Quantcast
Channel: ዓለም
Viewing all articles
Browse latest Browse all 231

የምክር ቤቱ ሥራ ከግል ፍላጎት አንፃር አይመዘንም

$
0
0

በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት የኢንፎርሜሽንና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት
እውነቱ ምንአየሁ የተባሉ ጸሐፊ መጋቢት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በወጣው የሪፖርተር ጋዜጣ የረቡዕ ዕትም ቅፅ 21 ቁጥር 1661 ‘’ልናገር’’ በሚለው ዓምድ ሥር በገጽ 17 እና 22 ላይ፣ ‘’ከፀረ ሙስና ተቋም ውስጥ የፍትሕ ሥራን መቀነስ የፀረ ሙስና ትግልን አለማወቅ ነው’’ በሚል ርዕስ የሰጡት አስተያየት ለንባብ በቅቷል።
ለአስተያየቱ መነሻ የሆነው ጉዳይ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ እንዲቋቋም የሚጠይቅ ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቅረቡና በይዘቱም የወንጀል ጉዳዮችን የመመርመርና የመክሰስ ሥልጣንን ከሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ ከገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና ከንግድ ውድድርና ሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን በማንሳት ለፖሊስና ለዓቃቤ ሕግ መስጠቱ ነው፡፡
 በሙስና ወንጀል ላይ የሚደረግ የምርምራና የመክሰስ ሥልጣን  ከኮሚሽኑ እንዳይወጣ ጸሐፊው ፍላጎት አላቸው፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ ኮሚሽኑ በጊዜ ሒደት ‘’በፀረ ሙስና ትግል ሙያ ከፍተኛ ልምድና ክህሎት ያዳበረ’’ መሆኑ፣ ሥልጣኑ ተቀንሶ የሚተላለፍላቸው ዓቃቤ ሕግና ፖሊስ በሥነ ምግባር ከኮሚሽኑ የባሱ መሆናቸውና ውሳኔው በጥናት ላይ የተመሠረተ አይደለም የሚሉ ናቸው፡፡ እነዚህን ጉዳዮች ከግምት ውስጥ በማስገባት የኮሚሽኑ ሥልጣን ተቀንሶ ወደ ዓቃቤ ሕግና ፖሊስ እንዳይሄድ ረቂቅ አዋጁ ላይ የጸሐፊውን ፍላጎት የሚመልስ ውሳኔ ምክር ቤቱ እንዲያስተላልፍ የቀረበው ጽሑፍ ይጠይቃል፡፡
ምክር ቤቱ የተለየ ውሳኔ በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ የሚያስተላልፍ ከሆነ፣ ምክር ቤቱ ለተቋሙ ጥሩ ዕይታ ያለው ባለመሆኑና የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረኮቹም ለይስሙሉ በመሆናቸው ነው ወደሚል ድምዳሜ እንደሚያደርሳቸውም የቀረበው ጽሑፍ ያመለክታል፡፡ ይህም የተለየ ሐሳብን ላለማስተናገድ ጸሐፊው ምክንያት ያዘጋጁ መሆኑን ያሳያል፡፡ የጸሐፊው ምክንያቶች የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን የማይመለከቱ ስለመሆናቸው የተወሰነ ማብራርያ ይቀርባል፡፡
ጥሩ ዕይታ ስለመኖሩ
የኮሚሽኑ ዓላማዎች አሁንም የሚያስፈልጉ ናቸው፡፡ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦት የሥርዓቱ አደጋዎች በመሆናቸው የተጠናከረ ትግል እየተካሄደባቸው ነው፡፡ የሙስና ወንጀል የፈጸሙትን ኅብረተሰቡ ለኮሚሽኑ በመጠቆም እንዲመረመሩ፣ እንዲከሰሱ፣ እንዲቀጡና የተመዘበረ ሀብት እንዲመለስ እያደረገ ነው፡፡ መንግሥትም ለዚህ ትግል ሕዝቡ ከጎኑ በስፋት እንዲሠለፍ እየሠራ ይገኛል፡፡
