ ፀረ ሽብርተኝነት ዘመቻ ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል ሊያሳትፍ ስላልቻለ፣ ሽብርተኝነትን ከመከላከል ይልቅ ለአሸባሪዎች መበራከት ምክንያት እንደሆነ ምሁራን ይገልጻሉ። በተለይም ሽብርተኝነትን የመዋጋት ስትራቴጂው ሙስሊሙን ኅብረተሰብ እንደ አጋርነት ከመጠቀም ይልቅ፣ ሁሉንም የሙስሊሙን ማኅበረሰብ እንደ አሸባሪነት የማየት አዝማሚያው አለው። በአንፃራዊነት የኦባማን ፖሊሲ ከቡሽ ፖሊሲ ትንሽ ለየት የሚያደርገው ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የሌሎች አገሮች አጋርነት ይበልጥ አስፈላጊ እንደሆነ  አጽንኦት መስጠቱ ነው። የኦባማ ስትራቴጂ ሙስሊሞችን እንደ አጋርነት በመጠቀም ሽብርተኝነትንና የእስልምና አክራሪነትን መዋጋት እንደሚቻል ያሳያል።

በአጠቃላይ እስካሁን የኦባማ አስተዳደር በአፍሪካ አገሮች በፀረ ሽብርተኝነትንና በአክራሪነት እንቅስቃሴዎች ላይ ፅኑ ተሳትፎ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን፣ በተለይም በናይጄሪያ ቦኮ ሐራም የተሰኘው ቡድን፣ በሰሜን አፍሪካ ማግረብ አካባቢ የሚንቀሳቀሰው የአልቃይዳ ክንፍ፣ እንዲሁም በሶማሊያና በአካባቢዋ የሚንቀሳቀሰውን አልሸባብን ለማጥፋት ከሚመለከታቸው አገሮች ጋር በአጋርነት ሲሠራ ቆይቷል። ለዚህም የአሜሪካ ወታደራዊ አማካሪዎችና  አሠልጣኞች በማግረብ አካባቢ፣ በጂቡቲና በናይጄሪያ ይገኛሉ። ሽብርተኝነትንና አክራሪነትን በተመለከተ በአዲሱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የፖሊሲ ለውጥ ሊኖር እንደማይችል በሴኔጋልና ጋምቢያ የአሜሪካ አምባሳደር የነበሩት ኸርማን ኮኸን ገልጸዋል። እንደ ኮኸን ግምት ከሆነ ዶናልድ ትራምፕ ሽብርተኝነትን በተመለከተ ያላቸው አቋም ጠንካራ ከመሆኑ የተነሳ፣ የኦባማን የደኅንነት ፖሊሲ ሊያስቀጥለው ይችላል።

ሐ. አሜሪካከአፍሪካ ቀንድ አገሮች ጋር ያላት የንግድ ግንኙነት

ዶናልድ ትራምፕ አሁን ባለው የዓለም አቀፍ ንግድ ሥርዓት አሜሪካ  ተጠቃሚ አለመሆኗን፣ በተለይም ከአንዳንድ አገሮች ጋር የምታደርገው የንግድ ግንኙነት ተገቢ አልመሆኑን ገልጸዋል። አዲሱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቻይና አሜሪካን የራሷን ጥቅም ብቻ በማስቀደም የገንዘብ ማስተካከያ እያደረገች አሉታዊ ተፅዕኖ ፈጣሪ መሆኑን፣ ደቡብ ኮሪያ ወደ አሜሪካ የምትልካቸውን ምርቶች ድጎማ እንደምታደርግ፣ እንዲሁም ሜክሲኮ የሠራተኞች ርካሽ ጉልበት እንደምትጠቀም በመግለጽ ወደፊት አሜሪካ የሁለትዮሽ ንግድ ግንኙነቶች ላይ አተኩራ ጥቅሞቿን ማስከበር እንዳለባት ገልጸዋል። በዚህ መሠረት በዶናልድ ትራምፕ ዕይታ ቀደም ሲል ከሰሐራ በታች ያሉ አገሮች ከአሜሪካ ጋር የሚኖራቸውን የንግድ ግንኙነትና ተሳትፎ ለማሳደግ ተብሎ አጎዋ (African Growth and Opportunity Act) እ.ኤ.አ. በ2000 የተጀመረው ፕሮግራም በዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ቀጣይነቱ የሚያጠራጠር ነው። ይህ ዕድል የአፍሪካ አገሮች በነፃ ያለምንም ገደብ ማንኛቸውንም ምርቶቻቸውን ወደ አሜሪካ ገበያ ማቅረብ እንደሚችሉ የሚያስችል ሲሆን፣ አሜሪካውያን በነፃ ምርቶቻቸውን ወደ አፍሪካ አገሮች መላክ ስለማይችሉ በዶናልድ አስተዳደር ይህ ዕድል ተቀባይነት አይኖረውም። በመሆኑም በዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር አሜሪካ ከአፍሪካ አገሮች ጋር የሚታደርገው የሁለትዮሽ ንግድ ግንኙነት ለሁለቱም አካላት ተመሳሳይ መሆን አለበት።

መ.አሜሪካለአፍሪካ ቀንድ የምታደርገው የኢኮኖሚዊ ልማት ድጋፍ

በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት በዶናልድ ትራምፕ ከተተቹት ጉዳዮች መካከል አንዱ  የኦባማ አስተዳደር ለሌሎች አገሮች ከፍተኛ ድጋፍ በማድረጉ ምክንያት፣ ለአሜሪካኖች ቅድሚያ አልተሰጠም የሚል ነው። እስካሁን ባለው ሁኔታ የኢኮኖሚ ዕድገታቸውን ለማሻሻል የአሜሪካን ድጋፍ ከሚሹት አገሮች መካከልም ዋነኞቹ የአፍሪካ አገሮች ሲሆኑ፣ ከዚህ በፊት የነበሩት ዘመናዊ የአሜሪካ መሪዎች የውጭ ፖሊሲያቸውም በዋነኝነት የሚያተኩረው ኢኮኖሚያዊና ፖሊቲካዊ ድጋፍ ለአኅጉሩ ማድረግ ነው። ግልጽነት የጎደለው ከአፍሪካ ጋር ያለው የዶናልድ ትራምፕ የውጭ ፖሊሲ ግን በአንድ በኩል ‹‹ቅድሚያው ለአሜሪካ›› የሚለው የምርጫ ቅስቀሳ፣ እንዲሁም የትራምፕ አማካሪዎች ለአፍሪካ የሚደረገውን ድጋፍ እንደ ብክነት በማየታቸው ምክንያት የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ለአፍሪካ የሚደረገውን ድጋፍ በመቀነስ፣ ለአሜሪካ እንደገና መልሶ ግንባታ ላይ ማዋል እንደሚችል ያሳያል።  በሌላ በኩል ደግሞ አፍሪካ የአሜሪካ አገር በቀል ኩባንያዎች የገበያ መዳረሻ እንደመሆኗ መጠን፣ በአኅጉሩ ውስጥ አስፈላጊ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች በአሜሪካ ድጋፍ እንዲካሄድላቸው ይፈልጋሉ። የዶናልድ ፖሊሲም ቢዝነስ ላይ ያለው አቋም ጠንካራ ሊሆን ስለሚችል፣ ለአፍሪካ አገሮች የሚደረግ ድጋፍ ቀጣይነት ይኖረዋል ተብሎ ይገመታል።

በአጠቃላይ አሜሪካ ለአፍሪካ አገሮች የምታደርገውን ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ ካቆመች በተለያዩ የፖሊሲ ጉዳዮች አፍሪካ ላይ ተፅዕኖ ማሳደር አትችልም። በተለይም በተባበሩት መንግሥት ድርጅት የአፍሪካን ድምፅ ማጣት፣ ወታደራዊ የአየር በረራ እንዳይደረግባቸው በማድረግና የአካባቢ ችግሮችን በተመለከተ አሜሪካ በአፍሪካ አገሮች የነበራት ተሰሚነቷ ይቀንሳል።

ሠ. አሜሪካበአፍሪካ ቀንድ ያላት የቢዝነስ ፍላጎቶች

አሜሪካ በተለያዩ አፍሪካ አገሮች በርካታ ቢዝነስና ኢንቨስትመንቶች በዋናነትም በነዳጅና ሌሎች መሰል በማዕድን የተሰማሩ ኩባንያዎች ሲኖሯት በማኑፋክቼሪንግ ዘርፍ የአሜሪካ ኩባንያዎች እንቅስቃሴ ጀምረዋል። በዚህ ረገድ ዶናልድ ትራምፕ ምንም ዓይነት የፖሊሲ ምልከታ ባይሰጡትም የአሜሪካ ኢንቨስተሮችን ከመደገፍ ወደኋላ እንደማይሉ ግልጽ ነው።

ረ. አሜሪካበአፍሪካ የምታደርጋችው ልዩ የልማት መርሐ ግብሮች

በቡሽ አስተዳደር ወቅት የተጀመሩት አስፈላጊ የሆኑ የተለያዩ መርሐ ግብሮች በኦባማ አስተዳደርም እያደጉ መጥተዋል። በቡሽ አስተዳደር በመላው አፍሪካ አገሮች ኤችአይቪ/ኤድስን፣ ወባንና የሳንባ በሽታን ለመከላከል ከተደረጉት ድጋፎች በተጨማሪ፣ የሚሊኒየም ተግዳሮት ኮርፖሬሽን የተሰኘው መርሐ ግብር የአፍሪካ አገሮች ፖሊቲካዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎቻቸውን ግምት ውስጥ በማስገባት ተጨማሪ ድጋፎችን ሲያደርግ ቆይቷል። የኦባማ አስተዳደርም ከላይ የተጠቀሱት መርሐ ግብሮችን ቢያስቀጥልም በዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር የመቀጠል አዝማሚያቸው በጣም ዝቅተኛ ነው። በሌላ በኩል በአሁኑ ጊዜ በኦባማ አስተዳደር የተጀመሩት የአፍሪካ አገሮች የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት በግሉ ዘርፍ አማካይነት ኢንቨስት መደረግ እንዳለበትና የግብርናውን ዘርፍ ዘመናዊ ለማድረግ የተጀመሩ እንቅስቃሴዎችን አዲሱ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ማስቀጠል እንደምችሉ ምሁራን ይገልጻሉ። ምክንያቱም አሜሪካ ከእነዚህ ፕሮግራሞች ተጠቃሚ ስለምትሆን።

ዶናልድ ትራምፕ በአየር ንብረት ለውጥ  ላይ ያላቸው አቋም

ለአየር ንብረት ለውጥ በከፍተኛ ደረጃ አስተዋጽኦ ከሚያደርጉት አገሮች አንዷ አሜሪካ ብትሆንም፣ ዶናልድ ትራምፕ የዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ የሚባል አለመኖሩን ይናገራሉ። ይህ ደግሞ  በፓሪስ የአየር ንብረት ጉባዔ ስምምነት መሠረት አሜሪካና ሌሎች ያደጉት አገሮች የአየር ንብረት ለውጡ የሚያስከትለውን በርካታ ጉዳቶችን ፋይናንስ ለማድረግ በጀመሩዋቸው እንቅስቀቃሴዎች ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አለው።

ሀ. የዶናልድትራምፕ አስተዳደር ከሪፐብሊካኖች አንፃር

በርካታ የሪፐብሊካን አባላትና መሪዎች የዶናልድ ትራምፕን የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ሲቃወሙ ቆይተዋል። በተለይም ትራምፕ መመረጣቸውን ተከትሎ ሃምሳ የሚሆኑ የቀድሞው የአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነት ባለሥልጣናት በሰጡት ቃል መሠረት፣ ትራምፕ በአሜሪካ ታሪክ ውስጥ የአሜሪካ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ላይ ዝቅተኛ ግንዛቤ ያላቸውና ለፕሬዚዳንትነት የማይመጥኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። በትራምፕ አስተዳደር የአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነትና መልካም ገጽታዋ አደጋ ላይ ይወድቃል በማለት ሥጋታቸውን የገለጹት እነዚህ ባለሥልጣናት፣ የግለሰቡ አጠቃላይ የፖለቲካ ሰብዕና ማለትም ባህርይ፣ እሴቶችና ልምድ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ለመሆን የማያስችሉ መሆናቸውን ይገልጻሉ። ከዚህ ጋር ተያይዞም ተመራጩ ፕሬዚዳንት መሠረታዊ የአሜሪካ ሕግ ዕውቀትና እምነት፣ የአሜሪካ ሕግጋትንና ተቋማት፣ የሃይማኖት መቻቻል፣ የፕሬስ ነፃነትና የፍትሕ ሥርዓቱ ገለልተኝነት ዕውቀት የሌላቸው በመሆኑ፣ አሁን አሜሪካ በዓለም ላይ ያላትን ተቀባይነትና የመሪነት ሚናዋን ያሳንሳል በማለት ፍራቻቸውን ይገልጻሉ። በአጠቃላይ ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ መሠረታዊ ብሔራዊ ፍላጎት፣ የአገሪቷን ውስብስብ ዲፕሎማሲያዊ ተግዳሮቶች፣ የአሜሪካ ህልውና የሆኑ አጋርና ወዳጅ አገሮችና የአገሪቷ ውጭ ግንኙነት ፖሊሲ የተመሠረተባቸው ዴሞክራሲያዊ እሴቶች በተመለከተ ያላቸው ግንዛቤ አናሳ መሆኑን ያስረዳሉ።

ለ. የአሜሪካ ተቋማዊ ጥንካሬና የዶናልድ ትራምፕ ሹማምንት ሚና

ከላይ የተጠቀሱትን የዶናልድ ትራምፕ ክፍተቶች የሚያሳየው ግለሰቡ የፖሊሲ ውሳኔዎችን ለማድረግ ከሌሎች ጋር ለመሥራት እንደሚገደዱ ነው። በተጨማሪም የአሜሪካ ተቋማዊ አቅም ጠንካራ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፣ ፕሬዚዳንቱ ብቻውን የሚያስተላልፋቸው ውሳኔዎች ተግባራዊ ሊሆኑ አይችሉም። በመሆኑም የአገሪቱ ተቋማዊ መዋቅሮች በተለይም የሴኔቱ ውሳኔዎችና የሌሎች ሹማምንት ማለትም የምክትል ፕሬዚዳንቱ፣ የአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት፣ እንዲሁም በስቴት ዲፓርትመንት የአፍሪካ ጉዳዮች ኃላፊ ሆነው የሚሾሙት ግለሰቦች በውጭ ፖሊሲው ላይ ወሳኝ ሚና ይኖራቸዋል።

ለ. በአፍሪካ ቀንድና በኢትዮጵያ ሊሆን የሚችሉ ቢሆኖች

በአሁኑ ጊዜ በአፍሪካ ቀንድ የአሜሪካ ቅርብ ወዳጅና አጋር የሆኑ አገሮች በዋናነት ኢትዮጵያና ጂቡቲ ቢሆኑም፣ የአሜሪካ ወታደራዊ ጣቢያ መገኛ የሆነችው ጂቡቲ እ.ኤ.አ. በ2016 ከቻይና ጋር ባደረገችው ስምምነት መሠረት ቻይና ለመጀመሪያ ጊዜ ወታደራዊ ጣቢያ በጂቡቲ ለማቋቋም እንደወሰነች ተገልጿል። ይህ የሚያሳየው ጂቡቲ ከአሜሪካ ይልቅ ከቻይና ጋር ተባብሮ ለመሥራት ፍላጎት እንዳላት ነው። በሌላ በኩል ደግሞ በኢትዮጵያ ውስጥ ከቅርብ ጊዜ ወደህ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ፣ እንዲሁም በዲያስፖራዎች ጉትጎታ ምክንያት አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የቆየ ወዳጅነት በተለይም የፀረ ሽብርተኝነት አጋርነት ታቆማለች የሚለው ግምት ነው።  በዚህ ምክንያት የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ስትራቴጂካዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቃሜታ ያላቸው አገሮችን ማለትም ኤርትራና ደቡብ ሱዳንን እንደ አጋርነት ለመጠቀም በአዲስ መልክ ዲፕሎማሲያዊ ግንኘኑት መፍጠር ይችላል። በተለይም ልምድ ያላቸው ኸርማን ኮኸን፣ ዴቪድ ሺንና ፕሪንስተን ለይማን የተባሉት የአሜሪካ ዲፕሎማቶች አሜሪካ ከኤርትራ ጋር እንደገና ዲፕሎማሳዊ ግንኙነት መፍጠር እንዳለበት ያምናሉ። ኤርትራ ከአሜሪካ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትዋን መልሳ ማደስ ከቻለች በተመድ የተጣለባት የኢኮኖሚ ማዕቀብ ይነሳላታል። ይህ ደግሞ ለኢትዮጵያ አሉታዊ ተፅዕኖ ይኖረዋል። ምክንያቱም  ሥልጣን ላይ ያለው የኤርትራ መንግሥት ቀደም ሲል ሲያደርግ እንደነበረው፣ አሁንም ኢትዮጵያን የማወክ እንቅስቃሴውን አጠናክሮ እንዲቀጥል ያደርጋል።

  1.  

አሜሪካ ከአፍሪካ ቀንድ አገሮች ጋር ያላትን ግንኙነት ለማጠናከርና በቀጣናው ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን  ጠንካራና የተረጋጋ መንግሥት እንዲኖር ትፈልጋለች። ኢትዮጵያ ከሌሎች የአፍሪካ ቀንድ አገሮች የተሻለና ጠንካራ መንግሥት ያላት አገር ናት። እንዲሁም በቀጣናው የተለያዩ ዓለም አቀፋዊና አኅጉራዊ ተቋማት፣ ለአብነትም የአፍሪካ ኅብረትና የተመድ ተቋማት መገኛ በመሆኗ አገሪቱ የአፍሪካ ስትራቴጂካዊ ሥፍራ ናት። በዚህ ምክንያት አሜሪካም ሆነ ሌሎች በአፍሪካ ላይ ፍላጎት ያላቸው አገሮች ኢትዮጵያን እንደ ስትራቴጂካዊ ሥፍራ ከማየት ባሻገር፣ በአገሪቷ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በቀጥታ ጣልቃ ከመግባት ይልቅ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በውይይትና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ችግሮችን መፍታት ይመርጣሉ። አዲሱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕም ሽብርተኝነትንና አክራሪነት ለመዋጋት ፅኑ አቋም ስላላቸው፣ ኢትዮጵያ በቀጣናው ያላትን የፀረ ሽብርተኝነት እንቅስቃሴዎችና በአኅጉሩ ያላትን ስትራቴጂካዊ ሥፍራ በመገንዘብ የነበረውን ወዳጅነት ሊያስቀጥሉ እንደሚችሉ መገመት ይቻላል።

  1.  

ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳው ወቅት በተደጋጋሚ እንደገለጹት አሜሪካ ከአገሮች ጋር የምታደርገውን ተሳትፎ በመቀነስ አገራዊ ግንባታ ማከናወን አለባት። በዚህም ቀደም ሲል ከሌሎች አገሮች ጋር የነበሩትን የውጭ ግንኙነትና አጋርነት መቀነስ እንደሚፈልጉ ገልጸዋል። እንዲሁም በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ከአፍሪካ አገሮች ጋር የሚኖረውን የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ አለመግለጻቸው ምናልባት በትራምፕ አስተዳደር አሜሪካ በአፍሪካ አገሮች ያላት ተሳትፎ አናሳ ይሆናል የሚል ግምት አለ። ዶናልድ ትራምፕ ከአጋርነት ይልቅ የሁለትዮሽ ግንኙነት ላይ በማተኮር፣ የአሜሪካን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ይበልጥ ለማስከበር እንደሚሠሩ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት በተደጋጋሚ ከመግለጻቸው ጋር ተያይዞ፣ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት ከሌሎች አገሮች ጋር አጋርነት ሳያስፈልግ አሜሪካ በተናጠል የሽብርተኝነት እንቅስቃሴ ይኖራል ብላ ባሰበችው አገር ውስጥ ገብታ መዋጋት እንደምትችል ያሳያል። ለአብነትም ከዚህ በፊት አንዳንድ የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ሲከተሉት የነበረው ‹‹አስከፊ ሰብዓዊ ቀውስን ለመከላከል›› በሚል ሰበብ በጦርነት ጣልቃ በመግባት ሽብርተኝነትንና አክራሪነትን መዋጋት እንደምትችል ግምት አለ።

ማጠቃለያ

የአፍሪካ ቀንድ አገሮች የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ከቀጣናው ጋር የሚኖረውን ግንኙነት በተመለከተ ተገቢውን ትኩረት በመስጠት ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ማድረግ ብቻ ሳይሆን፣ የቀጣናው ተጨባጭ ሁኔታዎች ማለትም የፖለቲካዊ ልዩነቶች፣ የሃይማኖት አክራሪነትና ሽብርተኝነት፣ እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመፍታት የአሜሪካ አጋርነት አስፈላጊ ነው። አሜሪካ ከአፍሪካ ቀንድ አገሮች ጋር በምታደርገው ግንኙነት የሚኖራት ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ሰፊ ነው። የትራምፕ አስተዳደር በዋናነት ኢኮኖሚያዊ ግንኙነቶች ላይ ስለሚያተኩር የአሜሪካና የአገራቸውን ተጠቃሚነት በጠበቀ መንገድ የቢዝነስና የንግድ ግንኙነቶችን በማጠናከርና በማስፋፋት ላይ ያተኮሩ አገሮች የአስተዳደሩ ተጠቃሚ ይሆናሉ። እንዲሁም የትራምፕ አስተዳደር በደኅንነት ላይ ያለው አቋም ከፍተኛ በመሆኑ፣ በዚህ ዘርፍም ከአገሪቱ ጋር የተለያዩ ትብብሮችን በማድረግ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን የሚያደርጉ የቀጣናው መሪዎች መልካም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ይኖራቸዋል። በአጠቃላይ ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ያላቸውን ጉዳዮች መሠረት በማድረግ፣ የአሜሪካ ተቋማዊ ጥንካሬና የዶናልድ ትራምፕ ሹማምንት ሚና ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት፣ እንዲሁም የቀጣናው አገሮች ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶችን ታሳቢ በማድረግ አሜሪካ ከአፍሪካ ቀንድ አገሮች ጋር የሚኖራት ግንኙነት ከዚህ በፊት ከነበረው ያን ያህል ልዩነት አይኖረውም።

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው Luskerget@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

የኢሬቻ ክስተት - ችግር ብቻ ወይስ ትምህርት የሚወሰድበት አጋጣሚ?

