Quantcast
Channel: ዓለም
Viewing all 231 articles
Browse latest View live

የምክር ቤቱ ሥራ ከግል ፍላጎት አንፃር አይመዘንም

$
0
0

በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት የኢንፎርሜሽንና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት
እውነቱ ምንአየሁ የተባሉ ጸሐፊ መጋቢት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በወጣው የሪፖርተር ጋዜጣ የረቡዕ ዕትም ቅፅ 21 ቁጥር 1661 ‘’ልናገር’’ በሚለው ዓምድ ሥር በገጽ 17 እና 22 ላይ፣ ‘’ከፀረ ሙስና ተቋም ውስጥ የፍትሕ ሥራን መቀነስ የፀረ ሙስና ትግልን አለማወቅ ነው’’ በሚል ርዕስ የሰጡት አስተያየት ለንባብ በቅቷል።
ለአስተያየቱ መነሻ የሆነው ጉዳይ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ እንዲቋቋም የሚጠይቅ ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቅረቡና በይዘቱም የወንጀል ጉዳዮችን የመመርመርና የመክሰስ ሥልጣንን ከሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ ከገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና ከንግድ ውድድርና ሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን በማንሳት ለፖሊስና ለዓቃቤ ሕግ መስጠቱ ነው፡፡
 በሙስና ወንጀል ላይ የሚደረግ የምርምራና የመክሰስ ሥልጣን  ከኮሚሽኑ እንዳይወጣ ጸሐፊው ፍላጎት አላቸው፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ ኮሚሽኑ በጊዜ ሒደት ‘’በፀረ ሙስና ትግል ሙያ ከፍተኛ ልምድና ክህሎት ያዳበረ’’ መሆኑ፣ ሥልጣኑ ተቀንሶ የሚተላለፍላቸው ዓቃቤ ሕግና ፖሊስ በሥነ ምግባር ከኮሚሽኑ የባሱ መሆናቸውና ውሳኔው በጥናት ላይ የተመሠረተ አይደለም የሚሉ ናቸው፡፡ እነዚህን ጉዳዮች ከግምት ውስጥ በማስገባት የኮሚሽኑ ሥልጣን ተቀንሶ ወደ ዓቃቤ ሕግና ፖሊስ እንዳይሄድ ረቂቅ አዋጁ ላይ የጸሐፊውን ፍላጎት የሚመልስ ውሳኔ ምክር ቤቱ እንዲያስተላልፍ የቀረበው ጽሑፍ ይጠይቃል፡፡
ምክር ቤቱ የተለየ ውሳኔ በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ የሚያስተላልፍ ከሆነ፣ ምክር ቤቱ ለተቋሙ ጥሩ ዕይታ ያለው ባለመሆኑና የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረኮቹም ለይስሙሉ በመሆናቸው ነው ወደሚል ድምዳሜ እንደሚያደርሳቸውም የቀረበው ጽሑፍ ያመለክታል፡፡ ይህም የተለየ ሐሳብን ላለማስተናገድ ጸሐፊው ምክንያት ያዘጋጁ መሆኑን ያሳያል፡፡ የጸሐፊው ምክንያቶች የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን የማይመለከቱ ስለመሆናቸው የተወሰነ ማብራርያ ይቀርባል፡፡
ጥሩ ዕይታ ስለመኖሩ
የኮሚሽኑ ዓላማዎች አሁንም የሚያስፈልጉ ናቸው፡፡ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦት የሥርዓቱ አደጋዎች በመሆናቸው የተጠናከረ ትግል እየተካሄደባቸው ነው፡፡ የሙስና ወንጀል የፈጸሙትን ኅብረተሰቡ ለኮሚሽኑ በመጠቆም እንዲመረመሩ፣ እንዲከሰሱ፣ እንዲቀጡና የተመዘበረ ሀብት እንዲመለስ እያደረገ ነው፡፡ መንግሥትም ለዚህ ትግል ሕዝቡ ከጎኑ በስፋት እንዲሠለፍ እየሠራ ይገኛል፡፡
ለሥርዓቱ አደጋ የሆኑ ጉዳዮችን ለመከላከል አንድ መሥሪያ ሆኖ የሚያገለግልን ተቋም  አምስተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥሩ ዕይታ ሊነፍገው አይችልም፡፡ ሙስና የሕዝቡ የልማትና የዕድገት ጉዞ ፀር ነው፡፡ የምክር ቤቱ አባላት በሕዝቡ የተመረጡት ልማት ለማምጣትና ዕድገት ለማስመዝገብ ነው፡፡ ሙስና ከተልዕኮቸው ጋር ይፃረራል፡፡ የኮሚሽኑ ዓላማዎች ደግሞ የምክር ቤቱን ተልዕኮ የሚጠብቅ ነው፡፡ የምክር ቤቱና የኮሚሽን የጉዞ አቅጣጫ ተመሳሳይና ተደጋጋፊ ነው፡፡ በመሆኑም ምክር ቤቱ ለተቋሙ ጥሩ ዕይታ የሚያጣበት ምንም የተለየ ምክንያት የለም፡፡
ይህ ማለት ደግሞ ምክር ቤቱ የኮሚሽኑን ሥራ አብጠርጥሮ አይፈትሽ ማለት አይደለም፡፡ ሕገ መንግሥቱ በሰጠው ሥልጣን መሠረት ያለውን ጠንካራና ደካማ ጎን ይፈትሻል፡፡ የመሰለውንም ዕርምጃ ይወስዳል፡፡ ይኼ ለድርድር የሚቀርብ ነገር አይደለም፡፡ ምክር ቤቱ በ2008 በጀት ዓመት ሁለት ጊዜ ኮሚሽኑን ገምግሟል፡፡ ጥንካሬን ከማሳየት ባሻገር የታዩ ጎላ ጎላ ያሉ ዕጥረቶችንም አውጥቶ አሳይቷል፡፡ በሚዲያም ኅብረተሰቡ እንዲያውቃቸውም አድርጓል፡፡ ሕዝቡ ከምክር ቤቱ የሚጠብቀውም እንደዚህ ዓይነት ሥራዎችን እንዲያከናውን ነው፡፡ ይህን ተግባር ምክር ቤቱ የፈጸመው ለተቋሙ ጥሩ ዕይታ ባለመኖሩ ነው፡፡ የጸሐፊው አስተያየት ፍፁም የተሳሳተ ነው፡፡ ጸሐፊው ይኼን አስተያየት አቀረቡም አላቀረቡም ሒደትን መግለጽ የማይቀበል፣ ግን ውጤትን የሚጠይቅ ጠንካራ ግምገማ ኮሚሽኑንም ሆነ ሌሎች የአስፈጻሚ ተቋማትን በቀጣይም የሚጠብቅ ይሆናል፡፡
የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅንም ኮሚሽኑን ለመበቀል አይጠቀምም፡፡ በረቂቅ አዋጁ ላይ የሚያደርገው ምርመራና የሚደርሰበት ግኝት የሚደርስበትን ድምዳሜ ይወስናል፡፡ ግኝቱ ‘’የፀረ ሙስና ተቋም መነካት የለበትም‘’ ካለ የፍትሕ ሥራ ከኮሚሽኑ አይቀነስም፡፡ በዳበረ ሙያውና ልምዱ ኅብረተሰቡን ያገለግላል፡፡ ግኝቱ ወደዚህ ድምዳሜ ካላደረሰ ጸሐፊው የፈሩት ነገር ይደርሳል፡፡ ሙስናን የመመርመርና የመክሰስ ሥራ ሥልጣን በቅደም ተከተል የፖሊስና የዓቃቤ ሕግ ይሆናል፡፡ ይኼ የተሻለ ልምድና ዕውቀት ወደዚያ ይሸጋገራል፡፡  
ይኼን ከግምገማ ጋር ማያያዝ ተገቢ አይደለም፡፡ የአስፈጻሚ አካላት የአደረጃጀት ጉዳይ የአምስተኛው ምክር ቤት አንደኛ ዓመት የሥራ ዘመን የቅድሚያ ሥራ እንደሆነ ፕሬዚዳንቱ በመክፈቻ ንግግራቸው የጠቆሙት ሥራ ነው፡፡ በመስከረም 2008 ዓ.ም. የአስፈፃሚ አካላትን አደረጃጀት ማሻሻያ ጥናት የውሳኔ ሐሳብና የአስፈጻሚ አካላትን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን የቀረበ ረቂቅ አዋጅ ምክር ቤቱ መርምሮ በማፅደቅ ነው፣ የፕሬዚዳንቱን ቃል በሥራ መተርጎም የጀመረው፡፡ የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ማቋቋሚያና የሌሎች የአስፈፃሚ አካላት ማቋቋሚያ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጆች ለምክር ቤቱ የቀረቡት ከዚህ የፕሬዚዳንቱ የመክፈቻ ንግግር ተነስቶ ነው፡፡ የአስፈጻሚ አካላት የአደረጃጀት ጉዳይ ከመስከረም ወር ጀምሮ እየተከናወነ ያለ ተግባር ነው፡፡ ኮሚሽኑ የተገመገመው ደግሞ ይህ ሥራ ከተጀመረ በኋላ ነው፡፡ ስለዚህ ነው ግምገማውን ከአደረጃጀቱ ሥራ ጋር ማያያዝ ተገቢ አይደለም የምንለው፡፡
ምክር ቤቱ በአደረጃጀቱ ጉዳይ ላይ የሚደርስበት ውሳኔ ከተለመደው የምክር ቤቱ የሕግ ማውጣት ተግባር ጋር ብቻ ተያይዞ ነው ሊመዘን የሚገባው፡፡ ከጸሐፊው ፍላጎት ጋር ተያይዞ የምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ ተግባር ሊመዘን እንደማይገባ፣ መልዕክታችንን ለሪፖርተር ጋዜጣ አንባቢያን ለማድረስ እንፈልጋለን፡፡
 የሕዝብ የውይይት መድረኮች ውጤታማነት
የሕዝብ የውይይት መድረኮች የዴሞክራሲ መገለጫዎች ናቸው፡፡ ሕዝቡ በመንግሥት የዕለት ከዕለት ሥራዎች እየተሳተፈ የመንግሥት የውሳኔ አካል የሚሆንበት አግባብ ነው፡፡
ምክር ቤቱ ረቂቅ አዋጁን ለሕዝብ ውይይት ሲያቀርብ  የሁለት ወገኖች ፍላጎት እንዲቻቻል ነው፡፡ የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግን መቋቋም የሚፈልጉ ወገኖች አሉ፡፡ የማይፈልጉም እንደዚሁ፡፡ መድረኩን በመጠቀም ሁለቱም ወገኖች ያላቸውን ልዩነት ያቻችላሉ፡፡ ሁሉም ይግባባሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡ በአንዱ መጎዳት ሌላው ሙሉ በሙሉ ይጠቀማል ተብሎም አይታሰብም፡፡ ሰጥቶ በመቀበል መርህ ልዩነት ያላቸው ወገኖች ይቻቻላሉ፡፡ የትራንስፖርት አገልግሎት አቅራቢ ተሳፋሪ እንዲጠፋበት አይፈልግም፡፡ ያቀረበው የክፍያ ተመን የአቅርቦቱን ያህል ተሳፋሪ የሚያስተናግድበት ደረጃ ማድረሱ አይቀርም፡፡ አገልግሎት ማቅረቡና በአገልግሎቱ መጠቀም የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች በመሆናቸው ነው፡፡ የሕዝብ ተሳትፎ መድረክ ሚናም ይኼው ነው፡፡
ሕገ መንግሥቱ የተለያዩ የሕዝብ ተሳትፎ ደረጃዎችን የያዘ ሲሆን፣ ምክር ቤቱም እንደ ሥራው ዓይነት መረጃ ከመስጠትና ከመቀበል አንስቶ እስከ ከፍተኛው ደረጃ ያሉትን የሕዝብ ተሳትፎ ደረጃዎች በሥራ ላይ እያዋለ ይገኛል፡፡
በተለይም በረቂቅ አዋጆች ላይ የሚዘጋጁ የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረኮች በከፍተኛ ደረጃ የሕዝብ ተሳትፎ የሚወሰዱ ናቸው፡፡ ተሳታፊዎቹ ያቀረቡዋቸው አስተያየቶች በቋሚ ኮሚቴው ተደግፈው የኮሚቴው የሪፖርትና የውሳኔ ሐሳብ አካል ሆነው ምክር ቤቱም ከቀረቡና ምክር ቤቱ ከደገፋቸው አስተያየቶቹ የምክር ቤቱ ውሳኔ ይሆናሉ፡፡ ሕግ ማውጣት የመንግሥት  አንዱ የዕለት ከዕለት ሥራ ነው፡፡ በሕዝብ አስተያየት መድረክ የሚሳተፍም በዚህ መልክ የመንግሥት የውሳኔ አካል ይሆናል፡፡
የሕዝብ አስተያየት መድረክ ካለው ጠቀሜታ አንፃር የበለጠ እንዲጠናከር ምክር ቤቱ የምክር ቤቱን የአሠራርና የአባላት የሥነ ምግባር ደንብ አሻሽሏል፡፡ ከማሻሻያው አንዱ በቅርቡ ነፃ የስልክ መስመር አገልግሎት ይኖራል፡፡ ይህም ተሳትፎውን የኤኮኖሚ ጥያቄ እንዳይገድብ ያደርጋል፡፡ መድረኩ ለሁሉም እኩል ያገለግላል፡፡
ሌላው ነገር ተሳታፊው እንዲካተት ያነሷቸው አስተያየቶች በግብዓትነት የሚካተቱ ከሆነም ከነምክንያታቸው፣ የማይካተቱ ከሆኑም የማይካተቱበትን ምክንያት መድረኩን ያዘጋጀው ኮሚቴ እንዲያብራራ ደንቡ ያስገድዳል፡፡ ለሚመለከታቸው አካላትም እንዲያሳውቅም እንደዚሁ ደንቡ ያስገድዳል፡፡  
መንግሥት ወይም ምክር ቤቱ የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረክ የሕግ አካል አድርጎ የቀረፀውና ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ ጉዳዮች ውስጥ የገባው የጉዳዩን አስፈላጊነት አምኖ ነው፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃም ተቀባይነት ያለው አሠራር ነው፡፡ ይኼን አሠራር ለማሳደግ ተቋማት ጭምር ተቋቁመው እየሠሩ ለመሆናቸው የአውሮፓ ልምድ ያሳያል፡፡
ይህን የታወቀ አሠራር ጸሐፊው፣ ‘’ለይስሙላ በቲቪ ኑና ተወያዩ ማለት ተገቢ አይመስለኝም‘’ በማለት ማንኳሰሳቸው ትክክል አይደለም፡፡
ጸሐፊው ይኼን አሠራር ያጥላሉት ከጥናት ጋር አያይዘው ነው፡፡ ረቂቅ አዋጁን ያቀረበው አካል ለአደረጃጀት ሥራው ጥናት ማካሄዱን የገለጸ ሲሆን፣ ሌሎችም መረጃው እንዳላቸው የገለጹበት ሁኔታ አለ፡፡ ረቂቅ አዋጆች ለቋሚ ኮሚቴ ለምርመራ የሚመሩትም የቀረበው ረቂቅ ሕግ አስፈላጊውን የሕግ አወጣጥ ደረጃ አልፎ ስለመምጣቱ ግንዛቤ ለመያዝ ጭምር ነው፡፡ የተፈለገውን ደረጃ አሟልቶ ረቂቅ አዋጁ ለምክር ቤቱ ካልቀረበ ረቂቅ አዋጁ ለአስፈጻሚ አካሉ ይመለሳል፡፡ የሕዝብ የውይይት መድረኩ ይህን ዕርምጃ ለመውሰድም ያገለግላል፡፡
የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረክ ሰፊ ጥቅም ያለው ቢሆን ጸሐፊው ካደረባቸው ስሜት በመነሳት አሠራሩን ለማንኳሰስ የሞከሩ ሲሆን፣ አሠራሩ ግን ዓለም አቀፋዊ የሆነና የምርጫ ዴሞክራሲ እንደሆነ ለአንባቢያን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡  የጸሐፊው አስተያየት የብስጭት ስለሆነ ምክር ቤቱን ቀርቶ ለምክር ቤቱ ተጠሪ የሆኑ ተቋማትን ጭምር ስለሚያብጠለጥል ወደ ዝርዝር ከመግባት ተቆጥበናል፡፡  
ማጠቃለያ
ጸሐፊው የረቂቅ አዋጁን መውጣት አስመልክቶ የመሰላቸውን ሐሳብ ሊያራምዱ ይችላሉ፡፡ ግን ምክር ቤቱ በሕገ መንግሥቱ መሠረት የሚያከናውናቸውን ተግባራት በምንም መልኩ መቀበል ይገባቸዋል፡፡ የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ ዘጠኝ መከበር ይኖርበታል፡፡ ምክር ቤቱም በትክክለኛ መንገድ የማይጓዝ ከሆነ ማረም ተገቢ ነው፡፡ ግን ጽሑፉ ለምክር ቤቱ ያሳየው ዕርምት የለም፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ጉድለት ሲኖር ከምክር ቤቱ ጋር ተቀራርቦ በመወያየት መፍታት እንደሚቻል ለመጠቆም እንወዳለን፡፡ የተሳሳተ ነገር ይዞ አንባቢ ፊት ከመቅረብ በፊት፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው namssialka@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡  

 

Standard (Image)

የቅዱስ ጊዮርጊስ ቡድን ችግሮችን ለመፍታት በአንድ ላይ መቆም አለብን

$
0
0

በቴዎድሮስ መኰንን

እግር ኳስ በአገራችን ከሚወደዱትና ከሚዘወተሩት የስፖርት ዓይነቶች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ ስፖርት ነው፡፡ እግር ኳስ በአገራችን ዝነኛና ተፈቃሪ እንዲሆን መሠረት ከጣሉት ክለቦች ደግሞ ቅዱስ ጊዮርጊስ የአንበሳውን ድርሻ ይይዛል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በቀድሞው አራዳ በአሁኑ አጠራር ፒያሳ አካባቢ በነበሩ ልጆች በ1920ዎቹ መጨረሻ እንደተመሠረተ ይነገርለታል፡፡ ወቅቱ በጣሊያን ወረራ ምክንያት የስፖርት ውድድሮች የተቀዛቀዙበት ጊዜ ሲሆን፣ በዚህ ጊዜ ጣሊያኖች የስፖርት ቢሮ ለተወላጆች የሚሰኝ ክፍል በማቋቋም ኢትዮጵያዊያን በራሳቸው ሜዳ እርስ በራሳቸውና በራሳቸው ተመልካች ፊት ብቻ እንዲጫወቱ ከመደረጉም በላይ፣ የቡድኖቹ ስሞችም ተለውጠው ነበር፡፡ ከነፃነት መልስ አንድ ዓመት በኋላ በ1934 ዓ.ም የስፖርት እንቅስቃሴዎች በተለያየ ሁኔታ ቀጥለው ቅዱስ ጊዮርጊስና የስድስት ኪሎ ቡድን ደጃዝማች ነሲቡ ሜዳ የመጀመሪያውን ከነፃነት መልስ ውድድር አደረጉ፡፡

በ1936 ዓ.ም. የማስታወቂያ ሚኒስትር በነበሩት ክቡር አቶ ዓምደ ሚካኤል ደሳለኝ በተደረገ ድጋፍና በአቶ ይድነቃቸው ተሰማ ኃላፊነትና ጥረት የመጀመሪያው የኢትዮጵያ የስፖርት ቢሮ በማስታወቂያ ሚኒስቴር ግቢ ውስጥ ተቋቋሟል፡፡ በ1940 ዓ.ም. የቅዱስ ጊዮርጊስ፣ የክብር ዘበኛ፣ የምድር ጦርና የአስመራ ቀይ ባህር እግር ኳስ ቡድኖች መሪዎች በጃንሜዳ ሬሲንግ ክለብ ባደረጉት ስብሰባ፣ የፌዴሬሽን ማቋቋም ሐሳብ ለንጉሡ እንዲቀርብ ተደርጎ በወቅቱ ጄኔራል ሙሉጌታ ቡሊ በሰጡት የገንዘብና የቢሮ ድጋፍ በጃንሜዳ ሥራውን እንዲያከናውን ከተደረገ በኋላ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በ1941 ዓ.ም. የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን እንዲቋቋም ተደረገ፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ጋር የማይነጣጠል ሰፊ ትስስር ያለው ሲሆን፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ እንዲመሠረት ያደረጉት እነ ክቡር አቶ ይድነቃቸው ተሰማም ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ምሥረታ በተጨማሪ፣ ለአፍሪካ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ምሥረታ ትልቅ ሚና ከመጫወትም በላይ በአመራር ደረጃ የጎላ አስተዋፅኦ አድርገው አልፈዋል፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ በአሁኑ ጊዜ በቅዱስ ጊዮርጊስ ውስጥ ያሉትን አጠቃላይ ችግሮች በመገምገምና በችግሩ ዙሪያ ተስፋ የቆረጠውንና የተከፋፈለውን ደጋፊ ለማዋሀድ ታሳቢ ያደረገ ሲሆን፣ ከላይ ለመንደርደሪያ የጠቀስኩት ታሪክ በወቅቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ የነበረውን የአመራር ብስለትና ብቃት ለማሳየት ተፈልጎ ነው፡፡

እንደሚታወቀው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከጣሊያን ወረራ በፊት ከ1928 - 1933፣ ከ1933 -1966፣ ከ1966 - 1983፣ እንዲሁም ከ1983 ዓ.ም. በኋላ አምስት ሥርዓተ ጊዜዎችን አሳልፏል፡፡ ከ1933 - 1936 ዓ.ም. ድረስ የነበረው ጊዜ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ምሥረታ፣ ለተወዳጅነቱና አሁን ላገኘው ተቀባይነት ትልቁን መሠረት የጣለበት ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ባለፉት 80 ዓመታት በነበረው የፖለቲካ መለዋወጥ ምክንያት በተለያዩ አደረጃጀቶችና አወቃቀሮች አልፏል፡፡ ከ1983 ዓ.ም. በኋላ መንግሥት በሚከተለው ነፃ ገበያ፣ እንዲሁም በተለያዩ ጊዜያት በስፖርቱ በተደረጉ መዋቅራዊ ለውጦች አማካይነት ስፖርት የጨዋታ ብቻ ሳይሆን የልማት ጉዳይም እንደሆነ በግልጽ ያስቀመጠ ሲሆን፣ የስፖርት ፖሊሲም ተቀርጿል፡፡

ክለቦች ሕዝባዊ ቅርፅ እንዲኖራቸው፣ የተጠሪ ድርጅት ወይም ባለቤት ድጋፍ እንዲኖራቸው፣ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራ፣ ትጥቅና መሣሪያ እንዲመቻችላቸው፣ የተስተካከለና ብቁ አመራር እንዲኖራቸው፣ የስፖርት መርሐ ግብር በተመቻቸ ሥልት እንዲቀየስላቸው፣ ስፖርተኛውን በመንከባከብና በማሳተፍ እንዲያድጉ፣ ባለሙያዎችን ያካተተ እንዲሆኑ፣ ከመንግሥት በጀትና ድጎማ እንዲላቀቁ የሚሉ መርሆችን በማንገብ ነበር፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በተለያዩ ወቅቶች የተለያዩ ለውጦችን ከውስጥም ከውጭም በመጣ ኃይል ለማስተናገድ የተገደደ ሲሆን፣ ከምሥረታው ጀምሮ በቋሚነት የዘለቀው ደጋፊው ለክለቡ ያለው ፍቅር ብቻ ነው፡፡ በዚህም ረገድ ክለቡ ከአሥራ ስድስት ዓመታት በፊት በ1992 ዓ.ም. ሕዝባዊነቱን ሲያገኝ በወቅቱ ያልተደሰተ የቅዱስ ጊዮርጊስ ደጋፊ ነበረ ለማለት እጅግ ይከብዳል፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ1992 ዓ.ም. በኋላ….

የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ሕዝባዊ እንዲሆን በአባላቱ ከተወሰነ በኋላ፣ በመጀመሪያውም ሆነ በታኅሳስ 8 ቀን 1997 ዓ.ም. ተሻሽሎ በፀደቀው በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ በግልጽ እንዳስቀመጠው፣ ጠቅላላ ጉባዔው የክለቡ የመጨረሻው የሥልጣን እርከን ነው፡፡ በወቅቱ የአባልነት መዋጮ ግዴታቸውን የሚወጡ አባላት የጠቅላላ ጉባዔ አባል ብቻ ሳይሆን የክለቡ ባለቤት ጭምርም እንዲሆኑ ሲደነገግ፣ በኅብረቱ ስምምነት መሠረት የሥራ ድርሻ ልዩነት ካልሆነ በስተቀር አንድ ተራ አባልና የቦርዱ ሰብሳቢ እኩል የባለቤትነት መብት እንዳላቸው ይደነግጋል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ላለፉት 16 ዓመታት ከጥቂት ግለሰቦች እንዲሁም ከተለያዩ ድርጅቶች በሚገኝ ድጎማ የሚተዳደር ሲሆን፣ የክለቡ የበላይ ጠባቂ ክቡር ዶ/ር ሼክ ዓሊ አል አሙዲና አቶ አብነት ገብረ መስቀል ክለቡን እስካሁን ለማቆየት ላደረጉት አስተዋፅኦ ምሥጋና ሊቸራቸው ይገባል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ በዘለቄታዊነት አለት ላይ ለማስቀመጥ ግን ገና ብዙ ያልተሠሩ ነገሮች እንዳሉ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ከእነዚህም መካከል ሕዝባዊ መሠረት እንዲኖረው ከማድረግ አንፃር፣ ከላይ በመግቢያዬ ላይ እንደጠቀስኩት የአንድ ክለብ ሕዝባዊነትን ከሚያረጋግጡ ነገሮች ዋነኛው ሕዝባዊነቱን የሚያረጋግጡ ሥራዎች ተፈጻሚነት ሲኖራቸው ነው፡፡ በቅዱስ ጊዮርጊስ መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 10 ንዑስ ቁጥር 10.4 መሠረት የማኅበሩ አባላት በማኅበሩ እንቅስቃሴ የመሳተፍ መብቶች እንዳሉት ሲደነግግ፣ በተጨባጭ የማኅበሩ አመራርና ደጋፊ (አባላት) የሚያገናኙ መድረኮች አለመኖራቸው አባላት በወቅታዊ የክለባቸው ጉዳይ ግልጽ ውይይት ለማድረግ የሚያስችሉዋቸው አጋጣሚዎች አልተመቻቹም፡፡ በሥራ አመራር ቦርዱ፣ በክለቡ አጠቃላይ ሁኔታ፣ በክለቡ የጽሕፈት ቤት አመራርና ቅጥር ዙሪያ በተጨማሪም የክለቡን ቴክኒካል ጉዳዮች የሚመሩ ግለሰቦች ስለሚመረጡበት ሒደት ግልጽነት የጎደለውና መሥፈርቱ ምን እንደሆነ በአግባቡ ስለማይገለጽ፣ ለበርካታ ችግሮች መጋለጡና አሠራሩ ሕዝባዊ ክለብ ከሚያደርገው ተግባራት በተፃራሪ የቆመ መሆኑ ይታያል፡፡

በአንቀጽ 15 ንዑስ ቁጥር 15.1 ‹‹የማኅበርተኞች ጠቅላላ ጉባዔ ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ በሥራ አመራር ቦርድ ወይም በማኅበሩ ፕሬዚዳንት መጠራት ይኖርበታል፤›› ብሎ ያስቀመጠ ሲሆን፣ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቦርድ አመራር አባላት ወይም ፕሬዚዳንቱ ጠቅላላ ጉባዔ ከጠሩ ከአራት ዓመት በላይ መሆኑ ሕዝባዊነቱን የጥያቄ ምልክት ውስጥ የሚከት ነው፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስ እንደ ዕድሜ ጠገብነቱ ሊኖሩት ከሚገቡ ነገሮች አንዱ ተቋማዊ ቅርጽ ሲሆን፣ በማንኛውም ጊዜ በአባላቱ (በጠቅላላ ጉባዔ) የሚመረጡ አመራሮች ገብተው ሊሠሩበት የሚያስችል አሠራርና ሥርዓት የተዘረጋ ባለመሆኑ ክለቡ በጥቂት ግለሰቦች ፈቃድ እንጂ እንደ ተቋም በተዋረድ የሥራ ክፍፍልና ድርሻ የሌለው መሆኑ አሳሳቢ ከመሆኑም በላይ፣ የክለቡን ቀጣይ ዕጣ ፈንታ አደጋ ላይ የሚጥል ነው፡፡ በተጨማሪም በሙያቸው አንቱ የተሰኙ ሰዎች በጊዮርጊስ ዙሪያ ቢኖሩም፣ አሁን ባለው የጓደኝነት አሠራር ክለቡን በመራቃቸው ከፍተኛ የአመራር ብቃት ክፍተት ይታያል፡፡

ግልጽነትን ከማስፈን አንፃር በግል ማኅበራት እንደሚታየው ዓመታዊ የኦዲት ሪፖርት በክለቡ ሰሌዳ ላይ ለማንኛውም አባላት የክለቡን ገቢና ወጪ እንዲያውቁ አለማድረግና ከወቅቱ ጋር የሚሄድ አሠራር አለመሆኑን ያለመገንዘብ ወይም ችላ የማለት ችግር ይታያል፡፡ በኢትዮጵያ ማኅበራት ማደራጃ አዋጅ መሠረት የተቀመጡ የመንግሥት ድንጋጌዎችን አለማክበርና ተፈጻሚ አለማድረግ አንዱ የአመራር ችግር ነው፡፡ ክለቡን ለቅጣት ብሎም ለከፋ አደጋ የሚያጋልጥ መሆኑን በአግባቡ አለመገንዘብ በተጨማሪ፣ በጠቅላላ ጉባዔው የተላለፉ ውሳኔዎችን አለማክበር ለምሳሌ የጽሕፈት ቤቱ ሥራ አስኪያጅ በጠቅላላ ጉባዔ እንዲነሱ ከተደረገ በኋላ ግልጽ ባልሆነ አሠራር በጓሮ እንዲገቡ መደረጋቸው ተጠቃሽ ነው፡፡

እግር ኳስ በአሁኑ ጊዜ ከገንዘብ ጋር ቀጥተኛ የሆነ ግንኙነት ያለው ስፖርት እንደመሆኑ ክለቡ የራሱ ገቢ ሊኖረው የሚያስችል ኢንቨስትመንት ላይ ትኩረት አድርጐ አለመሥራትና በተጨማሪም ከመቼውም ጊዜ በላይ ክለቡን የግለሰቦች ጥገኛ ማድረግ ቀጣይ ህልውናው በከፍተኛ ሁኔታ አደጋ ላይ መጣል በመሆኑ፣ ነገ ሊፈጠሩ የሚችሉ ነገሮችን አርቆ የማየት ችግር አለ፡፡ የግለሰቦችን ሹመት ‹‹ሥዩመ እግዚአብሔር››፣ ሥልጣናቸውን የመለኮት ያህል አግዝፎ ማየትና አልፎ ተርፎም እነዚህን ሰዎች ካስከፋችሁ ክለቡ ችግር ላይ ይወድቃል በሚል አሮጌ አስተሳሰብ ደጋፊውን በፍርኃት ሸብቦ የመያዝ ስልታዊ አካሄድ፣ ከክለቡ ይልቅ በራሳቸው ጥቅም ዓይናቸው የታወረ ጥቂት ግለሰቦች በሚያራግቡት አሉባልታ ለዕድገት እንቅፋት እንደሆኑና የክለቡን ሞት እያፋጠኑ መሆኑ ያለመገንዘብ ሰፍኗል፡፡ ከአመራር ብቃት ጋር ተያይዞ በ2002 ዓ.ም. ሊከናወኑ በታቀዱት አሥራ ሰባት መርሐ ግብሮች መሠረት ተፈጻሚ ሊሆኑ የቻሉት ስድስት ብቻ መሆናቸው ለመጥቀስ የሚከተሉትን ማየት ይበቃል፡፡

የተከናወኑ ሥራዎች

የስፖርት ትጥቅና መሣሪያዎች ማግኘት፣ የመለማመጃ ቦታዎችን ማግኘት፣ የልሳነ ጊዮርጊስ ጋዜጣን በወቅቱ ማሳተም፣ የክቡር አቶ ይድነቃቸው ተሰማ መታሰቢያ ውድድር ማዘጋጀት፣ በተለያዩ የስፖርት ዘርፎች በአገር ውስጥና በኢንተርናሽናል ውድድሮች መሳተፍ፣ የታዳጊ ወጣቶች አካዳሚ ግንባታ ማከናወን (ይህ እስካሁን ያላለቀ ኘሮጀክት ነው)፡፡

ያልተከናወኑ ሥራዎች

የስፖርቱ ማኅበሩን መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻል፣ ቀደም ሲል የወጡ ደንቦችንና መመሪያዎችን ማሻሻል፣ ጠቅላላ ጉባዔ ማከናወን፣ የአባላት ቁጥር ማብዛት፣ ቀጣይ የገቢ ምንጮችን መፍጠር፣ የስቴዲየም ግንባታ መከታተልና ማስፈጸም፣ የመዝናኛ ማዕከልና አገልግሎት ማስፋፋት፣ ለአባላት የስፖርትና የመዝናኛ ኘሮግራም ማስፋፋት፣ በማኅበራዊ ዘርፍ ተሳትፎ ማከናወን፣ ከአቻ ክለቦች ጋር የተጠናከረ ግንኙነት መፍጠር፣ የስፖርት ፋይናንስና አሠራር ኦዲት እንዲደረግ ማድረግ፡፡

ከላይ ከተዘረዘሩት ውስጥ ለመጥቀስ እንደተሞከረው አሁን በአመራር ላይ ያለው የጊዮርጊስ ክለብ ቦርድ ከስድስት ዓመት በፊት ለመሥራት አቅዶ ያልሠራቸው ሥራዎች ሲሆኑ፣ የአመራር ብቃቱን በግልጽ ጥያቄ ውስጥ ከተውታል፡፡ ከዚህ ጋር ሊጠቀሱ የሚገባቸው ነገሮች በተለይም የስፖርት ጽሕፈት ቤቱ አባላትን ከማሰባሰብና በአንድነት ለክለቡ እንዲቆሙ ከማድረግ ይልቅ በተራ አሉባልታ ወሬዎች መከፋፈል፣ ከሌሎች ክለቦችና ከፌዴሬሽኑ ጋር መልካም የሥራ ግንኙነት ከመፍጠር ይልቅ በንትርክና በሕገወጥ ነገሮች ክለቡ መጥፎ ስም እንዲያተርፍ ማድረግ፣ ከምንወደውና ለሌሎች አርዓያ ይሆናል ብለን ከምናስበው ቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ጋር የሚሄድ ባለመሆኑ በአጠቃላይ የአመራር ሰንሰለቱ የተበላሸ ከመሆን አልፎ  አሳሳቢ ያደርገዋል፡፡

በአጠቃላይ ቅዱስ ጊዮርጊስ

ከአገርም አልፎ በአፍሪካም ደረጃ አንጋፋና ቀዳሚ ከሆኑ ክለቦች የመጀመሪያው ረድፍ ላይ የሚገኝ ነው፡፡ አሁን ያለው አሠራር፣ አመራርና ወቅታዊ ሁኔታዎች ፈጽሞ ከክለቡ ጋር የማይሄዱ ናቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በአገር ውስጥ ለሌሎች ክለቦች አርዓያ እንደመሆን ከቅዱስ ጊዮርጊስ በኋላ የተፈጠሩ እንደ ወላይታ ድቻ፣ ኢትዮጵያ ቡና፣ ደደቢት፣ ወዘተ. የመሳሰሉት የተሻለ የክለብ ቅርፅና ራዕይ እንዲሁም ብዛት ያለው ደጋፊ ሊያፈሩ ችለዋል፡፡ በተቃራኒው ቅዱስ ጊዮርጊስ የነበሩትን አንጋፋ ደጋፊዎች እያሸሸና ብልሹ አሠራር ተግባራዊ እያደረገ ሞቱን እያፋጠነ ይገኛል፡፡ ስለዚህ ከመቼውም ጊዜ በላይ የቅዱስ ጊዮርጊስ ደጋፊዎች ይህን ችግር ለመፍታት በአንድነት መቆም ሲኖርብን፣ በጥቂት ሰዎች የግል አጀንዳዎች እንዳንታለልና ክለቡን ያለጥሪት በማስቀረት ታሪካዊ ስህተት እንዳንሠራ መረባረብ ያለብን መሆኑን አስገነዝባለሁ፡፡

አሁን በሥልጣን ላይ ያለው ቦርድም (ምንም እንኳን የሥልጣን ዘመኑ በመተዳደሪያው ደንብ መሠረት ያበቃ ቢሆንም)፣ የክለቡን ደጋፊዎች ድምፅ ለማፈንና ብልሹ አሠራሮችን ለመሸፈን በተለያዩ ወቅቶች የሚደረጉ የድግስ ጋጋታዎች የክለቡን ቀጣይ ህልውና ከማስጠበቅ አንፃር ምንም ፋይዳ ስለሌላቸው፣ በዘላቂነት ክለቡን የሚጠቅሙ ሥራዎች ለማከናወን በአስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔ በመጥራት የእርምት ዕርምጃ መውሰድ ይገባል፡፡ የኢፌዴሪ መንግሥትም ከሕዝብ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት የሕዝብን ፍላጎት በተለይም በስፖርት ፖሊሲና በማኅበራት ማደራጃ አዋጁ በግልጽ ያስቀመጣቸውን ድንጋጌዎች እንዲያስፈጽም፣ ወቅቱም የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ በየሴክተሩ ርብርብ እየተደረገ በመሆኑ፣ በስፖርቱም መስክ ያሉ ችግሮችን ነቅሶ በማውጣትና የሕዝብን ጥቅም ማስጠበቅ ለነገ የሚባል አለመሆኑን እያስታወስኩ ጽሑፌን እቋጫለሁ፡፡ ምንጊዜም ጊዮርጊስ!

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

 

 

Standard (Image)

የመሬት አስተዳደርና የመልካም አስተዳደር ትስስር

$
0
0

በነጋ ወልደ ገብርኤል

ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልካም አስተዳደርን አስመልክተው ከምሁራን ጋር ያካሄዱትን ውይይት ስከታተል ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ብቻ ሳይሆን፣ በተለያዩ የሥራ መስኮች ላይ ከተሰማሩ ምሁራንም ጋር ለመሥራት ፍላጎት እንዳለ የሚጠቁም መልካም ጅማሮ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ እኔም ከመሬት ጋር በተያያዘ በመንግሥት ተቋም ውስጥ ረዘም ላሉ ጊዜያት በመስኩ ተመድቤ ሳገለግል የቆየሁ በመሆኔ፣ አሁን በመታየት ላይ ላሉት የመሬትና መልካም አስተዳደር ችግሮች እምብዛም እንግዳ አይደለሁም፡፡ እንግዳ አለመሆን ብቻ ሳይሆን በመፍትሔ ፍለጋው ጥረት አቅሜ እስከፈቀደ ድረስ በመስኩ ጥልቅ ዕውቀት ካላቸው የሥራ ጓደኞቼ ጋር በንቃት ተሳትፌአለሁ፡፡

መሬት እንደ ሰው ልጅ ሕልውና መሠረትነቱና ተፈጥሮ ለጋስነቱ፣ መሬትን የማይመለከት ምንም ርዕሰ ጉዳይም ሆነ ውሳኔ (የሁሉም ዘርፍ የፖሊሲ ውሳኔን ጨምሮ) የለም፡፡ ይኼው ልዩ የመሬት ሁኔታ እንደ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ፣ ባህላዊ፣ ልማታዊ፣ ቁሳዊ (ፊዚካላዊ)፣ ከባቢያዊ፣ ኅብረተሰባዊ፣ ማኅበረሰባዊና ግላዊ ሀብት እንዲወሰድ ያደርገዋል፡፡ ይኼው የተለየ ባህሪው የመሬት አስተዳደርንና አመራርን ከመልካም አስተዳደር ጋር ያስተሳስረዋል፡፡

ቀላል ባይሆንም የዚህ ጽሑፍ ዓላማም መሬትን በአግባቡ አለመምራት ለልማት እንቅፋት መሆኑንና ለመልካም አስተዳደር መስፋፋት ምክንያት እንደሚሆን በመረዳት በመሬት አስተዳደር ጉዳይ ላይ ክርክሮችና ውይይቶች እንዲፈጠሩ ለመጋበዝ እንደ መነሻ የተወሰደ በመሆኑ፣ ከሚነሱት ሐሳቦች ይጠቅማሉ የሚባሉት ተለይተው መንግሥት ለፖሊሲም ሆነ ለስትራቴጂ ግብዓት የሚሆኑትን በሚመለከተው ተቋም በኩል መፈተሽ ያስችለዋል፡፡

መሬት ሰፊና ውስብስብ ጉዳዮችን እንደመያዙ አፈታቱም ሊለያዩ (ሊበዙ) ስለሚችሉ፣ በመካከልም ስህተቶች ሊፈጠሩ እንደሚችሉ ይገመታል፡፡ ስለመሬት አስተዳደርና ችግር አፈታት በርካታ የዘርፉ ባለሙያዎች ያካሄዷቸው የምርምር ውጤቶች (ኅትመቶች) በቂ መረጃዎችና ማስረጃዎች ናቸው፡፡ መሬትን በሚመለከት የዓለም ባንክ በየዓመቱ የሚያዘጋጃቸውን (Land and Poverty) ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶች ጨምሮ ሲካሄዱ የቆዩ አኅጉራዊ፣ ክልላዊና አገራዊ ሲምፖዚየሞች፣ ዓውደ ጥናቶች ውጤቶች የሚያስረግጡት ሀቅ ይኸው ነው፡፡ አገሮችም ከእነዚህ የተገኙ ውጤቶችን በመመርመር፣ ጠቃሚውን በመውሰድ፣ ከስህተታቸው በመማርና ማሻሻያዎችን በማድረግ በመሬት አስተዳደርና ልማት ላይ ከፍተኛ ለውጥ እያመጡ እንደሚገኙ ይገልጻሉ፡፡

እንደ አገራችን መሬት የመንግሥት (የሕዝብ) በሆነባቸው አገሮች ያለውን እንኳን ለማየት ቢሞከር፣ ለምሳሌ የሕዝባዊት ሪፐብሊክ ቻይና እ.ኤ.አ. በ1980ዎቹ መጀመሪያ ጥንቃቄ የተሞላበት የመሬት አስተዳደር የሪፎርም ፕሮግራም እንዳካሄደችና በአሁኑ ወቅት በእስያ ከሚካሄዱት የሪል ስቴት ጥናትና ምርምር ሥራዎች ውስጥ ከ50 በመቶ በላይ የሚሆነው ያተኮረው በቻይና ተሞክሮ መሆኑ ይገለጻል፡፡ እንደ ቬትናም ያሉ አገሮች የቻይናን ተሞክሮ እንዴት ተረድተው ቢወስዱት ነው እነሱም ለውጥ ለማምጣት የቻሉት? እኛስ ከእነዚህ አገሮች ምን እንማራለን? ከየት እንጀምር? ለሚሉት ጥያቄዎች መመካከርና ምላሽ መስጠት ያስፈልጋል፡፡

መሬትን ማስተዳደር ለምን አስፈለገ?

ከላይ እንደተመለከተው መሬትን የማይመለከት ጉዳይ ከሌለ የተለያዩ ፍላጎቶች (Interests) አሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ መንግሥታት (የከተማ አስተዳደሮች) የራሳቸውን ፍላጎት ለማስከበርም ሆነ ከግለሰብ ጀምሮ የተለያዩ ክፍሎችን (አካላት ፍላጎትን) ለማስጠበቅ ወይም ለማቻቻል፣ ደንብና መመርያ እያዘጋጁ ተፈጻሚ ያደርጋሉ፣ ይከታተላሉ፡፡ እዚህ ላይ ፍላጎት (Interest) የሚለው ቃል ከመሬት ጋር በተያያዘ አገላለጽ የመጠቀም መብት ተብሎ ይወሰድ፡፡

መሬትን በቁጠባና በአግባቡ ለመጠቀም የፕላንና የግንባታ ፈቃድ እንዲሟላ፣ መብትን ከማረጋገጥና ከመጠበቅ አንፃር ይዞታ ምዝገባ እንዲደረግ የመሳሰሉት የተለያዩ ጥያቄዎች የግድ በደንቦችና በመመርያዎች መስተናገድ ይኖርባቸዋል፡፡ ይህ አሠራር በሠለጠኑትና መሬት በግል ይዞታነት በሚተዳደርበት አገሮች ጭምር የሚፈጸም ሲሆን፣ በእኛም አገር ይህንን ኃላፊነት እንዲወጡ በከተሞች ከተደራጁት ተቋማት መካከል የመሬት አስተዳደር ይገኝበታል፡፡   

የመሬት አስተዳደር ምንድነው?

የመሬት አስተዳደር (Land Administration) ስንል የመሬት ማኔጅመንትና የፖሊሲ ጉዳዮችን ተግባራዊ ለማድረግ የመሬት ይዞታ ባለቤትነት (Ownership)፣ የመሬት ዋጋ ግምት (Value)፣ የመሬት አጠቃቀም (Use) በተመለከተ መረጃ መሰብሰብን፣ መረጃውን ማረጋገጥና መመዝገብን፣ መረጃውን መተንተንና ለሚፈለገው ጉዳይ ማከፋፈልን ያጠቃልላል፡፡ ይህም በይዞታው የመጠቀም መብትን ለማስከበር፣ የአካባቢን ዋጋ ለመገምገምና ለመከታተል፣ እንዲሁም ከተሞች በሚያስተዳድሩት ወሰን ክልል ውስጥ ያለውን መሬት አጠቃቀም በመመዝገብ ለመለየት የሚያስችሉ መረጃዎችን የሚያካትት ይሆናል፡፡

የመሬት (መልካም) አስተዳደር (Land Governance) ስንልም በመሬትና መሬት ነክ ንብረት ተደራሽነትና አጠቃቀም ላይ የውሳኔ መስጫ ሒደቱን የሚመለከት ሆኖ፣ የውሳኔ አሰጣጡን አፈጻጸምና በመሬት ላይ ያሉ የጥቅም ግጭቶች (የግልና የመንግሥት) የሚቻቻሉበት (የሚታረቁበት) ሒደት ነው፡፡ ይህም በእኩል ተጠቃሚነት ደረጃ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ አገልግሎት በመስጠት፣ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራርን በመፍጠርና የሕግ የበላይነትን በማረጋገጥ የመሳሰሉትንና ሌሎች አንኳር ጉዳዮች የያዙ መርሆዎችን አተገባበር ይመለከታል፡፡

እዚህ ላይ ለማሳየት የተሞከረው የመጀመሪያው የመሬት አስተዳደር ሥራው (ክንውን) ሲሆን፣ ሁለተኛው የመሬት አስተዳደር መልካም የሚሆነው በምን መልክ ሲተገበር እንደሆነ የሚያሳይ ነው፡፡ በዚህም መሠረት በከተሞች የመሬት አስተዳደር ሥራው ተዓማኒና በአግባቡ የተተነተነ ወቅታዊ መረጃን ያደራጀ መሆኑና ይህንን የመሬት መረጃ ለውሳኔ አሰጣጡ በምን መልክ እንደሚጠቀሙባቸውና ለሕዝቡ ተደራሽ እንደሚያደርጉ በመለየት፣ በመሬት አስተዳደሩ (Land Administration) እና በመሬት አስተዳደሩ (Land Governance) ላይ የማሻሻያ ዕርምጃ (የሪፎርም ፕሮግራም) መውሰድ ይገባል፡፡

በመሬት አስተዳደር ላይ የሚታዩ ችግሮች

የተደራጀ የመረጃ እጥረት

የመሬት አስተዳደር (Land Administration) ሥራውን በተገቢው መንገድ ለማከናወን ከተሞች የመሬት ይዞታን፣ የመሬት ዋጋና የመሬት አጠቃቀምን የተመለከቱ መረጃዎች በሚመለከታቸው ተቋማት በአግባቡ መደራጀቱ (መሰብሰብ፣ መተንተንና ማሰራጨት) ለሚሰጠው አገልግሎት መሠረታዊ መሆኑን በቅድሚያ በሁሉም አካላት መግባባት መፈጠር ይኖርበታል፡፡ በከተሞች የመሬት አስተዳደሩ አሠራር (ውሳኔ) በተሟላ መረጃ ላይ የተመሠረተ ባለመሆኑ፣ ዘላቂነት ያለው የመሬት ሀብት አስተዳደርን ለማረጋገጥና የከተማ መሬትን በአግባቡ ለመምራት አልተቻለም፡፡ ከመገለጫዎቹ መካከል መሬት ሲቀርብ የይገባኛል ጥያቄዎች መነሳትና በመሬት ወረራ መስፋፋት ምክንያት በተፈለገው መጠን ነፃ ቦታ አለመገኘት፣ በመሠረተ ልማት ዝርጋታ ወቅት የሚነሱ የይዞታ ማስከበርና የካሳ ክፍያ ጭቅጭቆች፣ በስም ዝውውር ወቅት የሚነሱ የድንበር ክርክሮች፣  አንድን ቦታ ለተለያዩ ሰዎችና አገልግሎት መስጠት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ይህም የሚያሳየው የይዞታ ባለመብቶች ተመዝገበው መረጃቸው አለመያዙን፣ የአካባቢው የንብረት ዋጋ መረጃ ተመዝግቦና ተተንትኖ አለመታወቁን፣ የእያንዳንዱ ይዞታ ድንበር ተለይቶ መረጃው አለመቀመጡን፣ እንዲሁም የከተማው መሬት ተቆጥሮና አጠቃቀሙ ተመዝግቦ አለመያዙን ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ያለው የመሬት አስተዳደር አሠራር በተመደበው ኃላፊና ባለሙያ ዕውቀት ደረጃና በጎ ፈቃድ የሚፈጸም ስለሚሆን ለመልካም አስተዳደር ችግር የሚያጋልጥ ይሆናል፡፡

የአሠራር ግልጽነት አለመኖር

ከተሰበሰበውና ከተተነተነው መረጃ በመነሳት የሚተላለፉ ውሳኔዎችም ሆኑ አገልግሎቶች ግልጽና ተደራሽ እንዲሆኑ በማድረግ የመሬት አስተዳደሩን (Land Governance) ማሻሻል ይቻላል፡፡ በከተሞች አስፈላጊው መረጃ ባልተደራጀበት፣ ፖሊሲዎችና ሕጎች ግልጽ ባልሆኑበት፣ ሠራተኛውም ሆነ ተገልጋዩ በእኩል ደረጃ ባልተረዱበትና አሳታፊ አሠራር ባልተፈጠረበት ሁኔታ ውሳኔዎቹ በቀላሉ ለአድልዎ (ምንም እንኳን ለግል ጥቅም ባይሆንም በዘርና በጎሳ፣ በፖለቲካ አቋምና ቤተሰባዊነት ምክንያት የአንዱን በንብረት የመጠቀም መብት ለሌላው ሲደረግ)፣ ለጉቦ (በተለይ የንብረት ምዝገባ ሲደረግ፣ በንብረት ዝውውር ወቅት፣ በካሳ ክፍያ፣ ስለንብረት መረጃ ሲፈለግ፣ የካዳስተር ቅየሳ ሲከናወን፣ የመሬት አጠቃቀም ፕላን ለውጥና የተለያዩ የመሬት ነክ አገልግሎቶች ሲጠየቁ) እና ለሰነድ ማጭበርበር (በዋናነት በንብረት ሽያጭ ወቅትና የመንግሥትን መሬት ወደ ግል አገልግሎት ለዚያውም አካባቢው መስጠት ከሚኖርበት አገልግሎት በታች እንዲውል ለማድረግ) የሚያጋልጥ በመሆኑ፣ የመሬት መልካም አስተዳደሩ ላይ ጥርጣሬው እየሰፋ ይሄዳል ማለት ነው፡፡ ጥርጣሬም ብቻ ሳይሆን ነዋሪው ስለንብረቱ ዋስትና ማጣት፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ቀውስ፣ የሥነ ምግባር ብልሹነት፣ የግል ኢንቨስትመንት አለመጠናከር፣ የከተሞች ገቢ መቀነስ ይታያል፡፡

ሙስና

ሙስና የመልካም አስተዳደር ጉድለት መገለጫ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ሙስና አንድን ሥራ በሞኖፖል ከመያዝና ከመምራት፣ የኃላፊው የማስተዋል ደረጃ፣ የተጠያቂነት ሥርዓት መኖር አለመኖርና ከአካባቢው የሥነ ምግባር ሁኔታ ጋር የሚገናኝ ነው፡፡ በመሬት መልካም አስተዳደር ችግር ምክንያት በመሬት አስተዳደርና ልማት ከሚታዩ የሙስና ተግባራት መካከል፣