ለሥርዓቱ አደጋ የሆኑ ጉዳዮችን ለመከላከል አንድ መሥሪያ ሆኖ የሚያገለግልን ተቋም  አምስተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥሩ ዕይታ ሊነፍገው አይችልም፡፡ ሙስና የሕዝቡ የልማትና የዕድገት ጉዞ ፀር ነው፡፡ የምክር ቤቱ አባላት በሕዝቡ የተመረጡት ልማት ለማምጣትና ዕድገት ለማስመዝገብ ነው፡፡ ሙስና ከተልዕኮቸው ጋር ይፃረራል፡፡ የኮሚሽኑ ዓላማዎች ደግሞ የምክር ቤቱን ተልዕኮ የሚጠብቅ ነው፡፡ የምክር ቤቱና የኮሚሽን የጉዞ አቅጣጫ ተመሳሳይና ተደጋጋፊ ነው፡፡ በመሆኑም ምክር ቤቱ ለተቋሙ ጥሩ ዕይታ የሚያጣበት ምንም የተለየ ምክንያት የለም፡፡
ይህ ማለት ደግሞ ምክር ቤቱ የኮሚሽኑን ሥራ አብጠርጥሮ አይፈትሽ ማለት አይደለም፡፡ ሕገ መንግሥቱ በሰጠው ሥልጣን መሠረት ያለውን ጠንካራና ደካማ ጎን ይፈትሻል፡፡ የመሰለውንም ዕርምጃ ይወስዳል፡፡ ይኼ ለድርድር የሚቀርብ ነገር አይደለም፡፡ ምክር ቤቱ በ2008 በጀት ዓመት ሁለት ጊዜ ኮሚሽኑን ገምግሟል፡፡ ጥንካሬን ከማሳየት ባሻገር የታዩ ጎላ ጎላ ያሉ ዕጥረቶችንም አውጥቶ አሳይቷል፡፡ በሚዲያም ኅብረተሰቡ እንዲያውቃቸውም አድርጓል፡፡ ሕዝቡ ከምክር ቤቱ የሚጠብቀውም እንደዚህ ዓይነት ሥራዎችን እንዲያከናውን ነው፡፡ ይህን ተግባር ምክር ቤቱ የፈጸመው ለተቋሙ ጥሩ ዕይታ ባለመኖሩ ነው፡፡ የጸሐፊው አስተያየት ፍፁም የተሳሳተ ነው፡፡ ጸሐፊው ይኼን አስተያየት አቀረቡም አላቀረቡም ሒደትን መግለጽ የማይቀበል፣ ግን ውጤትን የሚጠይቅ ጠንካራ ግምገማ ኮሚሽኑንም ሆነ ሌሎች የአስፈጻሚ ተቋማትን በቀጣይም የሚጠብቅ ይሆናል፡፡
የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅንም ኮሚሽኑን ለመበቀል አይጠቀምም፡፡ በረቂቅ አዋጁ ላይ የሚያደርገው ምርመራና የሚደርሰበት ግኝት የሚደርስበትን ድምዳሜ ይወስናል፡፡ ግኝቱ ‘’የፀረ ሙስና ተቋም መነካት የለበትም‘’ ካለ የፍትሕ ሥራ ከኮሚሽኑ አይቀነስም፡፡ በዳበረ ሙያውና ልምዱ ኅብረተሰቡን ያገለግላል፡፡ ግኝቱ ወደዚህ ድምዳሜ ካላደረሰ ጸሐፊው የፈሩት ነገር ይደርሳል፡፡ ሙስናን የመመርመርና የመክሰስ ሥራ ሥልጣን በቅደም ተከተል የፖሊስና የዓቃቤ ሕግ ይሆናል፡፡ ይኼ የተሻለ ልምድና ዕውቀት ወደዚያ ይሸጋገራል፡፡  
ይኼን ከግምገማ ጋር ማያያዝ ተገቢ አይደለም፡፡ የአስፈጻሚ አካላት የአደረጃጀት ጉዳይ የአምስተኛው ምክር ቤት አንደኛ ዓመት የሥራ ዘመን የቅድሚያ ሥራ እንደሆነ ፕሬዚዳንቱ በመክፈቻ ንግግራቸው የጠቆሙት ሥራ ነው፡፡ በመስከረም 2008 ዓ.ም. የአስፈፃሚ አካላትን አደረጃጀት ማሻሻያ ጥናት የውሳኔ ሐሳብና የአስፈጻሚ አካላትን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን የቀረበ ረቂቅ አዋጅ ምክር ቤቱ መርምሮ በማፅደቅ ነው፣ የፕሬዚዳንቱን ቃል በሥራ መተርጎም የጀመረው፡፡ የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ማቋቋሚያና የሌሎች የአስፈፃሚ አካላት ማቋቋሚያ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጆች ለምክር ቤቱ የቀረቡት ከዚህ የፕሬዚዳንቱ የመክፈቻ ንግግር ተነስቶ ነው፡፡ የአስፈጻሚ አካላት የአደረጃጀት ጉዳይ ከመስከረም ወር ጀምሮ እየተከናወነ ያለ ተግባር ነው፡፡ ኮሚሽኑ የተገመገመው ደግሞ ይህ ሥራ ከተጀመረ በኋላ ነው፡፡ ስለዚህ ነው ግምገማውን ከአደረጃጀቱ ሥራ ጋር ማያያዝ ተገቢ አይደለም የምንለው፡፡