$
0
0

ክፍል አንድ

በደጀኔ አሰፋ ዳምጠው

‹እንኳን ደስ አላችሁ› ለማለት የክልል ወይም የሆነ ርዕሰ መስተዳድር መሆንን የማይጠይቅ ከሆነ ከሁሉ አስቀድሜ የገዳ ሥርዓት በዩኔስኮ በመመዝገቡ ‹እንኳን ደስ አላችሁ እንኳን ደስ አለን› ለማለት እወዳለሁ:: ካልሆነ ግን ደስታዬን ለብቻዬ አጣጥመዋለሁ፡፡ ምክንያቱም ገዳ ማለት ለኔ የማይዳሰስ ቅርስ ሳይሆን የሚነካ፣ የሚጨበጥ፣ አስተማሪና አሳታፊ የሆነ ዴሞክራቲክ ትውፊት ነውና፡፡ አሳታፊነቱ ደግሞ ሁሉንም ነው፡፡ ሕፃናትንና ወጣቶችን ጭምር በተወሰነ ዕድሜያቸው ደረጃ ላይ ተሳታፊ እንዲሆኑ ያደርጋል፡፡ መሪነትን በሚመለከት በምርጫ ያከናውናል፡፡ ለዚያውም በተወሰነ የጊዜ ገደብ ታዲያ ‹ቢራ መጠጣትን› እንደ ባህላዊ ትውፊት አድርጋ ለማስመዝገብ እንደታገለቸው ቤልጅየምም ሆነ ‹ቂጣ ጋግሮ ከጎረቤት ጋር መካፈልን› ከማይዳሰሱ ቅርሶች ተራ ማስመዝገብ እንደቻለችው አዘርባይጃን ሳይሆን ገዳ ማለት ከቂጣ የዘለለ፣ አገራዊ ብቻ ሳይሆን አኅጉራዊ ፋይዳና በተለይም ለአፍሪካ ፖለቲካ ብዙ ምልከታና ትርጉም ያለው፣ የሚዳሰስና የሚነካ ባህል ነው፡፡ የሚማርበት ከተገኘ!

ስለዚህ የገዳ ሥርዓት አሁን በመመዝገቡ ድቤ ከመደለቅና የተለየ ሥራ ተሠርቶ እንደመጣ ከመለፈፍ ይልቅ፣ ከዚህ በተሻለ ሁኔታ ቀደም ብሎ ለምን አላስመዘገብነውም በማለት ልንቆጭና ለወደፊቱ ሌሎች የአገራችንን ቅርሶች ለማስመዝገብ በሚደረገው ሒደት ትምህርት መውሰድ ነው የሚገባን፡፡ በተረፈ የገዳ ሥርዓት መመዝገቡ ለራሱ ለዩኔስኮም ነው የሚጠቅመው፡፡ ካልሆነማ ቂጣ ጋገራን እየዞረ ይመዝግባ! አለቀ! ብቻ በኢሬቻ በዓል ስለተከሰተው ነገር ምንም ሲሉ ያልሰማኋቸውና የገዳ ሥርዓት በዩኔስኮ መመዝገቡን ተከትሎ በቴሌቪዥን መስኮትም ሆነ በቴክስት ሜሴጅ ‹‹እንኳን ደስ አለህ›› የሚሉኝን ተሿዋሚዎችን ‹‹እንኳን አብሮ ደስ አለን›› ለማለት እፈልጋለሁ፡፡ ከትዝብት ጋር! እዚህ ላይ ግን የክልል መስተዳድርም ባልሆን አሜሪካ 41ኛውን ሳይሆን 45ኛውን ፕሬዚዳንቷን እንደመረጠች አልስተውም፡፡ ገዳ በመመዝገቡም እየዘለሉ የነበሩ አባ ገዳዎች የደስ ደስ ወተት ቢጋብዙንም፣ ላሞቹ ከፊንፊኔ ውጪ ደጅ ላይ በመሆናቸው መጠጣት አልቻልንም፡፡ ምነው “ቴሌ ፓቲ” እንደሚባለው “ቴሌ ሚልኬ” ቢኖር አያስብልም? መልካም ንባብ!፡፡

እንደሚታወቀው በአገራችን ከሚከበሩ ዓመታዊ ክብረ በዓላት መካከል በዋናነት በኦሮሞ ማኅበረሰብ የገዳ ሥርዓት አካል የሆነው የኢሬቻ ባህላዊና ሃይማኖታዊ በዓል አንዱ ነው፡፡ ይሁን እንጅ በዕለተ ሰንበት መስከረም 22 ቀን 2009 ዓ.ም. በቢሾፍቱ ሆራ አርሰዴ ሐይቅ በደማቅ ሁኔታ ሊከበር ቀጠሮ ተይዞለት የነበረው የኢሬቻ በዓል ከወትሮው የተለየ ሁኔታን አስተናግዶ አልፏል፡፡ በታዳሚውና በመንግሥት መካከል በተፈጠሩ አለመግባባቶች ነገሮች መልካቸው በመቀየሩ የዜጎችን ሕይወት የቀጠፈ ክስተት ሆነ፡፡ በመሆኑም በዓሉ የምሥጋና በዓል (Thanks Giving Day) መሆኑ ቀርቶ የሦስት ቀናት ብሔራዊ ሐዘንን የጠራ እጅግ አሳዛኝ ክስተት ለመሆን በቃ፡፡ ክስተቱ ካለፈ እነሆ ድፍን ሁለት ወራትን አስቆጠረ፡፡ “ተጠያቂው ማን ነው?” የሚለው ጥያቄ እንደተጠበቀ ሆኖ ክስተቱ ግን አስደንጋጭ ከመሆኑ ባሻገር፣ የአብዛኛውን ኢትዮጵያዊ ልብ የሰበረና የህሊና ጉዳትን የፈጠረ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ በዚህ ክስተትም ዙሪያ ብዙ ተብሏል፡፡ ሁሉም እንደገባው መጠን ትንታኔ ሰጥቷል፡፡ ተናጋሪው ከሚናገርበት ጎራ አንፃር ለሚፈልገው ዓላማ ለማዋል ሞክሯል፡፡ ገሚሱም በልቡ የሆነ ነገር ብሎ ይሆናል፡፡

ጽሑፉም በሚከተሉት ዋና ጉዳዮች ላይ ያተኩራል፡፡ በኢሬቻ በዓል መስተጓጎልና የዜጎች ሕይወት መጥፋትን በሚመለከት ሲቀርቡ የነበሩ ወቅታዊ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች፤ የተላለፉ የሐዘን መግለጫዎችና በአጠቃላይ የታዩ መስተጋብሮችን በወፍ በረር ይቃኛል፡፡ በአንፃሩ ክስተቱ ካለፈ ከሁለት ወራት በኋላ የገዳ ሥርዓት በዩኔስኮ በመመዝገቡ የተላለፉ የደስታ መግለጫዎችን ይዳስሳል፡፡ በየመሀሉም ተያያዥ ጉዳዮችን በወግ መልክ በመጠረቅ የመስከረም 22ቱ ‹‹ክስተት እንደ ችግር ብቻ ወይስ ትምህርት ሊወሰድበት የሚችል አጋጣሚ?›› የሚል መሠረታዊ ጥያቄን ለውይይት ያቀርባል፡፡ ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል ባላቸው ጉዳዮች ላይ ደግሞ በተለያዩ የጽሑፉ ክፍሎች ዕይታውን ያካፍላል፡፡ የግል ዕይታዬን እነሆ!፡፡

የኢሬቻ ክስተትን ተከትሎ ኢቢሲ 1 ያቀረባቸው ፕሮግራሞች ምን ይዘት ነበራቸው? የሚለውን በጨረፍታ ለመዳሰስና ይኼንኑ የበለጠ ለማሳየት አንድ ምናባዊ ሰው ልሳል፡፡ ይኼ ምናባዊ ሰው የኢሬቻን አሳዛኝ ክስተት ያልሰማ ወይም በወቅቱ እዚህ ያልነበረ ነው እንበል . . . ቢሆንም ግን ከዚያ በኋላ በወቅቱ ይተላለፉ የነበሩ የሐዘን መግለጫዎችና የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን የመከታተል አጋጣሚ ነበረው ብንልና ከእነዚህ ፕሮግራሞች ምን ሊረዳ ይችላል? የሚለውን ልገምት፡፡ እንደኔ ዕይታ ከሆነ ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ ብሎ ሲያይና በሚያሳዝን ክላሲካል የታጀቡ በግራፊክስ የተቀረፁ እጥር እጥር ያሉ ሻማዋች እየበሩ ሲመለከት ይህ ሰው አገሪቱ ውስጥ ሐዘን እንዳለ በትክክል ይገነዘባል፡፡ ነገር ግን ይኼ ሐዘን በምን ምክንያት ነው የተፈጠረው? የሚለውን ጥያቄ ኢሬቻ በዮኔስኮ ባለመመዝገቡ እንደሆነ እንጂ ሕይወታቸውን ባጡ ዜጎች ነው ብሎ ለማሰብ የሚከብደው ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም በቴሌቪዥን የቀረቡት አስተያየት ሰጪዎችም ሆኑ ዜናዎች በሙሉ ማለት በሚያስችል ሁኔታ ሲገልጹ የነበሩት ኢሬቻ በዮኔስኮ እንዳይመዘገብ በመደናቀፉ እጅጉን እንዳዘኑ፣ ይህም አገርን በጥልቅ የጎዳ አሳዛኝ ክስተት እንደሆነና የአገርን ገጽታ እንደሚያበላሽ፣ ቱሪዝምን እንደሚጎዳና እንዲህ ያደረጉትን አካላት መንግሥት ተጠያቂ እንዲያደርጋቸው በሲቃ እየተማፀኑ ነበር ማይኩን ተራ በተራ ሲቀባበሉ የነበሩት፡፡

ለነገሩ ከተለያዩ ክልሎች የቀረቡት አስተያየት ሰጪዎች ተመሳሳይ ነገር ከመናገራቸው የተነሳ አንድ ወዳጄ “ሁሉም የሚናገሩትን ተጽፎ ነው እንዴ የተሰጣቸው?” አለኝ፡፡ እኔም ‹‹ይኼንን አላቅም፡፡ ሆኖም ግን ከደቡብ ክልል አስተያየት የሰጠውን ሰው በድሬዳዋው ፕሮግራም ያየሁት መስሎኛል፡፡ ይኼም ቢሆን ግን የኤዲቲንግ ችግር እንጂ ሌላ አይሆንም?” ብዬ ሳልጨርስ እንዲህ አለኝ፡፡ ‹‹ይኼንንማ ድሮም ለምደነዋል፡፡ እንዲያውም ካስታወስክ በአንድ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት የፌስቡክና የትዊተር ገጽ የሌላ አገርን የባቡር መስመር ከወልዲያ እስከ ናምን እየተገነባ ያለው ሐዲድ ብሎ ለጥፎ ነበር፡፡ በተመሳሳይም የሌላ አገርን ግድብ በኢትዮጵያ እየተገነባ ያለው ምን የሚባል ግድብ ብሎ ለጥፎ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ኧረ ይኼ የሌላ አገር ሐዲድና የሌላ አገር ግድብ ነው ብለው ሰዎች በመነዝነዛቸው ይቅርታ ጠይቋል?” አለኝ፡፡ ከዚያም ንግግሩን ዘለግ አድርጎ፣ ‹‹ይቅርታ አጠያየቁ ግን ትንሽ አስቂኝ ነበር፤›› አለ፡፡  ‹‹መሥሪያ ቤቱ ምንም እንኳን የሚሠራቸው ዜናዎች ትክክል ሊሆኑ ቢችሉም የፎቶ ክምችት እጥረት ስለነበረበት ደስ ደስ የሚሉ ማራኪ ፎቶዎችን ከሌላ ቦታ ኢምፖርት በማድረጉ ነው፤›› አለኝና በግርምት ተለያየየን፡፡

ከተለያየን በኋላ ግን ከኢሬቻ ክስተት ወዲህ በሕይወቴ ውስጥ አንድ ጥያቄ ተፈጠረብኝና መልስ ሳላገኝለት ይኼው አዕምሮዬን እንደጨመደደኝ ከእኔው ጋር ይኖራል፡፡ ይኼም በዮኔስኮ ከመመዝገብ ወይም አለመመዝገብና ከዜጎች ሕይወት የትኛው ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል? የትኛውስ ነው የበለጠ አሳዛኝ ሊሆን የሚገባው? የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ እንኳን ኢሬቻ ‹‹ገና ዘንቦ ተባርቆ›› እንደሚባለው ማለትም ኢሬቻ (ገዳ) ገና ተመዝግቦ፣ ለዓለም ሕዝብ ተዋውቆ፣ ሰው መምጣት ቢጀምርና የቱሪዝም ፍሰትን በተወሰነ ደረጃ ሊያሳድግ ቢችል፣ ከዚያም ለአገሪቱ ተጨማሪ ገቢን ወይም ሌሎች ጥቅሞችን ማስገኘት ቢችል . . . ወዘተ፣ እንደማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ መነሳት ያለባቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ አይደለም ኢሬቻ (ገዳ) ሥርዓት ብዙ ያልተሠሩ የቤት ሥራዎች ያሉበትና በዓመት አንድ ቀን ብቻ የሚከበር በዓል ቀርቶ በአገሪቱ የሚገኙ የተመዘገቡም ያልተመዘገቡም ቋሚና የማይዳሰሱ ወካይ የዓለም ቅርሶችና መስህቦችን በሙሉ ጨምሮ፣ ከቱሪዝም ኢንዱስትሪው የሚገኘው አጠቃላይ ገቢ ለብሔራዊ ጠቅላላ ምርት (GDP) የሚያበረክተው ድርሻ እዚህ ግባ የማይባል ነው፡፡ ይኼንን ስናነሳ ጎረቤታችን ኬንያ ባትሰማን ደስ ይለኛል!  ግን ኧረ ለመሆኑ ከዘመናት በፊት በዩኔስኮ በተመዘገቡት እነ ቅዱስ ላሊበላ፣ አክሱም ጽዮን፣ ጎንደር ፋሲለደስ፣ ሶፍ ኦማር ዋሻና ሌሎች ቋሚ ከሆኑ የቱሪዝም መስህቦቻችን በሚገኝ ትሩፋት ሙሉ የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርና ቅርሶቹ በሚገኙበት አካባቢ የሚኖረውን ማኅበረሰብ እንኳን በቀን ሦስት ጊዜ እንዲበላ ካላደረጉት፣ የኢሬቻ (ገዳ) በዮኔስኮ አለመመዝገብ (እንዲያውም የመመዝገብ ዕድሉ በዚያ ጊዜ ሙሉ ለሙሉ ተሟጦ ሳያልቅ ለዚያውም አሁን ተመዘገበ እሰይ! ምን ይውጣቸው?!)  እንዲያ ከወገኖቻችን ሞት በላይ አሳዛኝ ሆኖ መቅረቡ ሌላ ሕመምን ይፈጥራል፡፡

እዚህ ላይ የኮንሶ ቴሬሲንግን ያልጠቀስኩት በቅርብ ከተመዘገቡት ቅርሶች ስለሚመደብ እንጂ በሌላ አይደለም፡፡ ብቻ የዜጎች ሕይወት ዋጋው ስንት ነው? በፈጣሪ መልክና አምሳል የተፈጠረው የሰው ልጅ ተመኑስ ስንት ነው? የሚለው ነጥብ ስለሚያንገበግበኝ እንጂ . . . መቼም ትረዱኛላችሁ ቱሪዝም ማደግ የለበትም ወይም የኢሬቻ (ገዳ) ሥርዓት በዩኔስኮ መመዝገብ ጠቀሜታ የለውም እያልኩ እንዳለሆነ፡፡ ምክንያቱም አገሬ በየትኛውም መስክ መበልፀጓን በቅን ልብ ከሚሹና የበኩላቸውን ጥረት ከሚያደርጉ ወገኖች መካከል ልመደብ የምችል ዓይነት ሰው ነኝ፡፡ በነገራችን ላይ “ባለቤቱ ያቀለለውን አሞሌ ባለ ዕዳ አይቀበለውም” እንዲሉ የዜጎችን ዋጋ የሚተምነው መንግሥት በመሆኑ፣ ሌሎች አገሮች ዜጎቻችንን የሚያስተናግዱበትም ሁኔታ በዚሁ በወጣው ተመን ልክ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ‹‹አሞሌነት ብቻውን አያስከብርም፡፡ አሞሌ ነህ መባልንና በባለቤቱ መከበርን ይሻል›› ካልሆነ ግን ዜጎቼን እንዲህ አደረጋችሁብኝ ብሎ ለመወቃቀስ አያመችም፡፡ ወይም “ለሕይወትህ ዋጋ ስጥ” የሚለው መሪ ቃል ‹‹የስንት›› የሚልን ጥያቄ ማስነሳቱ አይቀርም፡፡ ብቻ ከዋጋ ጋር በተያያዘ ‹‹የአንድ ኢትዮጵያዊ ዋጋ ከአፄ ሚኒልክ እስከ ኢሕአዴግ›› በሚል ርዕስ አጭር መጣጥፍ በቅርብ ጊዜ (Coming Soon) ለፊልም ብቻ ያለው ማነው?፡፡

ወደ ዋና ጉዳዬ ልመለስ፡፡ ከላይ እንደተጠቀሱት አስተያየት ሰጪዎች የሚመስሉ ሌሎች ደግሞ ወረፋቸውን ጠብቀው የቀረቡ ነበሩ፡፡ እነዚህኞቹ ግን ሲታዩ እንደ አስተያየት ሰጪ የሚያደርጋቸው ሆነው “አዋቂ ተቺ”ነትም የሚነካካቸው ሦስት ብሎገሮች (ጦማሪያን) ነበሩ፡፡ በእኔ ግምት ከሦስት ብሔሮች የተወጣጡ ይመስሉኛል፡፡ ይሁን እንጂ በወቅቱ የቀረበው ዝግጅት የብሔር ብሔረሰቦች ፕሮግራም ካለመሆኑ ጋር ተያይዞ እንዲህ የሚል ጥያቄ ፈጠረብኝ፡፡ በአገሪቱ ካሉ ጦማሪያን መካከል (ለዚያውም ጦማሪያን በሚነቀፉበት ወቅት) እነዚህ ሦስት ጦማሪያ በምን መሥፈርት ተመርጠው በመንግሥት ሚዲያ እንደቀረቡና ሌሎች ጦማሪያንን የመዝለፍም ሆነ የመተቸት መብትን እንዴት ሊጎናፀፉ ቻሉ? የሚለው ግልጽ አለመሆኑ መገመት ግን ይቻላል፡፡ “መደገፍ” ሳይሆን አይቀርም የሚሉ ወገኖች አይጠፉም፡፡ “መደገፍ” ማለት “መድገም” ማለት ከሆነ ግን መቃወም በስንት ጣዕሙ! ያስብል ይሆን? እኔ እንጃ . . . ብቻ የሰነዘዋቸውን ዋና ዋና ሐሳቦች በጥቂቱ ላካፍላችሁና ትዝብቴን ልቀጥል፡፡

አንደኛው እንዲህ አለ፣ “እነ ጃዋርና መሰሎቹ የውጭ ተልዕኮን ለማስፈጸም ነው እንዲህ የሚረባረቡት፡፡ ይኼ ደግሞ ሕዝብን እንደ መናቅ ነው?” ብሎ እርፍ፡፡ እንደ እኔ ዕይታ ከሆነ ግን የውጭ ተልዕኮን ለማስፈጸም ነው በማለት የቀረበው ትችት በማን ተመዝኖ? በየትኛው ወገን ታይቶ? የሚል ጥያቄን ያስነሳል፡፡ የፍሬ ጉዳዩን ትክክለኝነት ወይም ስህተት እንደታየበት መነፅር (ጎራ) ሊወሰን የሚችልበት አጋጣሚ ስላለ ማለት ነው፡፡ ከዚያ በላይ ግን  “ይኼ ደግሞ ሕዝብን መናቅ ነው” ያለው ሐሳብ የተገላቢጦሽ ሆኖ ይታየኛል፡፡ ምክንያቱም ለአኔ ሕዝብን መናቅ ብዬ የማስበው ሕዝቡ የራሱ ጥያቄ የለውም? ይልቅ በጃዋርና መሰሎቹ  ነው የሚነዳው? የሚለው ሐሳብ ይመስለኛል፡፡ እንዲህ ብሎ መደምደም ደግሞ ምንም እንኳን ሊጫወት የሚችለው የራሱ ሚና ቢኖርም፣ ሕዝቡ የራሱ የሆነ ሕጋዊና ፍትሐዊ ጥያቄ የለውም ወደሚል ስለሚያዘነብል አግባብነት ላይኖረው ይችላል፡፡ ምክንያቱም ይኼኛው አካሄድ በሌሎች ወገኖች ዘንድ የሚሰጠው ትርጉም ሌላ ሊሆን ስለሚችል፡፡ ይኼም ወደ መንግሥት እየመጡ ያሉ የሕዝብ ጥያቄዎችን በመልክ በመልክ ሰድሮ ለሕዝቡ የሚሆን እውነተኛና አጥጋቢ መልስ በየደረጃው ለመስጠት ወይ አልተዘጋጀም ወይ አልፈለገም የሚል ይሆናል፡፡ ይኼ ዕይታ ትክክል ይሁንም የተሳሳተ ልብ ማለቱ ግን ለሁሉም ወገን ጠቃሚ እንደሚሆን አልጠራጠርም፡፡

ሌላኛዋ ጦማሪ ያነሳችው ሐሳብ ደግሞ እንዲህ ይላል፡፡ ‹‹ጃዋር በትዊተር ገጹ ቢቢሲን ተሳደበ፣ ሲኤንኤን ነቀፈ፣ . . . ምናምን ካለች በኋላ ለምን እነዚህን ዓለም አቀፍ ሚዲያዎችን ይሳደባል?›› ብላ በመጠየቅ ለማሳቀቅ የሞከረች ያስመስልባታል፡፡ ይኼም ጦማሪዋ ጦማሪ መሆኗ ቀርቶ የዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ተቆርቋሪ ተቋም በኢትዮጵያ ተወካይ ሊያስብላትም ላያስብላትም ይችላል፡፡ ለእኔ ግን ሌላ ወሳኝ ጉዳይ አንስታ በአመክንዮ ላይ የተመሠረተ ሙግት ብታቀርብ ውኃ የመቋጠር ዕድል ነበራት እላለሁ፡፡ ሦስተኛው ጦማሪ ደግሞ እንዲህ አለ፣ ‹‹እኛ ጃዋርን ነው የምንከተለው፤›› እንዲህ ሲል ትንሽ ደንገጥ ብዬ ነበር፡፡ ምክንያቱም መንግሥት አምኖት ሕዝብ ፊት ያቀረበው ብሎገር እሱን እከተላለሁ ሲል ማለቴ ነው፡፡ በልቤ ግን ምንም አላልኩም! ቀጠለና ‹‹እሱ (ማለትም ጁ . .) የሚጽፈውን ነገር እግር በእግር ስንከተለው ነበር ፕላን "A"ፕላን "B"አለን ሲል ነበር . . . ›› ብሎ ተናገረ፡፡ ይኼኛው አስተያየት ለእኔ የሚያሳየኝ ነገር ቢኖር እነዚህ ጦማሪያን አየር መቃወሚያ የደገኑ ወይም ግብረ መልስ ለመስጠት ያሰፈሰፉ እንጂ የራሳቸው አውሮፕላን (አጀንዳ) ያላቸው እንዳልሆኑ ነው፡፡