  • የመሬት አቅርቦቱ የነዋሪውን የመጠለያ ችግር በሚቀርፍ መልኩ (በቁጥርም ሆነ በተለይ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን ተጠቃሚ ከማድረግ) የሚዘጋጅ ባለመሆኑ ምክንያት የሚፈጠርን የመሬት ወረራ መስፋፋት ለመከላከል በሚደረግ እንቅስቃሴ የሚፈጠር ሙስና፣
  • የይዞታ መብት ዓይነቶች በግልጽ ተለይተው ባለይዞታው እንዲያውቀውና መብቶቹ የሚሰጡትን ጥቅም በተሻለ እንዲገለገልበት ባለመደረጉ ምክንያት ጥያቄዎች ሲቀርቡ ምላሽ የመስጠት ሒደቱ የተንዛዛ መሆኑንና የሚቀርቡ ማስረጃዎች መብዛትን ለማሳጠር የሚደረግ ሙስና፣
  • የከተማ መሬት አጠቃቀም ፕላን ከዝግጅቱ ጀምሮ የነዋሪው ተሳትፎ ዝቅተኛ መሆን ምክንያት ባለሙያው ብቻ የሚያውቀው ስለሚሆንና ሚስጥራዊ ስለሚያደርገው ጥያቄዎችን ለማስተናገድ ከባለሙያው ወይም ከኃላፊው የሚቀርብ ሙስና፣
  • የአካባቢ መሬትና መሬት ነክ ንብረት ዋጋ መረጃ በአግባቡ ባለመያዙ ምክንያት በተለይ የስም ዝውውር ክፍያና ግብር አከፋፈልን አሳንሶም ሆነ ከፍ አድርጎ በመገመት የሚፈጠር ሙስና፣
  • ስለእያንዳንዱ ይዞታ በቂ መረጃ ባለመያዙ ምክንያት በፍርድ ቤት ያሉ የመሬት ክርክሮች መጓተትን ለማስቀረት የሚደረግ ሙስና ይጠቀሳሉ፡፡

የመፍትሔ ሐሳቦች

መንግሥት በከተሞች የሚታዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ የተለያዩ የአደረጃጀት ማሻሻያዎችን፣ የመረጃ ሥርዓት ዝርጋታዎችን፣ የሰው ኃይል ሥልጠናን የመሳሰሉ ሥራዎችን ሲያከናውን እንደነበር ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በቅድሚያ ለምን የተፈለገው ለውጥ ወይም ማሻሻያ አልመጣም የሚለውን በመዳሰስ፣ ከዚህ በታች የተጨመሩትን በማካተት ተቋማዊ ለውጥ ማምጣት ይቻላል፡፡

ተቋማዊ ልማት

እኛ ወደ ከተማ መሬት አስተዳደር ሪፎርም እ.ኤ.አ. በ1990 ስንገባ ቻይና በአንድ አሥር ዓመት ብቻ (1980ዎቹ) ብትቀድመንም፣ በውጤት ደረጃ ስናነፃፅር ያለን ልዩነት እጅግ በጣም ሰፊ መሆኑ ቻይና ለተቋማዊ ልማት ከፍተኛ ትኩረት መስጠቷን ያሳያል፡፡ የአስፈጻሚ መሥሪያ ቤቶች አደረጃጀታቸውን ጨምሮ አሠራሩ የሚገባውን የፖሊሲና የሕግ ማዕቀፎች፣ ደንብና መመርያ፣ ፎርሞችና ቼክ ሊስቶች፣ መከታተያ ቅጾች ማሟላቱ መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የቢሮዎች አቀማመጥና የፀደቁት ሰነዶች ግልጽነት በተላበሰ ሁኔታ ቀልጣፋ አገልግሎት ለማቅረብ ማስቻሉን መፈተሽ፣ የአቅም ግንባታ (በተለይ ሥልጠና) የሚሰጠው ጥቅም ቢታወቅም እስካሁን በነበረው ክንውን ምን ለውጥ አመጣ? ምን ያህል ሰው ሠለጠነ? አሁን የት ይገኛሉ? ለምን? የነዋሪው ተሳትፎ በምን መልክ ይሁን? ተጠያቂነትስ እንዴት በፈጻሚዎች ላይ ተግባራዊ ይሁን? ለሚሉት ምላሽ በመስጠት ማሻሻያዎችን ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

የመሬት መረጃ ሥርዓት መዘርጋት

የመሬት ማኔጅመንት ሰፊ ጉዳዮችን እንደመያዙ ማለትም ከተሞች በሚያስተዳደሩት ክልል ውስጥ ያለውን መሬት በስፋትና በአገልግሎት ዓይነት፣ ወዘተ ቆጥረው ከመለየት ጀምሮ፣ መሬት ማልማትና ማዘጋጀት፣ ለገበያ ማቅረብና መብት መመዝገብ፣ የግንባታና የመጠቀሚያ ፈቃድ መስጠት፣ የአካባቢ የመሬትና መሬት ነክ ንብረት ዋጋን ግምት መከታተልና መገምገም፣ የመሬት ነክ ግብርን የመሳሰሉትን መረጃዎች ባለው የፋይናንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ የሰው ኃይል አቅም መሠረት ቅደም ተከተል በመስጠት በሚመለከታቸው ተቋማት የመረጃ ቋት ማደራጀት ይገባቸዋል፡፡

 

ከሰባት ዓመት በፊት መንግሥት የመሬት አስተዳደሩን የመረጃ ሥርዓት በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ በቅድሚያ መሠራት ያለበትን እንዳስቀመጠ አውቃለሁ፡፡ ቅደም ተከተል መስጠቱ መረጃ የሚሰበሰብ፣ የሚተነተንና ለአስፈላጊ ጉዳይ የሚሰራጭ እንደመሆኑ ዓላማና ዕቅድ (Purpose) አለው፡፡ በቀላል አገላለጽ አንድ ሰው ሱሪ ማሰፋት ቢፈልግ ባለሙያው (ልብስ ሰፊው) የሚፈልገው መረጃ ከወገብ በታች ቁመትና የወገብ ልኬት ብቻ እንጂ የአንገትና የጫማ ቁጥር ባለመሆኑ (ይህንን መረጃ የሚፈልጉት ሸሚዝና ጫማ ሠሪዎች በመሆናቸው)፣ እያንዳንዳቸው ተቋማትም የሚፈልጉትን መረጃ በየራሳቸው ሰብስበውና ተንትነው ለሚሰጡት አገልግሎት እንዲጠቀሙ የሚረዳቸው ሥርዓት መዘርጋት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህም መብት መዝጋቢው ተቋም፣ የከተማ መሬት አጠቃቀም ፕላን አዘጋጅና ፈጻሚውም፣ በመሬት ልማት የሚሳተፉ ድርጅቶችም፣ በመሬት ዋጋ ግመታና ግብር ላይ የተሰማሩ የፋይናንስ ተቋማትም እንዲሁ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስፈልጋቸውን መሬትን/ይዞታንና መሬት ነክ ንብረትን የተመለከቱ መረጃዎችን ብቻ በየተቋማቸው እንዲሰበሰቡና እንዲተነተኑ በማድረግ የሚከናወን ይሆናል ማለት ነው፡፡ ይህንን መፈጸም (ሥርዓቱን መዘርጋት) በራሱ ረጅም ጊዜና ገንዘብ የሚጠይቅ መሆኑን በመገንዘብ ቅደም ተከተል በመስጠት ጥራቱን የጠበቀ ሥራ አሁኑኑ ማስጀመርና መከታተል ያስፈልጋል፡፡ በቀጣይም የወቅቱን ቴክኖሎጂ በመጠቀም የመረጃ ቅብብሎሹን ማስተሳሰር እስከዚያውም የተተነተነውን መረጃ በሲዲም ቢሆን መቀባበል ይቻላል፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ተቋማት የሚፈለጉ መረጃዎች በአንድ ቦታ ለማጨቅ መሞከር መረጃውን በመተንተን ወቅታዊ የሚያደርግ አካል ስለማይኖር፣ አንዱንም የታለመለትን ጉዳይ ሳያስፈጽም በእንጥልጥል እንዲቀር ያደርገዋል፡፡

የመረጃ ተደራሽነትና የሕዝብ ተሳትፎን ማረጋገጥ

በሠለጠኑ አገሮች መረጃን ተደራሽ ለማድረግ በታወቁ የመረጃ መረቦች ውስጥ በመግባትና የሚፈለገውን ክፍያ በመፈጸም፣ ወይም ከየተቋማቱ የታተመ መረጃ በመግዛት ይዳረሳል፡፡ ይኼውም ከይዞታ መዝጋቢው ተቋም ማግኘት ስለተፈለገው ይዞታ (ንብረት) መረጃ፣ ከመሬት አቅራቢው ተቋም መሬት በሊዝ ለመገብየት ለፈለገ ስለአካባቢው የልማት ዕቅድና የአካባቢው የቀድሞው ዋጋ መረጃ፣ ከከተማ ፕላን ፈጻሚው ተቋም ስለሚፈለገው አካባቢ የመሬት አጠቃቀም ፕላን አገልግሎቶች መረጃ፣ ከንብረት ዋጋ ገማቹ ተቋም ስለአካባቢው አማካይ የንብረት ዋጋ መረጃ በአግባቡ ተደራጅቶ በማስቀመጥ ለፈላጊው በማዳረስ ይሆናል፡፡ ለዚህም  እንደ መረጃ ደህንነት ማለትም መረጃን ከእሳትና ከቫይረስ ጥቃት መጠበቅ፣ የግለሰብን መብትና ነዋሪው የመንግሥት መረጃን የመጠቀም ተደራሽነትን የመሰሉ ሕጎች ማውጣት የመሳሰሉት ቅድመ ጥንቃቄዎች ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የሕዝብ ተሳትፎን በተመለከተም ነዋሪው በሠፈርም ይሁን በቀጣና፣ በመገናኛ ብዙኃንና ሥልጠና በመስጠት ስለአገልግሎቶቹ እንዲያውቅና የፈለገውን መረጃ የሚያገኝበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ ነዋሪው ችግሮችን የሚያቀርቡ ተወካዮችን መርጦ የሚያቀርብበት አሠራር መፍጠሩ ለግልጽነት አሠራሩ ጠቃሚ ያደርገዋል፡፡

የአሠራር ግልጽነት መፍጠር

ግልጽነትን (Transparency) ለመፍጠር አሠራሩ የታወቁ ተግባራት እንዲኖሩትና አገልግሎት ሰጪውም ሆነ ተገልጋዩ በቀላሉ የሚረዱት እንዲሆኑ ይፈለጋል፡፡ ይህ አሠራር በጎ ሥነ ምግባርን ከመፍጠሩ በተጨማሪ የሕዝቡ የመረጃ ማግኘትንና በተለይ ኑሮውን ሊጎዱም ይሁን ሊጠቅሙ የሚችሉ ጉዳዮች ላይ በውሳኔ አሰጣጥ ላይ የመሳተፍ ሕገ መንግሥታዊ መብትን ማክበርም ስለሚሆን፣ የኃላፊዎችን በጎ ፈቃድ የማግኘት ጉዳይ መሆን አይገባውም፡፡

የሥነ ምግባር ብልሹነትን ማሻሻል

የሥነ ምግባር ብልሹነት በአገልግሎት ሰጪው ብቻ ሳይሆን በነዋሪው ውስጥም ይኖራል፡፡ በነዋሪው መካከል የሚኖር የሥነ ምግባር ጉድለት ከሚገለጽባቸው መካከል ታክስ ያለመክፈል፣ የይዞታ ካርታም ሆነ መብት ማረጋገጫ ሰነድ ሳይኖር ስም ማዘዋወር፣ የግንባታ ፈቃድ ሳይጠይቁ መገንባት፣ ቦታው ለተፈቀደለት አገልግሎት አለማዋል ይታያል፡፡ ስለዚህ ነዋሪውን የተመለከቱ የሥነ ምግባር ማሻሻያ ሥራዎች መሠራት ይኖርባቸዋል፡፡ አገልግሎት ሰጪውን በተመለከተም የጥቅም ግጭት እንዳይኖር የሚያስችል ሕግ (Conflict of Interest Law)፣ የሙያ ሥነ ምግባር ደንብ (Code of Professional Ethics/Conduct) መቅረጽ፣ ስለጠቋሚዎች ከለላ (Whistleblower Protection) እና የሥነ ምግባር ሥልጠና የመሳሰሉት ሰነዶች ማዘጋጀትና ማሳወቅ ያስፈልጋል፡፡ ለነዋሪው የአገልግሎት እርካታውን የሚገልጽበት የሪፖርት ካርድ ማዘጋጀት፣ ለዚህም ሚስጥራዊነቱን ማረጋገጥ፣ የሥነ ምግባር ችግር ሲያጋጥም ጠቋሚዎች የት እንደሚሄዱና በምን መልክ እንደሚጠቁሙና ማበረታታት እንደሚቻል ግልጽ የሆነ አሠራር መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ ይህም በነዋሪውም ሆነ በአገልግሎት ሰጪው የሚፈጠሩ የሥነ ምግባር ችግሮች እንዲቀረፉ ይረዳል፡፡

ነፃ የፀረ ሙስና ተቋም ማደራጀት

ከላይ ከተጠቀሱትና ለሙስና ከሚያጋልጡ ጉዳዮች በተጨማሪ ያሉትን ልምዶች መለየት አስፈላጊ ሲሆን፣ በዚህም ሕዝቡ ስለሙስና ያለው አረዳድ (ሙስናን የማይቀበል መሆኑ፣ የሙስና መስፋፋት ዕይታ፣ መንግሥት ሙስናን ለመግታት ያለው ፍላጎት፣ ያሉ ፀረ ሙስና ስትራቴጂዎች፣ የክትትል ሥልቶችና ተግባራዊነታቸው) ተመዝኖ መታየት ይኖርበታል፡፡ ነፃ የሚለው በእንግሊዝኛ (Independent) ለሚለው መተኪያ እንዲሆን የተቀመጠ ሲሆን፣ ከተጠቃሚው የሚቀርቡ የመሬት አስተዳደር የሥነ ምግባር (የሙስና) ጥቆማዎችን በመቀበል ለአመራሩ የሚያቀርብ ሆኖ፣ አደረጃጀቱም ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ከተውጣጡ አባላት የተዋቀረ ይሆናል፡፡

ማጠቃለያ

መልካም አስተዳደር የሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች ማለትም የመንግሥትን፣ የሕግ አውጪውን፣ የተርጓሚውንና የአስከባሪውን፣ የግሉን ዘርፍና የነዋሪውን ርብርብ ይጠይቃል፡፡ ከእነዚህ የኅብረተሰብ ክፍሎች አንዱ ችግሩን ለመቅረፍ በሚደረገው እንቅስቃሴ በሚፈለገው መጠን አለመሳተፍ ልክ አንድን ሕንፃ ለማቆም ከሚፈለጉ ምሰሶዎች አንዱ ቢጎድል በሕንፃው ላይ ሊፈጠር እንደሚችለው፣ የዲዛይንና የግንባታ ችግር የታለመለት ግብ ላይ ለመድረስ አይቻልም፡፡ ግልጽነት መረጃ በተፈለገው ጥራት መቅረብ እንዳለበት ላይ የሚያጠነጥን በመሆኑ፣ በመንግሥት ተቋም (በከተማ፣ በገጠር መሬት አስተዳደር) የሚገኝን መረጃ በጥራት በማደራጀት ለሁሉም ክፍት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ይህም ለጥናትና ምርምር ከፍተኛ ዕገዛ ያደርጋል፡፡ በመሬት (መልካም) አስተዳደር ጉዳዮች ላይ ያለውን የአቅም ግንባታ ክፍተት መለየትና የማሻሻያ ስትራቴጂዎችን መቅረፅ ትኩረት ሊሰጠው ከሚገባቸው መካከል አንዱ ነው፡፡ ይህም የአገልግሎት ሰጪውንና የፖሊሲ አውጪዎችን የአቅም ክፍተት ወደ ክህሎት፣ ዕውቀትና አመለካከት ለመቀየር የሚያስችል መሆኑ መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡

በመሬት አስተዳደር ተቋም እንዴት ግልጽና ቀልጣፋ አሠራር መፍጠር ይቻላል የሚለውንና የሥራ ኃላፊነት (Mandate)፣ የሥራ ሒደት፣ የመረጃ ቅብብሎሽና ቁጥጥር በምን መልክ እንደሆነ መዳሰስ ያስፈልጋል፡፡ የነዋሪውን የአገልግሎት ቻርተር የሚገልጽ (የደንበኛን ክቡርነት፣ የተጠቃሚውን የአገልግሎት ስታንዳርድና ችግሮች ሲፈጠሩ ስለሚደረገው የማስተካከያ ዕርምጃ) ሰነድ ማዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ የቢሮው አቀማመጥ፣ የመረጃ ዴስክ፣ ጉዳዮች በአንድ ክፍል/ቦታ እንዲያልቁ ከማድረግ፣ የአቤቱታ ሰሚ ክፍል ወይም አሠራር አደረጃጀት መጠናትና መዋቀር ይኖርበታል፡፡ በአጠቃላይ የመሬት አስተዳደሩን በመልካም አስተዳደር ቅኝት ውስጥ ለማስገባት ሰፊ ሥራና የሁሉንም አካላት ዝግጁነት እንደሚፈልግ ከላይ ለማመላከት ተሞክሯል፡፡ ሩጫ ከዕርምጃ እንደሚጀምር ሁሉ ዛሬ መጀመር ያለበት ተጀምሮ በሒደት የሚሻሻለው እየተስተካከለ ወደተፈለገው ግብ መድረስ ይቻላል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው nwgebreal@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

Standard (Image)

የኢጣሊያ ወረራ ድልና አርበኝነት

$
0
0

በተሾመ ብርሃኑ ከማል

በኢጣሊያ ወረራ ዋዜማ

የኢጣሊያ ወረራ፣ የአርበኞች ታሪክና ከዚህ ጋር ተያያዥነት ስላላቸው ሁኔታዎች ስናወሳ ከአንዱ የታሪክ አንጓ (ምዕራፍ) ካልጀመርን በስተቀር ብዙ ጉዳዮችን ማንሳታችንና መጣላችን አይቀርም፡፡ ስለዚህም ‹‹ኢጣሊያ ኤርትራንና ኢትዮጵያን አንድ አድርጎ የመግዛት ህልሟ በዓድዋ ጦርነት ቢከሽፍም አርፋ አልተቀመጠችም፤›› ከሚለው እሳቤ እንነሳ፡፡

ኢጣሊያ በአፍሪካ ቅኝ ግዛት ለመመሥረት በነበራት ፅኑ ዓላማ ሰሜን ኢትዮጵያን በመውረር ኤርትራን ይዛ በሰላም መኖር እንደማትችል በተግባር ስላረጋገጠች፣ በሰሜን በኩል በማርሻል ኢሚሎ ደቦኖ (የኢጣልያ ቅኝ ግዛት አገሮች ኮሚሽነር) የሚመራ 250,000 ነጮችን፣ 150,000 አፍሪካውያንን ከሊቢያ፣ ከሶማሊያና ከኤርትራ ሠራዊት ኢትዮጵያን አጠቃሎ ለመግዛት ከ1920ዎቹ መጨረሻ ጀምሮ ዝግጅት ማድረግ ተጀመረች፡፡ ይኼንን ዘመቻ በማያዳግም ሁኔታ ለማከናወን 300 የጦር አውሮፕላኖች ዝግጁ ሆኑ፡፡ በደቡብ በኩል በ100 የጦር አውሮፕላኖች የታገዘ በማርሻል ሮዶልፍ ግራዚያኒ የሚመራ ኃይል ወደ ሰሜን ተንቀሳቀሰ፡፡ ይህም የተደረገው አዲስ አበባን እጅግ አጭር በሆነ ጊዜ ውስጥ በመቆጣጠርና ሕዝቡ በደስታ ተቀብሎኛል በማሰኘት ሊግ ኦፍ ኔሽን ያደርስ የነበረውን ተፅዕኖ ለማስቀረት ነበር፡፡ 

የኢጣሊያ ወታደራዊ ምንጮች ደግሞ በምሥራቅ አፍሪካ በተለይም በኤርትራ ከነበራት በ3,300 መትረየሶች፣ በ200 ታንኮች፣ በ275 መድፎች የተጠናከረ 400,000 በተጨማሪ በሶማሊያ ከነበረው 285,000 ሠራዊት ነበር፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በሚያዚያ ወር 1928 ዓ.ም. ብዙ ቶን የሚመዝኑ ጥይቶች፣ ለወራት የሚበቁ ምግቦችና ሌሎች ድጋፍ የሚሠጡ አገልግሎቶች፣ በርካታ ሞተር ብስክሌቶች፣ በ6,000 አውቶማቲክ የጦር መሣሪያ (መትረየስ)፣ 2,000 መድፍ፣ 599 ታንክ፣ 390 አውሮፕላኖች የተጠናከረ፣ ከኢጣሊያ ዘውዳዊ መንግሥት የጦር ኃይል ተቀንሶ 650,000 ሠራዊት  ኤርትራ ገባ፡፡ ይህም ጦር የገባው በከፍተኛ ስንቅና ትጥቅ ተጠናክሮ ሲሆን፣ ጦርነቱንም ለመከታተል 200 ያህል ጋዜጠኞች መጥተዋል፡፡

ኢትዮጵያ የዚያን ጊዜ ያንቀሳቀሰችው በራሶች የሚመራ 300,000 ሠራዊት ሲሆን (ይኼንን ቁጥር አንዳንዶች 500,000 እንደሚደርስ ይገምታሉ፣ የኢጣሊያ ወታደራዊ ምንጮች ግን ኢትዮጵያ 350,000 እስከ 760,000 የሚገመት ሠራዊት ነበራት ይላሉ፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ የነበሩዋቸው 200 መድፎችና 1,000 መትረየሶች ሲሆኑ፣ ሠራዊቱም ከጠላት ጋር የማይመጣጠን ጠመንጃ የታጠቀ ነበር፡፡ አብዛኛው ሠራዊት የተሠለፈው ጎራዴ፣ ጦርና ጋሻ ይዞ ሲሆን፣ የተወሰነው ደግሞ ከሚወድቁ ወገኖቹ የጦር መሣሪያ አንስቶ ለመዋጋት ጀሌውን የተሠለፈ ነበር፡፡ ሠራዊቱ ሲመች ከሚሠጠው ጥይት በስተቀር ስንቁንም ሆነ የጦር መሣሪያውን ይዞ የተሠለፈው ከግሉ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ሠራዊት የራሱ የሆነ በቅሎ ፈረስ፣ ግመልና አህያ ይዞ ከመዝመቱ በስተቀር የጦር መኪና፣ የጦር አውሮፕላንና ታንክ የሚባል አልነበረውም፡፡

ይኼም ሆኖ የኢጣሊያ ወታደራዊ ምንጮች ኢትዮጵያ 400,000 ያህል ጥንታዊና ዘመናዊ ጠመንጃዎች፣ 200 ያህል ያረጁ መድፎች፣ 50 ያህል ቀላልና ከባድ የአየር መቃወሚያዎች፣ 3,000 ያህል በአንደኛው የዓለም ጦርነት አገልግሎት ላይ የዋሉ መድፎች፣ ለአየር አምቡላንስ የሚውሉ ጥቂት አውሮፕላኖች፣ አራት አብራሪዎች የነበሯቸው 13 የአየር ኃይል አውሮፕላኖች ነበሩ፡፡ እጅግ ኋላቀር የጦር መሣሪያ የታጠቀውና ዘመናዊ የውትድርና ሥልጠና ያላገኘው የኢትዮጵያ ሠራዊት እጅግ ዘመናዊ የጦር መሣሪያ ከታጠቀው የኢጣሊያ ሠራዊት ጋር በሽሬ ከታኅሳስ 7 እስከ 8 ቀን 1927 ዓ.ም.፣ በእንዳባጉና ከጥር 12 እስከ16 ቀን 1928 ዓ.ም.፣ በወርቃምባ ተንቤን ከጥር 19 እስከ 21 ቀን 1928 ዓ.ም.፣  ከየካቲት 1928 ዓ.ም. በዓቢይ ዓዲ ተንቤን፣ ከየካቲት 24 እስከ 27 ቀን 1928 ዓ.ም. ከዚያም ቀጥሎ በሰለኽለኻ፣ በአምባ አርአዶምና በእምባአላጌ ላይ ጦርነት አካሄደ፡፡ በእነዚህ ሥፍራዎች በተደረገው ጦርነት ቁጥሩ እጅግ ብዙ የሆነ ኢትዮጵያዊ ቢሞትም፣ በተለይም በሽሬ በተደረገው ጦርነት 300 ያህል መትረየሶች፣ ታንኮችና ሌሎችም ዘመናዊ የጦር መሣሪያዎች ተማረኩ፡፡

በዚህ ጦርነት በኢጣሊያ በኩል የደረሰውን ጉዳት በሚመለከት ማርሻል ባዶግሊዮ በላከው ሪፖርት በሽሬ ጦርነት ብቻ 63 የጦር መኮንኖች፣ 894 ኢጣሊያውያን፣ 12 ኤርትራውያን ሲሞቱ በኢትዮጵያ በኩል 4,000 ያህል ሞተዋል በማለት ገልጿል፡፡ በዚህ ጊዜ 400 የሚሆኑ ኤርትራውያን ኢጣሊያን በመክዳት ሽሬ ከነበረው ከራስ እምሩ ጦር ጋር ተቀላቅለዋል፡፡

በደቡብ ግንባር በኩል በማርሻል ግራዚያኒ የሚመራውን የጦር ኃይል የነራስ ደስታ፣ ደጃዝማች ነሲቡ፣ የራስ መኮንን የጦር ኃይል በኦጋዴን በተደረገው ጦርነት ገጥሞታል፡፡ በዚህ ጊዜ የማርሻል ግራዚያኒ የጦር ኃይል የገጠመው በጦር አውሮፕላኖች በሚረጭ የጋዝ መርዝ ጭምር ነበር፡፡ ምንም እንኳን በጦርነቱ አያሌ ኢትዮጵያውያን ቢጨፈጨፉም፣ 400 ያህል ኤርትራውያን የወገኖቻቸው መጨፍጨፍ አሳዝኗቸው ከኢትዮጵያ ሠራዊት ጋር ተቀላቅለዋል፡፡ 

ቦነያ ነቀምት ውስጥ በደጃዝማች ሀብተ ማርያም ከሚመራው የአርበኛ ጦር ጋር በተካሄደው ጦርነት በኢትዮጵያ የኢጣሊያ ምክትል መስፍንን ጨምሮ ከ13 የኢጣሊያ መኮንኖች 12፣ የአየር ማርሻሉ ማግሎዮኮው ሰኔ 18 ቀን 1928 ዓ.ም. ተገደሉ፡፡ በዚህ ጦርነት የተረፈ ኢጣሊያዊ ቢኖር አባ ቦሬሎ የተባሉ መንገድ መሪያቸውና ቡራኬ የሚሰጧቸው ነፍስ አባታቸው ብቻ ነበሩ፡፡