ምክር ቤቱ በአደረጃጀቱ ጉዳይ ላይ የሚደርስበት ውሳኔ ከተለመደው የምክር ቤቱ የሕግ ማውጣት ተግባር ጋር ብቻ ተያይዞ ነው ሊመዘን የሚገባው፡፡ ከጸሐፊው ፍላጎት ጋር ተያይዞ የምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ ተግባር ሊመዘን እንደማይገባ፣ መልዕክታችንን ለሪፖርተር ጋዜጣ አንባቢያን ለማድረስ እንፈልጋለን፡፡
 የሕዝብ የውይይት መድረኮች ውጤታማነት
የሕዝብ የውይይት መድረኮች የዴሞክራሲ መገለጫዎች ናቸው፡፡ ሕዝቡ በመንግሥት የዕለት ከዕለት ሥራዎች እየተሳተፈ የመንግሥት የውሳኔ አካል የሚሆንበት አግባብ ነው፡፡
ምክር ቤቱ ረቂቅ አዋጁን ለሕዝብ ውይይት ሲያቀርብ  የሁለት ወገኖች ፍላጎት እንዲቻቻል ነው፡፡ የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግን መቋቋም የሚፈልጉ ወገኖች አሉ፡፡ የማይፈልጉም እንደዚሁ፡፡ መድረኩን በመጠቀም ሁለቱም ወገኖች ያላቸውን ልዩነት ያቻችላሉ፡፡ ሁሉም ይግባባሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡ በአንዱ መጎዳት ሌላው ሙሉ በሙሉ ይጠቀማል ተብሎም አይታሰብም፡፡ ሰጥቶ በመቀበል መርህ ልዩነት ያላቸው ወገኖች ይቻቻላሉ፡፡ የትራንስፖርት አገልግሎት አቅራቢ ተሳፋሪ እንዲጠፋበት አይፈልግም፡፡ ያቀረበው የክፍያ ተመን የአቅርቦቱን ያህል ተሳፋሪ የሚያስተናግድበት ደረጃ ማድረሱ አይቀርም፡፡ አገልግሎት ማቅረቡና በአገልግሎቱ መጠቀም የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች በመሆናቸው ነው፡፡ የሕዝብ ተሳትፎ መድረክ ሚናም ይኼው ነው፡፡
ሕገ መንግሥቱ የተለያዩ የሕዝብ ተሳትፎ ደረጃዎችን የያዘ ሲሆን፣ ምክር ቤቱም እንደ ሥራው ዓይነት መረጃ ከመስጠትና ከመቀበል አንስቶ እስከ ከፍተኛው ደረጃ ያሉትን የሕዝብ ተሳትፎ ደረጃዎች በሥራ ላይ እያዋለ ይገኛል፡፡
በተለይም በረቂቅ አዋጆች ላይ የሚዘጋጁ የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረኮች በከፍተኛ ደረጃ የሕዝብ ተሳትፎ የሚወሰዱ ናቸው፡፡ ተሳታፊዎቹ ያቀረቡዋቸው አስተያየቶች በቋሚ ኮሚቴው ተደግፈው የኮሚቴው የሪፖርትና የውሳኔ ሐሳብ አካል ሆነው ምክር ቤቱም ከቀረቡና ምክር ቤቱ ከደገፋቸው አስተያየቶቹ የምክር ቤቱ ውሳኔ ይሆናሉ፡፡ ሕግ ማውጣት የመንግሥት  አንዱ የዕለት ከዕለት ሥራ ነው፡፡ በሕዝብ አስተያየት መድረክ የሚሳተፍም በዚህ መልክ የመንግሥት የውሳኔ አካል ይሆናል፡፡
የሕዝብ አስተያየት መድረክ ካለው ጠቀሜታ አንፃር የበለጠ እንዲጠናከር ምክር ቤቱ የምክር ቤቱን የአሠራርና የአባላት የሥነ ምግባር ደንብ አሻሽሏል፡፡ ከማሻሻያው አንዱ በቅርቡ ነፃ የስልክ መስመር አገልግሎት ይኖራል፡፡ ይህም ተሳትፎውን የኤኮኖሚ ጥያቄ እንዳይገድብ ያደርጋል፡፡ መድረኩ ለሁሉም እኩል ያገለግላል፡፡