ከሦስቱ ብሎገሮች የተረዳሁት ሌላው ነገር ቢኖር አሸባሪ አሊያም የጥፋት ኃይሎች ተብለው በመንግሥት የተፈረጁ ግለሰቦችን ወይም የሌላ ጎራ አክቲቪስቶችን እንደሚከተሉ ነው፡፡ እዚህ ላይ ማንሳት የፈለግኩት ለምን የእነሱ ተከታዮች ሆኑ የሚለውን አይደለም፡፡ ምክንያቱም የባላጋራውን የሙግት ሐሳብ የማያውቅ የራሱን መከራከሪያ ፍሬ ነገር በሚገባ አጥርቶ አያውቅም የሚል አባባል አለ፡፡ ወይም በእንግሊዝኛ ”Those who do not know the arguments of their opponents, do not know their own effusively” ይባላል፡፡ የእኔ ጥያቄና አትኩሮት ግን እነዚህ በሚዲያ የቀረቡት ጦማሪያን ለተጻፉ ጽሑፎች መልስ ከመስጠት በዘለለ በራሳቸው የተቀረፀ፣ የሚያምኑበትና የሚያራምዱት የራሳቸው የሆነ አጀንዳ የላቸውም ማለት ነው? የሚለው ነጥብ ነው፡፡

ለነገሩ ስለነዚህ ጦማሪያን አነሳሁ እንጂ እንኳንስ እነዚህ በግለሰብ ደረጃ ያሉት ቀርቶ መንግሥትስ ቢሆን አጀንዳ ቀርፆ ሕዝባዊ ንቅናቄን ከመፍጠር አንፃር ምን ያህል ውጤታማ ነበረ? ምን ያህልስ አበክሮ ይሠራል? ብንል የምናገኘው መልስ እምብዛም ነው፡፡ ‹‹ሰፊ ክፍተት አለ›› የሚል ይሆናል፡፡ ተቀዳሚ ሥራው “አጀንዳ መቅረፅ” እና ሕዝባዊ ንቅናቄን መፍጠር ሳይሆን፣ ለሚነሱ ጉዳዮች ምላሽ መስጠት ነው የሚመስለው፡፡ ከዚህ አንፃር አንድ ለእናቱ ለሆነው ሕዝባዊና ብሔራዊ ፕሮጀክታችን የህዳሴው ግድብ እንኳን በተለይ ሁከቱ ከተቀሰቀሰበት ጊዜ ጀምሮ ተገቢውን ሽፋን ሰጥቶ ሲንቀሳቀስ አልነበረም፡፡ ስንት ጊዜ ሆነው በተጀመረበት ግለት ለማስቀጠል፣ የማስተዋወቁን፣ የማስተባበሩንና ሕዝባዊ መነሳሳትን የመፍጠር ቁልፍ ተግባራትን ቸል ካለ፡፡ ብቻ መንግሥት የራሱ አጀንዳ ላይ ቢያተኩር ምንኛ በተሻለ ሥራዎችንም በግብር ይውጣ አሊያም በሰሞንኛ (Campaign Mentality) ከመከወን አባዜ ወጥቶ የነገሮችን “ከ እስከ” ሥልታዊ በሆነ መንገድ ተልሞ አንዳች ሳያስተጓጉል ቢተገብር ምንኛ ውጤታማ በሆነ እላለሁ፡፡

ይኼንን የበለጠ ለመግለጽ በወቅቱ ካዘንኩባቸው ጉዳዮች አንዱን ልጥቀስ፡፡ መንግሥት ሁሌም መንግሥት ነው፡፡ ሁሉ በእጁ ሁሉ በደጁ፡፡ ይኼም ሚዲያውን በመጠቀምም ሆነ በመረጠው አደረጃጀት ከሕዝቡ ጋር መገናኘትና መቆራኘት ሲችል (በነገራችን ላይ ኢሕአዴግ 17 ዓመታት በትጥቅ፣ 25 ዓመታት በከተማ፣ በአጠቃላይ 42 ዓመታት የፖለቲካ ታሪክ እንዳለው ልብ ይሏል) ትልቅና ሥልታዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ሊያተኩርና በዋናነት የራሱን አጀንዳ ማራመድ ሲገባው እንዲህ ወርዶ፣ ወርዶ፣ ወርዶ . . . ጦማሪያንን ቀምሮ፣ አስተያየት ሰጪዎችን ሰድሮ፣ ጎምቱ የትግል ጓዶችንና ትንታኔ ሰጪ ሊህቃንን ወድሮ፣ ዶክመንታሪ ሽፋን ሰጪ ፊልሞችን ተጠቅሞ ከአንድ በዕድሜው ገና ለጋ ከሆነና የተደራጀ ፓርቲ እንኳን ካልሆነ ግለሰብ ለዚያውም በዚህ አገር ከማይኖር ሰው ጋር የዚህ ዓይነቱን የፕሮፓጋንዳ ጦርነት መክፈቱ ገርሞኛል፣ አሳዝኖኛል፡፡ መንግሥት የሚባለውን ትልቅ ‹‹ጽንሰ ሐሳብም›› የሆነ ‹‹ሰውዬ›› አድርጌ እንድሥለው ከማድረጉ በተጨማሪ ከዚህ በፊት የነበረኝንም ግምት መልሼ እንድጠይቅ አስገድዶኛል፡፡ "ኢት ኢዝ ፒቲ!"እንደሚሉት፡፡

የበለጠ አሳዛኝ ሆኖ ያገኘሁት ደግሞ መንግሥት እነዚህ ሁሉ ሰዎችና መንገዶች እንኳን ተጠቅሞ አገርን ማረጋጋት አለመቻሉ ነው፡፡ በተለመደው የሕግ አግባብም ቀውሱን መቆጣጠር ባለመቻሉም አገሪቱ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንድትተዳደር ዳረጋት፡፡ ከሌሎች ዕርምጃዎችና ክልከላዎች በማይተናነስ ሁኔታ ማኅበራዊ ድረ ገጾችን መዝጋት እንደ ሥልት ተጠቀመ፡፡ ከዚያም “በኢቢሲ ሳሳያችሁ ካልሆነ በቀር . . . እነዚህ አሸባሪ የተባሉ ሰዎችንና ሚዲያዎችን ማየትም ሆነ መስማት፣ የእነሱን ገጽ ላይክ፣ ሼር ወይም ፎሎው ማድረግ ክልክል ነው . . .” ብሎ አወጀ፡፡ በዚህ ደግሞ ጥቂት ትዝብት እንጂ ቅሬታ የለኝም፡፡ ምክንያቱም አገሬ እንድትረጋጋ፣ ለውጦችም በሰከነ መልክ እንዲከወኑ እንጂ የአንድም ኢትዮጵያዊ ደም እንዲፈስ ስለማልፈልግ፡፡ ትዝብቴ ደግሞ ይኼንን እንዳናደርግ መንግሥት ራሱ ከከለከለ ለምን በኢቢሲ ያሳየናል የሚል ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ስለእነሱ መስማትም፣ ማየትም፣ ማወቅም፣ የማይፈልጉ ዜጎችን ነፃነት የተጋፋ ይመስለኛል፡፡ ብቻ መንግሥት እንደሚለው ከሆነ ይኼ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሆነ ጊዜ ላይ መነሳቱ አይቀርም፡፡ መንግሥትም ዳር ዳርታን እያሳየ ነው፡፡ የተነሱም ክልከላዎች አሉ፡፡ አዋጁ ሙሉ በሙሉ በሚነሳበት ወቅት ማኅበራዊ ድረ ገጾች መከፈታቸው አይቀርም፡፡ የተጀመረም ይመስለኛል፡፡ ታዲያ አገሪቱ አልፋበት የነበረቸው አጣብቂኝ የፈተና ጊዜ ተመልሶ እንደማይመጣ መንግሥት ምን ዋስትና አለው? የሚለው ጥያቄ ወሳኝ ይሆናል፡፡

እንደኔ ዕይታ ከሆነ በዚህ ወቅት መንግሥት ቆም ብሎ ይኼ ጉዳይ እንዴት ሊፈጠር ቻለ? ከየት መጣ? መንስዔውስ ምንድነው? አባባሽ ምክንያቶችስ ምን ምን ናቸው? የሚሉ ስትራቴጅካዊ ጥያቄዎችን እንደሚገባ መመርመርንና መመለስን እንደ ቁልፍ ተግባሩ በመውሰድ፣ ችግሮችን እንደ መስፈንጠሪያ መልካም አጋጣሚ ሊጠቀምባቸው የሚገባው ይመስለኛል፡፡ ይኼም በአገሪቱ ተከስቶ የነበረው አለመረጋጋት ዕውን በዚህ በተጠቀሰው ግለሰብ ብቻ የሚመራ ነበርን? ወይስ መንግሥት ከሕዝቡ ጋር የተሸዋወደበት ጉዳይ ይኖር ይሆን? ወይስ ኢሕአዴግ እንደ ፓርቲ በውስጡ ለዓመታት ሲነሱ የነበሩ ነገር ግን በተለያየ መንገድ ሲመለሱ አሊያም ሲዳፈኑ የቆዩ ፓርቲን መሠረት ያደረጉ የኃይል ሚዛን ጥያቄዎችና አለመግባባቶች አብጠው በመፈንዳታቸው ይሆን? ወይስ ናዳው ከፓርቲው ፍጥነት በላይ ሳይገመት በደራሽ መልክ በመምጣቱ? ወይስ  በተያያዙና በተቆላለፉ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮች ሳቢያ የተፈጠሩ? አሊያም የተራገቡ? መልሱ ምንም ይሁን ምን አንድ ነገር ማድረግን የግድ ይላል፡፡ በችግሮቹ ዙሪያ ጥልቅ ፍተሻ እውነተኛ መፍትሔና አፋጣኝ ምላሽ መስጠትን፡፡ ካልሆነ ግን የዚህን ያህል ጊዜና ወጪ ወስዶ እየተከናወነ ያለው ጥልቅ ተሃድሶ ዘለቄታዊ የሆነ አገራዊ ፋይዳ ያመጣል የሚል ግምት የለኝም፡፡

በዚህ በተጠቀሰው ግለሰብም ሆነ ሌሎች አክቲቪስቶች ምክንያት ነው ቀውሱ የመጣው ተብሎ ከታመነ ግን ለምን “መሪ አልባ እንቅስቃሴ” ሲባል ከረመ የሚል ትዝብትን ከመፍጠሩ ባሻገር፣ እንደ አገር ግን የከፋ ዝቅጠት ይመስለኛል፡፡ በተለይም ኢሕአዴግ በፅኑ መሠረት ላይ የተገነባች ኢትዮጵያን መሥርቻለሁ ብሎ በየምኩራቡ የሰበከውን ስብከት ፉርሽ ስለሚያደርግና በፅኑ መሠረት ላይ ተገነባች የተባለችው አገር የት አለች? የሚል ወሳኝ ተጠይቅን ስለሚያስነሳ ነው፡፡ ምክንያቱም ባለፉት ወራት የታየችው ኢትዮጵያ በፅኑ መሠረት የተገነባችው ሳይሆን በሁለት መስመር የትዊተር ወይም የፌስቡክ መልዕክት ለመፍረስ የምትንገዳገድ ኢትዮጵያ ነበረች፡፡ ይኼን ያልኩት እኔ ሳልሆን በመንግሥት ዘንድ ያለውን አመለካከትና ዝንባሌ በዚያን ወቅት በራሱ ሚዲያ ከሚቀርቡት ዝግጅቶችና መልዕክቶች በመረዳት ነው፡፡ ይሁን እንጂ ይኼ አስተሳሰብ አሁንም ካለ በጥልቀት የመታደሱን ሒደት የበለጠ ጥልቅ እንዲሆን፣ የአመራሩን ቁርጠኝነትና ተራማጅነትን የሚጠይቅ ይሆናል፡፡

እንዲህ ዓይነቱን አመለካከት “ለምን አትተውትም” በማለት ፋና ብሮድካስቲንግ ባዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ የሞገተችው ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ ነበረች፡፡ ምኑን መሰላችሁ ወ/ሮ ሰሎሜ ያነሳቸው? ኢቢሲ 1 ከዜና በኋላ እንደ ቋሚ ፕሮግራም ጃዋርንና መሰል አቋም አላቸው የተባሉ ግለሰቦችን በሚመለከት እንደ ተወዳጅ ተከታታይ ድራማ ዓይነት ማቅረቡን ነው፡፡ ምክንያቱም ይቀርቡ የነበሩት የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ይኼ ግለሰብ የት እንደሄደ? ከእነማን ጋር እንደዋለ? ዕቅዱ ምን እንደሆነ? (በነገራችን ላይ ጂቲፒ 2 እንደ አገራዊ የልማት ዕቅድ የጃዋር ዕቅድን ያህል የአየር ሽፋን የተሰጠው አይመስለኝም) የት ስብሰባ እያካሄደ እንደሆነ (እንደ ጠቅላይ ሚኒስትር ወይም የሆነ ልዑክ ቡድን)፣ ከማን ጋር ፎቶ እንደተነሳ? . . . ወዘተ ቀን በቀን ሲቀርብ ማየት ኢቢሲ የህዳሴና የብዝኃነት ድምፅ መሆኑን ዘንግቶ እንደ ፓፓራዚ ሲደክም ነበር የሰነበተው ያስብላል፣ ላስተዋለው፡፡ ነገር ግን “አቢሲ የህዳሴና የብዝኃነት ድምፅ ነበረ እንዴ?” ብላችሁ ከጠየቃችሁኝ መልስ የለኝም፡፡ በሙያው ብዙ ልምድ የለኝምና፡፡

የዚህን ጽሑፍ ተከታይ ክፍል በሚቀጥለው ሳምንት እንዲያነቡ በአክብሮት እጋብዛለሁ፡፡ የሳምንት ሰው ይበለኝ፣ ይበላችሁ፣ አሜን!

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dejeneassefa@yahoo.com.ማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

የኢሬቻ ክስተት - እንደ ችግር ብቻ ወይስ ትምህርት የሚወሰድበት አጋጣሚ?

$
0
0

ክፍል ሁለት

በደጀኔ አሰፋ ዳምጠው

በልማት ሥራ ውስጥ የፕሮጀክት ዑደት አመራር (Project Cycle Management) የሚባል ጽንሰ ሐሳብ አለ፡፡ አንድ ፕሮጀክት ከንድፈ ሐሳቡ ጀምሮ ክትትልና ምዘናን (Monitoring and Evaluation) ያጠቃልላል፡፡ በክትትልና ምዘና ደግሞ ተነድፎ የተተገበረው ፕሮጀክት ዓላማውን ማሳካት አለማሳካቱን፣ የትግበራ ሥልቶች አግባብነት፣ በወጣው ወጪና በተገኘው ውጤት መካከል መመጣጠን መኖሩን/አለመኖሩን ወዘተ. ለማወቅ ይቻላል፡፡ ታዲያ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ከምዕራባዊያኑ የምቀናበት አንድ ጉዳይ አለ፡፡

ይህም ከክትትልና ምዘና ማዕቀፍ ሳይወጡ በዋናነት የሚያተኩሩት ምን ውጤት አመጣ አላመጣ በሚለው ጉዳይ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ ምን ትምህርት ተገኘበት በሚለው ላይ ነው፡፡ በመልካም ጎን (በጥንካሬ) የሚነሱ ጉዳዮችን እንዴት የበለጠ ውጤታማ ማድረግ እንደሚችሉ ያውጠነጥናሉ፡፡ ክፍተቶች (ደካማ ጎኖች) ወይም በእነሱ አጠራር ሊሻሻሉ የሚገባቸው ጉዳዮች (ከሥልት፣ ከበጀት፣ ከሰው ሀብት ምደባ፣ ከጊዜ፣ ወዘተ. አንፃር) ካሉ ደግሞ ጉዳዮቹን አንጥረው በመለየት ለወደፊቱ እንዴት ሊሻሻሉ እንደሚገባቸው ይመክራሉ፣ ይዘክራሉ፡፡ ከተገኘው ትምህርት ሁሉም ይማርበት ዘንድ ደግሞ ዋና ዋና ትምህርቶችን በመቀመር ለሌሎች ያካፍላሉ፡፡ በእነሱ አጠራር “Knowledge Sharing” ይሉታል፡፡

ከዚህ አንፃር በእኛ አገር ያለውን አሠራር በወፍ በረር ስቃኘው ከእነሱ የተለየ ሆኖ ይታየኛል፡፡ በእኛ አገር ክትትል አለ፣ ግምገማ አለ፡፡ በዚህ ደግሞ ወይ ትወድቃለህ ወይም ዕድለኛ ከሆንክ ታልፋለህ፡፡ አለቀ፡፡ በመውደቅና በማለፍ ብቻ የተገደበ አማራጭ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ ምን ትምህርት ተገኘበት የሚለው ጉዳይ በውል አይጤንም፣ አይመዘንም፡፡ ግን እኮ አይደለም ፕሮጀክት ሕይወት ራሱ ከመውደቅና ከማለፍ የዘለለ ‹‹ወደፊት›› (Future) የሚባል ዕድል አለው፡፡ የሚቀረን፣ልንኖረውና ልናሳካው የምንችለው ብዙ ሕይወት፣ ብዙ መንገድ፣ ብዙ ግብ አለ፡፡ ስለዚህ አንዱ አንዱን በመጥለፍ ለመጣል፣ ሌላኛው ሌላውን ለማሳለፍ ከመራኮት ወይም በረባ ባልረባው ጊዜና ዕድልን በከንቱ ከማጥፋት ቅዱሱ መጽሐፍ ‹‹ይህም ለትምህርታችን ተጻፈ›› እንዲል፣ ለነገ ስንቅ የሚሆነን ትምህርት መቅሰሙ እንደ ግለሰብ፣ እንደ ተቋምም ሆነ እንደ አገር ጠቃሚ ሆኖ ይታየኛል፡፡

ይህንን የመንደርደሪያ ሐሳብ ያነሳሁት ባለፈው ሳምንት ለውይይት ካነሳሁት የኢሬቻ ክስተት ጋር በተያያዘ ምናልባት የሚሰጠን ትርጉም ይኖረው ይሆናል በሚል እሳቤ ነው፡፡ ኢሬቻና መሰል ክስተቶች ተከሰቱ፡፡ አለፉ፡፡ ጎርፍም፣ ድርቅም፣ ረሃብም፣ ወዘተ. ይከሰታሉ፣ ደግሞም ያልፋሉ፡፡ ብዙ ኩነቶች አልፈዋል፣ እያለፉ ነው፣ ያልፋሉም፡፡ መስከረም 22 ቀን 2009 ዓ.ም አለፈ፡፡ ቀኑ መቼም ቢሆን ተመልሶ አይመጣም፡፡ በዳግም ምፅዓትም ቢሆን፡፡ ፕሮጀክት ካለቀ አለቀ፣ ቀን ካለፈ አለፈ፣ ክስተት ካለፈም እንዲሁ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን በሌላ ጊዜ ተመሳሳይ ክስተት፣ ወይም ከዚህ የከፋ ወይም ያነሰ ክስተት እንደማይከሰት እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ ስለዚህ ካለፈው ክስተት እንደ አገር፣ እንደ ሕዝብ፣ እንደ መንግሥት ለወደፊት ዝግጅት የሚሆነን ምን ትምህርት ተገኘበት የሚለው መሆን አለበት፡፡ ካልሆነ ግን በክስተቶቹ ከተጎዳነው በላይ የሚጎዳን ትምህርት አለመውሰዳችን ሊሆን ይችላል፡፡

እዚህ ላይ በኢሬቻ የተፈጠረውን የሕዝብ እንቅስቃሴ በሌላ ዕይታ ማየት እፈልጋለሁ፡፡ ሕዝብ እኮ የመጨረሻ ሲከፋና ተስፋ ሲቆርጥ እንዲህ ዓይነት ጥያቄ በዚያ ዓይነት መንገድ አያቀርብም፡፡ አንድም ዝም ማለት ሲሆን፣ ወይም በሌሎች አገሮች እንደምናየው ማለቂያ ወደሌለው አመፅ፣ የማያቋርጥ ጥፋትና ብጥብጥ መግባት ነበር ምርጫው የሚሆነው፡፡ ስለዚህ ይህ የሕዝብ ጥያቄ (ጥያቄው ምንም ይሁን ምን) ለእኔ የሚያሳየኝ ነገር ቢኖር ሕዝቡ አሁንም የሚሰማኝ መንግሥት አለ ብሎ እንደሚያምንና በመንግሥት ላይ ያለው እምነት ሙሉ በሙሉ አለመሟጠጡን ነው፡፡ የሚሰማ መንግሥት የለም ብሎ ቢያስብ መጮህን ለምን ምርጫው ሊያደርግ ይችላል?