በራስ ደስታ ዳምጠው የጦር አበጋዝነት በሲዳሞ ውስጥ የተካሄደው ጦርነት ከፍተኛ ዕልቂት የተፈጸመበት ሲሆን፣ በእዚህም ጦርነት ጄኔራል ናቫሪኒ በሦስት አቅጣጫዎች ባደረገው ከበባ 4,000 የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን ተገድለዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ 1,600 ያህሉ ምርኮኞች ሲሆኑ በጥይት ተደብድበው እንዲገደሉ ተደርጓል፡፡ ጥቅምት 1 ቀን 1928 ዓ.ም. ደጃዝማች ኃይለ ሥላሴ ጉግሳ ከ1,200 ተከታዮቻቸው ጋር ዕዳጋ ሐሙስ ላይ ለማርሻል ደ ቦኖ እጃቸውን ሰጡ፡፡

ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ ከጎጃም ወደ ተንቤን በተለይም ማይ ጥምቀት ተብላ ወደምትጠራው ሥፍራ 4,0000 ሠራዊት አስከትለው ዘመቱ፡፡ ራስ ሥዩም መንገሻ ከ30,000 ሠራዊታቸው ጋር ዓቢይ ዓዲ አካባቢ ነበሩ፡፡ ራስ ካሳ ኃይሌ ዳርጌ 40,000 ያህል ሠራዊታቸውን አስከትለው ከደሴ ራስ ሥዩምን ለመርዳት ወደ ተንቤን ዘመቱ፡፡ ራስ ሙሉጌታ ይገዙ (የጦር ሚኒስትር) 80,000 ያህል ሠራዊታቸውን አሠልፈው ከራስ ሥዩም በስተቀኝ አምባ አርዓደላይ መሸጉ፡፡ አራቱም የጦር አበጋዞች በአጠቃላይ 19,000 ያህል ሠራዊት ነበራቸው፡፡ ተንቤን ላይ በተደረገው እጅግ አስከፊ ጦርነት 8,000 ያህል ኢትዮጵያውያን ተገደሉ፡፡ ከዚህ በኋላም መቀሌ በኢጣሊያ ተያዘች፡፡

እምባአርአደ ላይ በተደረገው የእንደርታ ጦርነት ራስ ሙሉጌታና ልጃቸውን ጨምሮ 6,000 ሰዎች ሲሞቱ 120,000 ያህል ቆሰሉ፡፡ በሽሬ ላይ በተደረገው ጦርነት 1,000 ያህል ኢትዮጵያውያን ሲገደሉ 4,000 ያህል ቆሰሉ፡፡ የኢትዮጵያ ሠራዊትም ተበታተነ፡፡ የራስ ካሳ ሠራዊት ተንቤን ላይ በጋዝ መርዝ አለቀ፡፡

1,000 ያህል ሠራዊት ከበጌምድር ተከዜን ተሻግሮ እንዳባጉና ደረሰ፡፡ በሽሬ ግንባር በኩል የኢጣሊያው የጦር መሪ ሜጀር ከሪኒቲ በሦስት ታንኮችና በዘመናዊ የጦር መሣሪያ የታገዘ 1,000 ሠራዊት አሠልፏል፡፡ እሱም እዚያ እንደደረሰ አካባቢውን የሚቆጣጠሩት 2,000 ያህል የኢትዮጵያ ሠራዊት አባላት እንደሆኑ ተገነዘበ፡፡ ስለሆነም የነበረው ዘመናዊ የጦር መሣሪያና የሠለጠነ የሰው ኃይል ከባበ ማድረግ በቦምብ በመደብደብ ድል ሆነ፡፡ ነገር ግን እሱና የተረፉት ጥቂት ወታደሮቹ አመለጡ፡፡ ኢትዮጵያ የዚያን ጊዜ 3,000 ባንዳዎችን መግደሏን አስታውቃ ነበር፡፡

በመጋቢት ወር 1928 ዓ.ም. ማይጨው ላይ የተደረገው ጦርነት በንጉሠ ነገሥቱ የሚመራና ከፍተኛ ቁጥር የነበረው ሠራዊት ቢሆንም 400 ኢጣሊያውያን፣ 837 ኤርትራውያንና 11,000 ያህል ኢትዮጵያውያን የሞቱበት ሲሆን የንጉሠ ነገሥቱ ጦር ድል ሆነ፡፡

በደቡብ በኩል ማርሻል ግራዚያኒ በደጃዝማች ነሲቡ ላይ ባካሄደው ዘመቻ 200 ኢጣሊያውያን ቢሞቱበትም፣ 15,000 ኢትዮጵያውያንን ገድሎ ኦጋዴንን ተቆጣጠረ፡፡

ማርሻል ባዶጋሊዮ የማያጨው ድል ከቀናው በኋላ ጉዞውን በደሴ በኩል በመቀጠል በግንቦት ወር አዲስ አበባ ገባ፡፡ ኢጣሊያ ግንቦት 23 ቀን 1928 ዓ.ም.  ኢትዮጵያን፣ ኤርትራንና ሶማሊያን በማዋሀድ በምሥራቅ አፍሪካ የኢጣሊያ ግዛት መሆናቸውን በይፋ አወጀች፡፡ 

ኢትዮጵያ በንጉሠ ነገሥቷ አማካይነት ላቀረበችው የድረሱልኝ ጥያቄ የዓለም መንግሥታት ጆሮ ነፈጓት፡፡ ይባስ ብለው በኢጣሊያ ላይ አስተላልፈውት የነበረውን ማዕቀብ በነሐሴ ወር 1928 ዓ.ም. አነሱ፡፡ በታኅሳስ ወር 1929 ዓ.ም. ጃፓን የኢጣሊያን ቅኝ ገዥነት ተቀበለች፡፡ ፈረንሣይና እንግሊዝም ተጨመሩበት፡፡ ከዓለም አገሮች ሁሉ የኢጣሊያን ቅኝ አገዛዝ የሚቃወሙ ሜክሲኮ፣ ቻይና፣ ኒውዚላንድ፣ ሶቪየት ኅብረት፣ ስፔይን ሪፐብሊክና አሜሪካ ብቻ ሆነው ተገኙ፡፡ ኢጣሊያን ሲወጉ ከነበሩት የኢትዮጵያ የጦር መሪዎች የተወሰኑት ለኢጣሊያ ፋሽሽት መንግሥት አደሩ፡፡ የኢጣሊያ መንግሥት በኢትዮጵያ የነበረውን መረጋጋት ሲመለከት የካቲት 12 ቀን 1929 ዓ.ም. እጅግ አሰቃቂ ግድያ የፈጸመው ማርሻል ግራዚያኒን በማንሳት የአዎስታውን መስፍን (ሲቪል መሆኑ ነው) ሾመ፡፡ ትግራይና ኤርትራ አንድ ላይ፣ ኦጋዴንና ሶማሊያ ደግሞ አንድ ላይ አድርጋ ለአስተዳደር በሚያመች መንገድ ከፋፈለችው፡፡

በ1930 ዓ.ም. ብሪታንያና ፈረንሣይ ኢጣሊያ በኢትዮጵያ ላይ ያላትን ቅኝ ገዥነት ከቃል ድጋፍ ወደ ጽሑፍ ስምምነት ቀየሩት፡፡ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን፣ ኤርትራንና ሶማሊያን በአንድ ላይ በምትገዛበት ጊዜ መንገድ፣ ስልክና መብራት መዘርጋት እንደ ዋነኛ የሕዝብ ማሳመኛና መግዣ ጥበብ አድርጋ ተጠቀመችበት፡፡ ትምህርት ቤትና ሆስፒታል መገንባትን፣ ዘመናዊ እርሻዎችንና ፋብሪካዎችን ማቋቋምን እንደ ዋነኛ ሥራዋ አድርጋ ወሰደችው፡፡ ሕዝቡን ሰጥ ለጥ አድርጋ ለመግዛትም 150,000 ሠራዊቷን በመላው ኢትዮጵያ አሰራጨች፡፡ ይኼ አኃዝ ባንዶቿን ጨምሮ በሦስት ዓመት ውስጥ ወደ ሩብ ሚሊዮን ከፍ አለ፡፡ የሠራዊቱ ቁጥር ከፍ በማለቱ በአስተማማኝ ሁኔታ ብዝበዛውንና ጭቆናውን መፈጸም ሲጀምር ‹‹አልገዛም›› ያለው ወደ ጫካ ገባ፡፡ የሽምቅ ውጊያ ተጀመረ፡፡ በቅኝ ገዥዋ ኢጣሊያ መሪዎች ላይ ጥቃት ለመፈጸም ጥይት በየቦታው ተተኮሰ፡፡ የሽምቅ ውጊያውን የሚያካሂዱት መኳንንቱና መሳፍንቱ ናቸው በሚል ጥርጣሬ በርካታዎቹ ታሰሩ፡፡ የአንዳንዶቹ ልጆችም በፋሽስታዊው መንግሥት ላይ በመሸፈታቸውና እነርሱ ራሳቸውም በመሸፈታቸው ምክንያት ይገደሉ ጀመር፡፡ ከእነዚህም ውስጥ እነ ራስ ካሳ፣ እነ ደጃዝማች ባልቻ፣ እነ ጄኔራል ኃይሉ ከበደ፣ እነ ራስ ደስታ ዳምጠው፣ ደጃዝማች በየነ መርዕድ፣ ወዘተ  ይገኙበታል፡፡

ይሁንና የቅኝ አገዛዝን የማይቀበለው የኢትዮጵያ፣ የኤርትራና የሶማሊያ ሕዝብ ወራሪውን ጦር ወግቶ በማሸነፍ ከምድረ ኢትዮጵያ በአምስት ዓመታት ውስጥ ያባረረ ሲሆን፣ ከኤርትራና ከሶማሊያም እንዲወጣ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል፡፡

የኢጣሊያ ቅኝ ገዥ የመጨረሻ ህቅታ

የኢትዮጵያ አርበኞችና ወራሪውን ኃይል ለአምስት አመታት ተዋግቶ ድል ለማድረግ በተቃረበበት ጊዜ የኢጣሊያም መንግሥትም ከጀርመን መንግሥት ጋር ተባባሪ በመሆኑ፣ የባለቃል ኪዳን አገሮች (እንግሊዝ፣ ፈረንሣይ፣ አሜሪካና ተባባሪዎቻቸው ምዕራባውያን) ፊታቸውን አዙረውበት ነበር፡፡ ስለሆነም በምሥራቅ አፍሪካ የነበረውን ኃይል ለማዳከም ስትል እንግሊዝ የኢትዮጵያ አጋር ሆና ተነሳች፡፡ በዚህም መሠረት የኢጣሊያን ኃይል ከኤርትራ ለማስወጣት የጦር ኃይሏን አሠለፈች፡፡

ኢጣሊያም እጇን ከመስጠቷ በፊት በኤርትራና በኢትዮጵያ የነበሩትን ኢጣሊያውያን ደኅንነት ለማረጋገጥ ይቻል ዘንድ፣ በዱክ አውስታና በኢድሪስ ዓዋተ የሚመራ ኃይል ከኤርትራ ወደ ትግራይ አንቀሳቀሰች፡፡

ለመሆኑ ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ ማን ነው?  ታሪኩስ ምንድነው? ግርማይ እዮብ የተባሉ የታሪክ ጸሐፊ እንደሚሉት፣ ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ በደቡብ ምዕራብ ኤርትራ፣ በጋሽና ሰቲት አውራጃ፣ በኦምሐጀርና በተሰነይ መካከል በምትገኝ ገርሰት ተብላ በምትጠራ ቀበሌ በ1902 ዓ.ም. ተወለዱ፡፡ ከ1927 እስከ 1928 ዓ.ም. የኤርትራ ቅኝ ገዥ በነበረው የኢጣሊያ መንግሥት በወታደርነት (አስካሪነት) እንዲያገለግሉ ጥሪ ቀረበላቸው፡፡ ጥሪውን ተቀብለውም ሲሄዱም የነበራቸውን ቅልጥፍና የተመለከቱት ኢጣሊያውያን አሠልጣኞች ከሮም ሰሜን ምሥራቅ 15 ኪሎ ሜትር ራቅ ብላ በምትገኘውና የኢጣሊያ ቅኝ ግዛት አፍሪካውያን ፖሊሶች በሚሠለጥኑባት ‹‹ቲቮሊ›› ተብላ በምትጠራ ሥፍራ እንዲሠለጥኑ ላኳቸው፡፡ ሥልጠናውንም ካገኙ በኋላ በትሪፖሊ፣ በቤንጋዚ፣ በአስመራ፣ በአዲስ አበባ፣ በሞቃዲሾ፣ በጎንደርና በሌሎችም ኮሚሳሪያት ውስጥ አገልግለዋል፡፡

ግርማይ እዮብ ጨምረው እንደሚገልጹት ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ በቤኒቶ ሙሶሊኒ (1922 እስከ 1943) ዓ.ም. ዘመን ካራቢኘሪ ተብሎ ከሚጠራው ኃይል ጋር በመሆን ኢጣሊያ በምሥራቅ አፍሪካ፣ በተለይም በኤርትራ፣ በሶማሊያና በኢትዮጵያ ግዛቷ ይገጥማት የነበረውን ተቃውሞ የማፈን ኃላፊነት የተጣለባቸው ሰው ነበሩ፡፡ እርሳቸውና ባልደረቦቻቸው በ1930ዎቹ በተካሄደው የኢጣሊያና የሐበሻ ጦርነት በኤርትራና በኢትዮጵያ ውስጥ ለተፈጸመው ግፍ በአፍሪካ የኢጣሊያ ፖሊስና ካራቢኘሪ ግንባር ቀደም ተጠያቂዎች ናቸው፡፡

በአፍሪካ የኢጣሊያ ፖሊስ ቡድን አባል መሆን የሚቻለው በሚያሳየው ታማኝነት ስለነበር ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተም የኢጣሊያን አገዛዝ አንቀበልም ብለው የሚታገሉትን ሱዳናውያን፣ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያንን በፈጸሙት ሊገለጽ የማይችል ግፍ የሚኮሩ፣ በአፍሪካ የኢጣሊያ ፖሊስና ካራቢኘሪ አባል ነበሩ፡፡ ለኢጣሊያ ቅኝ ገዥ ታማኝ ሆኖ በማገልገላቸውም በመጀመርያ የደኅንነት መኮንን ተብለው ተሾሙ፡፡ ቀጥሎም የምዕራብ ኤርትራና የከሰላ ምክትል ዋና አስተዳዳሪ ሆኑ፡፡ በ1932 ዓ.ም. የከሰላ (ሱዳን) አስተዳዳሪ በነበሩበት ጊዜ እንግሊዝ በ1933 ዓ.ም. የኢጣሊያን ሠራዊት እስክትወጋ ድረስ ከሰላን ከኤርትራ ግዛት ጋር አንድ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ያደርጉ ነበር፡፡ ከእዚህም ሌላ ከኢጣሊያ ባለውለታዎቹ ጋር በመሆን ከእንግሊዝ ጋር በተደረገው ጦርነት ተዋግተዋል፡፡

ኢጣሊያ በጦር ቃል ኪዳን አባላቱ እንግሊዝ፣ ፈረንሣይና አሜሪካ ድል ስትሆን፣ ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ እንደ ፋሽሽት ወታደርነታቸው የመረረ ሐዘን ተሰምቷቸዋል፡፡ እንግሊዝ ኢጣሊያን በ1933 ዓ.ም. ድል ካደረገች በኋላም አሚዶ ጉሌት ከተባለ ኢጣሊያዊ ጋር በመሆን የሽምቅ ውጊያ አካሂደዋል፡፡

ግርማይ እዮብ እንደሚነግሩን ከመጋቢት 30 ቀን 1901 ዓ.ም. እስከ ሰኔ 8 ቀን 2002 ዓ.ም. የኖረው አሚዶ ጉሌት ከ1932 እስከ 34 ዓ.ም. በነበረው ጊዜ ከ2,500 ኤርትራውያን፣ ኢትዮጵያውያንና የመናውያን ጋር ሸፍቶ እንግሊዝን በሽምቅ የተዋጋ ሲሆን፣ የተረገመ የጦር አዛዥ እንደነበረ ይነገርለታል፡፡ የእንግሊዝን ግስጋሴ ለመግታት ካደረገው ጦርነት ውስጥ አምባ አላጌና ቁርደት በሚወስደው ሥፍራ መካከል በምትገኝና  ጪሩ በምትባል ቦታ ላይ ያደረገው ይጠቀሳል፡፡ ጉሊት በከረን ተመትቶ የተበታተነው የኢጣሊያ ሠራዊት እንደገና እንዲሰባሰብ ከመርዳቱም በላይ፣ በአምባላጌ ጦርነት ተሸንፈው ሲሸሹ የነበሩ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢጣሊያውያንና ኤርትራውያን ሕይወት ለመታደግ ችሏል፡፡ ይኸው የሰሜን ጎንደር ባላባት ልጅ የሆነችና ከድጃ የምትባል ሚስት የነበረችው ኢጣሊያዊ እንግሊዝን በሽምቅ ለአንድ ዓመት ያህል ሲወጋ ከቆየ በኋላ በመጀመሪያ ወደ ሰሜን፣ ቀጥሎም ወደ አገሩ ለመግባት ችሏል፡፡ 

የዱቼ ሙሶሊኒን መንግሥት ለመመለስ ጥረት ያደርጉ የነበሩት ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ ጉሌት ወደ አገራቸው ከገቡ በኋላ 50 ተከታዮቻቸውን ይዘው እስከ 1938 ዓ.ም. ድረስ በእንግሊዝ ላይ ሸፈቱና በትውልድ ሥፍራቸው መኖር ጀመሩ፡፡ በዚህ ጊዜ ዋና ሥራቸው የኩናማ ሕዝብን ማሰቃየት ከብቶቻቸውን በመዝረፍ ወደ ከሰላ በመውሰድ መሸጥ ሲሆን፣ በዚህ ሁኔታ የተበሳጨው የእንግሊዝ መንግሥትም በ1941 ዓ.ም. እጃቸውን ይዞ ላቀረበለት 300 ፓውንድ እንደሚሰጥ አውጆ ነበር፡፡ እንደ ሐሚድ ኢድሪስ ዓወተ ሁሉ እንደ ወልደብኤል ሞሳዝጊ፣ በርኸ ሞሳዝጊ፣ ሐጎስ ተምነዎ፣ አስረሳኸኝ አምባየ የተባሉ ሽፍቶችም የዓረዛን፣ የደብሪ ዓዲ ጻዲቅ፣ በራኪት አባይ፣ የአከለጉዛይ፣ የሰራዬና የሐማሴን ሕዝብን ያሰቃዩ ነበር፡፡ በነዚህም ሽፍቶች ቁጥራቸው የማይታወቅ ጀበርቲዎች፣  ሳሆዎች፣ ኩናማዎች፣ ኸበሳዎች ተገድለዋል፡፡

በ1942 ዓ.ም. ለእንግሊዝ ጦር እጃቸውን ስለሰጡ ግን ሙሉ ምህረትና ይቅርታ ያደረገላቸው ከመሆኑም በላይ፣ የግል የጦር መሣሪያቸውን ሕይወታቸውን እንዲጠበቁበት ፈቅዶላቸዋል፡፡

የሃምሳ ዓመት ዕድሜ የነበራቸው ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ በ1953 ዓ.ም. በኤርትራ ነፃነት ግንባር (ኢኤልኤፍ) የጦር መሣሪያ ትግል እንዲያካሂዱ ጥያቄ ቀረበላቸው፡፡ በ1953 ዓ.ም የጦር መሣሪያ ትግሉ እንደገና መጀመሩን ለቀድሞ ተከታዮቻቸው አወጁ፡፡ የኢኤልኤፍን የጦር መሣሪያ ትግልን ለሃያ ወራት ያህል ከመሩ በኋላ ግንቦት 12 ቀን 1954 ዓ.ም. አረፉ፡፡ የሞቱት ከምግብ ጋር የተሰጣቸውን መርዝ በልተው ነው የሚል ጥርጣሬ አለ፡፡

የጦርመሣሪያትግልየተደረገበትአርበኝነት

በአማርኛችን ‹‹አርበኛ›› የሚለው ቃል ‹‹ዓርነት/ነፃነት በእኛ ዕውን ይሆናል፤›› እንደ ማለት ነው፡፡ ከጣሊያን ጋር አምስት ዓመት የተዋጉ ኢትዮጵያውያን «አርበኞች» ተብለው ይታወቃሉ፡፡ እነዚህ አርበኞች ቅኝ አገዛዝን አንቀበልም፣ ጭቆናን አንሻም፣ እንቃወማለን በማለት ጣሊያን ለመውጋት፣ በመውጋትም ድል ለማድረግ ቆርጠው ጫካ የገቡ ናቸው፡፡ 

ከዚህም በተጨማሪ «የጦር ሜዳ አርበኛ»፣ «የውስጥ አርበኛ» አለ፡፡ የጦር ሜዳው አርበኛ ጣሊያን ከገባበት ጊዜ ጫካ ገብቶ በጦር መሣሪያ ትግል የጀመረ ሲሆን፣ አገልግሎቱም ከአንድ ቀን እስከ አምስት ዓመት ሊደርስ ይችላል፡፡ የውስጥ አርበኛው ደግሞ የጦር መሣሪያ ትግል ባያደርግም የጣሊያን ደጋፊ መስሎ ወይም ሳይመስል፣ አርበኞቹን በልዩ ልዩ መንገዶች የሚረዳና ለመርዳቱ በምስክር የተረጋገጠለት ነው፡፡ ከእነዚህም የውስጥ አርበኞች መካከል የታወቁ የኢጣሊያ ባንዳዎች የነበሩ፣ ነገር ግን ውስጥ ለውስጥ ይረዱ ነበር ተብለው የሚታሰቡ ናቸው፡፡ ዕርዳታውም አርበኛውን በጨለማ ተቀብሎ ማስተናገድ፣ ልብስ መላክ፣ ኬላ አልፎ እንዲሄድ መፍቀድ፣ ቢታሰር ማስፈታት፣ ቤተሰብ መርዳት፣ መረጃ ማስተላለፍ ሊሆን ይችላል፡፡ ለምሳሌ ‹‹የጣሊያን ወታደሮች ዛሬ በዚህ በኩል ስለሚያልፉ ዘወር በሉ፤›› ወይም ‹‹ይህን ያህል ጦር ይዞ ስለተንቀሳቀሰ ጠብቃችሁ ግጠሙት፤›› የሚል ሊሆን ይችላል፡፡ 

በበኩሌ አርበኞች ምን እንደሚሉና እንደሚሰማቸው አላውቅም፡፡ መንግሥትም እንደ አንድ ጉዳዩ አድርጎ አያየውም የሚል ግምት የለኝም፡፡ ዳሩ ግን ነገርን ነገር ያነሳዋል በሚል ነገሩን ለማንሳት ያህልና ወጣቱም ትውልድ እግረ መንገዱን ስለድሮ አርበኞች ጥቂት ሐሳብ እንዲኖረው በማሰብ እንጂ፣ የጦር ሜዳ አርበኞች ጉዳይ በጣም ጥልቅና ወደር የሌለው በመሆኑ ወደ ልማት አርበኞች ላተኩር፡፡

የልማትአርበኞች

የልማት አርበኞች ስንል ምን ማለት እንደሆነ ለማብራራት እንችል እንደሆን አንዳንድ ሊሄዱ የሚችሉ መሠረታዊ ጉዳዮችን እናንሳ፡፡ በመግቢያው ላይ አርበኛ ማለት «ዓርነት/ነፃነት በእኛ ዕውን ይሆናል፤» የሚል አንድምታ እንዳለው ለመግለጽ ተሞክሯል፡፡ አርበኝነትንም ሆነ ነፃነትን ቅኝ ገዥ ጠላትን ተዋግቶ ከአገር ማስወጣት ማለት እንደሆነም ለማሳየት ጥረት ተደርጓል፡፡ ነገር ግን ዓርነት የሚያስፈልገው ከጠላት ጋር ለመዋጋት ብቻ ነው? የአሁኖቹ ሊቃውንት በዚህ አይስማሙም፡፡ የልማት አርበኛ በመሆንም ከፍተኛ ሰላም፣ ዴሞክራሲና ፍትሕ ማምጣት ይቻላል፡፡

የአገርፍቅርአርበኝነት

አገርን አርበኛ ሆኖ ለማልማት ከሁሉ አስቀድሞ የሚያስፈልገው ጥልቅ የአገር ፍቅር ነው፡፡ ወጣቱን ትውልድ በአሁኑ ጊዜ በግንባር ቀደምትነት ከሚያስፈልጉት ነገሮች አንዱ የአገር ፍቅር ስሜትና የአገር ፍቅር ወኔ ነው፡፡ የአገር ፍቅር ስሜትና የአገር ፍቅር ወኔ ከራስ ወዳድነት ስሜት ተላቆ፣ «እኔ ለአገሬ ዕድገት እሠራለሁ፡፡ ወገኖቼን ከረሃብና ከእርዛት ነፃ ለማውጣት ቆርጨ ተነስቻለሁ፡፡ ይህም ብርቱ ዓለማዬ ግብ እስኪደርስ ኃላፊነትና የሞራል ግዴታ ኖሮኝ አስፈላጊውን መስዋዕትነት እከፍላለሁ፤» ከሚል የሚመነጭ ነው፡፡ «አገሬ በድህነቷ ምክንያት ተዋርዳለች፣ ዝቅ ብላ ታይታለችና ከወደቀችበት አነሳታለሁ፤» የሚል ቁርጠኛ ውሳኔ በራስ ላይ ማስተላለፍንም ይጨምራል፡፡ በተወለድንባት፣ እየተጫወትን ባደግንባት፣ በተማርንባትና ከጓደኞቻችን ጋር በጨፈርንባት አገራችን ፍትሕና ዴሞክራሲ እንዲለመልም ተግቼ እሠራለሁ ብሎ መነሳትን ይጠይቃል፡፡ 

የመቻቻልአርበኝነት

አገራችን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ የመቻቻል አርበኛ ያስፈልጋታል፡፡ የአገር ፍቅር ስሜቱ ሊጎለብት የሚችለውም የእርስ በርስ መቻቻልና መፈቃቀር ሲኖር እንደሆነ አያጠያይቅም፡፡

መቻቻል በግለሰብ ወይም በተወሰኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች ብቻ የሚወሰን ሳይሆን በኅብረተሰብም ሊንፀባረቅ የሚገባው ዓቢይ ጉዳይ ነው፡፡ መቻቻል ብዙ አመለካከት፣ አስተሳሰብ፣ ፍልስፍና፣ ሃይማኖትና እምነት በሚስተናገድባት ዓለማችን በዓለማችን ዛሬ የምናያቸውን እጅግ አስቀያሚ ነገሮችን፣ ጠባብ አመለካከቶችንና የእርስ በርስ ጥላቻን ድል እንደምናደርግ አያጠያይቅም፡፡ 