ሌላው ነገር ተሳታፊው እንዲካተት ያነሷቸው አስተያየቶች በግብዓትነት የሚካተቱ ከሆነም ከነምክንያታቸው፣ የማይካተቱ ከሆኑም የማይካተቱበትን ምክንያት መድረኩን ያዘጋጀው ኮሚቴ እንዲያብራራ ደንቡ ያስገድዳል፡፡ ለሚመለከታቸው አካላትም እንዲያሳውቅም እንደዚሁ ደንቡ ያስገድዳል፡፡  
መንግሥት ወይም ምክር ቤቱ የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረክ የሕግ አካል አድርጎ የቀረፀውና ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ ጉዳዮች ውስጥ የገባው የጉዳዩን አስፈላጊነት አምኖ ነው፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃም ተቀባይነት ያለው አሠራር ነው፡፡ ይኼን አሠራር ለማሳደግ ተቋማት ጭምር ተቋቁመው እየሠሩ ለመሆናቸው የአውሮፓ ልምድ ያሳያል፡፡
ይህን የታወቀ አሠራር ጸሐፊው፣ ‘’ለይስሙላ በቲቪ ኑና ተወያዩ ማለት ተገቢ አይመስለኝም‘’ በማለት ማንኳሰሳቸው ትክክል አይደለም፡፡
ጸሐፊው ይኼን አሠራር ያጥላሉት ከጥናት ጋር አያይዘው ነው፡፡ ረቂቅ አዋጁን ያቀረበው አካል ለአደረጃጀት ሥራው ጥናት ማካሄዱን የገለጸ ሲሆን፣ ሌሎችም መረጃው እንዳላቸው የገለጹበት ሁኔታ አለ፡፡ ረቂቅ አዋጆች ለቋሚ ኮሚቴ ለምርመራ የሚመሩትም የቀረበው ረቂቅ ሕግ አስፈላጊውን የሕግ አወጣጥ ደረጃ አልፎ ስለመምጣቱ ግንዛቤ ለመያዝ ጭምር ነው፡፡ የተፈለገውን ደረጃ አሟልቶ ረቂቅ አዋጁ ለምክር ቤቱ ካልቀረበ ረቂቅ አዋጁ ለአስፈጻሚ አካሉ ይመለሳል፡፡ የሕዝብ የውይይት መድረኩ ይህን ዕርምጃ ለመውሰድም ያገለግላል፡፡
የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረክ ሰፊ ጥቅም ያለው ቢሆን ጸሐፊው ካደረባቸው ስሜት በመነሳት አሠራሩን ለማንኳሰስ የሞከሩ ሲሆን፣ አሠራሩ ግን ዓለም አቀፋዊ የሆነና የምርጫ ዴሞክራሲ እንደሆነ ለአንባቢያን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡  የጸሐፊው አስተያየት የብስጭት ስለሆነ ምክር ቤቱን ቀርቶ ለምክር ቤቱ ተጠሪ የሆኑ ተቋማትን ጭምር ስለሚያብጠለጥል ወደ ዝርዝር ከመግባት ተቆጥበናል፡፡  
ማጠቃለያ
ጸሐፊው የረቂቅ አዋጁን መውጣት አስመልክቶ የመሰላቸውን ሐሳብ ሊያራምዱ ይችላሉ፡፡ ግን ምክር ቤቱ በሕገ መንግሥቱ መሠረት የሚያከናውናቸውን ተግባራት በምንም መልኩ መቀበል ይገባቸዋል፡፡ የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ ዘጠኝ መከበር ይኖርበታል፡፡ ምክር ቤቱም በትክክለኛ መንገድ የማይጓዝ ከሆነ ማረም ተገቢ ነው፡፡ ግን ጽሑፉ ለምክር ቤቱ ያሳየው ዕርምት የለም፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ጉድለት ሲኖር ከምክር ቤቱ ጋር ተቀራርቦ በመወያየት መፍታት እንደሚቻል ለመጠቆም እንወዳለን፡፡ የተሳሳተ ነገር ይዞ አንባቢ ፊት ከመቅረብ በፊት፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው namssialka@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡  

 

Standard (Image)

Viewing all articles
Browse latest Browse all 231

Trending Articles