በነገራችን ላይ ከዚህ መንግሥት በፊት በነበረው የደርግ አገዛዝ እንዲህ ዓይነት የሕዝብ ተቃውሞ ማድረግ ቀርቶ ማሰብ እንደማይቻል በሁሉም ኢትዮጵያዊ ሕይወት ውስጥ ያለፈ የአገር ታሪክ ነው፡፡ ነገር ግን በትጥቅ ትግል በነፍሳቸው ተወራርደው በብዙ መስዋዕትነት የተገኘው ይህ የዴሞክራሲያዊ መስመር እንዲህ ዓይነቱን የሕዝብ ጥያቄና ጥያቄን የማቅረብ ተነሳሽነትን ለምን እንደ አንድ ትልቅ የዴሞክራሲና የትግሉ ፍሬ ተደርጎ ሊወሰድ አይገባም? የትግሉ ፍሬ ነው ብሎ በማሰብና ብሎም ይህን ፍሬ ሕዝቡ እንደሚገባ እንዲያጣጥም ቢመቻችለት ይህ ፍሬ እንዲመጣ ላስቻሉት ለእነዚያ እውነተኛ የኢትዮጵያ ወጣቶችና ድንቅዬ የትግል ሰማዕታት ዝክር የሚሆን ሐውልት ከማቆም በዘለለ፣ በሕዝቡ ልብ ዘለዓለማዊ ክብርና ሞገስ የሚያሰጣቸው የክብራቸው አደባባይ በሆነ ነበር፡፡ አልሆነም፡፡

በዚያ ላይ መንግሥት የደረሰውን ጥፋት ከመቀነስ አኳያ የተሰበሰበውን ሕዝብ በሚገባ ለመቆጣጠር (Crowd Management) በቂ ዝግጅት አድርጓል ለማለት የሚያስችል ነገር አልነበረም፡፡ ይህን የምለው ባዶ እጁን የወጣ ሕዝብ ግፋ ቢል ከፍተኛ ጩኸት ከማሰማት በቀር ምን ሊያደርግ ይችላል ብዬ በማሰብ ነው፡፡ መንግሥት ደግሞ እንደ ባቢሎን ግንብ በጩኸት የሚፈርስ አይደለም፡፡ ባዶ እጁን አልነበረም ተብሎ ከታመነ ወይም ይህን የሕዝብ መሰባሰብ ሌሎች ‹‹የጥፋት ኃይሎች›› ወደ ሌላ አቅጣጫ ሊወስዱት ይችላሉ የሚል መንግሥታዊና ሕጋዊ ሥጋት ከነበረ ደግሞ (በእርግጥ በዚያ ሰሞን እዚህም እዚያም እየታየ ከነበረው አለመረጋጋትና የፀጥታ ችግር አንፃር እንዲህ ዓይነት ሥጋት መኖሩ ምንም የሚደንቅ ባይሆንም)፣ መንግሥት የሕዝቡን ደኅንነት የመጠበቅ ዋነኛ ኃላፊነቱን ከመወጣት አንፃር አመርቂ ዝግጅት ነበረው ማለት አያስችልም፡፡

ቢያንስ የተወሰዱት ዕርምጃዎች ሁኔታው ከሚፈልገው ጊዜ መቅደማቸውን ልብ ይሏል፡፡ መንግሥት በዋናነት ሲያተኩር የነበረው ለደረሰው ጥፋት የሆነ አካልን ተጠያቂ ለማድረግ መረጃና ማስረጃ የማፈላለግ ሁለተኛ ጉዳይ ላይ ነበር፡፡ እዚህ ላይ የታዩ ጉድለቶችን በውል በመመዘን ለፖሊስ ሠራዊቱ፣ ለደኅንነት ኃይሉና ለመከላከያ ሠራዊቱ በሚገባ የታቀዱ የአቅም ግንባታ ሥራዎች በተከታታይነት ሊደረግላቸው ይገባል እላለሁ፡፡ እየተናገርሁ ያለሁት ስለ አንድ ኢሬቻ ወይም ስለ አንድ ብሔር ሳይሆን አገራዊ ነገር በመሆኑ፣ ምናልባት የፖሊሲ ምልከታ ሊኖረው ስለሚችል አመራሩ ለዚህ ጉዳይ ቦታ እንዲሰጠው ለማሳሰብም እወዳለሁ፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ትልቅ ጉዳይ መሆን ያለበት የኢሬቻ በዓል ለምን በሰላም ተከብሮ አላለፈም የሚለው ሐሳብ አይደለም፡፡ በነገራችን ላይ ‹‹በሰላም ተከብሮ›› ብዬ ከምገልጸው ይልቅ ‹‹በተያዘለት የበዓል መርሐ ግብር ተከብሮ›› አላለፈም ብለው ይሻለኛል፡፡ ምክንያቱም ሰላም ማለት የጦርነት አለመኖር ብቻ አይደለም ብዬ ስለማምን፣ ሕዝቡ ደግሞ የራሱን ጥያቄ በአደባባይ መግለጽ መቻሉንና ድምፅ ማሰማቱን እንደ ትልቅ ውጤትና ዕረፍት ሊሰማው ስለሚችልም ጭምር ነው፡፡ ከበጣም መጥፎ፣ መጥፎ ይሻላል እንዲሉ ጥያቄን ይዞ ከመሞት ድምፅን አሰምቶ መሞት የሚለው ምርጫ ጥያቄውን ባቀረበው ሕዝብ ዘንድ እንደ ትልቅ ፍሬ ሊታሰብ የሚችልበት አጋጣሚም አለ ለማለት ነው፡፡ ዋና ጉዳይ መሆን ያለበት በዓሉን ለማክበር የታደመው ሕዝብ ይህንን የሚወደውን በዓል ሰውቶ እንዲህ ዓይነት ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ አስተዳደራዊና መሰል የፍትሕ ጥያቄዎችን ለማቅረብ ለምን ተገደደ የሚለው ሐሳብ ነው፡፡

በእኔ ዕይታ የበለጠ ሊታዘንለት የሚገባው ሕዝቡ ነው፡፡ ምክንያቱም አምላኩን በኅብረት ተሰባስቦ ለማመስገን ትውፊታዊ ወጉን ለማስጠበቅ በዓመት አንድ ጊዜ እንደ መስቀል ወፍ ከያለበት በናፍቆት ጠብቆ የሚገናኝበትንና የማንነቱ መገለጫ የሆነውን ክብረ በዓል ማክበርን ወደ ጎን ትቶ፣ በቤቱ የሚያሰላስላቸውን ያልተመለሱ ጥያቄዎችን እንደ ኢሬቻ ባሉ በጉጉት በሚጠበቁ ክብረ በዓላት የሚፈጥሩለትን የመገናኘት መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ጥያቄውን ማቅረቡ የሚያስፈርድበት ሳይሆን የሚታዘንለት ያደርገዋል፡፡ ይህም ሕዝቡ ያሉትን የትኛውንም ዓይነት ጥያቄዎች ከዚህ ቀደም የመሰብሰብም ሆነ ሰላማዊ ሠልፍ የመውጣት መብቱ ተጠብቆለት ቢሆን ኖሮ፣ በስስት የሚያከብረውን ክብረ በዓል በወጉ ሳያከብርና ይልቁኑም ውድ የሆነ ሕይወትን ባላስከፈለው ነበር፡፡

እዚህ ላይ በጣም አሳዛኝ ሆኖ ያገኘሁት ከዚህ ሁሉ ትዕይንት በኋላ ይህንን ክስተት ማን ቀሰቀሰው? ማን አስተባበረው? ስንት ሰው ሞተ? ስንት ሰው  ቆሰለ? በጥይት ነው በጭስ? በመረጋገጥ ነው በገደል? የሚሉና መሰል ጥያቄዎች እንጂ ይህ ክስተት በምን ገፊ ምክንያት ተነሳ? የሕዝቡ ዋነኛ ጥያቄዎች ምንድን ናቸው? እንዴት ሊፈቱ ይችላሉ? ወዘተ. የሚሉ መሠረታዊ ነጥቦች በሚገባ ደረጃ ተነስተዋል ወይም ተብላልተዋል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ምናልባት የጥልቅ ተሃድሶው ፍሬ ይመልሳቸው ይሆናል ብዬ ግን እመኛለሁ፡፡ ስለዚህ ከሌሎቹ ጉዳዮች ይልቅ እንዲህ ሕዝቡን ዋጋ ያስከፈሉት ጥያቄዎች ምንድን ናቸው የሚለው ሐሳብ ላይ ማተኮር ሁሉንም የሚመለከታቸውን አካላት በማሳተፍ ወደ ተከታዩ የመፍትሔ አቅጣጫ ለመሄድ ያስችላል፡፡ ካልሆነ ግን ይህን ያህል መስዋዕትነት የተከፈለበት የሕዝብ ጥያቄ በሦስት ቀናት ብሔራዊ ሐዘን ይደመደማል፡፡

እዚህ ላይ መጠቀስ ያለበት ነገር የሕዝብ ጥያቄ ይመለስም አይመለስም ሌላ ጉዳይ ሆኖ፣ የሕዝቡን ጥያቄ እንደወረደ ማድመጥና መረዳት የመጀመሪያው ቁልፍ ተግባር ይሆናል፡፡ በአንፃሩ መንግሥትም ሆነ የትኛውም አካል የሕዝብን ጥያቄ እንደፈለገ የመተርጎም፣ የማስተካከል፣ የማጣመምም ወይም ወደሌላ አቅጣጫ እንዲፈስ ማድረግ ተቀባይነት የማይኖረው ጉዳይ ነው፡፡ ምክንያቱም እንዲህ ዓይነቱ ‹‹እኔ አውቅልሃለሁ›› ወይም ‹‹እኔ አስብልሃለሁ›› የሚል አመለካከትም ሆነ አካሄድ ʻከባለቤቱ ያወቀ ቡዳ ነውʼ እንዲሉ፣ ሕዝብ የሚፈልገውንና የሚጠይቀውን ጉዳይ አያውቅም የሚል ምልከታ ስላለው ሕዝብን የሚያከብር አይሆንም፡፡ ሕዝብ ክቡር ነው፡፡ ሕዝብ አዋቂ ነው፡፡ ሕዝብ ለራሱ የሚያስፈልጉትን ጉዳዮች እውን ለማድረግ ለጊዜው አቅም የሌለው መስሎ ሊታይ ቢችልም ስለራሱ ግን ያሉበትን ችግሮች፣ የሚፈልጋቸውን ጉዳዮች፣ እንዲመለሱለት የሚፈልጋቸውን ጥያቄዎች በሚገባ ያውቃል፡፡ ልንማርበት ወደሚገባን ትምህርት ከመግባታቸን በፊት በመጀመሪያ እንዲህ ዓይነቱን የሕዝብ መሰባሰብን ተጠቅሞ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት የሚሞክር የተደራጀም ይሁን ያልተደራጀ አካል ካለ፣ በሚከተሉት ነጥቦች በወንጀል መጠየቅ ይኖርበታል የሚል ግምት አለኝ፡፡

አንድ እንደ ኢሬቻ ባሉ ክብረ በዓላት የሕዝቡ መሰባሰብ በዋናነት በዓሉን ለማክበር በመሆኑ ነው፡፡ ይኼ ነጥብ ሁሉንም ጉዳዮች በየፈርጁ ማየት ስለሚያስፈልግ እንጂ ከላይ ካነሳሁት ጉዳይ ጋር የሚጣረስ አይደለም፡፡ ምንም እንኳን መተንፈሻ ያጣ ሕዝብ እንዲህ ዓይነቱን ክብረ በዓላት ተጠቅሞ ጥያቄን ማሰማቱ ለኢትዮጵያውያን አዲስ ባይሆንም፣ ሌሎች ሦስተኛ አካላት ግን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ መገፋፋታቸውን ሕጋዊ አያደርገውም፡፡ ሁለት ኢሬቻን በመሰሉ ክብረ በዓላት ላይ የተገኘው ሕዝብ ተብሎ በጅምላ ሲጠራ በተባለው የፖለቲካ አጀንዳ የሚስማማ እንዳለ ሁሉ፣ የማይስማማም ወይም በጉዳዩ መሳተፍ የማይፈልጉ ሰዎችን ስለሚያካትት የእነዚህን ዜጎች መብት የሚጥስ ነው፡፡ ሦስት በዚህ በዓል ላይ ምንም ነገር የማያውቁ በዕድሜ ሕፃናት የሆኑ አሊያም ከችግሩ ሩጠው ማምለጥ የማይችሉ ወይም ራሳቸውን ማዳን የማይችሉ አካል ጉዳተኞች፣ ነፍሰ ጡሮች፣ አዛውንቶች ወዘተ. የሚገኙበት በመሆኑ ነው፡፡ አራት በእንደዚህ መልኩ የተተገበረ የፖለቲካ እንቅስቃሴ በውጤት ደረጃ በአገር ደረጃ መሠረታዊ የሚባል ለውጥን የማምጣት ዕድሉ ውስን መሆኑና ከዚህ በተጨማሪም የሚያስከፍለው ዋጋ ኢምንት ከሆነው ውጤት ጋር ሲመዘን ተገቢ (Worth Paying) ባለመሆኑ ነው፡፡ አምስት ነፃ የሆነ፣ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ መንገድን የሚያበረታታ ባለመሆኑና ከዚያ በኋላ በመንግሥት የሚወሰዱ ዕርምጃዎች ወዳልተሻለ መንገድ እንዲገባ የሚያስገድዱት ስለሚሆን ነው፡፡ ስድስት እንዲህ ዓይነት ክስተት ጥሎ የሚያልፈው ትዝታ ጥሩ ባለመሆኑ የማኅበረሰቡን ሥነ ልቦና (Social Psychology) የሚጎዳ ስለሚሆን፣ ከዚያ በኋላ ሕዝቡ በተጀመሩ በዴሞክራሲያዊና በልማት ጎዳናዎች ሊኖረው የሚገባውን ተሳትፎ እንዲቀንስ ያደርጉታል፡፡ በአጠቃላይ በእነዚህና መሰል ምክንያቶች እንደ ኢሬቻ ባሉ ክብረ በዓላትም ይሁን ሌሎች ሕዝባዊ፣ ባህላዊና ሃይማኖታዊ በዓላትን ለፖለቲካ ፍጆታ ማዋል ተቀባይነት ይኖረዋል ብዬ አላምንም፡፡

በአንፃሩ እንደኔ ዕይታ ካለፈው ክስተት የሚከተሉትን ነጥቦች መረዳትና መማር የሚቻል ይመስለኛል፡፡ በመንግሥት ያልተመለሱ ነገር ግን በሕዝቡ ውስጥ ያሉ መሠረታዊ ጥያቄዎችና አንገብጋቢ ጉዳዮች መኖራቸውን፣ ከዚህ ቀደም የሕዝብ ጥያቄዎች በሰላማዊ መንገድ የሚስተናገዱበትና ሕዝብ ብሶቱንም ሆነ ጥያቄውን የሚተነፍስበት አሳታፊ የሆነ የተመቻቸ ሥርዓት በወጉ ያለመኖሩን አሊያም አለመተግበሩን፣ የተመቻቸ አሳታፊ ሥርዓት ባለመኖሩ/ባለመተግበሩ በየጊዜው ሲነሱ ለነበሩ ጥያቄዎች ከሥር ከሥር ምላሽ ባለመሰጠቱ ሳቢያ ህልቆ መሳፍርት የሆኑ ጥያቄዎች መፈጠራቸውና ጥያቄዎቹም የተወሳሰቡና ቅርፅ አልባ (Amorphous) እንዲሆኑ ማስገደዱን፣ መንግሥት አሁንም ከሕዝብ የሚነሱ ሕጋዊና ሰላማዊ ጥያቄዎችን ለመመለስ ያለው ፖለቲካዊ ዝግጁነት በአመርቂ ሁኔታ እያስመሰከረ እንዳልሆነ፣ እንዲሁም የእነዚህ ጥያቄዎች አለመመለስ ብቻ ሳይሆን ምላሽ እየተሰጠበትም ያለው አግባብ አገሪቱን ወዴት ሊወስዳት ይችላል የሚል ሥጋትን ኃላፊነት በሚሰማቸው ኢትዮጵያውያን ዘንድ ሥጋት መፍጠሩን ያመላክታል፡፡

ከላይ ያነሳሁት ማለትም ያልተፈቱ ጥያቄዎች ሲያድጉ ውስብስብና ቅርፅ አልባ የመሆናቸውን ነጥብ የበለጠ ለማብራራት፣ ትዳራቸውን በሕጋዊ መልኩ ከማፍረሳቸው በፊት የመጨረሻ የመታረቅ ዕድሉን ለመጠቀም የትዳር አማካሪዎች ዘንድ ራሱንና ሚስቱን ይዞ ስለሄደ ሰው ታሪክ ላካፍላችሁ፡፡ እነዚህ ባልና ሚስቶች ለረዥም ዓመታት በትዳር የዘለቁ ቢሆንም፣ በተለያዩ ጊዜያት በተፈጠሩ አለመግባባቶችና በተለይም በሴቷ ላይ ይደርስባት ከነበረው ግፍና በደል የተነሳ ቢመስል ቢገዘት መፋታትን አንድና አንድ ምርጫዋ ያደረገችበት ጊዜ ነው፡፡ ሆኖም ግን ለብዙ ዘመን ቢበድልም ፍቺውን ግን አልፈለገም፡፡ ባል እንዳልኳችሁ የትዳር አማካሪዎች ዘንድ ይዟት ሄደ፡፡ ከዚያም አማካሪዎቹ ከተቀበሏቸውና ተጣልተው የመጡበትን ጉዳይ እንዲያስረዱ ካመቻቹ በኋላ የመጀመሪያውን ዕድል ለባል ሰጡ፡፡

አቶ ባልም እንዲህ አለ፡፡ ‹‹. . . በመጀመሪያ ይህንን የቤተሰብ ጉዳይ እንዳብራራ ለተሰጠኝ ዕድል አመሰግናለሁ፡፡ ለዚህም ሲባል ይህንን የመሰለ አሳታፊ መድረክ ላዘጋጁ አካላት በራሴና በወከለኝ ቤተሰብ ስም እንዳመሰግን ይፈቀድልኝ . . .››፡፡ ጥቂት ቤተሰባዊ ጭብጨባ ከተስተጋባ በኋላ ንግግሩን ቀጠለ፡፡ ‹‹ . . . ስለ ባለቤቴ መናገር የምፈልገው ነገር ቢኖር . . . ሚስቴን እወዳታለሁ በእጅጉም . . .  አከብራታለሁ፡፡  እዚህ ላይ ሊሰመርበት የሚገባው ጉዳይ ሚስቴን እወዳታለሁ የሚለው ነው . . .›› ካለ በኋላ ንግግሩን ለአፍታ ቆም ሲያደርግ አማካሪዎቹ እርስ በእርስ እየተያዩ መጠነኛ ፈገግታ ቸሩት፡፡ እሱ ግን ንግግሩን ቀጠለ፡፡  ‹‹. . . እንዲያውም እሷን አግብቼ በአንድ ጎጆ ኑሮ ከመጀመራችን በፊት ባለቤቴ የሌላ ሰው ሚስት ሆና ትኖር ነበር፡፡  . . . ባሏም በጣም ጨካኝ፤ አረመኔና ጡንቸኛ ነበር፡፡ ልጆቿንም በቤት ውስጥ ማሰቃየት፣ የጉልበት ብዝበዛ መፈጸምና ገፋ ሲልም አስገድዶ መድፈርን የቀን ተቀን ተግባሩ አድርጎ ይኖር የነበረ ሰው ነው፡፡ የራሱን ጥቅምና ዝና ለማስጠበቅ ሲልም ትርጉም የለሌው የቤት ለቤት ሽኩቻ እየፈጠረና የቤተሰብ ግጭትን እያነሳሳ አንዱን የቤተሰብ አካል ከሌላኛው ጋር ማጣላትና ለእንግልት መዳረግ የትዳሩ ዋነኛ መርሆዎች ነበሩ፡፡ ይህ የቀድሞ ባሏ በሚከተለው አረመኔያዊ የቤት አስተዳደር አገኘዋለሁ ብሎ የሚመኘውን ያህል እርካታ ካላገኘና በዚህ አልበቃ ሲለው፣ ከቤቱ እልፍ ይልና ከጎረቤት ጋር ጠብ ይጭር ነበር፡፡ በዚህ ግጭትም እንዲፋለሙለት በመከራ ያሳደገቻቸው ልጆቿን ይማግድባታል፡፡ የዚህ ግጭት ውጤትም አብዛኛውን ጊዜ አስከፊ የሆነ የወጣት ልጆቿ ሞትና የአካል ጉዳት ስለሚሆን፣ መላ ቤተሰቡን ለጥልቅ ሐዘንና የልብ ስብራት ይዳርጋቸው ነበር፡፡ እኔም በዚህ ጨካኝ ሰውዬ ይደርስባት የነበረውን ስቃይ በውል ተመልክቼ፣ በእርሷ ጫማ ቆሜና ሐዘኗን እንደ ራሴ ሐዘን ቆጥሬ የዛሬዋ ሚስቴንና ከተለያዩ ባሎች ያፈራቻቸውን የስስት ልጆቿን ካሉበት አስከፊ ኑሮ ለማውጣት ወሰንኩ፡፡ ነፃ ቤተሰብ እንዲሆኑ ለማስቻል የነበረኝን ምኞት ለማሳካት ይረዳኝ ዘንድም ከባልንጀሮቼ ጋር መከርኩ፡፡ በሐሳቡም በመስማማታችን እኔና ጓደኞቼ ሕይወታችንን አደጋ ላይ ጥለንና ብዙዎችን አስከትለን በእልህ አስጨራሽ ትግልና መስዋዕትነት እነሆ የዛሬ ስንት ዓመት ገደማ ከመጀመሪያ ባሏ ለማፋታት ቻልን፤›› ካለ በኋላ በኩራት ፊቱን ቀና አድርጎ ወደ ሚስቱ ሲመለከት የእርሷን ይሁንታ እንደፈለገ ቢያሳብቅበትም ንግግሩን ቀጠለ፡፡  ‹‹በእርግጥ ይህን የቤተሰብ ታሪክም ሆነ የእኔና የባልንጀሮቼን ውለታ እሷም አትዘነጋውም፤›› በማለት ዘርዘር አድርጎ የነበረውን ግፍና መከራ ተረከ፡፡

በረዥም ንግግሩ ምንም መሰላቸት እንዳልተፈጠረ በሚመስል ሁናቴ ጉሮሮውን በመቃኘት ድምፁን ለሌላ ገለጻ አስተካከለ፡፡ ቀጠለና እንዲህ አለ፣ ‹‹. . . የተከፈለው መስዋዕትነት እሷን ከቀድሞ ባሏ በማለያየት ብቻ የተወሰነ አልነበረም፡፡ ይልቁን ለእርሷ የሚሆን ዘለቄታዊነቱን ያረጋገጠ፣ ግልጽና ተጠያቂ የሆነ ባል ማፈላለግ ነበረብን፡፡ ምንም እንኳን በዚህ ሰዓት ከእናንተ መደበቅ የማልፈልገው ነገር ቢኖር ለእርሷ ያንን ያህል መስዋዕትነት ከባልንጀሮቼ ጋር ከፍዬ ከእኔ ሌላ የትኛውም ሰው እንዲያገባት አልፈልግም ነበር፡፡ ቢሆንም ግን ሌላ ሰው አያገባትም ብለን ብንናገር የከፈልነውን እውነተኛ መስዋዕትነት ጥያቄ ምልክት ውስጥ ስለሚያስገባው ሌላ አማራጭ መውሰድ ነበረብን፡፡ ይህም በዋናነት የባልነት መሥፈርቱን ትንሽ ውስብስብ ማድረግ፣ የባል ምርጫ ሒደቱን በበላይነት መምራትና ለተወሰነ ጊዜ እሷን የሚያስተዳድር ሞግዚት ባል መመረጥ የሚል ነበር፡፡ ከመሥፈርቱ መካከል ‹‹ፋሞክራሲ›› የሆነ ሰው መሆን አለበት የሚል ይገኝበታል፡፡ ‹‹ፋሞ›› ማለት ‹‹ፋሚሊ›› ሲሆን፤ ‹‹ክራሲ›› ማለት ደግሞ አስተዳደር ማለት ነው፡፡ በዚህም መሠረት እናንተም እንደምታስታውሱት እሷን ለማግባት በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጭ ያሉ ሰዎችና ድርጅቶች በእጮኝነት ብፌ ላይ ተመዝግበው ተደረደሩ፡፡ ሆኖም ግን ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት እነሱን የፈለግናቸው እንዲያገቧት ሳይሆን የቤተሰብ ሕጉ ሲረቀቅ እንዲገኙ ብቻ ነበር፡፡ እኔም ለዘለቄታው የተመኘኋትን ባለቤቴን እንዳገባት የሚያስችለኝን ሕጋዊ ማዕቀፍ ፋሞክራሲነቱን በጠበቀ ሁኔታ አመቻቸሁ፡፡ ከዚያም አገባኋት፡፡ በእጮኝነት የተመዘገቡትም ሆኑ ታዛቢዎቹ ቆመው አጨበጨቡ፣›› ብሎ እርፍ፡፡ 