አንድ ሰው ጠባብ የጎሳ፣ የብሔር ብሔረሰብ፣ የሕዝብ፣ የዘር፣ የሃይማኖት፣ የእምነት፣ የቋንቋና የቀለም ጠባብ አመለካከት ሲኖረው በጠባብ ዓለሙ ውስጥ በብቸኝነት እንደሚኖር አያጠያይቅም፡፡ በአንድነት ላይ የተመሠረተ ብዝኃነት በተቃራኒው የመቻቻል መሠረት ሲሆን የሌሎቹ መኖር ሀቅነትን፣ የእነሱ መኖር ለእርሱ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ሲቀበል ይልቁንም በአንድነት ላይ የተመሠረተ ብዝኃነትን ማስወገድ የማይችል መሆኑን ሲገነዘብ ራሱንም ሌሎችንም መጥላት ይጀምራል፡፡ በተቃራኒውም በአካባቢው ከእሱ ጋር ተመሳስሎ ተቻችሎ የሚኖር መሆኑን ሲረዳ ያኔ አዲስና አብሮ ለመኖር የሚያበቃ ሀቅ ይኖረዋል፡፡

የልማትአርበኝነት

በአሁኑ ጊዜ በአገራችን ከፍተኛ የልማት ሥራዎች እየታዩ ነው፡፡ እነዚህን የልማት ሥራዎች ለማፋጠን የፖለቲካ አመለካከት፣ የሃይማኖት፣ የዘር ወይም የሌላ ልዩነት አያግደንም፡፡ በተጠቀሱትና ባልተጠቀሱት ጉዳዮች ልዩነታችን እንደተጠበቀ ሆኖ አገራችንን ማልማት ያለብንም በአንድ ላይ ሆነን መሆን ይኖርበታል፡፡ በአሜሪካ ውስጥ ብዛት ያላቸው ፖለቲካዊ አመለካከቶችና ሃይማኖቶች እንዲሁም ዘሮች አሉ፡፡ ቅራኔያቸው ግን ሥርዓቱን እኔ የተሻለ አንቀሳቅሰዋለሁ ከሚል ነው፡፡ ያም ቢሆን በሕዝብ ድምፅ አሸናፊዎች ሲሆኑ ነው፡፡ አብርሃም ሊንከን የተባሉ ፕሬዚዳንቷ አገራቸው እርስ በርስ ጦርነት ስትናጥ በነበረበት ጊዜ የተናገሩት አንድ ትልቅ ቁም ነገር፣ «የመርከቧን መሪ ጨብጠን ወደፈለግነው አቅጣጫ ልንመራት የምንችለው ከሁሉ አስቀድሞ መርከቧ ስትኖር ነው፤» በማለት ሕዝብ የእርስ በርሱን ጦርነት አቁሞ ለልማት እንዲተጋ ማሰባቸው ለሁላችንም ምክር ሊሆን ይችላል፡፡ አገራችን ዘላለማዊት ስትሆን ማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ግን ተለዋዋጭ ነው፡፡ ዘርም፣ ቋንቋም ተለዋዋጭ ነው፡፡ ትውልድ አልፎም ትውልድ ይተካል፡፡ ስለሆነም የጥላቻን መርዝ አስወግደን የተጀመረውን የልማት ለውጥ ማካሄድ ተቃውሞ ቢኖረንም፣ በአግባቡ እያቀረብን ለማስተካከል የበኩላችንን አወንታዊ ሚና መጫወት ይጠበቅብናል፡፡ 

ፈትሁላህ ጉለን የተባሉ ቱርካዊ የመቻቻልና በሰላም አብሮ የመኖር መሐንዲስ «የነፍሳችን ሐውልት» በሚለው መጽሐፋቸው ውስጥ እንዳስቀመጡትም፣ «ፈጣሪ የምድር ወራሽነትን ለአንድ የተወሰነ ነገድ፣ ጎሳ፣ አገር፣ ወይም ዘር ለመስጠት ቃል አልገባም፡፡ ወራሾቹ ባሪያዎቹ በአስተሳሰባቸውም ሆነ በእምነታቸው ትክክል የሆኑ፣ የአንድነት፣ የስምምነት፣ የአብሮነትና የወንድማማችነት አመለካከትን የሚያስተምሩ፣ በተግባር የሚገልጹና አጥብቀው የሚይዙ፣ ያሉበትን ዘመን የሚረዱ፣ በሳይንስና በዕውቀት የበለፀጉ፣ የዚህን ዓለምና የሚቀጥለውን ዓለም ሚዛን ጠብቀው የሚኖሩ. . .  ናቸው፤» ካሉ በኋላ፣ «በዚህ ያልታደለ ጊዜ የአስተዳደርና የአስተዳዳሪዎች ድክመት በግልጽ ለመናገር ልቦናን የሚሰብር (የሚያሳዝን) ነው፤» ሲሉ የሚከተለውን አስተያየት «የነፍሳችን ሐውልት» በተሰኘው መጽሐፋቸው ይተነትናሉ፡፡ 

በአጭሩ አርዓያ፣ ምሳሌ፣ መነሻና፣ መለኪያ የሚሆኑን ወኔያችን፣ ቆራጥነታችን፣ የሚያነሳሳ መንፈሳችን፣ በሃይማኖት ረገድ ፍሬያማ መሆናችንን፣ (ያለፈውን ታሪካችንን) ለማረጋገጥ የሚያስችል ከባቢ ሁኔታ፣ ጽናታችን፣ በመካከላችን ውስጥ የሚገኘው ስበታችን፣ ኮስታራንታችን ምክንያት በማቅረብና በነገረ ጥበብ ችሎታችን፣ የማንናወፅ መሆናችን ለራሳችን ነፃነት የሚያጎናጽፈን ሰብዓዊ ሩኅሩህነታችን ናቸው፡፡ የፍልስፍና ጥልቀት፣ የማጣራት፣ የማሻሻል፣ ወደፊት የማራመድ፣ በኪነ ጥበብና በፍልስፍናችን ውስጥ የሚገኝ በጥልቅ እሳቤ የተሞላ አመለካከታችን፣ ይህም ሁሉ ከዋናው ማዕከል ጥራት ያለውና በአሠራር ሊያስኬድ በሚችል አስተሳሰብ ላይ የተመሠረተና በራዕይ የተነሳሳ ሊሆን ይገባል፡፡ 
ማጠቃለያ
ውድ አንባቢያን የአርበኝነትን፣ በተለይም የልማት አርበኝነትን ትርጉም ከዚህ ከተጠቀሰው ሁሉ ሰፋ አድርገን ልናየው እንችላለን፡፡ ዋናው ቁም ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ ሰፊ የልማት ሥራዎች እየተካሄዱ ሲሆን፣ እነዚህም ሥራዎች ዓለም አቀፍ አድናቆት የተቸራቸው ናቸው፡፡ ችግሮች እንኳን ሊኖሩ ቢችሉ የልማቱ ትሩፋት ለእያንዳንዳችን ቢደርስም ባይደርስም በአገርና በወገን ፍቅር ስሜት በርትተን ልንሠራ ይገባል፡፡ በእርግጥም ተደጋግሞ ሲነገር እንደሚሰማው ችግር ፈቺዎች እንጂ ችግር ፈጣሪዎች ወይም ጨለምተኞች ሆነን ልንገኝ አይገባም፡፡ በአጭሩ ለማለት የሚቻለው ማንም የፈለገውን ቢል የልማት አርበኝነቱ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡ በዚህ አጋጣሚ በነፃነት ሰንደቅ ዓላማችንን እያውለበለብን ለዚህ ዘመን እንድንደርስ ላደረጉን ጀግኞች አርበኞችቻችን ዘለዓለማዊ ክብር ይገባቸዋል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው   bktesheat@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

 

 

Standard (Image)

እግር ኳሳችን ከቻይና እግር ኳስ ቢማርስ?

$
0
0

ስለ እግር ኳሳችን ስናወሳ ሁሌም የኋላ ታሪኩን መነሻ አድርገን መጻፋችን ክፋት አለው የሚል እሳቤ ባይኖረኝም፣ ታሪክ እንዳለን ማሳያ መሆኑ እሰየው የሚባልለት ነው ብዬ መግለጽ እወለዳሁ፡፡ ነገር ግን ሁሌም ያለፈውን ታሪክ እንደ ጀብዱ ቆጥረነው መሥራች በመሆናችን ብቻ፣ ልንኮራበትና አለፍ ሲልም ልንኮፈስበት የሚያስችለን ዘመን እያበቃ ለመሆኑ ራሳችን ደፍረን መናገር መቻሉ ነውር ያለው አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም ሆነን ለመገኘት በታሪክ ዋሻ ተደብቆ በመኖር ብቻ ዋስትና ሊሆን አያስችለንምና፡፡

የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን መሥራች ነን በማለት ራሳችንን የአፍሪካ ቁንጮ አገር አድርገን ስንተርክ፣ በጣም ብዙ አገሮች የእግር ኳስ ሥራን እንዴት መሥራትና አሸናፊ መሆን እንደሚቻል ተገንዝበውና አውቀው በተግባር በማዋል ቀድመውንና ጥለውን ትልቅ ደረጃ አድርሰውታል፡፡ እኛ ግን አሁን ‹አትንኩኝ! አትንኩኝ!› እያልን በቀረርቶና በሽለላ ዕድሜያችንን በመቁጠር ላይ እንገኛለን፡፡

ለእግር ኳሳችን አዲስ ሐሳብ ይዞ የመጣን ግለሰብ እንደ ጠላት ቆጥረን በማዋከብና በማብጠልጠል ሌላ ለዕድገት የሚጠቅም ሐሳብ ይዞ እንዳይመጣ በማድረግ፣ ወይም ሁለተኛ ‹‹ይቺን ደጃፍ እንዳትረግጥ›› በሚል ዛቻና ማስፈራሪያ አዘል ማስጠንቀቂያ ማስተናገድ የተመደበለት አካባቢ እንደሆነ ይታወቃል፡፡

የተለያዩ ሐሳቦችን ማስተናገድ የማይችለው እግር ኳሳችን የትውልድ ቅብብሎሽን የማይቀበል፣ ለተሻለ ለውጥና ዕድገት የማይተጋ፣ ሁሌም ‹‹ኳስ በእኛ ጊዜ ቀረ›› በሚል ኋላቀርና ልማዳዊ አሠራር የተተበተበ አካባቢ ሆኗል፡፡ ይህን ፀረ ዕድገትና ፀረ ለውጥ አስተሳሰብና አመለካከት የወረረውን እግር ኳሳችን ችግሩን ተረድቶ ለመለወጥና ለማሳደግ የተለያዩ አገሮች ተሞክሮ መቅሰምና መቀበል እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡

በዋናነት የዚህ ጽሑፍ መልዕክት በእግር ኳሳችን ዙሪያ ያሉትን ብልሹ አሠራሮችና በአጠቃላይ ኋላ ቀር ባህሎችን በመጠቆም ሌላውን አካል ለማብጠልጠል የሚሞክር ሳይሆን፣ ላለፉት 70 ዓመታት በአንድ ዓይነት ቅኝት ተቃኝቶ ለሚጓዘውና አሁን አሁን ግራ ለገባው አማተር አይሉት ፕሮፌሽናል እግር ኳሳችን ለለውጥ እንዲዘጋጅ ለመጠቆም ነው፡፡ በመሆኑም ከዚያ አልፈው በምጽፈው ጽሑፍ የማይደሰቱ ወገኖች ሊኖሩ ይችላሉ ብዬ ብገምትም እንኳን፣ ተነካንና ተደፈርን ብለው ሊቆጡኝና ሊያስፈራሩኝ ይችላሉ ብዬ ግን አልገምትም፡፡ ምክንያቱም ዘመኑ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት በሕገ መንግሥታችን የተደነገገበት ነውና፡፡

በተጨማሪ እየጻፍኩኝ ያለሁት ስለግለሰቦች ክብርና ጥቅም ሳይሆን ሕዝባችን እየተቃጠለበትና ስሜቱ እየተጎዳበት ስላለው ደካማው እግር ኳሳችን ነው! እየጻፍኩኝ ያለሁት የወጣቶችንና የሕፃናቶቻችን ሥነ ልቦና በተሸናፊነት ሞራሉንና ጉልበቱን እየሰለበው ስለመጣው እግር ኳሳችን ነው፡፡ እየጻፍኩኝ ያለሁት ራሱን መቻል አቅቶት እየተንገዳገደና እየተልፈሰፈሰ ስለሚገኘው እግር ኳሳችን ነው፡፡ እግር ኳሳችን ከተጠቀሱት ችግሮች እንዴት አድርጎ ወጥቶ ሕዝባችንን ያስደሰትና በደስታ ይጨፍር ነው፡፡ እየጻፍኩኝ ያለሁት እግር ኳሳችን እንዴት ሀብታም ሆኖ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሕፃናትና ወጣቶችን አሠልጥኖ ውጤታማ ተጫዋቾች ተፈጥረው አገራችንን የዓለም እግር ኳስ የበላይ ትሁንልን ነው፡፡ እየጻፍኩኝ ያለሁት እንዴት በሺሕ የሚቆጠሩ ሜዳዎችን ሠርተን ሕፃናትና ወጣቶች ይሠልጥኑባቸው ነው? እየጻፍኩኝ ያለሁት ኢትዮጵያችን እንዴት አድርጋ አሸናፊ ትሁንና የዓለምን ቀልብ ትሳብ ነው! እንግዲህ ሐሳቤ ሲጠቃለል እግር ኳሳችን እንዴት ጠንካራ፣ ሀብታምና አሸናፊ ሆኖ ሕዝባችን ያስፈንድቅ፣ ያዝናና፣ በኢኮኖሚም ይጥቀመን ነው፡፡ በዚህ የማይስማማ ግለሰብ ካለ ሌላ ስም አልሰጠውም፡፡ የአገር ልማት የማይመኝ ስለሆነ ደካማ አስተሳሰቡን እንዲያሻሽል መምከር ነው፡፡

በመሠረቱ የአሁኑ እግር ኳስ ከማዝናናቱ ባሻገር ከፍተኛ የኢንቨስትመንት ኢንዱስትሪ በመሆን በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡ ቢሊዮን ዶላሮች እያንቀሳቀሱበት የሚገኘው ይህ ኢንዱስትሪ የብዙ ኃያላን አገሮች ሕዝቦችን ቀልብ እየሳበ በመሄዱ መንግሥታትም እየገቡበት መሄድ አጀማመሩ ሰንበትበት ብሏል፡፡ የሕዝቦችንም ቀልብ እየሳበ በመሄዱ መንግሥታትም እየገቡበት መሄድ ከጀመሩ ሰንበትበት ብሏል፡፡ በቅርቡ የቻይና እግር ኳስ ማኅበር እየሄደበት ያለውን በእርግጥም አስፈሪና ድፍረት የተሞላበት ጅማሮ እየታዘብን ነው፡፡ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ የአገራቸውን እግር ኳስ ወደ ተፎካካሪነት ጎራ ለመቀላቀል አቅደው ተነስተዋል፡፡ ኳታርና ሩሲያም የዓለም ዋንጫ ውድድርን ለማዘጋጀት እያወጡት ያለው በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር አሁንም ደግሜ ልጥቀሰው የእግር ኳስ ኃያልነት፣ ሀብት አመንጪነትና የሕዝቦች ቀልብ ሳቢነቱ እየጨመረ ለመሄዱ ማሳያ ምልክት ነው፡፡

በዓለማችን በአሁኑ ጊዜ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካዊና በማኅበራዊ ይዞታዋ ተጠቃሽ እየሆነች ስለመጣችው ቻይና ብዙ እየተነገረ ነው፡፡ በአጠቃላይ በሥልጣኔ ተራምደዋል ከተባሉ ኃያላን የዓለማችን አገሮች ግንባር ቀደምትነት ተራ ይዛ የምትገኝ አገር ናት፡፡ በቴክኖሎጂ፣ በወታደራዊና በኮንስትራክሽን … ወዘተ. ተወዳዳሪ በመሆን መላውን ዓለም እንደ ሞዴል እየተጠቀመባት ያለች አገር ነች፡፡ ነገር ግን በእግር ኳስ ወደ ኋላ የቀረች፣ በዓለም ደረጃ ይቅር በእስያም እዚህ ግባ የሚባል እግር ኳስ የላትም፡፡ በዓለም ዋንጫም እ.ኤ.አ. በ2002 ጃፓንና ኮሪያ ባዘጋጁት የዓለም ዋንጫ ከመሳተፍ የዘለለ ሪከርድ አልነበራትም፡፡

የቻይናውያን ስሜትና ፍላጎት ብቻ ሳይሆን ከዓለም እግር ኳስ ቀደምት ተርታ እንዴት አልተሠለፍንም በሚል ቁጭት ተነሳስተው፣ ለቀጣይ 30 እና 40 ዓመታት ራዕይ ሰንቀውና ዕቅድ ነድፈው የዓለም እግር ኳስን በበላይነት ለመጎናፀፍ ተነስተዋል፡፡ ከዚህ ከመንደርደርም ራዕያቸውንና ዕቅዳቸውን ለመተግበር ሌት ተቀን ደፋ ቀና እያሉ ይገኛሉ፡፡ ለዚህ ዕቅድ ትግበራ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ቻይናውያን ሕፃናትና ወጣቶች ተሳታፊ የሚሆኑበት ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ነድፏል፡፡

በዕቅዳቸው ትልቁ በረዥም ጊዜ ሊሳካ ይችላል ብለው ተማምነው ያስቀመጡት ግብ እ.ኤ.አ. በ2050 ቻይና የዓለም እግር ኳስ ኃያል አገር እንሆናለን በማለት ለዛሬ 34 ዓመታት ለመሥራት ማቀዳቸው በእርግጥም ልንማርበት ይገባናል፡፡ በዕቅዱ መሠረት እ.ኤ.አ. በ2050 የዓለም እግር ኳስ ኃይል (World Football Super Power) ለመሆን የሚያስችላቸውን ሥራ ለመጀመር የአጭር፣ የመካከለኛና የረዥም ጊዜ ዕቅድ ተግባራዊ በማድረግ ተነስተዋል፡፡ በዚህ መሠረትም በአጭር ጊዜ እ.ኤ.አ. በ2020 ግባቸው ሃምሳ ሚሊዮን ሕፃናትንና ወጣቶችን እግር ኳስ መጫወት እንዲችሉ ተሳታፊ ያደርጋሉ፡፡ በተጨማሪም እ.ኤ.አ. በ2030 ለአሥር ሺሕ ሰዎች አንድ የእግር ኳስ ሜዳ እንዲኖር የሚያደርግ ዕቅዱ ውስጥ አስቀምጠዋል፡፡

በሌላ በኩልም የአገሪቱ እግር ኳስ ዕድገት መገለጫ ከሆኑት ውስጥ የብሔራዊ ቡድኖቻቸው ጥንካሬ አንዱና ወሳኙ ሥራ ነው ብለው አስቀምጧል፡፡ በዚሁ መሠረትም የቻይና ወንዶች ብሔራዊ ቡድን በእስያ አገሮች በቅርብ ጊዜ የበላይነት እንዲጎናፀፍ ማስቻል ሲሆን፣ በሴቶች እግር ኳስ ብሔራዊ ቡድናቸው ደግሞ እ.ኤ.አ. በ2030 በዓለም ደረጃ በበላይነት የሚጠቀስ እንዲሆን መሥራት ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ግባቸው ነው፡፡

በአጠቃላይ እ.ኤ.አ. በ2050 ቻይና ለዓለም አቀፍ እግር ኳስ በስጦታ ልታበረክተው ያሰበችው ዕቅዷ ውስጥ የተቀመጡና ለተግባራዊነቱም በመንቀሳቀስ የዓለማችን እግር ኳስ በአንደኛ ደረጃ ኃያል የእግር ኳስ አገር መሆኗን ማረጋገጥ ነው፡፡ በእርግጥ በአሁኑ ጊዜ የፊፋ የደረጃ ሰንጠረዥ ላይ ከ204 አገሮች 81ኛ ላይ የምትገኝ ሲሆን፣ ይህንን ሁሉ እመርታ ለማሳየት ከ30 እና ከ40 ዓመታት በኋላ ስለሚሆነው አቅዶ መነሳት ቁርጠኝነትን ይጠይቃል፡፡ ከነፓናማ፣ ሐይቲና ቤኒን በታች የምትገኘው ቻይና አሁን ያለው ደረጃዋ እኔን አይገልጽም ብላ በቁርጠኝነት ተነስታ ጉዞዋን ቀጥላለች፡፡

ሌላው የእግር ኳስን ጥራት ለማስጠበቅ የቻይና ሱፐር ሊግ ውድድርን ወደ ፕሮፌሽናል ሊግነት ማሳደግና ከአውሮፓ ሊጎች ጋር ተወዳዳሪ ማድረግ ነው፡፡ ስለሆነም ይህንን ለመተግበር የአውሮፓ ታላላቅ፣ ስመ ጥርና ገናና ተጨዋቾችን እየገዙ በየክለቦቿ ተመዝግበው በመጫወት ላይ ናቸው፡፡

ብራዚላዊው የቼልሲ ተጨዋች ራሚረስ፣ አሌክስ ቴክሴራና ጃክሰን ማርቲኔዝ የመሳሰሉትን በሊጉ ውስጥ ተካተው እንዲጫወቱ በማድረግ የሊጉን ደረጃን ከፍ ለማድረግ እየሠራች ነው፡፡ ነገር ግን የውጭ ተጨዋቾች ቁጥርን ከአራት ተጨዋቾች በላይ ሜዳ ገብተው መጫወቱን አይፈቅዱም፡፡ የውጭ አገር በረኛ ቻይና ክለቦች ውስጥ ተመዝግቦ መጫወት አይፈቀድም፡፡ ምክንያቱም የአገር ውስጥ በረኞች በትልልቅ የሊጉ ጨዋታዎች የመጫወት ዕድል እንዲያገኙና ልምድ እንዲቀስሙ ያበረታታሉ፡፡ ይህ ትልቅ ውሳኔ የሚፈልግ ሐሳብ ለኢትዮጵያ እግር ኳስም ወሳኝነቱ አያጠራርጥም፡፡ ፌዴሬሽናችንም እነዚህን የመሳሰሉ ውሳኔዎችን የመወሰን ድፍረት መማር ይኖርበታል፡፡ ለአንድና ለሁለት ክለቦች ጥቅም የአገርን ጥቅም አሳልፎ የሚሰጥ አሠራር ነው እየተከለተ ያለው፡፡ ስለዚህ አርቆ የሚያስብ ፌዴሬሽን ቅድሚያ ከ90 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ የሚወክለውን ብሔራዊ ቡድን ለማጠናከር ነው ማቀድ ያለበት፡፡

የቻይና እግር ኳስ ተወዳዳሪነቱን በዓለም ደረጃ ከፍ ለማድረግ የፕሮፌሽናል ሊግ ምሥረታን አስቀድሞ እ.ኤ.አ. በ2004 ጀምሮ እያሟሟቀው ይገኛል፡፡ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ የሚያፈሱ ክለቦችን ለመመሥረት የዓለማችን ታዋቂ አሠልጣኞችን ወደ ቻይና ክለቦች ለመሳብ ችሏል፡፡ ኤሪክሰን የቀድሞ የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሠልጣኝ፣ ፍሊፕ ስኮላሪ የቀድሞ የብራዚል ብሔራዊ ቡድን ዋና አሠልጣኝ የመሳሰሉ አሠልጣኞችን በየክለቦቻቸው ተቀጥረው እየሠሩ ይገኛሉ፡፡

በአጭሩ ቻይናውያን የአገራቸውን እግር ኳስ ዕድገት በመመኘት በእግር ኳስ ዙሪያ እየሠሩዋቸው ያሉት ሥራዎች እጅግ የሚያኮሩና ተስፋ የተጣለባቸው ዕቅዶች ናቸው፡፡ የአገሪቱ መሪዎች ፕሬዚዳንቱና ጠቅላይ ሚኒስትሩ የበኩላቸውን ዕገዛ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ከያዙዋቸው ዕቅዶች መካከል ፕሬዚዳንቱ የሚፈልጉት በሚቀጥሉት 15 ዓመታት የዓለም ዋንጫ በቻይና እንዲዘጋጅ ማድረግ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለቻይና በጣም ቀላል ይሆንላታል ተብሎ ይገመታል፡፡ እ.ኤ.አ. 008 ኦሊምፒክን ያዘጋጀች አገር የዓለም ዋንጫ ማዘጋጀት አይከብዳትም፡፡ በመሆኑም የቻይናውያንን ህልም ለማሳከት ሕዝቡ፣ ባለሀብቱና መንግሥት ተረባርበው ለውጥና ዕድገት ለማምጣት ተነስተዋል፡፡

ትልቁ የዚህ ጽሑፍ መልዕክት እግር ኳሳችን ከቻይና እግር ኳስ ምን ይማራል? የሚል ነውና የእግር ኳስ መሪዎቻችን ከቻይናውያን እግር ኳስ መሪዎች ተምረው ለለውጥ መነሳት አለባቸው፡፡ ከረዥም ዓመታት ጀምሮ አቅጣጫው የጠፋበት መርከብ ሆኖ የሚንገዋለለውን እግር ኳሳችን፣ አቅጣጫውን ለማሳየት የተደገፈ ሙያተኛ የሚመራው አካሄድ መከተል አለበት ነው የምንለው፡፡ በስሜትና በፍላጎት ሳይሆን በእግር ኳስ ዕውቀት እየተመራ ለዘላቂ ዕድገት የሚያስብ ሩቅ አስቦ ተግቶ የሚሠራ አመራር መሆን አለበት፡፡ ስለአሁን ማሸነፍና መሸነፍ ሳይሆን እግር ኳስን በሕፃናትና በወጣቶች ተወዳጅ ስፖርት በማድረግ በሚሊዮኖች ከሚቆጠሩ ተሳታፊ ሕፃናትና ወጣቶች በመቶ የሚቆጠሩ ጥበበኛ ባለክህሎት ተጨዋቾች ማፍራትን ነው፡፡ አሁን እየጠፋ ያለው በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር የመንግሥትና የሕዝብ ገንዘብ ከንቱ አይቅር! መፍሰስ ባለበት ይፍሰስ፡፡ ለእግር ኳስ መዋል ያለበት በእግር ኳስ ይዋል ነው እያልኩ ያለሁት፡፡ በአጠቃላይ በእከክልኝ ልከክልህ፣ በአድርባይነት፣ በመንደርተኝነትና በመሳሰሉት የተዘፈቀው እግር ኳሳችን ይፅዳና ውጤታማ ይሁን ነው፡፡