የነበረውን ሒደት ሲናገር በተከናወኑት ፋሞክራሲያዊ ተግባራት ትንሽ እንደ መጀነን ቢልም ባለቤቱ ግን አንገቷን እንደ ደፋች ከመቀመጫዋ ትቁነጠነጥ ነበር፡፡ የመቁነጥነጧ ምክንያትም በዚህ ዓይነቱ የጋብቻ ሒደት ውስጥ እሷ ባል የመምረጥ መብቷ እንዳልተከበረላትና በአንፃሩ ግን ሚስት የመመረጥ መብታቸውን ያስከበሩት የዛሬው ‹‹ባሏ›› እና ‹‹እጮኛ›› ተብዮዎቹ ብቻ መሆናቸውን ማስታወሷ ሳይሆን አይቀርም፡፡ አጅሬ ባል ግን ንግግሩን ቀጠለ ‹‹ . . . ከዚህ ሁሉ ውጣ ውረድና ሐሜት በኋላ እኔ እንደ ባል እሷ እንደ ሚስት ሆነን ለመኖር በቃን፡፡ እኔም ለቤቴ ታማኝ ሆኜ፣ የቤቴም ማድጋ ከቀን ወደ ቀን እየሞላ፣ አስቤዛም ሳይጓደል ለመኖር ቻልን፡፡ በዚህ ትዳርም ብዙ የሚባሉ ትልልቅ ሀብቶችን አፈራን፡፡ ትዳሩን ከነበረበት የድህነት አደጋ ለመውጣት ሞከርን፡፡ የቤተሰቡን የትምህርትና የጤንነት ደረጃ በከፍተኛ ደረጃ ተሻሻለ፡፡ በቤተሰቡ መካከል የነበረውን የመንገድ ብልሽት ከመጠገን አልፈን ታይተው የማይታወቁ የቤተሰብ መጓጓዣ አውታሮችንና መስመሮችን ዘረጋን፡፡ አማራጭ የኃይል ምንጮችንም አጎለበትን፡፡ ከጎረቤት ጠላቶችም እየጠበቅኩ ትዳሬን አላስደፈርኩም፡፡ ባይሆን ከዚህ የሥራ ኃላፊነት ጫና የተነሳ ለባለቤቴ በቂ ጊዜ አልሰጣትም ነበር፡፡ በሚገባም አላወራትም ነበር፡፡ በሚጠበቅብኝም ደረጃ የእርሷን ሐሳብ፣ ጥያቄ፣ ምርጫም ሆነ ዝንባሌ  አልተረዳሁም፡፡ ምክንያቱም እኔ ከእርሷ የተሻለ አስባለሁ ስለምልና ኃላፊነቱም የእኔ ነው ብዬ ስለምወስድ ነበር፡፡ በዚህም ባለቤቴን ጎድቻታለሁ፣ በድያታለሁ፡፡ ባለቤቴ አሁን አልጋ ከለየች ሰነበተች፡፡ የድሮውንም ፍቅር ልትሰጠኝ አልቻለችም፡፡ ለወራትም ብሞክር ልቧ ሸፈተብኝ፡፡ ለዚህ ለተፈጠረው ችግር ነው ዛሬ በፊታችሁ ቆሜ ታሸማግሉኝ ዘንድ ወደ እናንተ የመጣሁት . . .››  በማለት ነበር አሳዛኝ የሆነውን ነገር ግን ለመጀመሪያ ጊዜ ያልሆነውን ዲስኩሩን የደመደመው፡፡

አማካሪዎቹም የእርሱን ንግግር በጥሞና ካደመጡ በኋላ የመናገር ዕድሉን ለሚስት ሰጡ፡፡ ሚስት ግን አንገቷን እንዳቀረቀረች ዝም አለች፡፡ ከዝምታዋም የተነሳ አማካሪዎቹ እጅግ ተጨነቁ፡፡ እንደ መንደርደሪያ ያገለግላትም ዘንድ የራሳቸውን መላ ምት ማለትም ትዳሯን ለመፍታት እንዲህ ሊያስጨክናት የሚያስችሉ ጉዳዮች ብለው የሚገምቱትን ዋና ዋና የትዳር ጠሮች እየዘረዘሩ በማግባባት ይጠይቋት ጀመር፡፡  ‹‹. . . ባለመናገርሽ ምክንያት ተጨነቅን፡፡ እንዲያው . . . ከሌላ ሴት ጋር ሲማግጥ አግኝተሽው ነው . . . ወይስ ደግሞ . . .›› ብለው ሳይጨርሱ የዘመናት ጉዳቶቿ በዓይነ ኅሊናዋ ድቅን አለባትና ስቅስቅ ብላ አለቀሰች፡፡ ከዚያም በብዙ እንባና ንዴት እየተንቀጠቀጠች እንዲህ አለች፡፡ ‹‹. . . እ እ እ እ እንዲያው እናንተን መድፈር ባይሆንብኝ . . . እኔ የዚህን ሰው ዓይኑን እንኳን ማየት አልፈልግም . . .›› ስትል፣ በሁኔታዋ የተደናገጡት አማካሪዎች እንዲህ አሉ  ‹‹. . . ቆይ ቆይ እስቲ ተረጋጊ፡፡ እንባሽንም እንዲህ በየሜዳው መዝራት ለእርሱም ቢሆን ለተወለዱት ልጆች አይበጅም፡፡ የሴት ልጅ እንባ በወንድ ላይ ጦስና እርግማን ነው የሚያመጣው . . .››  እያሉ ለማባበልና ለማረጋጋት ሞከሩ፡፡  ቀጠሉና፣  ‹‹. . . እስቲ የበደለሽን ዘርዝረሽ አስረጂን? ዋና ዋና ጥያቄዎችሽ ምንድን ናቸው . . .›› ቢሏት እርሷ ግን ዓይኗ በእንባ እንደተሞላ እንዲህ አለች፡፡ ‹‹. . . በአጠቃላይ ዓይኑን ማየት አልፈልግም . . . ኧ ኧ ኧ ኧ ኧ  በጭራሽ ዓይኑን ማየት አልፈልግም፡፡ እንዲያው ስንቱን ስንቱን ኧረ የቱን አንስቼ ምንስ ብዬ ልናገር? ብቻ ከዚህ በኋላ ዓይኑን ማየት አልፈልግም፤›› ብላቸው እርፍ፡፡

እነርሱም እርስ በርስ እንዲህ ተባባሉ፡፡ ‹‹እንዲያው በትዳር አማካሪነት ብዙ ዓመት ስናገለግል የተረዳነው ነጥብ ቢኖር ይህ ነው፡፡ ጥቃቅን የሚባሉ ችግሮች ሲያድጉና ሲደማመሩ መጨረሻ ላይ ትልቅ ችግር የሚሆኑት፣ ጥያቄንና ችግርን  እንኳን በቅጥ ማስረዳት ከባድ መሆኑን ነው፡፡ . . . ይልቅ አሁን አንች እየሆንሽ እንዳለሽው ጥያቄዎችሽ ድቡልቡል በመሆናቸው ሳቢያ አፍና አፍንጫቸው የማይለይ ቅርፅ አልባ ይሆናሉ፡፡ . . . እንዲያውም እዚህ ላይ ትልቅ ችግር የሚሆነው ችግሩን መተንተንና በቅደም ተከተል ማስረዳት ነው፡፡ ከዚያም ጥያቄዎቹ ከጥያቄነት ዘለው ጥላቻ ይሆናሉ፡፡  በአንድ ትዳር ውስጥ ችግሩ እንዲህ ዓይነት ደረጃ ከደረሰ ትዳሩ ብዙውን ጊዜ የሚቋጨው በመለያየት ነው፡፡ ፍቺው ካላማረም አላስፈላጊ ዋጋን ሊያስከፍል የሚችልበት አጋጣሚም ብዙ አለ፡፡ ስለዚህ በእንዲህ ዓይነቱ ደረጃ ሆነው ወደ እኛ ለሚመጡ የትዳር ጓደኞች የምናካፍላቸው ምክር ቢኖር ኃላፊነት በሚሰማው መንገድ ፍቺውን እንዲያሳምሩ ነው፡፡ የእኛም ኃላፊነት የሚሆነው ከሀብት ጅምሮ እስከ ሌሎች ጉዳዪች ድረስ ሁለቱም ወገኖች የማይጎዱበትን ሁኔታ ማመቻቸትና ከፍቺም በኋላ ሊኖራቸው ስለሚገባ መልካም ግንኙነት መምከር ይሆናል . . .›› ካሉ በኋላ ሻይ ቡና ለማለት የዕረፍት ጊዜ ወሰዱ፡፡ ከዕረፍት መልስ ግን ሁሉም በአንድ ድምፅ አንድ የመጨረሻ አማራጭ አቀረቡ፡፡ ይህም በትዳራቸው የተከሰተውን አደጋ ለማስወገድና መሠረታዊ ለውጥ ለማምጣት ባልና ሚስቱ ብቻቸውን ሆነው በጥልቀት እንዲነጋገሩ የሚል ሐሳብ፡፡ ባልም በተሰጠው የመጨረሻ ዕድል ደስተኛ በመሆን በኃላፊነት እንደሚሠራና ከቤተሰቡ ጋር ተነጋግሮ እውነተኛ ለውጥን እንደሚያመጣ ቃል ገብቶ፣ በዚህ ሒደትም የሚስቱን ዕርዳታ እንደሚፈልግ አስታውቆ በብሩህ ተስፋ ምሳ ተገባበዙ፡፡

የዚህን ጽሑፍ ተከታይ ክፍል በተለይም ችግሮችን ወደ መልካም አጋጣሚነት ስለመቀየር የሚለውን በሚቀጥለው ሳምንት እንዲያነቡ በአክብሮት እጋብዛለሁ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dejene_assefa@yahoo.com. ማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

በአዳማ ከተማ የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ የ‹‹ጥልቅ ተሃድሶው›› ነፀብራቅ ቢሆን?

$
0
0

በመኮንን ሻውል ወልደ ጊዮርጊስ

ኅዳር 11 ቀን 2009 ዓ.ም. የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ለማ መገርሳ ከአዳማ ከተማ ሕዝብ ጋር በገልማ አባ ገዳ አዳራሽ ተገኝተው ተወያይተው ነበር፡፡ ውይይቱን በከፈቱበት ወቅትም በርዕቱ አንደበታቸው ለከተማ ነዋሪው ተወካዮች ይፋ እንዳደረጉት፣ የአዳማ ከተማን ዘርፈ ብዙ ችግርና በነዋሪዎች ላይ እየደረሰ ያለውን አስተዳደራዊ በደል ለማስወገድ ቆርጠው መነሳታቸውን ገልጸዋል፡፡ እንዲሁም አዳማ በተለምዶ እንደምትባለው ‹የስምጥ ሸለቆ እንቁዋ ከተማ›› ሆና እንድትገኝ ለማድረግ ታላቅ ሕዝባዊ ንቅናቄ ወይም አብዮት እንደሚያስፈልግ አስገንዘበዋል፡፡ ለዚህም ስኬት ወይም አብዮቱን ለድል ለማብቃት፣ የክልሉ መንግሥት ለከተማው መስተዳድር ያልተቋረጠ ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግም ዋስትና ሰጥተዋል፡፡

ይኼንን ሕዝብ አሳታፊ ታላቅ የለውጥ አብዮት የሚመሩለት ብቃት ያላቸው የክልሉ ዜጎች እንዲሆኑ በማመን፣ በዕውቀትና በችሎታቸው ብቻ ሳይሆን በመልካም ሥነ ምግባራቸው የተመሰከረላቸውን በጥንቃቄ መርጦ መሾሙን ለሕዝብ አሳውቋል፡፡

የክልሉ መንግሥት የአዳማ ከተማን የአሁን ገጽታ ለመለወጥና አዳማን እውነተኛ ‹‹እንቁ ከተማ›› ለማስባል የሚያስችል አቅም አላቸው ብሎ ያመነባቸውን ከንቲባ፣ ምክትል ከንቲባ፣ ሥራ አስኪያጅ፣ የመሬት አስተዳደርና የድርጀት ጉዳይ ኃላፊዎች ሾሟል፡፡

የአዳማ ከተማ ሕዝብም ምናልባትም በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ የከተማ ከንቲባ የሆኑትን ሴትና እናት በታላቅ ደስታ በእልልታና በጭብጨባ ሹመታቸውን አፅድቆላቸዋል፡፡ በሙያቸው ዳኛ የሆኑትን ወ/ሮ አዳነች አቤቤን እንኳን መጡልን፣ የልማታችን አብዮት መሪ እንኳንም እርሰዎ ሆኑ፣ ስለሕግ ያውቃሉና በማለት ነው ከልቡ ደስታውን የገለጸው፡፡

ነዋሪው የአዳማን ሁለንተናዊ ወይም ‹‹ከ . . . እስከ›› የማይባለውን ችግር ጠንቅቆ ያውቃልና ሕግ አዋቂ መሪ ሲሆንለት መደሰቱ አይገርምም፡፡ በተዋረድ ያሉ ባለሥልጣናት ስለሕግ እንዲያውቁና አዳማን ‹እንቁ› ለማድረግ እንዲጥሩ ከንቲባዋ ያደርጓቸዋል ብሎ በማመኑ ደስታውን ቢገልጽም፣ ከቀድሞዎቹ ከንቲባዎችና ካቢኔዎቻቸው ያልተገባ አካሄድ በመነሳት ሥጋቱንም ገልጿል፡፡ እነዚህ አዳዲስ የሕዝብ አገልጋዮችም የክልሉ ፕሬዚዳንት እንዳሉት ‹‹ሐሺሽ በመቅመስ ከአብዮቱ መስመር ውጪ ቢነጉዱና አብዮቱን ቢቀለብሱትስ? . . . በአዳማ ከተማ ውስጥ ያለው የደላላና የአቀባባይ እንዲሁም በአቋራጭ ለመክበር ፈላጊ የአብዮቱ እንቅፋት ሊሆን አይችልም ወይ? . . . ›› በማለት ጥያቄ አንስቷል፡፡ ጸሐፊው ሐሳቡን ጠቅለል አድርጎ እንዳቀረበው፡፡

ባለ ፈርጀ ብዙ ችግር በዕድሜዋ ልክ እንዳትበለፅግ ያደረጋትን ይህቺን ለእንቁነት የታጨች ከተማ ዛሬ በቁመናዋ ላይ የሚታየውን አስከፊ ገጽታ (በመሀል ከተማዋ ያለው ቆሻሻ፣ በየአርጅኑ የተከማቸው ግሳንግስ፣ የከተማዋ ትልቅ አስከፊ ዕድፍ እንደሆነ ይታወቃል) እንዲሁም የነዋሪዎችዋን የመልካም አስተዳደና የፍትሕ ዕጦት (ፍትሕ በገንዘብና በሥልጣን ጉልበት ሳትሸራረፍና ሳታጋድል ለዜጎች በእኩልነት ታገለግል ዘንድ ከላይ ጀምሮ በተዋረድ በሰንሰለቱ ያሉ ባለሥልጣን መንግሥት የሾመው ለአገልጋይነት መሆኑን በቅጡ ተገንዝቦ፣ የተሰጠውን የማገልገል ኃላፊነት በወጉ እንዲጠቀምበትና እውነተኛ እንደሁም ታማኝ አገልጋይነቱን በተግባር እንዲያሳይ ‹‹የተጠያቂነት አሠራር›› መንግሥት ተግባራዊ እንዲሆን ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ የተጠያቂነትን አሠራር ለመተግበርም ራሱን የቻለ የክትትልና ምዘና ተቋም መመሥረት የሚያስፈልግ ይመስለኛል)፡፡ በኦሮሚያ ክልል መንግሥት ጥብቅ የሆነ የበላይ ቁጥጥርና ድጋፍ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት ይቻላል፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመርያዋ የሴት ከንቲባ በመባል ስማቸው በታሪክ ሊጻፍላቸው የቻለው ወ/ሮ አዳነች አቤቤም የሕግ ባለሙያ እንደመሆናቸው መጠን፣ በአዳማ ነዋሪዎች ላይ የተስተዋለውን አስተዳደራዊና ፍትሐዊ ችግር፣ እንዲሁም በከተማ ፅዳትና አረንጓዴ ልማት አሠራር ውስጥ በዕቅድ፣ በሕግና በመመሪያ ያልተደገፈውን አካሄድ ወደፊት ከካቢኔዎቻቸው ጋር በባለሙያ በመታገዝ ስለሚያወጡት ዕቅድ አካሄዳቸው በግልጽ አሳይቶናል፡፡ የነገ ሰው ይበለንና፡፡

ይሁንና ለወደፊት ሥራቸው በሚያወጡት ዕቅድ ላይ መካተት ይኖርባቸዋል የምለውን እኔም እንደ ከተማዋ ነዋሪነቴ መጠቆም እንደሚኖርብኝ በመገንዘብ፣ የአዳማ ቁልፍ ችግሮችን እንደሚከተለው አቀርባለሁ፡፡ ዋነኛዋ የአዳማ ከተማ ቁልፍ ችግር የሆነው ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት›› ነው፡፡ በሁሉም ሴክተር መሥሪያ ቤቶች ከቀበሌ ጀምሮ ወደ ላይ ባሉት አገልግሎት ሰጪዎች የሚስተዋለውና ለከተማዋ ዕድገት ማነቆ የሆነው ሙስናዊ አሠራር ወይም ኪራይ ሰብሳቢነት ወይም ሕግና ሥርዓት ለማስከበር ሳይሆን ‹‹ኪስን ለማስከበር›› መሯሯጥ ነው፡፡ ከኪራይ ሰብሳቢነት ጎን ለጎን ተያይዘው የመልካም አስተዳደርና የፍትሕ ዕጦቶች በኃላኝነትና በሦስተኛነት ቁልፍ ችግር ናቸው፡፡  

በአራተኛነት የማስቀምጠው ይኼን ችግር ለመፍታት የፌዴራል መንግሥትንም እገዛ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ የጎዳና ተዳዳሪነትና ለምኖ አዳሪነት የከተማዋን ገጽታ እያበላሸ ያለ ቁልፍ ችግር ነው፡፡ እርግጥ ነው የጎዳና ተዳዳሪዎችና የለምኖ አደሮች ችግር የመላው የአዳማ ነዋሪም ችግር ነው፡፡ የእኔም፣ የአንተም፣ የአንቺም፣ የሁላችንም ችግር ነው፡፡ ችግሩ ያገባናል፣ ይመለከተናል፣ በወጣን በገባን ቁጥር የምናስተውለው፣ በየቀኑ እያየንም ህሊናችንም የሚቆስልበት ሕመማችን ነው፡፡ ስለሆነም እኛ አያገባንም፣ አይመለከተንም ማለት አንችልም፡፡ ጎዳና ላይ ያሉት ዜጎች አባቶቻችን፣ እናቶቻችን፣ ወንድምና እህቶቻችን ናቸው፡፡ ‹መወለድ ቋንቋ ነው› እንዲሉ፡፡

አምስተኛውና የመጨረሻ ያልኩት ቁልፍ ችግር ደግሞ ‹‹ሕገወጥ የጎዳናና የጥጋጥግ ንግድ ነው››፡፡ ይኼ ለዘመናት የቆየና በጎዳና ንግድና በየጥጋጥጉ ያላንዳች የንግድ ፈቃድ ተሠማርተው ያሉትን ዜጎች የሚመለከት ነውና በጥንቃቄ ሊታይ ይገባዋል፡፡

ይኼንን ሕገወጥ ንግድ ሥርዓት ለማስያዝ ከተለፈገ ለእነዚህ በሺሕ የሚቆጠሩ ዜጎች (በተለይም በቀበሌ 08) የሚገኝ ሥፍራ ሊመቻችላቸው ይገባል፡፡ ለምን? ቢሉ ዜጎች ሕገወጥ ሥራን እንደ ሕጋዊነት ቆጥረው መተላለፊያ መንገዶችን ሞልተው ለዘመናት ሲነግዱ፣ እየነገዱም ቤተሰባቸውን ሲመግቡ፣ ሲያስተምሩና ለቁም ነገር ሲያበቁ ኖረዋልና ዛሬ ደርሰን ዞር በሉ ወደ ምትሄዱበት ሂዱ የማለት መብት የለንምና፡፡

ስለሆነም ይኼ ጉዳይ በጥልቀት ተመርምሮ የመገበያያ ሥፍራ ለእነዚህ የመንገድ ዳር ነጋዴዎች ሊዘጋጅላቸውና ሕጋዊ ሆነው እንዲሠሩ በማድረግ፣ ራሳቸውንና አገርን ጠቃሚዎች ማድረግ ይቻላል ብዬ አስባለሁ፡፡

በአዳማ ከተማ ተጨባጭ ሁለንተናዊ ለውጥ ለማምጣት ከላይ የዘረዘርኳቸውን፣ ለዘመናት የቆዩና እያደጉ የመጡ ቁልፍ ችግሮች መፍታት ያስፈልጋል፡፡ የክልሉ ፕሬዚዳንት እንዳሉትም ‹‹አብዮት›› ያስፈለገው ለዚህ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡

የአዳማ ከተማ ሕዝብ በክልሉ ፕሬዚዳንት የተበሰረውን (የአዳማ ከተማን ቢያንስ ከሐዋሳና ከባህር ዳር ጋር አቻ ለማድረግ) አብዮታዊ እንቅስቃሴ በእልልታ ተቀብሏታል፡፡ አብዮታዊ እንቅስቀሴውን በእልልታ የተቀበለውም አብዮቱን የሚያካሂዱ አዳዲስ የካቢኔ አባላት ለከተማው በመሾማቸው የነገን በተስፋ በማየት ነው፡፡

ዛሬና በአሁኗ ሰዓት የሥልጣን ኳሱ በወ/ሮ አዳነች አቤቤ እግር ሥር ናት፡፡ ይህቺን ኳስ ከካቢኔዎቻቸው ጋር በመሆን ሕዝቡን በማስተባበር ግብ ሊያስቆጥሩ የሚችሉ ከሆነ፣ እልልታውና ጭብጨባው ይቀጥላል፡፡

እርግጥ ነው መሪ እንደ መሆናቸው መጠን ኳሷ በእግራቸው ሥር መገኘቷ ግድ ቢሆንም፣ እንዴት በኳሷ ተጫውቶ ግብ እንደሚያስቆጥር ለሕዝቡ የሚያስረዳ፣ የሚያስተምር፣ የሚያሠለጥን ሰፊ ዕቅድ፣ የአፈጻጸም ደንብና መመርያ በቅርቡ አዘጋጅተው ሕዝብን እንደሚያወያዩ አምናለሁ፡፡