ለማንኛውም በዚሁ ጽሑፍ ቅሬታ የሚያድርበት ካለ እሱ የአገራችን እግር ኳስ ዕድገት የማይመኝ ‹‹ለሆዱ አዳሪ›› ብቻ መሆን አለበት ብዬ ነው ልገልጸው የምችለው፡፡ በሌላ ጽሑፍ እስከምንገናኝ መልካሙ ይግጠማችሁ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው  abrhilo14@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

 

 

Standard (Image)

የ‹‹ቁምራ›› ዘመን ቁጠባ

$
0
0

በጌታቸው አስፋው

የመዋዕለ ንዋይ ገንዘብ ምንጭ ቁጠባ በመሆኑ ስለቁጠባ በተደረገው ቅስቀሳና ንግድ ባንኮች እስከ ገጠሩ ዘልቀው በመግባታቸው ብዙ ሰው በርካታ ጥሬ ገንዘብ ቆጥቦ፣ በ2002 ዓ.ም. የመጀመሪያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዝግጀት ወቅት 9.5 በመቶ ብቻ የነበረው ቁጠባ በዕቅዱ መጨረሻ ዓመት 2007 ዓ.ም. በዕቅድ ከተያዘው 15 በመቶው በጣም በልጦ 21.8 በመቶ ሆኗል፡፡ በሁለተኛው ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን መጨረሻ ዕቅድ ዓመት 2012 ዓ.ም. ቁጠባ የአገር ውስጥ ጥቅል ምርትን ሲሶ ወይም 29.6 በመቶ እንዲሆንም ታቅዷል፡፡

በብሔራዊ ባንክ እ.ኤ.አ. 2014/15 ዓመታዊ ሪፖርት መሠረት የቁጠባው መጣኝ በ2002 ዓ.ም. ከነበረበት 9.5 በመቶ ወደ 17.2 በመቶ በእጥፍ የዘለለው፣ በጥቅል የአገር ውስጥ ምርት መለኪያ ዋጋ መከለስ ምክንያት ኢኮኖሚው በወረቀት ላይና በኢኮኖሚ ባለሟሎች ጭንቅላት ውስጥ ሦስት እጥፍ ባደገበት በ2003 ዓ.ም. ነው፡፡

ነገር ግን ሌላ ምክንያት ቢኖር ነው እንጂ የምርቱ በመጠን ሦስት እጥፍ ማደግ ለቁጠባው መጣኝ በአንድ ዓመት ውስጥ እጥፍ መሆን ምክንያት ሊሆን አይችልም፡፡ ምክንያቱም በምርት ዕድገቱ ምክንየት ቁጠባ ብቻ ሳይሆን ፍጆታም በተመሳሳይ ሁኔታ ስላደገ የፍጆታና የቁጠባ ድርሻ መጣኙ ብዙ ሊለወጥ አይችልም፡፡

የቁምራ ዘመን በኢትዮጵያ ወጣቶች የተፈጠረ ስያሜ ሲሆን፣ ትርጉሙ ከቁርስ ምሳና ራት በቀን ሦስት ጊዜ መብላት የቀድሞ ዘመን ወደ ቁምራ (ቁርስን ምሳን ራትን) አጠቃሎ በቀን አንድ ጊዜ መብላት የተሸጋገርንበትና ላለመራብ ቁምራው የሚበላበትን ሰዓት የማስላት ዘመን ነው፡፡ የቁምራ ተጠቃሚ ቁጥር እየበዛ ስለመጣ እንደ ክብደታችንና እንደ ቁመታችን ሰዓቱን የምናሰላበት የቁምራ ሶፍትዌር መመረት ሳያስፈልግም አይቀርም፡፡

እኛ ኑሯችን በሙሉ ቁጠባ ነው፡፡ በዕድርና በዕቁብ አማካይነት ገንዘብ እንቆጥባለን፡፡ ራስጌ ሥር ለክፉ ጊዜ ብለን ገንዘብ እንቆጥባለን፡፡ በቀን አንድ ጊዜ ብቻ ተመግበን ምግባችንን እንቆጥባለን፡፡ አንድ ካናቴራ፣ ሸሚዝ፣ ሱሪ፣ ኮት ወይም ጫማ ለስድስትና ለሰባት ዓመታት ለብሰንና ተጫምተን፣ የቤት ዕቃዎቻችን ለብዙ አሥርት ዓመታት ተጠቅመን፣ ዛኒጋባ ቤቶቻችን ሁለትና ሦስት ትውልድ አሳልፈው ቁሳቁሶች እንቆጥባለን፡፡

ዘመድ ናፍቆን ለመጠየቅ የሄድን መስለን ሰው ቤት በመቀላወጥ ቁምራውንም መልሰን ለነገ እንቆጥባለን፡፡ የማናውቀው ሰው ሲሞት ሳንጠራ ቀብረን የእዝን በመብላት እንጀራና ወጥ ቢጠፋም ንፍሮውን በእጃችን ሙሉ ዘግነን ቁምራውን መልሰን ለነገ እንቆጥባለን፡፡ የቁጠባ ቁጠባ መሆኑ ነው፡፡

ቁጠባ አላሳለፈልንም እንጂ እንደኛ የሚቆጥብ የለም፡፡ ኑሯችን ሁሉ ቁጠባ ነው፡፡ እንኳንስ እኛ ሰዎቹ የቤት እንሰሶቻችንም ይቆጥባሉ፡፡ የቤት ውሾችና ድመቶቻችን ከተሰጣቸው ምግብ ግማሹን በልተው ግማሹን መሬት ቆፍረው ይቀብራሉ፡፡ ከእኛው ነው የተማሩት፡፡ ወይም የእኛን አቅም ስለሚያውቁ በፈለጉት ጊዜ ልንሰጣቸው እንደማንችል ገብቷቸው ነው፡፡

መንግሥት ብዙ ብር ገበያ ውስጥ አፍስሶ ሸቀጥህን በፈለግኸው ውድ ዋጋ ሸጠህ ብቻ ከምታገኘው ግዙፍ ትርፍ ለእኔም ግብሬን ክፈለኝ፣ ለአንተም ባንክ አስቀምጥ፣ አቶ ጌታው ለሕንፃ መሥሪያ ይፈልገዋል ብሎ ሳያስተምረን በፊትም ቆጣቢዎች ነበርን፡፡

ቁጠባና ፍጆታ ከጽንሰ ሐሳባዊ ትርጉም ባሻገር በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ምን እንደሚመስል መሠረታዊ ጥናት የሚሻ ነው፡፡ ምክንያቱም በብሔራዊ ኢኮኖሚ ትርጉሙ ቁጠባ ማለት ትናንትና ዛሬ ከተመረተው ምርት ውስጥ ለነገና ለተነገ ወዲያ ማቆየት ማለት እንጂ፣ ጥሬ ገንዘብ ወይም ብር ባንክ ውስጥ ማስቀመጥና ማከማቸት ስላልሆነ ነው፡፡

ለብሔራዋ ኢኮኖሚ ባንክ ውስጥ የሚቀመጥ ጥሬ ገንዘብ በባንኩ ደላላነት ከአቶ በዛብህ ወደ አቶ ጌታው ዞረ እንጂ ኢኮኖሚያዊ ድምር ውጤቱ ባዶ ነው፡፡ አቶ ጌታሁን ተበድሮ መዋዕለ ንዋይ ባያደርገው ኖሮ አቶ በዛብህ ለፍጆታ ያውለው ነበር የሚለው ጽንሰ ሐሳብ ከኢትዮጵያ ኢኮኖሚና የኑሮ ደረጃ ሁኔታ ጋር፣ ከአበዳሪውና ከተበዳሪው ባህሪያት ጋር ሊጠና ይገባዋል፡፡

በዕድገት ውስጥ ያለ ድህነት

በመርህ ደረጃ ጥቅል የአገር ውስጥ ምርት (GDP) በሦስት መንገድ ተሰልቶ በሦስቱም መንገድ እኩል ይሆናል፡፡ አንደኛው መንገድ የተጨማሪ እሴት ወይም የምርት ቀጥታ ቆጠራ (Value Added or Product Approach) በየአንዳንዱ ሰውና ድርጅት የተፈጠረ ተጨማሪ እሴት ወይም የምርት ቆጠራ መንገድ ነው፡፡ ሁለተኛው የገቢ ስሌት መንገድ (Income Approach) ምርቱን ላመረቱ የምርት ግብረ ኃይሎች፣ ለሠራተኛው፣ ለመሬት፣ ለካፒታል፣ ለድርጅት ባለቤቶች በደመወዝ፣ በወለድ፣ በኪራይ፣ በትርፍ መልክ ተከፋፍሎ ጠቅላላ ገቢው ጠቅላላ የተመረተውን ምርት (ተጨማሪ እሴት) ያክላል፡፡ ሦስተኛው መንገድ የወጪ ስሌት (Expenditure Approach) የምርት ግብረ ኃይሎች ባለቤቶች ባገኙት ገቢ በሙሉ የፍጆታና የመዋዕለ ንዋይ ሸቀጦችን ይገዛሉ፡፡ ስለዚህም ወጪዎች ገቢን ያክላሉ፡፡ ገቢዎችም ምርትን ያክላሉ፡፡ ሦስቱም እኩል ይሆናሉ፡፡

የገቢ መጠን የሚለካው በግብዓተ ምርቶች ገበያ ውስጥ ሲሆን፣ ወጪ ግን የማለካው በምርት ገበያ ውስጥ ነው፡፡ ስለዚህም ገቢ በግብዓተ ምርት ገበያ ወጥቶ ወደ ምርት ገበያ ውስጥ እስከሚገባ ድረስ በሁለት መንገድ ጎድሎ ነው የሚመጣው፡፡ አንዱ ጉድለት ለመንግሥት የሚከፈል ግብር ሲሆን ሌላው ጉድለት ቁጠባ ነው፡፡

በግብዓተ ምርቶች ገበያ ውስጥ የተገኘው የአምራቹ ገቢ ከምርት ገበያ ወጪ ጋር እኩል ለመሆን የጎደለው መሞላት አለበት፡፡ የግብር ጉድለት በመንግሥት ወጪ ሲሞላ የቁጠባ ጉድለት ደግሞ የመዋዕለ ንዋይ ወጪ ይሞላል፡፡

ስለዚህም የግለሰቦች ፍጆታ ወጪ፣ የመንግሥት ፍጆታ ወጪና የግልና የመንግሥት መዋዕለ ንዋይ ወጪ በአጠቃላይ ሸመታዎች (ፍላጎት) ተዳምረው የአምራቾችን ገቢና ምርትን (አቅርቦትን) ያክላሉ፡፡ ሦስቱም የሸመታ ወጪ፣ ገቢና ምርት እኩል ይሆናሉ፡፡ በዚህ ሒሳብ ስሌትም ፍላጎትና አቅርቦት ይጣጣማሉ፡፡ በስንት ብር ዋጋ እኩል እንደሚሆኑ የዋጋ አወሳሰን ኢኮኖሚስቶች ይንገሩን፡፡

የግልና የመንግሥት ፍጆታ ወጪዎች ለዛሬ ለሚጠቅም ምርት ሸመታ የሚወጡ ወጪዎች ሲሆኑ፣ በግብር አማካይነት ከገበያ ወጥቶ በመንግሥት የካፒታል ወጪዎች አማካይነት ወደ ገበያው ውስጥ ተመልሶ የሚገባውና በቁጠባ መልክ ከገበያ ወጥቶ በመዋዕለ ንዋይ መልክ ተመልሶ ወደ ገበያ የሚገባው በረዥም ጊዜ ውስጥ ኢኮኖሚውን ቢያሳድጉም፣ የዛሬውን የሰዎች ችግር ስለማይፈቱ የዛሬን ድህነት ያባብሳሉ፡፡

ቁጠባ በመዋዕለ ንዋይ ከበለጠም እንደዚሁ የሸማቾች ገቢ በሸመታ መልክ ተመልሶ ወደ አምራቾች ስለማይሄድ፣ የተመረተ ምርት ሳይሸጥ ይቀርና አምራቾች ለሚቀጥለው ጊዜ ምርታቸውን እንዲቀንሱ ስለሚያደርጋቸው የምርት መቀነስንና ሥራ አጥነትን ሊፈጥር ይችላል፡፡

ስለዚህም ስለቁጠባ ማደግ ብቻ ሳይሆን የተቆጠበው በገንዘብ ገበያ አማካይነት መዋዕለ ንዋይ ስለሚሆንበት ሁኔታ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ በላይ የተገለጸው የዕድገትና የድህነት ሁኔታ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ጎልቶ የሚታይ ነው፡፡ መሠረተ ልማቶች እየተስፋፉ ስለሆነ መዋዕለ ንዋይ እንዳደገ እናያለን፡፡ የኑሮ ውድነትም ገበያችን ውስጥ ስለሚታይ ድህነት የተንሰራፋ ስለመሆኑና ፍጆታ በቂ ስላለመሆኑ ማስረጃ ነው፡፡

እየኖሩ ማደግ ሳለ እየሞቱ ማደግ

ብዙ ሰዎች በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጥ ያለውን የኑሮ ሁኔታ የሚገልጹት ኢኮኖሚው የሚወራለትን ያህል አላደገም በማለት ነው፡፡ ነገር ግን የብሔራዊ ኢኮኖሚ ሒሳብ ባለሙያዎቹና የስታስቲክስ ባለሥልጣን ብዙ ሺሕ መረጃ ሰብሳቢዎችን አሰማርተው፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ስሌት ዘዴ ተጠቅመው የለኩትን ነገር ትክክል አይደለም ብሎ ለማለት ትክክለኛው ነው የሚሉትን የራስን ማቅረብ ይጠይቃል፡፡

በናሙና ጥናት ደረስንበት የሚሉት የዓለም ባንክ፣ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ወይም የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽንም ቢሆኑ፣ በመጠኑ ከመንግሥት ቁጥር ዝቅ አድርገው ውጤታቸውን የሚያቀርቡት ፈራ ተባ እያሉ በመንታ ልብ ነው፡፡ መንግሥት ለእነርሱም አስፈሪ ሆኗል፡፡በቁጥሮቹ ላይ ከመከራከር ይልቅ ውሸቱን እንደ ውሸት ተቀብሎ በተሰጠው ቁጥርና ገበያ ውስጥ በሚታየው የኑሮ ሁኔታ መካከል ያለውን ልዩነት መመርመር ይሻላል፡፡

ከዚህ ቀደም የጻፍኩትን ልድገምና ሰዎች በጭንቅላታቸው ላይ ባለው ፀጉር ብዛት ቢከራከሩ ምንም ፋይዳ የለውም፡፡ በፀጉሩ ጥቅም ላይ ቢከራከሩ ግን ትርጉም አለው፡፡ የፀጉሩ መብዛት ጥቅም ከዝናብና ከፀሐይ ለመከላከል ጉዳቱም የተባይ ቤት መሆን ይሆናል፡፡ የኢኮኖሚ ዕድገቱም እንደዚሁ ነው፡፡

የኢኮኖሚ ዕድገቱ ሕዝብን ብቻ ሳይሆን ኢሕአዴግንም ይፈትነዋል፡፡ ምክንያቱም ኢሕአዴግ ራሱን ያዘጋጀው የግብርና ኢኮኖሚን ለመምራት ብቻ ሳይሆን፣ በኢንዱስትሪ የበለፀገች የግሎባላይዜሽን ዘመን አገር መሪ ለመሆን ከፍተኛ የገንዘብ አስተዳደር ችሎታን ይጠይቃል፡፡ የአቅም ማነስ ምልክቶቹ አሁንም መታየት ጀምረዋል፡፡

ለቁጥር የትርጉም ዋጋ ሳይሰጠው ለብቻው ቢነገር ይበልጣል ያንሳል ለማለት ካልሆነ በቀር ምንም ጥቅም የለውም፡፡ የኢኮኖሚው በይበልጣል ጠንቋይ ማደግ ካለፉት ጊዜያት መብለጥ ለዋጋ ንረትና ለከፋ ድኅነት ዳረገን እንጂ ጥቅም አላገኘንበትም፡፡

በሦስት መቶና በአራት መቶ ዶላር ዓመታዊ ነፍስ ወከፍ ገቢያችን በሸቀጦች ዋጋ ከአውሮፓና ከአሜሪካ ተስተካከልን፡፡ እንደነርሱ ነፍስ ወከፍ ገቢያችን ሰላሳ ሺሕና አርባ ሺሕ ዶላር ሲደርስ የሸቀጦቻችን ዋጋ የት ሊደርስ ነው?

ከዚህም በላይ ሌላ የምንጠብቀው አደጋ አለ፡፡ ለህዳሴው ግድብ መንግሥት ከሕዝብ የተበደረውን ብዙ ቢሊዮን ብር የቦንድ ግዢ ከነወለዱ ለሕዝብ ሲመልስ የዋጋ ንረት ከፍተኛ እንደሚሆን ለኢኮኖሚስቶች ሚስጥር አይደለም፡፡ ማቀድ አይቸግረንምና መንግሥት ላለመክፈል ካላቀደ በቀር የዋጋ ንረት አደጋ ላይ ነን፡፡ አስፈሪ የዋጋ ንረትና ግሽበትን መንግሥት ለወደፊት እየገፋውና እያስተላለፈው ነው እንጂ እየቀረፈው አይደለም፡፡

የኢኮኖሚ ባለሟሎች የሚበልጡና የሚያንሱ ቁጥሮች መፈብረክ ላይ ችግር የለባቸውም፡፡ ቁጥር የሚፈበርኩ ብዙ የኢኮኖሚ ልኬት ሞዴሎች (Econometric Models) አሉ፡፡ ችግሩ ቁጥሩን መተርጎሙ ላይ ነው፡፡ ቁጥርን መተርጎም ሳይቻል ሲቀር ደግሞ ኢኮኖሚክሱ ተጠቃሎ ማሳረጊያው ይበልጣል ያንሳል ይሆናል፡፡

መሠረታዊ ሁኔታዎች ተሟልተውለት እንደ ሰው ለመኖር የሚፈልገው ሕዝብና እንደ ቻይና ለማደግ የሚፈልጉት የኢኮኖሚ ባለሟሎች የኢኮኖሚ ቁጥሩን በመተርጎም ላይ አልተግባቡም፡፡ ፍጆታ ለዛሬ ነው፣ መዋዕለ ንዋይ ግን ለነገ ነው፡፡ ሕዝቡ ነገ ለመኖር ዛሬ መሞትን አልመረጠም፡፡ መንግሥት ዛሬ ሙትና ነገ ትኖራለህ እያለው ነው፡፡

ኢኮኖሚስቶች ኢኮኖሚን በአጭር ጊዜና በረዥም ጊዜ ውጤት ከፋፍለው መተንተናቸው አዲስ አይደለም፡፡ የብሔራዊ ኢኮኖሚ ሊቁ ኬንስም እንደ ፌዝ ‹‹በረዥም ጊዜኮ ሁላችንም ሟቾች ነን፡፡ ለምን ስለረዥሙ ጊዜ እንጨነቃለን?›› አለ ይባላል፡፡ ለረዥም ጊዜ ማሰብ ቢያስፈልግም እንኳ ነገ ለመኖር ዛሬን እየሞቱ መሆን የለበትም፡፡ ዛሬን ሳንሞት ነገ መኖር የምንችልበት መንገድ አለ፡፡ የዛሬ ኑሮ ሁኔታ የሚገለጸው በፍጆታ መልክ ነው፡፡ የነገ ዕድገት ሁኔታ የሚገለጸው ግን በመዋዕለ ንዋይ መልክ ነው፡፡ ፍጆታና መዋዕለ ንዋይ ሀብት የሚሻሙ ተፃራሪዎች አይደሉም፡፡

ይልቁንም የሚደጋገፉ ሒደቶች ናቸው፡፡ ነገር ግን መደጋገፋቸው ችሎታ ባለው ባለሙያ መገራት አለበት፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ችግርም ከይበልጣል ያንሳል ትንታኔ ወጥቶ፣ የፍጆታንና የመዋዕለ ንዋይን መደጋገፍ የሚፈጥር ባለሙያ ባለመኖሩ እየኖሩ ማደግ ሲቻል እየሞቱ ማደግ እንደ አማራጭ መወሰዱ ነው፡፡

ለዚህም ነው ቁጠባ ላይ ያተኮረ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ከምንም በላይ ትኩረት የተሰጠው፡፡ የቤት እንሰሶቻችን በዓመት በዓል ቀን በሰው ተግጦ ከተሰጠ የአጥንት ቀለባቸው ውስጥ ግማሹን በልተው ግማሹን ቆጥበው ምድር ውስጥ ይቀብሩታል፡፡ የኢትዮጵያ ደሃም እንደዚሁ ሀብታም ከጋጠው ቆጥበህ አስቀምጥ ነው የተባለው፡፡

አንድ ካናቴራ፣ የውስጥ ሱሪ፣ ኮት፣ ጫማ፣ ወዘተ ለዚያውም የተቀዳደደውን ሰፍቶና ቆጥቦ ስድስትና ሰባት ዓመታት ከመልበስ አልፎ በቁምራ ስሌት በቀን አንዴ በልቶ ከመኖር አልፎ፣ በደሳሳ ጎጆ ከመኖር አልፎ ብር ቆጥብና ባንክ አስቀምጥ፣ ባንኮች ለሕንፃ ገንቢው አበድረው ከተማችን በሕንፃ ትጥለቀለቃለች ይባላል፡፡

የመዋዕለንዋይ ገንዘብ አቅርቦት ችግር

ነጋዴው በገንዘብ ዕጦት ሥራ ሊቆም ነው ይላል፡፡ ንግድ ባንኮች መንግሥት በምናበድረው ገንዘብ ሃያ ሰባት በመቶ ቦንድ እንድንገዛ ያስገድደናል ይላሉ፡፡ ብሔራዊ ባንክ በሚያዘጋጀው ዓመታዊ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ሪፖርት ንግድ ባንኮች በሕግ ተደንግጎ በብሔራዊ ባንክ ማስቀመጥ ከሚገባቸው መጠባበቂያ ተቀማጭ በላይ እስከ ቢሊዮን ትርፍ ብር በየዓመቱ ያስቀምጣሉ፡፡ የባንክ ለባንክ መበዳደርም እጅግ በጣም ዝቅተኛ ነው፡፡

ሪፖርተር ጋዜጣ እሑድ ታኅሳስ 19 ቀን 2007 ‹‹የፋይናንስ አቅርቦት አሁንም እያከራከረ ነው›› በሚል ርዕስ ለንግዱ ማኅበረሰብ የብሔራዊ ባንክ ባለሥልጣን የአክሲዮን ባንክ ሳይስፋፋ የመዋዕለ ንዋይ ባንክ ማቋቋም ዋጋ የለውም በማለት የሰጡትን መልስ፡፡ የልማት ባንክ ባለሥልጣንም ልማት ባንክ ብሔራዊ ባንክ የፈቀደለትን ገንዘብ እንኳ አበድሮ አልጨረሰም በማለት የሰጡትን መከራከሪያ መልስ አውጥቶ ነበር፡፡

ስብሰባውን ያልተካፈለው የገንዘቡ ምንጭ የሆነው ቆጣቢው ድምፁን የማሰማት ዕድል አጥቶ እንጂ፣ የእርሱን ያህል የተጎዳ የለም፡፡ በአሥራ ሁለት በመቶ የዋጋ ንረት የገንዘብ ሸቀጦችን የመግዛት አቅም በአሥራ ሁለት በመቶ ስለሚወድቅ፣ አምስት በመቶ የቁጠባ ወለድ እያገኘ ገንዘቡን ባንክ የሚያስቀምጥ ሰው ለተበዳሪው ሰባት በመቶ ከፍሎ እንዳበደረ ወይም ገንዘቡን በኪሳራ እንደሸጠ ይቆጠራል፡፡ ይህን ለማትረፍ ሳይሆን ለችግር ጊዜ ብሎ እየከሰረ የሚያበድር ቆጣቢ መንግሥትም በዛብህ ብሎ ከአምስት በመቶዋ ወለድ ላይ የካፒታል ዕድገት ታክስ ያስከፍላል፡፡

ሰዎች ገንዘብ የሚቆጥቡት ለሁለት ጉዳይ ነው፡፡ አንድም ለችግር ጊዜ ይሆነኛል በማለት አለበለዚያም ወለድ አግኝቶ ለማትረፍ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ሁኔታ ቆጣቢው ኪሳራ እንጂ ትርፍ ስለማያገኝ፣ መቆጠቢያ ምክንያቱ በድሆች ለችግር ጊዜ ተብሎ ነው፡፡ ሀብታም እንደሆነ ድንጋይ እንጂ ገንዘብ አይቆጥብም፡፡

ለችግር ጊዜ ብቻ ተብሎ በደሃው የገቢ ሲሶ ከተቆጠበ፣ ለማትረፍ ተብሎም ቢቆጠብ ከጥንካሬያችን የተነሳ ቁምራቸውን በሦስት ቀን አንድ ቀን ተመግበን ብዙ እንቆጥብ ነበር፡፡ ለኑሮ ብለን ዓረብ አገር ለመሰደድ አሸዋና ባህር የበላን ሰዎች ለዚህ አናንስም ነበር፡፡

ከዚህ አበድሮ በገዛ ገንዘብ መክሰርም ይባስ ብሎ መንግሥት በእኔ መስመር ካልሆነ በቀር ገንዘብ ልትበዳደሩ አትችሉም በማለት ሕግ አውጥቶ ከሳሽ ተቋም መሥርቶ ዘብጥያ ይወረውራል፡፡

በአውሮፓና በአሜሪካ እንዲሁም በቻይና ዕድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ያደረጉት ሕጋዊ የቁጠባ ተቀማጭ ሒሳብ መያዝና ብድር የመስጠት የንግድ ባንክ ሥራ ፈቃድ ሳይኖራቸው፣ በሥውር የባንክ ሥራ (Shadow Banking) ገንዘብ የሚያገበያዩ የገንዘብ አስተላላፊ ተቋማት ሲሆኑ፣ ሕጋዊ የንግድ ባንኮችም በተባባሪዎቻቸው አማካይነት በዚህ ተግባር በስፋት ይሳተፋሉ፡፡

እነኚህ እንደ ንግድ ባንክ የተቀማጭ ሒሳብ ጥሬ ገንዘብ ለመቀበል ሕጋዊ መሠረት የሌላቸው የገንዘብ ተቋማት በአውሮፓ፣ በአሜሪካና በቻይና ከንግድ ባንኮቹ ያልተናነሰ ሀብት ያንቀሳቅሳሉ፡፡ በቻይና ሃያ ትሪሊየን ዶላር የሚጠጋ ሀብት አላቸው፡፡ በአሜሪካም እስከ ሃያ አምስት ትሪሊየን ዶላር ይንቀሳቀሳል፡፡

ኢትዮጵያ የመዋዕለ ንዋይ ገንዘብ አጠረኝ እያለች እየጮኸች ለምን ይሆን ሕዝቡ በነፃነት ገንዘቡን እንዳይገበያይ በሕግ የከለከለችው? ይህ ነፃ ገበያ የሚባለው ነገር ደርግ በ1967 ዓ.ም. ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ ቃሊቲ ወህኒ ቤት ከላከው ጀምሮ የተመለሰ አይመስልም፡፡

በቁምራ ስሌት እየኖረ ለባለፀጎች ራሱ ከፍሎ የሚያበድረው ቆጣቢ ከአገር ውስጥ ምርት ቁጠባው 21.8 በመቶ መድረሱ ኢኮኖሚው የተዋቀረበት ሥርዓት ለሀብታም ያደላ እንደሆነ የሚያመለክት ነው፡፡ በተለይም ከሦስት ዓመት በፊት ለቤት ሥራ ተብሎ በውዴታ ግዴታ እንዲቆጥቡ የተደረጉት ጫማ አሳማሪዎች፣ ሳልቫጅ ነጋዴዎች፣ የቤት ውስጥ አገልጋዮች፣ የቀን ሙያተኞች በዚህ ስሌት ምን ያህል ለተበዳሪ ሀብታም እየከሰሩ እንደገበሩ ሲታሰብ፣ ከጪሰኛና ከባላባታዊ ሥርዓት የከፋ ለጨቋኝ መደብ የቆመ ዘመናዊ የኢኮኖሚ ብዝበዛ ሥርዓት ነው፡፡

ከእንግሊዙ ታላቁ ትራንስፎርሜሽን ምን እንማር?

መንግሥት ትራንስፎርሜሽኑ የሚመጣው ቁጠባና መዋዕለ ንዋይ ከጨመሩ ነው ብሎ ይገምታል፡፡ ለማኑፋክቸሪንግ የሚሆን መዋዕለ ንዋይ ከገበሬውና ከከተሜው ጥሮ ግሮ ለፍቶ አደር ከተገኘ ትራንስፎርሜሽኑ በራሱ ጊዜ እንደሚመጣ ያምናል፡፡ ይህ ግን ሊሆን እንደማይችል በዘንድሮው ድርቅ አይተናል፡፡

ከቁጠባውና ከመዋዕለ ንዋዩ ማደግ ትራንስፎርሜሽኑ መቅደም እንዳለበት ከታላቁ የእንግሊዝ ትራንስፎርሜሽን ምን እንማራለን? የሌለውን ሰው ተርበህ ቆጥብ ማለት ይሻላል ወይስ በቅደሚያ እንዲኖረው ማድረግ? ምክንያትና ውጤትን መለየት አለብን፡፡

ስለእንግሊዙ ትራንስፌርሜሽን ሚካኤል ፐርልማን የተባሉ በካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር የካፒታሊዝም አፈጣጠር (The Invention of Capitalism Duke University Press 2000) በተሰኘ መጽሐፋቸው፣ ገበሬዎች በገዛ ንብረታቸው ራሳቸውን በራሳቸው ቀጥረው ከሚኖሩበት የግብርና ሥራ ኑሮ ለመላቀቅና በፋብሪካ ተቀጥረው ለመሥራት ፈቃደኛ እንደማይሆኑ የነፃ ገበያ የመጀመሪያዎቹ ጠንሳሾች እንደተረዱ ጽፈዋል፡፡

ስለሆነም በጊዜው የፖለቲካ ኢኮኖሚ አስተሳሰብ ዝነኛ የሆኑት አዳም ስሚዝ፣ ዴቪድ ሪካርዶ፣ ጀምስ ስቱዋርት ሚልና ሌሎችም ከርዕዮተ ዓለም ቀኖናዊ እምነታቸውና ከነፃ ገበያ ፍፁም ነፃነት አስተምሮታቸው ውጪ ከአርሶ አደርነት ወደ የእርሻና የገጠር ፋብሪካ ወዛደርነት ለሚደረገው ትራንስፎርሜሽን፣ የመንግሥት ጣልቃ በመግባት ተፅዕኖ መፍጠርን አስፈላጊነት አሳስበዋል፡፡

ፋብሪካ በከተማ ብቻ ሳይሆን በገጠርም ሊቋቋም የማይችልበት ምክንያት የለም፡፡ የአውሮፓ ፋብሪካዎች ወደ አፍሪካ የሚመጡት በከተሞቹ ማማር ሳይሆን ጥሬ ዕቃ፣ ርካሽ ጉልበት፣ መሬትና ገበያ ፍለጋ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ያለውም ከተማ ሳይሆን ገጠር ነው፡፡

በመንግሥት የገጠር መሬት ፖሊሲ ኢሕአዴግና ቅንጅት በ1997 ዓ.ም. ባደረጉት ክርክር የኢሕአዴግ ፅኑ እምነት የነበረው መሬት የገበሬው የግል ንብረት ከሆነ ሸጦ ወደ ከተማ ይሰደዳል የሚል ነበር፡፡ ኢሕአዴግ ያንኑ ፖሊሲ እስካሁን ድረስ እንዳልለወጠ በተለያዩ ስትራቴጂዎቹና የፖሊሲ ዶኩሜንቶቹ ደጋግሞ ይገልጻል፡፡ የእንግሊዝ መንግሥት አርሶ አደር ወዝ አደር እንዲሆን ተፅዕኖ አሳደረ፡፡ የእኛ መንግሥት በፖሊሲ ተከላከለ ወይም ከለከለ፡፡

ይህ የኢሕአዴግ እምነት ከእንግሊዙ ታላቅ ትራንስፎርሜሽን በተቃራኒ መንገድ ነው፡፡ ወይ እነርሱ ወይ እኛ ተሳስተናል፡፡ የተሳሳትነው እኛ መሆናችንን በማስረጃዎች ማረጋገጥ ይቻላል፡፡

እነርሱ በሁለት በመቶ የገበሬ ቁጥር መላውን ሕዝብ ሲመግቡ፣ እኛ በሰማንያ አምስት በመቶ ቁጥር እንኳ ራሳችንን መመገብ አልቻልንም፡፡ እነርሱ ከተፈጥሮ ጥገኝነት ተላቀው የአየር ንብረት ለውጥ አያስጨንቃቸውም፡፡ እኛ ድርቅ በመጣ ቁጥር ለዕርዳታ ጥሪ እንጮሃለን፡፡ እጆቻችን ወደ ላይ ይዘረጋሉ፡፡ የኤምባሲዎችን በር እናንኳኳለን፡፡ የእኛን ግማሽ ያህል ዕድገት ያላስመዘገቡት አፍሪካውያን በረሃብ ስማቸው ሳይጠራ እኛ በማደግም አንደኛ፣ በመራብም አንደኛ እንሆናለን፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው   Getachewasfaw240@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

የኢትዮጵያና የኤርትራ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ምን ፍሬ አፈራ?

$
0
0

በቃለአብ ወልደኪዳን

የሕዝብ ለሕዝብ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት በሁለት ሉዓላዊ አገሮች ውስጥ የሚካሄድን ግንኙነት ለማጠናከር የሚረዳ የዘመናዊ ዲፕሎማሲ አካል ነው፡፡ በተለይ አገሮች በግጭት ውስጥ ካሉ ሊያግባባቸው የሚችል አወዛጋቢ ጉዳይ ካለ ወይም የባለቤትነት ጥያቄም ሆነ የታሪክ ሽሚያ የሚታይበት መንግሥታዊ ፉክክር ከነገሠ፣ መፍትሔ አምጪው አንዱ መድረክ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን ማጠናከርና በሒደት ወደ መንግሥታትና ሥርዓት ደረጃ ማሳደግ ነው፡፡

በዚህ ረገድ በዓለም አቀፉ የሕዝብ ለሕዝብ መድረክ ተጠቃሽ የሆኑ ተሞክሮዎች እንዳሉም ይታወቃል፡፡ በቀዳሚነት የእስራኤልና የፍልስጤም ተሞክሮ ይጠቀሳል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1975 በአንድ ኖርዌጂያዊ ምሁር አነሳሽነት ግንኙነቱ ተጀምሮ የቀድሞው የእስራኤል መሪ ይስሃቅ ራቢንና የፍልስጤም ነፃ አውጪ ድርጅት መሪ የነበሩት ያሲን አራፋት የኦስሎ ስምምነትን ፈርመዋል፡፡ እንደ አገር ዕውቅና የመሰጣጣትና የሰላም ድርድሮችም የተጀመሩት ከዚያ በኋላ ነበር፡፡

ከእንግሊዝ ቅኝ አገዛዝ ነፃ ከወጡ በኋላ ለሁለት የተከፈሉት ህንድና ፓኪስታን ከሦስት ጊዜ ጦርነት በኋላ የጀመሩት የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትም በመስኩ ተጠቃሽ ተግባር ነው፡፡ በአፍሪካ የሩዋንዳና የብሩንዲ፣ ከእስያ የጃፓንና የቻይና ተሞክሮዎችም አብነቶች ናቸው፡፡

ወደ አገራችን ሁኔታ ስንመለስ ኢትዮጵያ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ በግብፅና በሱዳን በኩል ለሚነሱ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥያቄዎች የሕዝብ ዲፕሎማሲ (Public Diplomacy) አንዱ መፍትሔ ሆኗል፡፡ በዚህም በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ደረጃ ራሱን የቻለ ዳይሬክቶሬት ተቋቁሞለት፣ ሙያተኞች ተቀጥረውለት እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡ እንደ አገርም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ የሚመራ የፖለቲከኞች፣ የምሁራን፣ የማኅበራት መሪዎች፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የሥነ ጥበብና የመገናኛ ብዙኃን መሪዎች የተካተቱበት የሕዝብ ዲፕሎማሲ ግብረ ኃይል ተቋቁሟል፡፡

ከዚያም አልፎ ቡድኑ ከአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርና ፕሬዚዳንት ጋር ተገናኝቶ በመምከር ግብፅና ሱዳን ተጉዞ የኢትዮጵያን ሕዝብ በመወከል ምክክር አድርጓል፡፡ ከዓመት በፊት የግብፅን የሕዝብ ለሕዝብ ቡድን በቅርቡም የሱዳን ልዑካን በመቀበልም አዎንታዊ ግንኙነትና መተማመን መፍጠር ተችሏል፡፡

ከአሥራ ስምንት ዓመታት በፊት ጦርነት ውስጥ ገብተው ‹‹በሰላም የለም ጦርነት የለም›› ውስጥ ያሉት ኢትዮጵያና ኤርትራ ግን በሕዝብ ለሕዝብ መስክ ያሳዩት ጥረት የለም፡፡ በኢትዮጵያ በኩል የተቋቋመው ግብረ ኃይልም ስለ ኢትዮ-ኤርትራ ጉዳይ እስካሁን ያለው ነገር የለም፡፡ እንዲያውም የዚህ ቡድን አባል የሆነ ምሁር ‹‹የኢትዮጵያና የኤርትራን የሕዝብ ለሕዝብ መጋረጃ በጥሶ ጠንከር ያለ የንቅናቄ ሥራ ለመሥራት መንግሥታት ያጡት ቁርጠኝነት ዋነኛ እንቅፋት ሆኗል፤›› ማለታቸው አይዘነጋኝም፡፡

ከዚህ ይልቅ መንግሥታዊ የሆነውና ተጠሪነቱ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሆኑ የሚታወቀው ‹‹የኢትዮጵያ የሰላምና የልማት ዓለም አቀፍ ኢንስቲትዩት›› እያደረጋቸው ያሉ ሙከራዎች እንዳሉ ይሰማል፡፡

በተለይ ካለፉት አራትና አምስት ዓመታት ወዲህ ተቋሙ በኢትዮጵያ በኩል የሕዝብ ለሕዝብ ዲፕሎማቶች አመራረጥና ሽማግሌዎች መለየት ላይ ግልጽነት ያለው አሠራር፣ መድረኮች፣ ልዩ ልዩ ጥናቶችና ኅትመቶችን በመሥራት ላይ ነው፡፡ ስደተኞቹ የትምህርት ዕድል፣ አመቺ የሥራ ሁኔታና ወደፈለጉት አካባቢ የመጓዝ ዕድል እንዲያገኙም የመንግሥት ፖሊሲን እየተከተለ በመሥራት ላይ እንደሆነ ይታወቃል፡፡

ግን አሁን ጥያቄው ‹‹የኢትዮ-ኤርትራ ሕዝብ ለሕዝብ ጥረት ምን ፍሬ አፈራ!?›› የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ እውነት ለመናገርስ ከሁለቱ አገሮችና
ሕዝቦች የታሪክ፣ የባህል፣ የሃይማኖት፣ የቋንቋና የጂኦግራፊ ጠቀሜታ አንፃር ሲታይ የግብፅና የሱዳን በልጦና ቅድሚያ የሚሰጠው ሆኖ ነው የሰሜኑ የሕዝብ ለሕዝብ በር የተዘጋበት!? ነው ወይስ የኤርትራ መንግሥት በጀመረው መንገድ ፀረ ዴሞክራሲያዊ አገዛዙንና ፀብ አጫሪነቱን ከቀጠለ ሳይወድ በግድ ራሱን ጠልፎ ስለሚጥል ችግሩ ይፈታል በሚል?

በእርግጥ የኤርትራ ሕዝብ አሁን በገጠመው የኑሮ ጣርና አፈና በስፋት እየተሰደደ ነው፡፡ ምሁራን፣ የአገርና የሃይማኖት ሽማግሌዎች እንዲሁም የተወሰኑ የአገሪቱ ተቆርቋሪ ፖለቲከኞችን ሻዕቢያ አስሯል፣ አሳድዷል፡፡ ያመቸውንም አሰቃይቶ ገድሏል፡፡ ቀደምት የግንባሩ ታጋዮች ላቀረቡት ሥልጣንን በሒደት ለሕዝብ የእናስረክብ ጥያቄ እንኳን በአጸፋው እስራትና አደገኛ ቅጣት ነው ያከለበት፡፡

በተለይ የኢሳያስ አፈወርቂ መራሹ የኤርትራ አምባገነናዊ አገዛዝ ይበልጡኑ በራሱ ግፊትና ጀብደኝነት ከአገራችን ጋር ጦርነት ውስጥ መግባቱ ይታወቃል፡፡ በተለይ ከ1990 እስከ 1993 ዓ.ም. ድረስ ባሉት ጊዜያት ውስጥ በብዙ ሺዎች ለሚቆጠሩ የሁለት አገሮች ወጣቶች እልቂትና ከደሃ አገሮች ኢኮኖሚ አንፃር ከፍተኛ የሚባል ሀብት ለጦርነቱ ተማግዷል፡፡ በዚህም ምክንያት ሻዕቢያ ለከፍተኛ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ተደርጓል፡፡

ከላይ እንደተገለጸው ለብዙዎች እስራትና ስደት መንስዔ ከሆነ የፖለቲካ ውዝግብ ባሻገር የሕዝብ ድምፅ ያሰሙ የነበሩ የግል ጋዜጦችም ተዘጉ፡፡ ጋዜጠኞችም እስካሁን ያሉበት ሁኔታ እንኳን አይታወቅም፡፡ በዜጋው ደጃፍና አደባባይ ሳይቀር የስለላና የጆሮ ጠቢዎች ትስስር በመዘርጋት ፍርኃትና አለመተማመን እንዲንሰራፋ መደረጉን፣ ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ሳይቀር የዘገቡት እውነት ነው፡፡

የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብቶችን የሚያነሱ የአስመራ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ወደ በረሃ እስር ቤቶች ተግዘው ተቋሙ መዘጋቱ፣ ወጣቱ በብሔራዊ ግዳጅ ስም በወታደርነት ተጠምዶ መቆየቱ፣ የሥርዓቱ ቁንጮዎች ሙስና፣ ፈላጭና ቆራጭነትም ኤርትራዊያኑን በአገራቸው ባዳና ተሰዳጅ አድርጓቸዋል፡፡ በዚህም ለከፋና ትልቅ ስደት እንዳደረጋቸው ይታወቃል፡፡

መውጫ እንዳጣ ጭስ ባገኘው ክፍት ቦታ ሁሉ እየተሰደደ ያለው የኤርትራ ወጣትና አምራች ኃይል አምባገነናዊ ጭቆናውንና ምዝበራውን ሊቋቋመው ባለመቻሉ ነው፡፡ ያም ሆኖ ወደ ኢትዮጵያ የሚደረገው ሰፊ ፍልሰትና ስደት ‹‹የቸገረው እርጉዝ ያገባል›› የሚያስብል አይደለም፡፡ ምክንያቱም የሁለቱ አገሮች ሕዝቦች ከነበሯቸው የጋራ እሴቶችም በላይ በታሪክ አጋጣሚ በአንድ ሉዓላዊ ግዛት ሥር የነበሩና ክፉውንም ደጉንም በጋራ ያሳለፉ ነበሩ፡፡

እንዲያም ሆኖ በተለይ በአዲሱ የኤርትራ ትውልድ ላይ ላለፉት 25 ዓመታት ሲነዛ የኖረው ጥላቻና የበቀል ፕሮፓጋንዳ ሳይሟሽ፣ በመጠጋገንና በውሸት ሲገመድ የኖረው የአገራቱ የታሪክ ዳራና ፈለግ በሀቅና በጥናት ሳይዳሰስ፣ ከታሪክ ይልቅ ፖለቲካና ጦረኝነት ወሳኝ በነበሩበት ሁኔታ ቅልቅል የመሰለውን ስደትና የስደት ተቀባይነት ማስቀጠል አስቸጋሪ እንደሆነ ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ ምናልባት ዘላቂ መፍትሔ ሊሆን የሚችለው ከፖለቲካ ጫና ነፃ የሆነ አገርን ሊወክል የሚችል የሕዝብ ለሕዝብ ቡድንን በሁለቱም ወገን አቋቁሞ መሥራት ይሻል ነበር፡፡

በእርግጥ በአንድ እውነት መተማመን ይገባል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ለሰላም፣ የኤርትራ ስደተኞችን ለማስተናገድና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱም እንዲሻሻል ከሻዕቢያ የተሻለ ፍላጎትና ቁርጠኝነት ያለው መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይህን ሁኔታ በተጨባጭ መገለጫዎች ማየት ይቻላል፡፡

በኤርትራው አመፀኛ አገዛዝ ውስጥ እንኳንስ የኢትዮጵያ ስደተኞች ሊኖሩ ይቅርና የራሱንም ዜጎች አላስቆም አላስቀምጥ ያለ ነው፡፡ ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት ግን አንዳንዴ ከሕዝቡ ፍላጎትም ያለፈ የሚመስል ዕገዛና ድጋፍ ለኤርትራውያኑ በማድረግ ላይ ነው፡፡

ለአብነት ያህል የኤርትራ ስደተኞች በተለያዩ የሠፈራ ጣቢያዎች ማለትም ሽመልባ፣ ማይህይኒ፣ አዲሃሩሽ፣ አሳሂታ፣ በርሐለ በመቀበል እንደ ማንኛውም ስደተኛ እንዲኖሩ ያደርጋል፡፡ የውኃ፣ የእንጨት፣ የመሬትና የጥበቃ አቅርቦት ያደርጋል፡፡

ኤርትራውያን ስደተኞች ግን ከሌሎች አገሮች ስደተኞች በተለየ የመንቀሳቀስ፣ የመሥራት፣ ከዘመድ አብሮ የመኖር መብቶችን ያገኛሉ፡፡ ለዚህም የሚጠቀሰው ዋነኛ ምክንያት በኤርትራ ካሉት ዘጠኝ ብሔረሰቦች አምስቱ (ትግረኛ፣ አፋር፣ ሳሆ፣ ብሌንና ኩናማ) ኢትዮጵያ ውስጥ ስላሉ የቅርብም ይሁን የሩቅ ዘመድ ስላላቸው ነው፡፡ ለነገሩ ከሃያ አምስት ዓመታት በፊትና ከዚያም በኋላ እስከ 1990 ዓ.ም. ድረስ እንደ አንድ አገር ሕዝብ በመኖራቸው ብቻና መወለድ አስተሳስሯቸው እንደነበር አይካድም፡፡

ኤርትራውያን ወጣቶች እንኳን ተሰደው በአገራቸው እንኳን ያላገኙት የከፍተኛ ደረጃ የትምህርት ዕድልም እንዲያገኙ በመፈቀዱ በሺዎች የሚቆጠሩ የኤርትራ ወጣቶች ከመጀመርያ ዲግሪ እስከ ድኅረ ምረቃ በመላው አገሪቱ ይማራሉ፡፡ ሌላው ተጠቃሚነታቸው የሚገለጸው ደግሞ እስካሁን ወደ ኢትዮጵያ መሰደድ ከጀመሩ ከሃምሳ ሺሕ የሚበልጡ ኤርትራውያን ወደ ምዕራባውያን መልሶ ስደት አግኝተው መጓጓዛቸው ነው፡፡ ይህ በህንድ ውቅያኖስ በየበረሃው ተሰቃይተው እንኳ ከማያገኙት ዕድል አንፃር ሲታይ ትልቅ አማራጭ ሆኗቸዋል፡፡

በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ጊዜ ቤት ንብረታቸውን ትተው ወደ ኤርትራ ተመልሰው የነበሩ ሰዎችም አዲስ ዕድል ተፈጥሮላቸዋል፡፡ ይኸውም የዋስትና መብታቸውን በመጠበቅ በፈለጉት ጊዜና ሁኔታ ተመልሰው ንብረታቸውን እንዲረከቡና በወኪላቸው በኩል እንዲሸጡና እንዲለውጡ መፈቀዱ ነው፡፡ በእርግጥ ይህ ተግባር የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ለኤርትራ ሕዝብ ያላቸውን ፍቅርና አክብሮት በተግባር ያሳዩበት ትልቅ ዕርምጃ ነው፡፡

በሌላ በኩል ማንም በውጭ አገር የሚኖር ኤርትራዊ ኢትዮጵያ ውስጥ የፈለገውን ዓይነት ኢንቨስትመንት (እስከ ግሮሰሪና ሽሮ ቤት ድረስም ቢወርድ የሚከላከል አይመስለኝም) እንዲያደርግ ተፈቅዷል፡፡ ይህም ቢሆን በአገራቸው ሊያገኙት ያልቻሉትን የዜግነት መብት በኢትዮጵያ እንዲቋደሱ ተደርጓል፡፡

ለዚህም ነው በተለይ በአዲስ አበባ አንዳንድ ሠፈሮች የኤርትራ ስደተኞች በብዛት ከትመው የፈለጉትን እየሠሩ መኖር ከመቻላቸውም ባሻገር ‹‹እስመራ››፣ ‹‹አባ ሻውል›› ‹‹ደቀመሐሪ›› … ዓይነት የመንደርና የብሎክ ስሞች ዳግም እየተፈጠሩ ነው ያሉት፡፡

በተቃራኒው ሻዕቢያ አሁንም ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በማጥላላት ላይ ተጠምዷል፡፡ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃንን ማየትና ማንበብ ከመከልከል ባሻገር የአማርኛ ሙዚቃን እንኳን ሕዝብ ውስጥ ለውስጥ እየኮመኮመ ቢሆንም፡፡ አንድ የቅርብ ጊዜ የኤርትራ ስደተኛ፣ ‹‹የኤርትራ ሕዝብ ከኢትዮጵያ ወገኑ በመነጠሉ ብቻ ሳይሆን ሻዕቢያን ለመሰለ ፀረ ዴሞክራሲያዊ አገዛዝ ተደርጎ ችግር ላይ በመውደቁ ክፉኛ የሚፀፀትበት ጊዜ አሁን ነው፤›› ብሏል፡፡

እንግዲህ በሁለቱ አገሮች በኩል ያሉት መንግሥታት ፖሊሲ ይህን ያህል የጎላ ልዩነት ያለው ቢሆንም፣ ሕዝቦቹ እንደ ሕዝብ ይበልጥ እንዲቀራረቡ እየተሠራ ያለው ሥራ ግን በቂ የሚባል አይደለም፡፡ በአንድ ወቅት በተለይ በአፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ያለምንም የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ውህደት ከመሀል አገር ወደ ኤርትራ ብዙ ዜጎች እየተጋዙ እንደሚሰፍሩ፣ አሁንም ያለበቂ ትስስር ብዙ ኤርትራዊያ ወጣቶችን ወደ ኢትዮጵያ አስገብቶ ማስፈሩ ብቻ ትስስርን አይፈጥርም፡፡

እንዲያውም ሕዝብ ለሕዝብ ጠንከር ያለ መቀራረብ፣ ይቅር መባባል፣ ብሔራዊ ዕርቅና የአብሮነት መንፈስን የሚያመጡ ፖለቲካዊ ዕርምጃዎች አለመወሰዳቸው በኢትዮጵያውያኑ በኩል ‹‹ተመልሰው መጡብን፣ ኑሮ ውድነት አባባሱብን (በተለይ የኮንዶሚኒየም ቤት ኪራይ)፣ አንዳንዶቹ የኤርትራ መንግሥት መረጃ ሰዎች ቢሆኑስ? ሕገወጥ ተግባር ላይ ተሰማርተው (ኮንትሮባንድ፣ ኢንተርኔት፣ ስልክ) መንግሥት ዝም አላቸው …›› ዓይነት ጥርጣሬን ይፈጥራል፡፡ ደግሞም እየፈጠረ ነው፡፡

በኤርትራ ስደተኞች በኩልም በመተማመንና ይበልጥ በመቀራረብ ከአገሬው ጋር አብሮ ከመኖር ይልቅ መጠራጠርና ‹‹የራስን ወገን›› ብቻ የመፈለግ ዝንባሌ ይታያል፡፡ አሁን ለሻይ ለቡናም ሆነ ለመኖር እንዳለው መሳሳብ ዓይነት፡፡ በሌላ በኩል ይፋዊ የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር አለመደረጉም ኢትዮጵያን ለመሸጋገሪያ የመጠቀም እንጂ፣ በዘላቂነት ለመኖሪያ እንዳይመርጡት (በተለይ እዚህ ዘመድ የሌላቸው) እያደረጋቸው መሆኑን ይናገራሉ፡፡

በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ከኤርትራ ብቻ ሳይሆን ከሁሉም የጎረቤት አገሮች ሕዝቦች ጋር የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት እንዲጠናከር መሥራት አለባት፡፡ ታላቅ ሕዝብ ያላት በኢኮኖሚም እየተቀየረች ያለችና ስትራቴጂካዊ ቦታ የያዘችው ኢትዮጵየ ጉርብትናዋን በመንግሥታት ፖሊሲ ብቻ ቀይዳ ረዥም ርቀት መሄድ አይቻላትም፡፡ በተለይ ደግሞ በታሪክ አጋጣሚ በአንድ ባንዲራ፣ ድንበርና ሉዓላዊነት ሥር የኖሩት የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦች የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት በትኩረት ሊታይ ይገባል፡፡ የኢትዮጵያ የሰላምና የልማት ዓለም አቀፍ ኢንስቲትዩት አጀማመርም በአንድ እግር እንደ መራመድ በመሆኑ፣ ሁሉን አቀፍ ጥረት በአዲስ መልክ ሊጀመር ይገባዋል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው kwold2@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

Standard (Image)

የበላይ አለቆችን ትኩረት ለመሳብ የቋንቋ አጠቃቀምን ማወሳሰብ

$
0
0

በመርሐጽድቅ መኮንን አባይነህ

ይነስም ይብዛ እያንዳንዱ ዲሲፒሊን ከመደበኛው ቋንቋ ወጣ ያለ የራሱ ቴክኒካዊ ልሳን እንደሚያዳብር ይታመናል። ፖለቲከኞችና ሐዋሪያዎቻቸውም ለዚህ ዓይነቱ ልምድ የተጋለጡ ናቸው። የሐኪሞች፣ የመሐንዲሶች፣ የሕግ ባለሙያዎችም ሆኑ የምጣኔ ሀብት ጠበብት ያላቸውን ያህል ፖለቲከኞችም የራሳቸው ቋንቋ ቢኖራቸው እምብዛም ላያስገርም ይችላል።

ይህንን ጸሐፊ የሚያስገርመውና አንዳንዴም ከልቡ የሚያበግነው ግን፣ በትክክለኛው መስመር አንዱንም ሳይሆኑ አለቆቻቸውን ለመምሰል ብቻ ቋንቋቸውን የሚያጐሳቁሉ ሰዎች ጉዳይ ነው።

እንደየፖለቲካ ዘመኑ እንዲህ ያሉትንና በራስ መተማመን አብዝቶ የሚጐድላቸውን ወገኖች አዘውትሮ ማየት እየተለመደ የመጣ ይመስላል። በደርግ ዘመን ‹‹ኢሠፓና አብዮታዊው መንግሥት›› የሚለው ሐረግ ጆሯችንን እስኪሰለቸው ድረስ ዘወትር የምንሰማው ነበር። በመሠረቱ ኢሠፓና አብዮታዊው መንግሥት በቅርጽም ሆነ በይዘት አንድና አንድ ነበሩ። በፓርቲና በመንግሥትነት ስም የተጠሩ ለማስመሰል የሚደረገው ሙከራ ታዲያ ሰፊውን ሕዝብ ከማደናገር የተለየ ውጤት አልነበረውም።

በተመሳሳይ ሁኔታ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ‹‹ኢሕአዴግና ኢሕአዴግ የሚመራው መንግሥት›› የሚለው ሐረግ ዛሬ ዛሬ በከፍተኛ የመንግሥት ሥራ ኃላፊዎች አንደበት ሳይቀር ተደጋግሞ ሲደመጥ አጋጥሞን ይሆናል። ለመሆኑ ሁለቱን አካላት በምን ዓይነት ማጣሪያ መለየት ይቻላል? ኢሕአዴግ የመንግሥትን ሥልጣን ተረክቦ አገር ሲመራ በፓርቲነት መጠሪያው ያው ኢሕአዴግ ከሆነ ሁለቱ መሆኑ ከታወቀ፣ ሁለቱ አካላት በይዘት እንደማይለያዩ ግልጽ ነው። ስለዚህ ሁለቱን አካላት ‹‹እና›› በሚለው መስተዋድድ ለማገናኘት ያን ያህል መድከሙ ለምን ይጠቅመናል?