ዛሬና አሁን በምንገኝበት ተጨባጭ ሁኔታ የትኛውም ባለሥልጣን ሕዝብን ሳያሳትፍ ኳሷ በእግሬ ሥር ናት ብሎ እንዳሻው መጠለዝ እንደማይችል የተገነዘብንበት ወቅትና ሁኔታ ላይ እንገኛለን፡፡ መንግሥት ሥልጣን በእጄ ነው ብሎ እንዳሻው ለመሆን የሚሞክር ማንኛውንም ባለሥልጣን የሚታገስበት ልብ እንደሌለውና ጨከን ያለ ዕርምጃ እንደሚወስድ አሳስቧል፡፡ ሕዝብም ኳሷ በእግሬ ሥር ናት ብሎ እንዳሻው የሚጠልዝ፣ በሕግ አግባብ ይጠየቅልኝ ማለቱን ዛሬም ሆነ ነገ እንደማያቆም አሳስቧል፡፡ የሁለቱም ወገን ማሳሰቢያዎች ለአገር ልማትና ብልፅግና እንጂ ለሌላ አይደለም፡፡ በአዳማ ከተማ የተጀመረው ትልቅ ትኩረት የተደረገበት ወደ ልማትና ዕድገት የሚወስድ እንቅስቀሴም ፋይዳ ከዚህ አንፃር የሚታይ ነው፡፡ እንቅስቃሴውም ‹‹የጥልቅ ተሃድሶው ነፀብራቅ›› ይሆናል ተብሎ ይታሰባል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው the999invisible@gmail.com. ማግኘት ይቻላል፡፡     

 

 

 

 

 

 

 

Standard (Image)

ኤርትራና የዓረብ አገሮች ቁርኝት

$
0
0

አፄ ምኒልክ የጣሊያንን ወታደሮች መረብ ምላሽ አድርሰው ወደ መናገሻ ከተማቸው  ሲመለሱ ጀምሮ ከኢትዮጵያ ተገንጥላ የቀረች አገር እየተባለች በታሪክ የሚነገርላት ኤርትራ፣ ከኢትዮጵያ ጋር ዓይንና ናጫ ሆና ዓመታትን ተሻግራለች፡፡ የኤርትራ ሕዝብ ነፃ አውጪ ግንባር (Eritrean People Liberation Front) ከሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ግንባር (Tigray People Liberation Front) ጋር በመሆን የአምባገነኑንና በምሥራቅ አፍሪካ ግዙፍ ኃይል እየተባለ ይጠራ የነበረውን የደርግ መንግሥት ካስወገዱ በኋላ ሁለቱም አገሮች የየራሳቸውን የአስተዳደር ሥርዓትና የድንበር ወሰን በአግባቡ ሳያበጁ መኖር ቢጀምሩም፣ ወደ ጦርነት ሲገቡ ግን ጊዜ አልወሰደባቸውም ነበር፡፡ በሁለቱ አገሮች መካከል በተፈጠረው የድንበር ይገባኛል ጥያቄ ከሁለቱም ወገኖች በብዙ ሺሕ የሚቆጠር ሰው ከመሞቱ በላይ፣ በብዙ ዓመት ሊተካ የማይችል ኢኮኖሚም ወድሟል፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ጀምሮ ጦርነትም ሰላምም በሌለበት (No war No Peace) ሁኔታ ውስጥ ይገኛሉ፡፡

በዚህም የተነሳ የሁለቱ አገሮች ኢኮኖሚ ሰፊ ልዩነት እየታየበት መምጣቱን አንዳንድ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ሲናገሩ ይደመጣል፡፡ ባለሙያዎቹ ኢትዮጵያንና ኤርትራን በዛሬዎቹ ሊቢያና ቻይና ይወክሏቸዋል፡፡ ኤርትራ የሊቢያን ውክልና ስትወስድ ኢትዮጵያ ደግሞ የሩቅ ምሥራቋን ቻይና ትወስዳለች፡፡ በሌላ አገላለጽ ሲገልጿቸው ደግሞ በአይብና በጠመኔ (ቾክ) ሲወክሏቸው ይታያል፡፡ ኢትዮጵያ የአይብን ኤርትራ ደግሞ የጠመኔን ውክልና ይወስዳሉ፡፡ ይህንንም ባለሙያዎች ሲያስቀምጡት ኤርትራ የተስፋ ዳቦ ከመብላት ባሻገር፣ ጠብ የሚል ተጨባጭ ለውጥ የማይታይባት አገር መሆኗን በማብራራት፡፡

የዛሬዋ የኤርትራ ዜጐች የበረሃና የውቅያኖስ ሰለባ እየሆኑ ነው፡፡ የቀደመ ታሪኳ እንደሚዘክረው በእነ ግብፅና ሳዑዲ ዓረቢያ ትከሻ ላይ ተንጠልጥላ ዛሬ ላይ የደረሰችው ኤርትራ፣ በደቡብ ምሥራቅ በኩል በቀይ ባህር የምትዋሰን ትንሽ አገር ነች፡፡ እንደ ተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የምጣኔ ሀብትና ማኅበራዊ ጉዳዮች ሪፖርት፣ በአሁኑ ወቅት ኤርትራ አጠቃላይ የሕዝቧ ቁጥር 5,390,379 ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 49.3 በመቶ የሚሆነው ወንድ፣ 50.3 በመቶ ደግሞ ሴት ነው፡፡ ይህ አኃዛዊ መረጃ ከዓለም አቀፍ የፆታ ንጽጽር ጋር ሲወዳደር ከደረጃ በታች መሆኑን ይገልጻል፡፡ ዓለም አቀፉ የፆታ ንፅፅር 1,016 ወንዶች ለ1,000 ሴቶች ነው የሚለውና፡፡ በመሆኑም የኤርትራ ዜጐች የፆታ ንፅፅር ከዓለም አቀፉ የፆታ ንፅፅር ጋር ሲወዳደር ከደረጃ በታች የሆነበትን ምክንያት አንዳንድ ባለሙያዎች ሲገልጹ፣ ወንዶች ከሴቶች የበለጠ ለስደትና ለጦርነት ተጋላጭ በመሆናቸው እንደሆነ ያብራራሉ፡፡ አጠቃላይ የአገሪቱ የቆዳ ስፋትም 117.6 ቢሊዮን ስኩየር ኪሎ ሜትር ነው፡፡ ኤርትራ በአሁኑ ወቅት በስድስት ክልሎች ተከፋፍላ ትገኛለች፡፡

በአሜሪካ የኮንግረስ አባል፣ የውጭ ጉዳይ ኮሚቴ ምክትል ጸሐፊና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የሆኑት ክርስቶፎር ኤች ስሚዝ (ከኒውጀርሲ የሪፐብሊካን አባል) ‹‹ኤርትራ የተገለለችው የሰሜን ምሥራቋ አፍሪካዊት አገር›› በሚል ርዕስ እ.ኤ.አ. መስከረም 2016 ‹‹አትላንቲክ ካውንስል›› ለተሰኘው ድርጅት ባቀረቡት ሪፖርት፣ ‹‹የኤርትራ ሕዝብ እ.ኤ.አ. በ1991 ነፃነቱን ሲያውጅ ተስፋ የሰነቀና ለአገሪቱ ብርሃን የናፈቀ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ጉዳዩ የተገላቢጦሽ ሆኖ አገሪቱን በአሁኑ ወቅት የኋሊት እያስኬዳት ቢሆንም ቅሉ. . .›› ሲሉ ያብራራሉ፡፡ እንደ ባለሙያው ገለጻ ኤርትራውያን በአሁኑ ወቅት አካላቸው ከቀይ ባህር ማዶ ልባቸው ደግሞ ወደ አውሮፓና አሜሪካ ተሰዶ ያለ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆን በየወሩ ከ5,000 በላይ ኤርትራውያን ስደተኞች በቀይ ባህር፣ በሱዳን፣ በደቡብ ሱዳን፣ በኬንያ፣ በሶማሊያና በኢትዮጵያ አድርገው ከአገራቸው የሚሰደዱ መሆናቸውን በማብራራት፡፡

በዓለም አቀፍ የስደተኛ ጉዳዮች ተጠሪ ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት ጃይ ጀሪማን በሌላ በኩል፣ በየዓመቱ ታኅሳስ 18 ቀን የሚከበረውን ዓለም አቀፍ የስደተኞች ቀን ምክንያት በማድረግ ከአልጄዚራ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር በነበራቸው ቆይታ እ.ኤ.አ. 2016 በዓለም ታሪክ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የስደተኞች ቁጥር የተመዘገበበትና ዜጐችም ለከፉ ጉዳት የተዳረጉበት ወቅት እንደነበር አብራርተዋል፡፡ ኤርትራውያን ስደተኞችን ከሶሪያ፣ ከሊቢያ፣ ከየመንና ከአፍጋኒስታን ስደተኞች ጋር በማነፃፀር፡፡

ኤርትራ በአሁኑ ወቅት የዓለም ዓይንና ጆሮ ሆናለች፡፡ በአንድ በኩል መቆሚያ የሌለው የዜጎች ስደት፣ በሌላ በኩል አገሪቱን በአሁኑ ወቅት እያስተዳደራት ያለው የመንግሥት ሥርዓት አምባገነንነትና ከአውሮፓ ብሎም ከአሜሪካ ጋር ያለው ግንኙነት እዚህ ግባ የሚባል ካለመሆኑ ባሻገር በተቃራኒው ከዓረብ አገሮች  ጋር ያላትን ወዳጅነት በመጥቀስ፡፡

የዛሬዋ አስመራ አልሸባብን ከመደገፍ በተጨማሪ በኢትዮጵያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሸባሪ ተብለው የተፈረጁ እንደ ኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)፣ ግንቦት ሰባትና ሌሎች ቡድኖችን ከመደገፍና ከማስታጠቅ ባሻገር የአሸባሪ ቡድኖች መናኸሪያ ሆናለች ሲሉ አንዳንድ ባለሙያዎችና ሚዲያዎች ይናገራሉ፡፡ በግብፅና በሳዑዲ ዓረቢያ ድጋፍ አንገቷን ቀና አድርጋ የምትሄደው የዛሬዋ የኢሳያስ አፈወርቂ ኤርትራ በዓለም ፊት ውግዘትንና መገለልን እያስተናገደች ነው፡፡ በተደጋጋሚ ጊዜም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የማዕቀብ ሰለባ ሆናለች፡፡

ኤርትራ ዛሬ አፏን ሞልታና ደረቷን ነፍታ እንደ አገር መቀጠል የቻለችው በዓረብ አገሮች የገንዘብና የወታደራዊ ሎጅስቲክስ ድጋፍ ነው፡፡ በተለይ ከዓረብ አገሮች ጋር ጥሩ ወዳጅነት ለመመሥረት ያስቻላት ጉዳይም የባህር በሯ ነው፡፡ ከስዊዝ ቦይ ጋር የሚገናኘው ይህ የቀይ ባህር ዳርቻ ኤርትራን የዓረብ አገሮች ምርጫ አድርጓታል፡፡ ይህ ታሪክ የሚወድቀው ደግሞ ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ መነሻ በመሆኗና ይኼንን ወንዝም እገድባለሁ የምትል ከሆነ የታችኛው የተፋሰስ አገሮችን በዋናነት ግብፅን ስለሚነካ፣ በዓባይ ወንዝ ላይ መተማመኛ ድምፅ ለማግኘት ብሎም ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ስለሚፈልጉ ኤርትራን ወዳጅ አድርገው መርጠዋታል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ሲናገሩ እንደሚደመጠው፣ ኤርትራ ከግብፅና ከሳዑዲ ዓረቢያ ጋር ያላትን ቀጣናዊና አኅጉራዊ ሚና ለማዳከም ብሎም በዓለም ፊት ደካማ የሆነ አቅም እንዲኖራት ለማስቻል ነው ይላሉ፡፡ ከሳምንታት በፊት የየመኑ ‹‹አልሃዳዝ›› የተሰኘው የዜና አገልግሎት ባሰራጨው መረጃ ‹‹ግብፅና ኤርትራ ኢትዮጵያን ለመውጋት በቀይ ባህር በኩል ተጠባባቂ ኃይል ለማሰማራት ተስማሙ›› የሚል ዜና አስነብቧል፡፡ይህ ዜና የተፈበረከ የሐሰት ኘሮፓጋንዳ ነው እያሉ ብዙ ሚዲያዎች ቢያጣጥሉትም፣ ኢትዮጵያ ግን ይህንን ጉዳዩ በአጽንኦት መከታተል እንዳለባት የሚናገሩ ብዙ ናቸው፡፡  

ሳዑዲ ዓረቢያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ በየመን ሁቲ አማፂያን ላይ በሚያደርጉት ዘመቻ ኤርትራ ከ2,000 በላይ ወታደሮችን ወደ ግንባሩ ልካለች በማለት የተለያዩ ድርጅቶች ያስረዳሉ፡፡ ኤርትራ ወታደሮቿን ወደ የመን ከመላኳ ባሻገር ለአገሪቱ የአየርና የባህር ክልሏን ፈቅዳለች ሲሉም ያክላሉ፡፡ እዚህ ላይ ኤርትራ በየመን በፀረ ሁቲ አማፂያን ዘመቻ ላይ ‹‹የዓረብ ኅብረት›› (Arab Coalition) እየተባለ የሚጠራውን ጥምረት በመደገፍ ለምን ተሳታፊ ሆነች? የአየርና የባህር ክልሏንስ ለምን ፈቀደች? የሚል ጥያቄ ብናነሳ መልሱ ሊሆን የሚችለው ኤርትራ በተደጋጋሚ ጊዜ ከአውሮፓም ሆነ ከአሜሪካ ጋር ይህ ነው የሚባል የንግድም ሆነ የኢንቨስትመንት ግንኙነት ስለሌላት ነው፡፡ ይህንን ጉዳይ ማካካስና ወታደራዊም ሆነ ሌሎች ድጋፎችን ማግኘት የምትችለው ከእነዚህ አገሮች እንደሆነ በመገንዘብ ነው (ታሪካዊ ግንኙነታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ)፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ታሪካዊ ጠላቴ ነች ብላ ከምትፈርጃት ኢትዮጵያ በሁሉም ነገር ልቆ ለመገኘት እንደሆነ ማሰብ ይቻላል፡፡ ከእነዚህ አገሮች ጋር ባላት ጥብቅ ግንኙነት የወታደራዊ ሎጅስቲክስ አቅርቦት፣ ሥልጠናና ሌሎች የገንዘብ ድጋፎችን ስታገኝ ኖራለች (አሁንም እያገኘች ነው)፡፡ ይህንን ድጋፍ በማግኘት የተጠናከረ መከላከያ ኃይል በመገንባት አካባቢያዊና ቀጣናዊ አቅሟን ከፍ ለማድረግ እንደሆነ ግልጽ ጉዳይ ነው፡፡

‹‹አናዱሉ›› የተሰኘው የዜና አገልግሎት ከኤርትራ ታማኝ ዲፕሎማቶች አገኘሁት ብሎ ባሰራጨው መረጃ መሠረት፣ የኤርትራ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በተደጋጋሚ ጊዜ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ በማቅናት ከንጉሥ ሳልማን ጋር መክረዋል፡፡

‹‹አህራም›› ኦንላይን የተሰኘው የግብፅ የመረጃ መረብ ደግሞ ከሦስት ሳምንታት በፊት ባሰፈረው መረጃ፣ ‹‹የኤርትራ ፕሬዚዳንት ካይሮ ገቡ›› ሲል አስነብቧል፡፡ መረጃው አክሎም ፕሬዝዳንቱ ካይሮ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባል የሆኑት ሸሪፍ እስሜል ተቀብለዋቸዋል፡፡ በቆይታቸውም ከግብፅ አቻቸው ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ጋር የሚመክሩ ሲሆን፣ በዋናነት በሁለቱ አገሮች መካከል ስለሚኖረው ትብብር በተለይም በእርሻና በዓሳ ሀብት ልማት ዙሪያ ተባብሮ ለመሥራት ስምምነት ላይ እንደሚደርሱ ይጠበቃል ሲል ዘግቧል፡፡ 

ይህንን የፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የግብፅ ጉብኝት ዓላማ በተመለከተ  የተለያዩ ሚዲዎች የዘገቡት ሲሆን፣ በዘገባቸውም የተለያየ ፈር ሲያስይዙት ተስተውሏል፡፡ የተወሰኑት ሚዲያዎች የፕሬዚዳንቱ የካይሮ ጉብኝት ዋና ዓላማ ሁለቱ አገሮች በቀይ ባህር በኩል ስለሚያቋቁሙት ኮማንድ ፖስት ለመምከር ነው ሲሉ፣ የተወሰኑት ደግሞ በሶሪያ ያለውን ቀውስ ለመፍታት ያካሄዱት ግንኙነት እንደሆነ ያብራራሉ፡፡

ያም ሆነ ይህ ሁለቱ አገሮች በአሁኑ ወቅት እጅና ጓንት ናቸው፡፡ በሁለቱ አገሮች ውስጥ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያን መንግሥት የሚቃወሙ ቡድኖች ይኖራሉ፡፡ ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ጊዜ እንደተባለው እነዚህ አገሮች ለእነዚህ ቡድኖች መሸሸጊያ ከመሆን አልፈው፣ አስፈላጊውን ወታደራዊ ሎጅስቲክስ በማሟላት ኪሳቸው የፈረጠመ እንዲሆን በገንዘብ እየረዷቸው ነው፡፡ የእነዚህ ቡድኖች በገንዘብ መፈርጠም ደግሞ  ለነገዋ ኢትዮጵያ የሚፈጥረውን ሥጋት ከወዲሁ መገመት ይቻላል፡፡

በሌላ በኩል ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከግማሽ በላይ እያደረሰችው ያለውን ታላቁ የህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ተከትሎ ለግብፆች የሞት ሽረት ጉዳይ እንደሆነ የሚረዱ ወገኖች እስካሉ ድረስ፣ ግብፅና ኤርትራ ወዳጅነታቸው ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑ አይቀርም፡፡ እንዳተባለውም በቀጣናው ኮማንድ ፖስት የማያቋቁሙበት ሁኔታ አይኖርም ብሎ አለመገመት ሞኝነት ነው፡፡ ስለሆነም ኢትዮጵያ አሁን ያለችበትን ውስጣዊ ችግር በቶሎ ፈትታ ሁሉም ዜጋ በአንድነት ለአገሩ የሚቆምበትን ሁኔታ ማመቻቸት አለባት፡፡

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የህዳሴውን ግድብ የመሠረት ድንጋይ ካስቀመጡ በኋላ ዓባይን ለመገንባት ኅብረተሰቡ ያሳየውን መነሳሳትና ቁርጠኝነት ቀጣይነት እንዲኖረው ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ከልጅ እስከ አዋቂ፣ ከሊቅ እስከ ደቂቅ አሻራውን ያሰረፈበት የህዳሴው ግድብ በዓይነ ቁራኛ ለሚያዩት አገሮችም ሰለባ መሆን የለበትም፡፡ ‹የአገሩን ሰርዶ በአገሩ በሬ› እንደሚባለው የአገሬ ሰው የውስጣችንን ችግር በራሳችን ፈትተን፣ ኤርትራ ከዓረብ አገሮች ጋር ያላትን ቁርኝት በተገቢው ሁኔታ ማጤን ያስፈልጋል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው zemenutenagn09@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

 

 

 

Standard (Image)

ሕዝቡ እንዳያዝን መሬቱ እንዳይባክን

$
0
0

በሳሙኤል ረጋሳ

ጊዜ እየጨመረ በሄደ ቁጥር የሕዝብ አቋም እሱ ራሱ እንደሚፈጽመው ጉዳይ ወይም በሌሎች እንደሚፈፀምለት ጥያቄ መጠን የእርካታ ወይም የመከፋት ስሜት ግልጽ እየሆነ ይሄዳል፡፡ በአብዛኛው ሕዝባዊ ፍላጎት የሚረካው መንግሥት ያሉትን ችግሮች አውቆ መፍትሔያቸውን በቃል ሳይሆን በተግባር ሲያሳይ ነው፡፡

ከሰሞኑ ሲጠበቅ የነበረው የአዲስ አበባ ዙሪያ አርሶ አደሮች የመፈናቀያ ካሳ ጉዳይ ፍንጭ እየታየ ነው፡፡ በመሠረቱ ለአርሶ አደሮች የሚከፈለው ገንዘብ ካሳ ነው? ወይስ መንግሥት ብቸኛ መተዳደሪያ ይዞታቸውን በተለያየ ምክንያት የወሰደባቸው አርሶ አደሮች ሌላ የሚያኖር ገቢም ሆነ ጥሪት ስለሌላቸው ሥራቸውን ወደ ሌላ መስክ ቀይረው ለዘለቄታ የሚያኖር የሕይወት ዋስትና ነው? ይኼ የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊና የሥነ አዕምሮ ጫና የሚያሳድር የይዞታ ማስለቀቅ ሥራ ውጤቱ የሚለካው በሕዝቦች ውስጥ በሚያስከትለው የፖለቲካ ጣጣና አመፅ መሆኑን በተጨባጭ አይተናል፡፡

 ቀደም ሲል በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የተነሳውና ወደ ሌሎችም ተዛምቶ የበርካቶችን ሕይወትና ንብረት ሊያጠፋ የቻለው የሁካት መነሻ ነው፡፡ ይኼ ጥያቄ መነሳት እንደሚችል ተገምቶ በሕገ መንግሥቱ ቅድሚያ መፍትሔ ተቀምጦለታል፡፡ ሕገ መንግሥቱ አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ስለምትገኝ ለመስፋፋትም ሆነ ለሌሎች አገልግሎቶች በክልሉ ላይ የተለያዩ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጫና ስለምትፈጥር፣ ክልሉ ልዩ ጥቅም እንዲያገኝ ደንግጓል፡፡ ይኼ ድንጋጌ የኢሕአዴግ መንግሥትን ያህል ዕድሜ አስቆጥሯል፡፡ ነገር ግን የመጀመሪያዎቹ የፈጠሩትን ሕገ መንግሥት የኋለኞቹ ሊያሳምሩት ባለመቻላቸው ጉዳዩ አገራዊ የሆነ ፖለቲካዊ ቀውስ ፈጥሯል፡፡ መንግሥት ገቢ የሚያስገኙለትን የሊዝ፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንት የመሳሰሉት ሕጎች ወጥተው ተደጋጋሚ ማሻሻያ ጭምር ተደርጎላቸዋል፡፡ ይኼ የአዲስ አበባ አካባቢ አርሶ አደርን ያላግባብ መፈናቀልን ያስቀራል ወይም መፍትሔ ያበጅለታል የተባለው ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌ ግን የመንግሥትን በር በኃይል እስኪያንኳኳ ድረስ ሰሚ አላገኘም፡፡ ይኼ ጉዳይ በቂ ጥናትና በሕዝብ ጥምር የተደገፈ የመፍትሔ ሐሳብ ያስፈልገዋል፡፡ በተወሰኑ ባለሥልጣናት ወይም ካድሬዎች የሚቀርብ መፍትሔ በምንም መልኩ የተሟላ ሊሆን አይችልም፡፡ በአሁኑ ወቅት የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥታት መዋቅሮችን በአዲስ አደረጃጀት በከፍተኛ ምሁራን አዋቅረዋል፡፡ ይኼ ጥሩ ሐሳብ ነው፡፡ ጥሩ ሐሳብ የሚሆነው ካልተማረ የተማረ ይሻላል ከሚለው ተለምዶአዊ አባባል ነው፡፡ ነገር ግን የማስተርስና የዶክትሬት ዲግሪ በያዙ ሰዎች መዋቅሮችን በመሙላት ብቻ ተዓምር ይኖራል ማለት የበዛ የዋህነት ነው፡፡

አዲሱ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ሥራውን መጀመር ያለበት ሕዝቡን ያስመረሩና መፍትሔ የሚያስፈልጋቸውን ችግሮች ለይቶ አውጥቶ ተግባራዊ የመፍትሔ ሐሳብ በማምጣት ነው፡፡ ከእነዚህ ችግሮች ውስጥ የመጀመሪያው መሆን ያለበትና አስፈላጊ ያልሆነ መስዋዕትነት የተከፈለበት የፊንፊኔ ዙሪያ ጉዳይ ነው፡፡ ታዲያ ምነው እስካሁን ቄሱም ዝም መጽሐፉም ዝም ሆነ፡፡ ቄሱ ካልተናገሩ የመጽሐፉ ዝምታ እኮ ዘለዓለማዊ ነው፡፡ መጽሐፉ ለብቻው አይናገርም፡፡

ይኼንን ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌ የያዘ አጀንዳ ወደ ጎን በመተውና ባለመፈጸም የክልሉም ሆነ የፌዴራል የሕግ አውጪ አካላት በቅድሚያ ተጠያቂዎች ናቸው፡፡ አሁን ከሚሰማው ፍንጭ የፊንፊኔ ዙሪያ ተፈናቃይ ገበሬዎች በአንድ ሔክታር እስከ አምስት መቶ ሺሕ ብር ድረስ ተከፍሎ ከይዞታቸው እንደሚለቁ እየተነገረ ነው፡፡ በዚህ አካባቢ ሰፊ ማሳ አለው የሚባል ገበሬ ያለው ይዞታ ሁለት ሔክታር ቢሆን ነው፡፡ ይኼ ገበሬ አንድ ሚሊዮን ብር ድረስ ያገኛል፡፡ ሚሊየነር ሆነ እንበል፡፡ አንድ ሚሊዮን ብር በአሁኑ የአገራችን የኑሮ ሁኔታ አንድ ሰፊ ቤተሰብ ለማስተዳደር የሚታሰብ አይደለም፡፡ ቦታ ፈልጎ አንድ አነስተኛ የቤተሰብ መኖሪያ ቤት ለመሥራት ብቻ አንድ ሚሊዮን በቂ የሚባል ገንዘብ አይደለም፡፡ መንግሥት ለእነዚህ ሰዎች የሚከፍለው ክፍያ ሊከብደው ይችላል፡፡ መሬቱን ለሚፈልጉ ባለሀብቶች ገበሬው የሚበቃውን መቋቋሚያ ለማስከፈል ግን በጣም ቀላል ነው፡፡

እስካሁን ድረስ በማስፋፊያ አካባቢ የተሠሩ የግል ቤቶችም ሆኑ ኮንዶሚኒየሞች የሚገኙት አብዛኛዎቹ በመጀመሪያዎቹ መሥራቾች እጅ ሳይሆን፣ በተደጋጋሚ ተሸጠውና ተለውጠው፣ በርካታ ነጋዴዎችንና ደላሎችን ባለብዙ አሥር ሚሊዮን ብር ባለቤት አድርገው፣ ባለይዞታ የነበሩትን አርሶ አደሮችና ቤተሰቦችን አደህይተውና ከአካባቢው አባረው ነው፡፡

አንድ ከአካባቢው የተፈናቀሉ ዕድሜዬ 80 ዓመት ነው ያሉት አባት ምሳሌያዊ አነጋገር እንሆ፡፡ ‹‹ፆም በሁለት ይከፈላል›› አሉ አዛውንቱ፡፡ ‹‹ሁለት ሰዎች በተለያየ ምክንያት ፆማቸውን ይውላሉ፣ ምግብ ሳይበሉ፡፡ አንደኛው ሀብታም አንደኛው ደሃ ናቸው፡፡ ሀብታሙ ሰው ያልበላው ሃይማኖቱ የሚያዘውን የፅድቅ ፆም ሊያደርስ ነው፡፡ ደሃው ያልበላው የሚላስ የሚቀመስ ከቤቱ አጥቶ ነው፡፡ ሁለቱም ፆም ውለዋል፡፡ ረሃቡ እኩል ነው ስሜቱ ይለያያል፡፡ መሠረቱም ለየቅል ነው፡፡ ለነፍሱ ሲል በፈቃዱ የፆመው የገነትን መግቢያ በር ለመክፈት እየሞከረ በመሆኑ፣ የረሃብ ስሜቱ የሰማይ ቤት ተስፋውን ያለመልመዋል፡፡ ወደ ቤቱ ሲመለስ ፆም በመዋሉ የሚዘጋጅለት ምርጥ ምግብ፣ በማኅበራዊ ኑሮው ፆሙ የሚያስገኝለት ትልቅ ሥፍራና ፍላጎቱን በማሸነፉ የሚሰማው ውስጣዊ ደስታ በሰማይም በምድርም የሚያስገኝለት ትርፍ ካለመብላቱ ጋር ሲያስበው ነፍሱ በሀሴት ትሞላለች፡፡ ደሃው ሰው ግን ፆሙን የዋለው በማጣቱ እንጂ በፍላጎቱ ባለመሆኑ የረሃብ ስሜቱ ትልቅ ነው፡፡ ገብቶም የሚቀስመው ነገር ባለመኖሩ ውስጡ ይሟሟታል፡፡ የዛሬው ፆም መዋልን ነገ የሚከተለው በዛሬው ረሃብ ላይ የሚጨመር ሌላ ረሃብ መሆኑን ሲያስበው ሰማይ ተደፍቶበት ቢያድር አይከፋውም፡፡ ፋሲካ በማይከተለው የሁልጊዜ ረሃቡ ዕድሉን እንዲያማርርና ለዚህ ያበቃውን ምክንያት እግዚአብሔርና ሰውን እንዲጠይቅ ይገደዳል፤›› አሉ አዛውንቱ፡፡ እንግዲህ ሁለቱም በተግባር የደጸሙት አንድ ዓይነት ረሃብ መራብ ነው፡፡ መሠረቱና ውጤቱ በግለሰቦቹ ላይ የሚያስከትሉትን ውጤት ባለ ህሊና ሁሉ ሊገምተው ይችላል፡፡

የአዛውንቱ የምሳሌያቸው መነሻ የሆነው ከመሬቱ ላይ የተነሳውን ገበሬና የእሱን ይዞታ ወስዶ በሚሊዮኖች ሸጦ የተነሳውን ከተሜ ከግምት የሚያስገባ ነው፡፡ ሁለቱም ባለ ይዞታዎች ነበሩ፡፡ ሁለቱም ይዞታቸውን ለቀው ከአካባቢው ሄደዋል፡፡ አንደኛው የለቀቀው እንደ ሀብታሙ ፆመኛ በተስፋና በደስታ ነው፡፡ ገበሬው የለቀቀው ደግሞ እንደ ፆመኛው ሀብታም ሳይሆን፣ እንደ ፆም አዳሪው ደሃ በደነዘዘ ስሜት፣ በሐዘንና በተስፋ መቁረጥ ነው፡፡

ታዲያ ይህን ችግር ይፈታል ተብሎ የተቀመጠው የሕገ መንግሥት ድንጋጌ ያስገኛል የተባለው ልዩ ጥቅም ምንድነው? ለማንና ለመቼስ ነው የተቀመጠው? ይኼ ችግር የሚፈታው ለአካባቢው መንገድ ስለተሠራ፣ ትምህርት ቤት ስለተከፈተ፣ የባቡር ሐዲድ ስለተዘረጋ፣ ወዘተ አይደለም፡፡ ይኼ ጠቀሜታው ለአፈናቃዩ እንጂ ለተፈናቃዩ አይደለም፡፡ ተፈናቃዩማ አካባቢውን ለቆ ይሄዳል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ሲተረጎም ከፆመኛው ሀብታም ወስዶ ለፆም አዳሪው ደሃ የድርሻውን የሚከፍልበት አሠራር ሊያበጅ ይገባዋል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ እነዚህ አርሶ አደሮች ወደየትም ሳይሰደዱና የመንግሥትን ወጪ ሳይጠይቁ ባሉበት ቦታ ወደ ከተሜነት ተለውጠው በተስፋና በደስታ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡

በአሁኑ ጊዜ መንግሥት ከገበሬዎቹ የሚረከበውን ማሳ በጨረታ የሚሸጠው እያንዳንዱን ካሬ ሜትር ከአሥር ሺሕ ብር በላይ ነው፡፡ ታዲያ መንግሥት በእያንዳንዱ ካሬ ሜትር አንድ ሺሕ ብር ለገበሬው ካሳ (የሕይወት ዋስትና) ጭማሪ ቢጠይቅና በትክክል ገበሬው የሚጠቀምበትን አቅጣጫ ቢያስቀምጥ፣ ባለሀብቱም ሆነ ገበሬው ሁለት ሔክታር መሬት ሲለቅ የሚገኘውን ገንዘብ ሲያሰላው ራሱን ሊያመው ይችላል፡፡ የደላላውና የመሬት ነጋዴው ገቢ ግን በመንግሥት በኩል የማይተላለፍ ስለሆነ አስልቶትም አያውቅም፡፡ በሁለት ሔክታር መሬት ላይ ያሉ ንብረቶችም ሆኑ ባዶው መሬት በእነዚህ ሕገወጦች በኩል ሲተላለፉ ለገበሬው ይከፈል ከተባለው አያንስም፡፡

ለገበሬው በሔክታር አምስት መቶ ሺሕ ብር ሲከፈል ገንዘቡ ትንሽ አይደለም፡፡ ነገር ግን መንግሥት ቆሜለታለሁ የሚለውን ገበሬ ከመተዳደሪያውና ከቄዬው ሲያስነሳው ኑሮው ሊሻሻል ወደሚችልበት ደረጃ ወይም እንዲቆይ አስፈላጊውን ሁሉ የማድረግ ግዴታ  አለበት፡፡ ሁለት ሔክታር ወይም ከዚያ በታች ይዞታ ያለው ገበሬ በካሬ ሜትር ተሰልቶ የሚደርሰውን ገንዘብ መንግሥት ለልማት በሚውል መንገድ እንዲጠቀሙበት ሊረዳቸውና ሊያስተምራቸው ይገባል፡፡ ገበሬዎች ተደራጅተውና መሬት ተጫርተው በሊዝ ገዝተው ኮንዶሚኒየም ሠርተው እንዲኖሩበትና እንዲያከራዩት ቢደረግ፣ በኢንዱስትሪው መንደር ግንባታ ውስጥ ገንዘባቸውን ኢንቨስት በማድረግ ለራሳቸውና ለልጆቻቸው ዘላቂ ሥራ ቢያመቻቹ፣ ቦንድና አክስዮን በመግዛት ቢሳተፉና ሌሎች ተጨማሪ ሥራዎች ቢመቻቹላቸው ያገኙት ገንዘብ ተመልሶ ለልማት ዋለ ማለት ነው፡፡

እነዚህና መሰል አሠራሮች መንግሥት ባቀደው የመዋቅራዊ ለውጥና የአዲስ አበባ ዙሪያን ወደ ከተማ ሕይወት በመለወጥ ሒደቱ ላይ ከፍተኛ ሚና ይኖራቸዋል፡፡ ፆመኛውና ፆም አዳሪው እኩል ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ የፍትሕ፣ የእኩልነትና የመብት ጉዳዮችም በፅኑ መሠረት ላይ ይቆማሉ፡፡ የጥልቁ ተሃድሶም አንድ ዋነኛ መገለጫ ሊሆን ይችላል፡፡ ያለነገር በጥልቀት የሚለው ቃል አልተጨመረም፡፡ ነገር ግን አሁን በሚታየው ፍንጭ መሠረት በሔክታር ይከፈላል ተብሎ የታሰበው ገንዘብ አርሶ አደሩን በቁጥር በመሸንገል ዘለቄታ በሌለው ተስፋ ገብቶ ገንዘቡን የሚያባክነው እንጂ፣ መሠረታዊ ለውጥ አውጥቶ ሕይወቱን ለመምራት የሚበቃ ገንዘብ አይደለም፡፡ ይኼ ገንዘብ ለልማት የሚውል አይሆንም ማለት ነው፡፡

መንግሥት አንድን ባለመብት ያለፍላጎቱ ከይዞታው ሲያስለቅቅ በካሳ መልክ ጉርሻ ሰጥቶ መሆን የለበትም፡፡ በመሠረቱ አንድ ሰው ይዞታውን በግዴታ መልቀቅ ያለበት ለመንግሥታዊ የአገልግሎት ተቋማትና መሠረተ ልማት ብቻ ሲሆን ነው ሕጉ የሚደነግገው፡፡ ለመንግሥትና ለግል ኢንቨስተሮች ወይም ለተለያዩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የሚለቀቅ ቦታ ከላይ በተጠቀሰው መሠረት የገበሬውን ተስፋ ብሩህ በማድረግ በፈቃደኝነት መሆን አለበት፡፡ ለዚህ ሁሉ አፈጻጸም የሚረዳው በሕገ መንግሥቱ ላይ የተቀመጠው ድንጋጌ ሆኖ ሳለ በጎን በተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች በሚወጣ ሕግ መሆን የለበትም፡፡ የከተማ ነዋሪ ተከራዮችም ሆኑ ባለይዞታዎች ከመኖሪያ ቤታቸው ሲለቁ እኮ የተሻለ ቤት ወይም ቦታና የቤት መሥሪያ ገንዘብ እየተከፈላቸው ነው፡፡ ታዲያ የኢሕአዴግና የአርሶ አደሩ ወዳጅነት ከመቼው ቀዝቅዞ ነው አቋም የተቀየረው?

ሌሎች ከፊንፊኔ ዙሪያ መሬት አጠቃቀም ጋር ተያይዞ የሚመጡ የዘለቄታ ችግሮችም አብረው መታሰብ አለባቸው፡፡ የፊንፊኔ ዙሪያ አርሶ አደሮች የያዙት መሬት በአገሪቱ ውስጥ እጅግ ለም ከሚባሉት የጤፍና የስንዴ አምራች አካባቢዎች ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፡፡ ይኼ ለአዲስ አበባ ነዋሪዎች እጅግ መልካም አጋጣሚ ነው፡፡ ለአዲስ አበባ ካላቸው ቅርበት አንፃር ለከተማይቱ ነዋሪዎች በቀላሉ መኪና ባይገባ እንኳ በእንስሳት ተጭኖ በፍጥነት እህል ያቀርባሉ፡፡ በተለይም የአዲስ አበባ ሕዝብ ዋና ምግብ ጤፍ ደግሞ በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍል በብዛትም ሆነ በጥራት የሚመረት አይደለም፡፡ የአደአና የበቾ ጤፍን የመሳሰሉ በብዛታቸውና በጥራታቸው ወደር የማይገኝላቸው ዝርያዎች ምንጫቸው የአዲስ አበባ አካባቢ መሬትና ገበሬ ነው፡፡ የእነዚህ አካባቢዎች የጤፍ ምርት በመሬት ጥበት ምክንያት ለወደፊት በእጅጉ እንደሚቀንስ ይታመናል፡፡ እነዚህ ማሳዎች በልማትና በኢንቨስትመንት ስም አምራችነታቸው ለዘለቄታ እየቀረ ነው፡፡

ለደረቅ ወደብ ግንባታ፣ ለሰፋፊ የአበባ እርሻዎች፣ ለሕንፃዎች፣ ለመንገዶች፣ ለካምፖች፣ ለድርጅቶች፣ ወዘተ ግንባታዎች የሚሰጡ የእርሻ መሬቶች ለዘለቄታው ወደ ማሳነት ሊመለሱ አይችሉም፡፡ የሕዝብ ቁጥር በየዓመቱ በሚሊዮን የሚጨምር ሆኖ ሳለ በብዛትና በጥራት የሚያመርቱ ብርቅዬ የማይተኩ ማሳዎቻችን ከአገልግሎት ውጪ ማድረግ ትኩረት የሚያሻው የወቅቱ አጀንዳ መሆን አለበት፡፡ ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ መሬቶች በጥናት ላይ ተመሥርቶ ከአዲስ አበባ ርቀውም ቢሆን ሊሰጡ ይችላሉ፡፡ የኢንዱስትሪ ምርቶች ፍለጋ የቀለብ ምርቶቻችንን ማሳጣት የለበትም፡፡ ሁለቱም በየፈርጁ ይስተናገዱ፡፡ ሰፋፊ ጭንጫ መሬቶች እያሉ ምርጥ ማሳዎች መምከን የለባቸውም፡፡ ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ የአደአና የበቾ ምርጥ የጤፍና የስንዴ ዝርያዎች ሲጠፉ የማየት ዕድል የሚገጥማቸው በርካታ የዚህ ዘመን ሰዎች ይኖራሉ፡፡

በአዲስ አበባ ዙሪያ ሕዝቡንም መሬቱንም በአግባብ እንጠቀምበት፡፡ ሕዝቡም መሬቱም እየባከነ ነው፡፡ ለወደፊት አዳዲስ የማያፈናቅሉ ሥራዎች የሚካሄዱ ከሆነ፣ መንግሥት የሚወስነው ውሳኔና ደንብ መነሻው ከሕዝብ የሚመነጭ መፍትሔን የሚያካትት መሆን አለበት፡፡ ብዙው ሕዝብ ለጥቂቶች ሥልጣን ሰጥቷል፡፡ ሥልጣን ማለት ማዘዝ ለአንዱ፣ መታዘዝ ለብዙው ብቻ መሆን የለበትም፡፡ ጥቂቶች የተስፋ መንገድ መቀየስ አለባቸው፡፡ ያኔ ሁሉም በፍቅርና በመቻቻል ይኖራል፡፡ ያኔ መንግሥትና ሕዝብ ሊበጠስ በማይችል ገመድ ይተሳሰራሉ፡፡

መቼም በአገራችን አሁን አሁን መንግሥትን መተቸት ተገቢ የመሆኑን ያህል ማመስገን አልተለመደም፡፡ አንድ ምሥጋና እነሆ፡፡ ከላይ የተዘረዘረው ሐሳብ ወደፊት ይዘታቸውን ለሚለቁ የሚያገለግል ነው፡፡ የዚህ ሐሳብ ምክንያት በቀድሞ ተፈናቃዮች ላይ የደረሰውን ችግር መነሻ በማድረግ ነው፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ መንግሥት ያለፈው ስህተቱ ስለፀፀተው ቀደም ሲል ባክነው የቀሩ የቀድሞ ተፈናቃዮችን በማፈላለግ ለዘለቄታው ሊያቋቁማቸው የጀመረው ጥረት የሚያስመሰግን ነው፡፡ መሳሳት አንድ ነገር ሆኖ መታረም ደግሞ የትልቅነት ማሳያ ነው፡፡ ለወደፊት ሕዝቡ እንዳያዝን መሬቱ እንዳይባክን የከፍተኛ ምሁራን ስብስብ የሆኑት የክልልና የፌዴራል መንግሥት ካቤኔዎች የሚሉትን እንጠብቅ፡፡ ሁሉንም የሚያቻችል መሪ ሳይጠፋ ቂም የሚያያይዙ ፆመኛና ፆም አዳሪ አንፍጠር፡፡

ከአዘጋጁ፡ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

 

Standard (Image)

አቅጣጫው የማይገመተው የምሥራቅ አፍሪካ ፖለቲካ

$
0
0

(የዓረቦቹና የኢትዮጵያ ሰሞነኛው ሽርጉድ)

በያየሰው ሽመልስ

የምሥራቅ አፍሪካ ፖለቲካ እንደዚህ ሰሞን ማዕበል በዝቶበትም የሚያውቅ አይመስልም፡፡ የኤርትራው ሰው ወደ ካይሮ አቅንተው ከጄኔራል መኮንኑ አብዱልፈታህ አልሲሲ ጋር መክረዋል፡፡ የኢሳያስና የአልሲሲ ውይይት ማዕከላዊ ትኩረት በመስኖና በዓሳ ሀብት ዘርፍ በጋራ ለመሥራት እንደሆነ በግብፅ መገናኛ ብዙኃን ሲዘገብ ቢቆይም፣ ሁለቱ መሪዎች የቀይ ባህር ኮማንድ ፖስት ለማቋቋም መስማማታቸው ግን የኋላ ኋላ ተጋልጧል፡፡ የወዲ አፎም መንግሥትም ለመጀመሪያ ጊዜ ይህንን ጉዳይ አምኖ ለሕዝብ ይፋ አድርጓል፡፡

የመንግሥቱ ቴሌቪዥን ‹‹በቀይ ባህር አካባቢ ያሉ የሽብር እንቅስቃሴዎችን ለመግታት የተቋቋመ ኮማንድ ፖስት ነው›› ሲል የመሪዎቹን ስምምነት አምኗል፡፡ ሕግዴፍ-ሻዕቢያ እንዲህ ያለን መረጃ በሕዝብ ፊት ሲያምን ምናልባትም ለመጀመሪያ ጊዜ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ከአሁን በፊት የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶችም ሆነች ኢራን፣ የኤርትራን ወደቦች ያለገደብ ሲከራዩ ለኤርትራ ሕዝብ አልተነገረውም፡፡ ኤርትራ ከ400 በላይ ሠራዊት የመን አስገብታ እንደምታዋጋ ሕዝቡ አያውቅም፡፡ አሁን ግን ከግብፅ ጋር የገቡትን ውል ለአደባባይ አዋሉት፡፡

የእዚህን ምክንያት የሚገምቱ ሰዎች ሦስት መላምቶችን ያስቀምጣሉ፡፡ አንደኛው መላምት ኢትዮጵያ ለውስጥ ፖለቲካዊ ቀውሷ በተደጋጋሚ ግብፅን እየከሰሰች በመሆኑ፣ ኢሳያስ ከእነ አልሲሲ ጋር የአደባባይ ሽርክና በመፍጠር እነ ኃይለ ማርያም ደሳለኝን ማበሳጨት ፈልገዋል የሚለው ነው፡፡ እናም ኢሳያስ ራሳቸው የጋብዙኝ ጥሪ ለአልሲሲ ማስተላለፋቸውን አንዳንድ ምንጮች በሹክሹክታ ሲያወሩ ይደመጣል፡፡ ካይሮ ከገቡ በኋላም በውኃ ሚኒስትሩ አቀባበል ሲደረግላቸው ሲታይ፣ ነገርየው በፕሬዚዳንት አልሲሲ በኩል ትኩረት እንዳልተሰጠው ጠቋሚ ነው የሚለው መከራከሪያ ይኼኛውን መላምት የበለጠ አጽንኦት አሰጥቶታል፡፡

 በኤርትራ መንግሥት ሠፈር አዲስ አሉባልታ እየተራወጠ እንደሆነ ይደመጣል፡፡ ይኼኛው አሉባልታ ኢትዮጵያ የመኸር ምርቷን ሰብስባ ስትጨርስ ወረራ ልትፈጽምብን እየተዘጋጀች ነው የሚል ነው፡፡ እናም ግብፅን በዚህ ላይ ለማማከር/የሚወራው እውነት ቢሆን እገዛሽ እስከምን ድረስ ነው በማለት የተለመደ ጥያቄዋን ለማቅረብ፣ (በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ጊዜ በዛ ያሉ ግብፅ ሠራሽ መሣሪያዎች በኢትዮጵያ መማረካቸውን ያስታውሷል)፣ ስለዚህም ለኤርትራ ሠራዊት ‹አይዞን ግብፅ ዛሬም ከእኛ ጋር ናት› የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ነው የሚለውም ሁለተኛው መላምት ነው፡፡

ሦስተኛው ምክንያት በአስመራ በኩል ይፋ የተደገረው የቀይ ባህር ኮማንድ ፖስት መቋቋም ጉዳይ ነው፡፡ መቼም ይኼኛውን ጉዳይ ግብፅ አብዝታ እንደምትፈልገው ዕሙን ነው፡፡ ግብፅ በሶሪያ ፖለቲካ ላይ የበሽር አላሳድን መንግሥት ደግፋ ከሩሲያ ጎን መቆሟ የሱኒ እስልምና እናትና አባት ነኝ የምትለዋን ሳዑዲ ዓረቢያን ፀጉር አስነጭቷል (ሳዑዲ የበሽር አላሳድ መንግሥት ከሶሪያ መንበር እንዲፈራርስ እየሠራችና እየፀለየች መሆኑን ልብ ይሏል)፡፡ የነገሥታቱ አገር ለፈርኦኖቹ ታቀርብ የነበረውን ነዳጅ ዘይት ያቋረጠችውም ከዚህ ውዝግብ በኋላ ነው፡፡

እናም ካይሮና ሪያድ ሆድ ተባብሰዋል፡፡ በዚሁ ሰሞን ሳዑዲ ዓረቢያ ጂቡቲ የጦር ሠፈር ልትገነባ እንደሆነ ይፋ አድርጋለች፡፡ ስለዚህ በቀይ ባህር አካባቢ ያለውን የሳዑዲ ዓረቢያን እንቅስቃሴ በቅርበት ለመከታተል በመሻት አብዱልፈታህ አልሲሲ ከኢሳያስ አፈወርቂ ጋር የቀይ ባህር ኮማንድ ፖስት ለማቋቋም እንዲወስኑ አድርጓቸዋል የሚል ግምት አለ፡፡

የሆነ ሆኖ ኤርትራና ግብፅ በወቅታዊ ሽርክናቸው የመሠረቱት የቀይ ባህር ኮማንድ ፖስት አቅጣጫው አይታወቅም፡፡ ኮማንድ ፖስቱ በኢትዮጵያ ላይ የሚኖረው ተፅዕኖ ምን ሊሆን እንደሚችል ግን መገመት አይከብድም፡፡

አልሲሲ፣ ሞሴቬኒና ኦማር ጊሌህ

የግብፁ አልሲሲ ወደ ኡጋንዳ ያቀኑት፣ የጂቡቲው ጊሌህም ወደ ካይሮ የተጓዙት በዚሁ ሰሞን ነበር፡፡ የአልሲሲና የሞሴቬኒ የካምፓላ ውይይት በዓባይ ወንዝም ላይ ያተኮረ እንደነበረ የኡጋንዳ መገናኛ ብዙኃን ጽፈዋል፡፡ በእርግጥ የሞሴቬኒ አገር በዓባይ ውኃ አጠቃቀም ፍትሐዊነት ላይ ጠንካራ አቋም እንዳላት ይታወቃል፡፡ የግብፆቹ ፍላጎትም ይህንን ደንዳና አቋም አቅም እንዲያጣ ማድረግ ነው፡፡ ባለባርኔጣው ፕሬዚዳንት ዮሪ ሞሴቬኒ በዚህ ረገድ አቋማቸው ይሸረሸራል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ከኢትዮጵያ ጋር ጠንካራ ወዳጅነት ያላቸው መሆናቸውም በቀላሉ እጅ እንዳይሰጡ ሊያደርጋቸው ይችላል፡፡ ምንም እንኳ በፖለቲካ ዘላቂ ጥቅም እንጂ ዘላቂ ወዳጅ ባይኖርም፡፡

የጂቡቲው ኦማር ጊሌህም ወደ ግብፅ አቅንተው ነበር፡፡ የትንሿ አገር ፕሬዚዳንት ወደ ካይሮ ሄደው የመከሩት ጉዳይ በይፋ ባይገለጽም፣ ከሳዑዲ ዓረቢያ ጋር ሊገናኝ እንደሚችል ግን ይገመታል፡፡ ዓረባዊቷ አገር በጂቡቲ እገነባዋለሁ ያለችውን የጦር ቀጣና በተመለከተ ሳይወያዩ እንዳልቀሩ ይታመናል፡፡ አሜሪካንም፣ ቻይናንም፣ ፈረንሣይንም… አስማምታ የጦር ሠፈር የሰጠችው ጂቡቲ፣ በግብፅ ፍላጎትና ግሳጼ ሳዑዲን ትከለክላታለች ተብሎ አይጠበቅም፡፡ የግብፅም ሆነ የሳዑዲ በዚህ ሠፈር ማንዣበብ ግን ከ90 በመቶ በላይ የወጪና ገቢ ንግዷን በምሥራቅ ላደረገችው ኢትዮጵያ እንቅልፍ የሚነሳ መሆኑ የማይቀር ነው፡፡

ኳታር፣ሳዑዲ ዓረቢያና ኢትዮጵያ

የአውሮፓውያኑ አሮጌ ዓመት መገባደጃ ሰሞን፣ ዓረባውያኑ ከጦቢያ ጋር እፍፍ ያለ ፍቅር ውስጥ ነን ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ወደ ሪያድ ሄደው በተመለሱ ማግሥት የነገሥታቱ ልዑካን ቡድን አዲስ አበባ መጥተው ነበር፡፡ በአዲስ አበባ ሳይወሰኑም እስከ ጉባ ድረስ ተጉዘው የህዳሴው ግድብ ግንባታን ጎብኝተዋል፡፡ ቡድኑ የተመራው አህመድ አል-ቃቲብ በተባሉት የንጉሣዊ መንበሩ የቅርብ ሰው ነበር፡፡

የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሼክ ሃሚድ አልታኒ ያስከተሉት ቡድን ከአቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ መንግሥት ጋር አሥራ አንድ ስምምነቶችን ተፈራርሞ ተመልሷል፡፡ የኳታር አየር መንገድ የአስመራ በረራውን አቋርጦ ወደ አዲስ አበባ በሳምንት ሦስት ቀን ሊመጣ ወስኗል፡፡ የኳታሮቹ የቀናት ውሎ በሁለቱም ቤተ መንግሥቶች፣ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና በመሰል አካባቢዎች ነበር፡፡

እንዲህ ያለውን ግንኙነት ወቅታዊ ምክንያት፣ ስትራጂካዊነትና ፖለቲካዊ ዳራ መፈተሽና ለምን ብሎ መጠየቅ ያሻል፡፡

ኳታር

ይህቺ አገር በ1990ው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ጊዜ ከአስመራ ጀርባ እንደነበረች ለአደባባይ የዋለ ሚስጥር ነው፡፡ በወቅቱ የተማረኩ የኤርትራ ወታደሮች ይዘዋቸው ከተገኙ ጦር መሣሪያዎች መካከል በዛ ያሉቱ የኳታርና የግብፅ እንደሆኑ ይታወሳል፡፡ ኢትዮጵያ ደም በተቃባችበት ጉዳይ ዓረባዊቷ አገር አቀጣጣይ ሆና መቆየቷ ታሪካዊ ጠላትነቷን ያጎላዋል፡፡ ይህም ሳያንስ እ.ኤ.አ በ2008 ኢትዮጵያ የደምና የገንዘብ ዋጋ በምትከፍልበት የሶማሊያ ጦርነት ላይ አልሸባብን ስታስታጥቅና ስንቅ ስትሰፍር ተገኝታለች ተባለ፡፡ የአቶ መለስ ዜናዊ መንግሥትም በዶሃ የነበረውን ኤምባሲውን ዘግቶ ወጣ፡፡ ወትሮም ቢሆን በአዲስ አበባ ኤምባሲ ያልነበራት ኳታር፣ በአስመራና በሞቃዲሾ በከፈተቻቸው ኤምባሲዎች የአፍሪካን ቀንድ በሽብር ልትሞላው እየታገለች መሆኑን ከአዲስ አበባ የሚወጡ መግለጫዎች ሲያትቱ ሰነበቱ፡፡

የሁለቱን አገሮች ግንኙነት የከፋ ጫፍ ያደረሰው ደግሞ በኳታር ልዑላን አይዞህባይነት፣ ዕውቅናና የገንዘብ ምንጭነት የተቋቋመው የአልጄዚራ ቴሌቪዥን የኢትዮጵያ መንግሥትን የሚያበሳጭ ድርጊት መፈጸሙ ነበር፡፡ ‹የኦጋዴንን ጉዳይ የዘገበበት መንገድ ውሸትና ግነት የበዛበት፣ ኦብነግንም የሚያሞካሽ ነው› ተብሎ ቴሌቪዥኑ ከአዲስ አበባ ተጠራርጎ አንዲወጣ ተደረገ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህም ‹ኳታር  ምሥራቅ አፍሪካን ለማተራመስ እየሠራች ነው፣ አልሸባብንም እየደገፈች ነው› በሚለው ክሷ ኢትዮጵያ ገፋችበት፡፡ ኳታርም ከአዲስ አበባ ጋር ያላትን ውል ፈትታ ከአስመራ ጋር ያላትን ሽርክና አጠበቀች፡፡ ይልቁንም ኤርትራንና ጂቡቲን ለማስታረቅ ደፋ ቀና ማለት ቀጠለች፡፡

እ.ኤ.አ. በ2012 ወደ ሥልጣን የመጡት አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ  ወገባቸውን አስረው ከከወኗቸው ተግባራት መካከል ይህንን የኳታርን ግንኙነት ማሻሻላቸው እንደሆነ ይጠቀስላቸዋል፡፡ በጥቅምት 2005 ዓ.ም ሁለቱ አገሮች ዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነታቸው ወደ ነበረበት መመለሱ ተነገረ፡፡ የኳታሩ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ዳግም ተከፈተ፡፡ ዓረባዊቷ አገርም ለመጀመሪያ ጊዜ አምባሳደር ልካ በአዲስ አበባ ኤምባሲ ከፈተች፡፡

ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ ነው እንግዲህ ሰሞኑን ወደ አዲስ አበባ የመጣው የኳታሩ መንግሥት ልዑክ በዛ ያሉ ስምምነቶችን የተፈራረመው፡፡ የአስመራ በረራውን ባልታወቀ ምክንያት ያቋረጠው የኳታር አየር መንገድም ወደ አዲስ አበባ በሳምንት የሦስት ቀን በረራ ለማድረግ የወሰነው ሼኩ የመሩት ቡድን ውደ ኢትዮጵያ ሳይመጣ ነው፡፡

እዚህ ላይ ይህንን ያህል ምላ ተገዝታ ኢትዮጵያን የሙጥኝ ያለችውን ኳታርን ማመን ይቻላል ወይ ብሎ መጠየቅ ያሻል፡፡ አንዳንድ ታዛቢዎች በቀንዱ ፖለቲካ ላይ የማይገመትና የማይታመን ርዕዮት ካላቸው ዓረባውያን መካከል ኳታርን ግንባር ቀደም አድርገው ይጠቅሷታል፡፡ ከኤርትራ ጋር ፍቅር ስለመጨረሷ ውስጥ ውስጡን ሲወራ ቢከርምም ምክንያቱ ግልጽ አልተደረገም፡፡ ተመልሳ ወደ አስመራ ፊቷን ላለማዞሯም ዋስትና የለም፡፡ ከጂቡቲ ጋር የኢሳያስን መንግሥት ለማስማማት ስትጥር ከርማ በመጨረሻ አውሮፕላኗም ወደዚያ እንዳይበር ከለከለች፡፡ ይልቁንም አየር መንገዱ የጂቡቲውን በረራውን መቀጠሉ፣ ሁለቱን አገሮች ስታደራድር የኖረችው አገር በይፋ ወገንተኛ መሆኗን የሚያሳይ ነው ሲሉ የአስመራ ልሂቃን ሲናገሩ ተደመጡ፡፡

እ.ኤ.አ ከ2012 ወዲህ (የሁለቱ አገሮች ወዳጅነት ዳግም ካንሰራራ በኋላ) ኤርትራንና ኢትዮጵያን ለማስታረቅ እየደከሙ ነው ተብሎ በዲፕሎማቲክ ማኅበረሰቡ ሲወራላቸው ከነበሩ ጥቂት አገሮች አንዷ ኳታር ነበረች፡፡ አሁን ግን ያንን ተልዕኮዋን የት እንዳደረሰችው ሳይታወቅ የኢሳያስን አስተዳደር ችላ ብላ የኃይለ ማርያም ደሳለኝን መንግሥት አቀረበች፡፡ በውክልና ጦርነት (Proxy War) ጦር የሰበቀችባትን ወዳጅ አድርጋ ኢትዮጵያን የተጠጋችው ኳታር የነገ አቅጣጫዋ ወዴት ይሆን? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ የማይታመነውንና ተለዋዋጩን የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ባህል በጥልቀት ማወቅ ይጠይቃል፡፡

ከላይ እንደተብራራው ኳታርና ኤርትራ ፍቅራቸውን ካቆሙበት ላለመቀጠላቸው ዋስትና የለም፡፡ ዛሬም ኢትዮጵያ ዋጋ እየከፈለችበት ባለው የሶማሊያ ፖለቲካ ኳታር የራሷን ፍላጎት የሚያስፈጽሙ የጎሳ ቡድኖችን በማደራጀት ላይ መሆኗ ይነገራል፡፡ ሰሞኑን በተጠናቀቀው የአገሪቱ እንደራሴዎች ምርጫም እጇን በረጅሙ እንዳስገባች ሲወራ ከርሟል፡፡ ይህ ለደሃዋ ኢትዮጵያ ትልቅ ፈተና ነው፡፡ ፕሮፌሰር አሌክስ ዲ ዎል ለሪፖርተር እንዳብራሩት፣ በውክልና ጦርነት ፍልሚያ በፔትሮሊየም ዶላር ጡንቻቸውን ያፈረጠሙ አገሮችን ኢትዮጵያ ልትቋቋም የምትችልበት አቅም የላትም፡፡ እሷ ወታደር ስትልክ እነሱ ዶላር እያሰረጉ የጎረቤት አገርን ሰላም ከድጥ ወደማጡ ላለማድረጋቸው ምንም ማረጋገጫ የለም፡፡ ኳታር የዚህ ጉዳይ ዋነኛ ተዋናይት ነች፡፡ እናም በሞቃዲሾ ጉዳይ አዲስ አበባና ዶሃ እንዴት እንደሚደማመጡ አይታወቅም፡፡ እስካሁንም ፍርጥርጥ አድርገው ያወጡት ማብራሪያ የለም፡፡

ሪያድና አዲስ አበባ

ሳዑዲ ዓረቢያ ከኢትዮጵያ ጋር የተሻለ ዝምድና አለኝ ስትል የተደመጠችውም በዚሁ ሰሞን ነው፡፡ አቶ ኃይለ ማርያም እ.ኤ.አ. 2016 መገባደጃ የመጨረሻ ወራት ወደ ሪያድ ሄደው በተመለሱ ጊዜ፣ የሳዑዲ ሰዎች ዱካቸውን ተከትለው ለይፋዊ ጉብኝት ወደ አዲስ አበባ መጡ፡፡ የሳዑዲ ልዑክ ህዳሴ ግድብ ድረስ ሄዶ ጉብኝት ማድረጉ ግብፅን በእጅጉ አስከፍቷል፡፡ አንዳንድ የካይሮ መገናኛ ብዙኃን ‹ሳዑዲ በግብፅ ላይ ጦርነት እንደማወጅ ያለ ተግባር ፈጸመች› ሲሉ የልዑኩን ጉብኝት አውግዘዋል፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ‹ሳዑዲ ለህዳሴው ግድብ የገንዘብ ድጋፍ አደረገች› ሲሉ ጽፈዋል፡፡ የነገሥታቱን አገር ወክለው ልዑካኑን እየመሩ የመጡት ባለሥልጣን ደግሞ ይኼኛውን የግብፆችን (ስለገንዘብ ድጋፍ የተወራችውን) “ዜና” እውነት የሚያስመስሉ ናቸው፡፡

ሰውዬው ሳዑዲ ፈንድ ፎር ዴቨሎፕመንት (SFD) የተባለን ድርጅት በቦርድ ሊቀመንበርነት የሚመሩ ናቸው፡፡ ይህ ተቋም ደግሞ ሳዑዲ ዓረቢያ በውጭ አገሮች ለምታካሂደው ዕርዳታና ድጋፍ ገንዘብ የሚለቅ ነው፡፡ ለዚያም ነው ግብፆቹ ‹ኢትዮጵያ ለምትገነባው ግድብ ከሪያድ ድጋፍ አገኘች› ሲሉ መክረማቸው፡፡ ይህንን ወሬ ግን ሳዑዲዎቹ ውሸት ነው ሲሉ በይፋ ተናግረዋል፡፡

የሆነ ሆኖ ‹ሳዑዲ ለምን በዚህ ሰሞን ህዳሴ ግድብ ድረስ የዘለቀ ሽርጉድ አደረገች? ለምንስ ግብፆቹ ተበሳጩ? ስለምንስ ከወትሮው በተለየ ሁለቱ አገሮች ወዳጅነታቸው የመገናኛ ብዙኃን አጀንዳ ሆነ?› ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ እነሱ ከመምጣታቸው በፊት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሳዑዲ ያመሩት ምናልባትም የባህረ ሰላጤው አገሮች በኤርትራ ከሚያደርጉት ወታደራዊ መስፋፋት ጋር በተገናኘ ውይይት ለማድረግ እንደሆነ ተገምቶ ነበር፡፡ ምንም እንኳ እዚህ ግባ የሚባል ማብራሪያ ባይሰጥበትም፡፡

በእርግጥ ምጣኔ ሀብታዊና ኢንቨስትመንታዊ የጋርዮሽ ግንኙነቶችን ለማጠናከር የተደረገ ጉዞ መሆኑን የመንግሥቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡ እውነት ነው ይኼኛውም ጉዳይ በውይይቱ ወቅት መነሳቱ የማይቀር ነው፡፡ ምክንያቱም ሳዑዲ በኢትዮጵያ በዛ ያለ መዋዕለ ሀብት ካላቸው አገሮች አንዷ ነችና፡፡ ይሁንና የሰላምና የፀጥታ ጉዳይ፣ የየመን ጦርነትና የሳዑዲ መራሹ ጣልቃ ገብነት፣ የኤርትራና የባሕረ ሰላጤው አገሮች ወቅታዊ ሽርክና፣ ወዘተ የጠቅላይ ሚኒስትሩና የንጉሡ መወያያ እንደሚሆን አስቀድሞ የተገመተ ጉዳይ ነው፡፡

ለማንኛውም ከአቶ ኃይለ ማርያም የሳዑዲ ጉብኝት በኋላ የንጉሡ መልዕክተኞች አዲስ አበባንና ህዳሴ ግድብን መጎብኘታቸው የግብፅን ጨጓራ ለመላጥ መሆኑ ዕእሙን ነው፡፡ ዋነኛው ምክንያት ደግሞ ከላይ የተገለጸው የካይሮና የሪያድ ፍቅር መጨረስ ነው፡፡ ከዚህ ሃልዮት የሚነሳው ጥያቄ ‹ይህ የሳዑዲ ጠብ እርግፍ ማለት ስትራቴጂካዊ ነው ወይስ ሥልታዊ?› የሚለው ነው፡፡ በዚህ ጸሐፊ እምነትና በአንዳንድ የቀንዱ ፖለቲካ ታዛቢዎች አስተያየት ግን የሳኢዱ ግንኙነት ሥልታዊ ነው፡፡ ዘላቂ ጥቅምን ያላሰላ፣ ግልብ ምክንያትን ያዘለና መነሻውን ወቅታዊ ቁርሾ ያደረገ ነው፡፡

የዛሬ ዓመት አካባቢ በግብፅ መገናኛ ብዙኃን ሰፊ ሽፋን ካገኙ ዜናዎች መካከል ኢትዮጵያንና ግብፅን ለማደራደር ሳዑዲ እየጣረች ነው የሚለው ዋነኛው ነበር፡፡ በዚያን ሰሞን ካይሮና ሪያድ እብስ ያለ ፍቅር ውስጥ ሆነው የደሴት ስጦታ እስከ መለዋወጥ ደርሰው ነበር፡፡ ሆኖም እንደ ቀዝቃዛው የዓለም ጦርነት ዓለምን በሁለት ጎራ የከፈለው የሶሪያ ጦርነት ዱብ እዳ ሆነና ሳዑዲንና ግብፅን ሆድ አባባሳቸው፡፡

ለዚያም ነው ሳዑዲ፣ ግብፅ ከቆመችበት የፖለቲካ ትወራና የዲፕሎማሲ ጥግ በተቃራኒ ሆና መታየት የጀመረችው፡፡ ህዳሴ ግድብ ድረስ በመምጣት ጉብኝት ያደረገችውም ግብፅን በውጭ ጉዳይ ፖለቲካዋ ላይ  ወደ ራሷ ለማምጣት አስገዳጅ መላ በመሻት ነው፡፡ የሳዑዲ አለሁ ባይነት ዘላቂ ጥቅምን ያነገበና ስትራቴጂካዊ ሳይሆን ቅርብ አዳሪነት የተጠናወተውና ሥልታዊ ነው መባሉም ለዚህ ነው፡፡

እናም ሳዑዲም ሆነች ኳታር ከኢትዮጵያ ጋር እየፈጠሩ ያሉትን ወቅታዊና ሥልታዊ አጋርነት፣ ወደ ስትራቴጂካዊነትና ዘላቂ ወዳጅነት በመቀየር በኩል መንግሥት ትልቅ የቤት ሥራ ከፊቱ አለ፡፡ የአቶ ኃይለ ማርያም አስተዳደር አጋጣሚውን ተጠቅሞ ዓረቦቹን ከልማትና ኢንቨስትመንት ባሻገር፣ የሰላምና የፀጥታ ወዳጅ ሊያደርጋቸው ይገባል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው ጋዜጠኛ ሲሆኑ፣ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው enn.newsroom@gmail.com  ማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

 

Standard (Image)
Viewing all 231 articles
Browse latest View live