በአገራችን የመንግሥት ሥርዓት ለውጥ ተካሂዶ ኢሕአዴግ በአሸናፊነት መንበረ ሥልጣኑን ከተቆናጠጠ ወዲህ፣ በአንዳንድ ወገኖች ዘንድ አዘውትረን የምንሰማቸው ያልተለመዱ አንዳንድ ጊዜም የአማርኛ ቋንቋ ሕግጋትን ክፉኛ የሚጥሱ ቃላትና ሐረጐች እየበረከቱ መጥተዋል። ቋንቋ ከማኅበረሰቡ አስተሳሰብ ጋር ያድጋል ቢባልም ብዙዎቹ በእርግጥ የዕድገት ምልክቶች አይደሉም። ይበልጥ የሚገርመው ደግሞ መገናኛ ብዙኃኑ እየተቀባበሉ ያላግባብ የሚያስተጋቧቸው መሆኑ ነው።

ከእነዚህ ቃላትና ሐረጐች መካከል በሰፊው ተሠራጭቶ በበርካታ ጥራዝ ነጠቆች ሲደጋገም የምናዳምጠው ‹‹ያለበት ሁኔታ ነው ያለው›› የሚለው የተጥበረበረና ያላግባብ ከመለጠፉ በስተቀር አንዳች ስሜት የማይሰጠው ሐረግ ነው። ለምሳሌ ሰውየውን ምሳ በላህ ወይ? ብላችሁ ብትጠየቁት በቀላሉና በተለመደው አነጋገር አዎ በልቻለሁ ወይም አይ አልበላሁም ብሎ በቀጥታ ከሚመልስላችሁ ይልቅ፣ ‹‹የበላሁበት ሁኔታ ነው ያለው›› የሚል ግራ አጋቢ መልስ ይሰጣችኋል። አሁን ይህንን ሰው ምን ትሉታላችሁ? እንዴትስ ትረዱታላችሁ? ለጥያቄያችሁስ ተገቢውን መልስ አግኝታችኋልን? ለመሆኑ በሰጣችሁ የተጥበረበረ መልስ መሠረት ሰውየው ምሳውን በልቷል ወይስ አልበላም? በቀጥታ በልቻለሁ ወይም አልበላሁም ማለት እየቻለና የቋንቋው ትክክለኛ ሕግም ይኸው ሆኖ ሳለ፣ ያን ሁሉ አጠራጣሪ የቃላት ጋጋታ ማስከተል ለምን አስፈለገው?

አሁን አሁን በተለይ በመካከለኛና በዝቅተኛ የመንግሥት አስተዳደር እርከን ተሹመው ወይም ተቀጥረው የሚያገለግሉ አመራሮችና ተራ ሠራተኞች፣ እንዲሁም እነርሱን ተጠግተው ወይም ከእነርሱ ጋር ወዳጅነት ፈጥረው የምታዩዋቸው አንዳንድ የኅብረተሰባችን አባላት በሕዝባዊ መድረኮችም ሆነ በአደባባይ ከሚያሰሟቸው አሰልቺ ሐረጐች መካከል ምናልባት ዋነኛው ይኸው ‹‹ያለበት ሁኔታ ነው ያለው›› የሚለው ሳይሆን አይቀርም። ‹‹ምንጩ የደረቀበት ሁኔታ ነው ያለው››፣ ‹‹መንገዱ የተሠራበት ሁኔታ ነው ያለው››፣ ‹‹ሆስፒታሉ ቢገነባም በቂ ቁጥር ያላቸው ሐኪሞች ያላገኘንበት ሁኔታ ነው ያለው››፣ ‹‹ሴት ተማሪዎችን ከኃይል ጥቃት የተከላከልንበት ሁኔታ ነው ያለው››፣ . . . ሲሉ የዞን፣ የወረዳ ወይም የቀበሌ አመራሮችን መስማት ምን ያህል አሰልቺ እንደሆነ ያጋጠመው ሁሉ ያውቀዋል። እጅግ በጣም ባጠረና ስሜት በሚሰጥ አነጋገር ምንጩ ደርቋል፣ መንገዱ ተሠርቷል፣ በቂ ሐኪሞች አላገኘንም፣ ሴት ተማሪዎችን ከኃይል ጥቃት ተከላክለናል ማለት እየተቻለ ‹‹ያለበት ሁኔታ ነው ያለው›› የሚለውን ካድሬያዊ ሐረግ ያላግባብ መለጠፍና አድማጮችን ወይም ታዳሚዎችን ማደናገር ምን የሚሉት ፈሊጥ ነው?

ይህ ችግር በመገናኛ ብዙኃኑ ይብሳል። ‹‹የአንቶኔ ሚኒስቴር ሚኒስትር››፣ ‹‹የእገሌ አባበሉ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር››፣ ‹‹የዚያኛው ወይም የዚህኛው ኮሚሽን ኮሚሽነር”፣ . . . ወዘተ የሚሉትን የቋንቋ ሕግ የማይገዛቸው አነጋገሮች ነጋ ጠባ ከሬዲዮና ከቴሌቪዥን ጣቢያዎቻችን ሳይቀር ሳንፈልግ እንድንሰማ እየተገደድን መምጣታችን በእርግጥ ያሳዝናል። ሰውየው የአንድ ዘርፍ ሚኒስትር ከሆኑ ዘርፉን ብቻ ጠቅሶ ማዕረጋቸውን ማስከተል ይበቃ ነበር። በሌላ አነጋገር ሚኒስትሩ የሚመሩት ዘርፍ የትምህርት ዘርፍ ከሆነ የትምህርት ሚኒስትር ናቸው ማለት ነው። ድሮ እኮ የምንጠራቸው በዚሁ ስያሜ ነበር። የትምህርት ዘርፉን በአገር ደረጃ የሚመሩትን ከፍተኛ ባለሥልጣን ‹‹የትምህርት ሚኒስትር›› እያልን መጥራታችን ትክክልና ተገቢ ሆኖ እያለ፣ የመሥሪያ ቤቱ መጠሪያ የሆነውን ‹‹ሚኒስቴር›› የሚለውን ቃል ለምን መደረብ ያስፈልገናል?

ወጋችንን በዚሁ መስመር እያዋዛን ትንሽ እንቀጥል። ከጥቂት ዓመታት በፊት የአካባቢ አስተዳደር በጠራው አንድ ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ የመገኘት ዕድል አጋጥሞኝ ነበር። በዚያ ስብሰባ ላይ የመጀመሪያውንና አንድ ሰዓት ያህል የወሰደውን ሰፊ ገለጻ ያደረገው አንድ ወዳጄ በገለጻው ውስጥ ያለ ይሉኝታ እየደጋገመ ይሰነቅረው የነበረው ቃል መቼውንም ጊዜ አይረሳኝም። በቅርብ የማውቀው ይህ ሰው የአፍ መፍቻ ቋንቋው አማርኛ መሆኑን ጠንቅቄ አውቃለሁ። ይሁን እንጂ ‹‹ነፃነት›› የሚለውን የአማርኛ ቃል ‹‹ናፅነት›› እያለ ሲጠቅስልን እንስቀው የነበረው ሳቅ ጣራ ይነካ ነበር። ሰውየው ይህንን ያደርግ የነበረው ‹‹ነፃነት›› ማለት አቅቶት ሳይሆን፣ ከትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች ጋር መታገሉን ምክንያት በማድረግ የራሱን ልሳን ረስቶ ‹‹ናፅነት›› የሚለውን ቃል እንደወረሰ ሊያስተጋባልን በማሰብ እንደነበር ለመገመት እምብዛም አላዳገተንም። መታገሉ እውነት ቢሆን ኖሮ እኮ ትንሽ ይሻል ነበር። ሰውየው እስከምናውቀው ድረስ ዘግይቶ የተቀላቀለ የድል አጥቢያ አርበኛ እንጂ በእርግጥ ታጋይ አልነበረም። ሆኖም ከታጋዮች አንደበት ጋር የሚመሳሰሉ አዳዲስ ቃላትና ሐረጐችን እየመረጠና እያጠና አለቆች ናቸው ብሎ የሚገምታቸውን ሰዎች መምሰሉን ሲለማመድብን ነበር። 

አሁን አሁን በብዙኃን መገናኛ ተቋማትም ሆነ በተራው ሰው አንደበት ያላግባብ እየተጣመሙ የሚሰሙትን ተመሳሳይ ቃላትና ሐረጐች በእርግጥ ቆጥሮ መጨረስ አይቻልም። ለሁለተኛ ዙርም ቢሆን አንዳንዶቹን ጨምሬ ላስታውሳችሁ። ለምሳሌ ‹‹ግልጸኛ›› እና ‹‹ግልጸኝነት›› የሚሉት ቃላት በየትኛውም የአማርኛ መዝገበ ቃላት ውስጥ ስንፈልግ ውለን ብናድር የማናገኛቸው ናቸው። በተደጋጋሚ ስለሰማናቸው ብቻ ትክክል የሆኑ ሊመስለን እንዳይችል አጥብቄ ለማሳሰብ እወዳለሁ። እንደ እውነቱ ከሆነ የእነዚህ ቃላት ሥርወ-ቃል ወይም መሠረታዊ ግስ ‹‹ገለጸ›› የሚለው ሲሆን፣ የዚህ ቃል ቅጽሉ ‹‹ግልጽ›› እንጂ ‹‹ግልጸኛ›› አይደለም። ‹‹ግልጸኝነት›› የሚለውም ቢሆን ‹‹ግልጽነት›› ተብሎ መታረም በተገባው ነበር።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ‹‹ተያይዞ›› የሚለው ቃል ያለቦታው እየተሰነቀረ ጆሯችንን እስኪታክተው ድረስ መስማት እንድናዘወትር ተገደናል። ቢያያዝም ባይያያዝም ‹‹እንዲህ ወይም እንዲያ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ›› የሚለው ሐረግ በበርካታ ተናጋሪዎች ዘንድ ሲዘወተር እየሰቀጠጠንም ቢሆን እንከታተላለን። ከሕዝቡ ሊቀድሙ ይችሉ ይሆናል ብለን ተስፋ የምናደርግባቸው የሬዲዮና የቴሌቪዥን ጋዜጠኞቻችን ራሳቸው አንዳች እሴት የማይጨምሩ ቃላትና ሐረጐችን ያላግባብ እየደነቀሩ ቀስ በቀስ መገናኛ ብዙኃንን ከመከታተል እንዳያርቁን እፈራለሁ። ‹‹ተከታዩን ፕሮግራም የምናደርስላችሁ ይሆናል›› ከሚለው አዘውትረን ከምንሰማው ሐረግ ውስጥ ‹‹ይሆናል›› የሚለው ቃል አጓጉል ልማድ ካልሆነ በስተቀር ለምን እንደሚያስፈልጋቸው ግልጽ አይደለም። ‹‹ተከታዩን ፕሮግራም እናቀርብላችኋለን ወይም እነርሱ እንደሚሉት እናደርሳችኋለን›› የሚለው እንኳ ይበቃ ነበር። የሚነበብ ይሆናል፣ የሚደመጥ ይሆናል፣ የሚቀርብ ይሆናል፣ የሚተላለፍ ነው የሚሆነው። ብቻ ምን አለፋችሁ ‹‹ይሆናል›› ወይም ‹‹የሚሆነው›› የሚል አጠራጣሪ ትርፍ ቃል ካልታከለበት የሚሰማ ነገር እየጠፋ መጥቷል።

አንዳንዶቹ ቃላትና ሐረጐች መቸውንም ቢሆን የማናስተካክላቸው እስኪመስሉ ድረስ ሥር የሰደዱ መስሎ ይታየኛል። እንደ እንግሊዝኛ ባሉ ሌሎች ቋንቋዎች ባህል ውስጥ የተለመዱትን አነጋገሮች በጥሬው ተርጉሞ በመዋስ ብቻ ‹‹እንደ አጠቃላይ››፣ ‹‹እንደ ምናምን መጠን››፣ ‹‹ብሎ መውሰድ ይቻላል››፣ ‹‹እዛው ሳለ››፣ . . . ወዘተ የሚሉት ባዕድ አባባሎች ክፉኛ ተጣብተውናል።

ለመሆኑ የዚህ ሁሉ ችግር መሠረቱ ምን ይሆን? በእኔ ግምት የሚጀመረው እንደ ዘበት ሊሆን ይችላል። የኋላ ኋላ ግን ሳይታሰብ እየተዘወተረ በቀላሉ ወደማይለቅበት ደረጃ እየተሸጋገረ ይሄዳል። እነዚህ ቃላትና ሐረጐች በተለይ ከፍ ያለ ሥልጣን ባላቸው ሹማምንት አማካይነት ነው መነገር የሚጀምሩት። ከዚያም የበላይ አለቆቻቸውን ትኩረት የሳቡ እየመሰላቸው ዝቅተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የበታች ሠራተኞች አንዱ ወደ ሌላው እየተቀባበሉ ያለ ይሉኝታ ያስተጋቧቸዋል። ከላይ የተቀበሉትን ፈሊጣዊ አነጋገር የመግባቢያ ቋንቋው ሕግ ፈቀደው አልፈቀደው እምብዛም አይገዳቸውም። ከዚህ ይልቅ ለእነሱ ዋናው ቁም ነገር በአደባባይ ሲናገሩ የበላይ አለቆቻቸውን መምሰል መቻላቸው ብቻ ነው። ለዚህ ሲሉ በአጓጉል ኩረጃ የቋንቋ አጠቃቀማቸውን በማወሳሰብ ማንነታቸውን ስለመሸርሸራቸውና ሰብዓዊ ክብራቸውን በገዛ ራሳቸው ዝቅ ስለማድረጋቸው አንዳች ጉዳያቸው አይደለም፣ አይቆረቁራቸውም።

እንደ እውነቱ ከሆነ ይህ ተላላፊ በሽታ ፈጽሞ ፈውስ የሌለው አይደለም። በጊዜ ከነቃንበት ሊድን ይችላል። ማንኛውም ሰው መኖር ያለበት የራሱን እንጂ የሌላውን ሕይወት አይደለም። ከሌሎች የምንወርሳቸው ስፍር ቁጥር የሌላቸው ፀጋዎች ቢኖሩም፣ በጥንቃቄ እየመርጥን እንጂ በግዴለሽነት እየኮረጅን መሆን አይኖርበትም። ራስን የሚያሳጣ ኩረጃ ደግሞ አጥፊ እንጂ አልሚ ሊሆን ፈጽሞ አይችልም። ሌሎችን ለመምሰል ብለን የመግባቢያ ቋንቋችንን አናወሳስብ። ልንመስል የምንገለብጣቸው ወይም ሳናጣራ ኮፒ የምናደርጋቸው ሰዎች ሳይቀሩ ክፉኛ ይታዘቡናል።

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው clickmerha1@gmail.com   ማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

Standard (Image)

አደገኛው የዚካ ቫይረስ በጥያቄና መልስ ሲፈተሽ

$
0
0

በአሸናፊ ዋቅቶላ (ዶ/ር)

የዚካቫይረስምንድንነው?

ዚካ በቢንቢዎች የሚተላለፍ ቫይረስ ሲሆን፣ የሚገኝበት የቫይረስ ቤተሰብ ዌስት ናይል ቫይረስ፣ ደንጊ፣ ቲክ-ቦርን ኢንሰፋላይቲስና ((መዥገር-ተሸካሚ የአንጎል መቆጣት ቫይረስ)፣ ቢጫ ወባ (የሎው ፊቨር) ይገኙበታል። ፍላቪ በላቲን ቋንቋ ቢጫ ማለት ሲሆን፣ ስሙ የተገኘው ከቢጫ ትኩሳት (ቢጫ ወባ) ነው። ቢጫ የተባለውም ቢጫ ወባ ጉበትን አሳምሞ የዓይንን ቢጫነት (ጆንዲስ) ስለሚፈጥር ነው።

የቀድሞወረርሽኞችታሪክምንይመስላል?

ዚካ ቫይረስ በመጀመሪያ የተገኘው በአፍሪካ ኡጋንዳ ዚካ ጫካ ለቢጫ ወባ ምርምር የተቀመጠ ሪህሰስ 776 ተብሎ በተሰየመ አንድ ጦጣ ላይ ነበር። ከዚያ በኋላ ለብዙ ዓመታት በሰዎች ውስጥ አነስተኛ ወረርሽኞች ሲደርሱ ቆይተዋል። በዚህ ሁኔታ በ60 ዓመታት ጊዜ ውስጥ 14 ሰዎች ብቻ በበሽታው ሲያዙ፣ ተጨማሪ ሁለት ሰዎች ከምርምር ጋር የተገናኘ የዚካ በሽታ ይዟቸዋል። እነኚህ በሙሉ ያሳዩት ለአጭር ጊዜ የቆየ ያልጠና ሕመምና ከበሽታውም ሙሉ በሙሉ ድነው ነበር።

እ.ኤ.አ. በ2007 ፓስፊክ ውቅያኖስ በሚገኙት ማይክሮኔዥያ ፌደራላዊ ክፍለ አገሮች ያፕ ደሴት ውስጥ ትልቅ ወረርሽኝ ተከስቶ 5,000 የሚገመት ሕዝብን ይዞ ነበር። ይህ ደግሞ ከነዋሪዎች 70 በመቶ በላይ ማለት ነው። በዚህ ወረርሽኝ ምክንያት ሆስፒታል የተኛም ሆነ የሞተ አልነበረም።

የሚቀጥለው ወረርሽኝ የታየው እ.ኤ.አ. ከ2013 እስከ 2014 ሲሆን በፍሬንች ፖለኔዥያ ነበር። 30,000 ሰዎች ከመያዛቸው ሌላ ወደ ተጨማሪ ሰባት ደሴቶች ተሰራጭቷል። በወረርሽኙ የሞተ አልነበረም። ነገር ግን የነርቭ ሥርዓት መዛባቶች መታየት የጀመሩት በዚህ ጊዜ ከመሆኑ ሌላ 42 ሰዎች ጉሊያን ባሬ የተባለ የጠና የነርቭ ሥርዓት መዛባት ደርሶባቸው ነበር። 16 ሰዎች ሕመም በጣም የጠናባቸው መታከሚያ ውስጥ (ኢንቴንሲቭ ኬር) ውስጥ ሲታከሙ፣ 12ቱ የሰው ሠራሽ መተንፈሻ ዕርዳታ አስፈልጓቸው ነበር።

እ.ኤ.አ. በማርች 2014 ቺሌ በኢስተርን አይላንድ ውስጥ የዚካ መተላለፍ ሲዘገብ በሜይ 2015 በሰሜን ምሥራቅ ብራዚል ሥርጭቱ ተረጋግጦ ነበር። ክኦክቶበር 2015 በኋላ ብዙ አገሮችና ግዛቶች የቫይረሱን መኖር አሳውቀዋል።                             

የዚካቫይረስየሚተላለፈውእንዴትነው?

  • ቫይረሱ ወደ ሰዎች የሚተላለፍበት ዋነኛ መንገድ በቫይረሱ በተያዘች የኤዲስ ሴት ቢንቢ ንክሻ ነው። የኤዲስ ቢንቢዎች ቀን በቀን ከቤት ውጪና ውስጥ ኃይለኛ (አግረሲቭ) ተናካሾች ናቸው። ቢንቢዎቹ በምሽትም ይናከሳሉ።
  • የዚካ ቫይረስ በእርግዝና ጊዜና በወሊድ ጊዜ ከእናት ወደ ልጅ ይተላለፋል።
  • በግብረ-ሥጋ ግንኙነት ከወንድ ወደ ሴት ይተላለፋል።
  • የደም ከአንድ ሰው ወደ ሌላ ሰው መዘዋወር (ብለድ ትራንስፉዥን)፣ የክፍለ-አካልና የኅብረ-ሕዋስ መተካከል (ኦርጋን ኤንድ ቲሹ ትራንስፕላንቴሽን) ቫይረሱን ማስተላለፍ የሚችሉ መንገዶች ናቸው።

የዚካቫይረስንየሚያስተላልፉትቢንቢዎችየትኞቹናቸው?

ኤዲስ ኢጂፕቲ ቢንቢዎች በምድር ወገብ አካባቢና በአንዳንድ ቀዝቀዝ ያሉ (ቴምፐሬት) አየር ንብረቶች ውስጥ ይኖራሉ። ዚካ፣ ደንጊ፣ ቺኩንጉንያና ሌሎች ቫይረሶችን የሚያስተላልፉት ዋነኛ ቢንቢዎች ኤዲስ ኢጂፕቲ ቢንቢዎች ናቸው። ሰዎችን ተጠግተው የሚኖሩና ከሌሎች እንስሳት የሚመርጡት ሰዎችን መንከስ ስለሆነ፣ ከሌሎች ቢንቢዎች ይበልጥ እነዚህን ቫይረሶች የማስተላለፍ ዕድል አላቸው።

ኤዲስ አልቦፒክተስ የተባሉት ቢንቢዎች በምድር ወገብ አካባቢና ቀዝቀዝ ያሉ ቦታዎች ውስጥ እንደ ኤዲስ ኢጂፕቲ ቢንቢዎች መኖር ከመቻላቸውም በላይ፣ ይበልጥ ስፋት ባላቸው አየር ንብረቶችና በጣም በቀዘቀዙ ቦታዎች ውስጥ መኖር ይችላሉ። እነዚህ ቢንቢዎች እንስሳትና ሰውን የሚነክሱና ከኤዲስ ኢጂፕቲ ቢንቢዎች ጋር ሲወዳደሩ ቫይረሶችን ወደ ሰው የማስተላለፍ ብቃታቸው አነስተኛ ነው።

ከኤዲስኢጂፕቲቢንቢዎችውስጥምንያህሉቢያዙነውአሁንበአሜሪካኖችየሚታየውንዓይነትትልቅወረርሽኝማስተላለፍየሚችሉት?

ብራዚል ውስጥ በተደረገ ክትትል (ሰርቬላንስ) ምርመራዎች ከ1,000 ቢንቢዎች ውስጥ ሦስት ብቻ በዚካ ቫይረስ መያዛቸው ታውቋል። በሌሎችም የቢንቢ ወረርሽኞች በበሽታ አምጪው የሚያዙት በዚሁ ቁጥር አካባቢ ነው።

የኤዲስቢንቢከአገርወደአገር፣ከክልልወደክልልሊበርይችላል?

የኤዲስ ቢንቢ ደካማ በራሪ ነው። ከ400 ሜትር በላይ አይበርም። ነገር ግን በሰዎችና በተሽከርካሪዎች አማካይነት ከቦታ ቦታ እየተጓዘ አዳዲስ ቦታዎች ውስጥ መንሰራፋት ይችላል።

የዚካቫይረስበሽታመደላደልጊዜ(ኢንኩቤሽንፔሬድ) ምንያህልነው?

ቫይረሱ ሰውነት ወስጥ ከገባ በኋላ የመጀመሪያ የሕመም ስሜቶች እስኪከሰቱ ድረስ ያለው ጊዜ ማለትም የመደላደል ጊዜው (ኢንኩቤይሽን ፔሬድ) ከቢንቢ ንክሻ በኋላ ብዙ ጊዜ ከሦስት እስከ 12 ቀናት ነው።

የዚካቫይረስበሽታየሕመምስሜቶች(ሲምፕቶምስ) ምንድንናቸው?

ቫይረሱ ከያዛቸው 80 በመቶ የሚሆኑ ሰዎች ምንም የሕመም ስሜት ስለማይኖራቸው ቫይረሱ እንደያዛቸው እንኳን አያውቁም፡፡ በተቀሩት ላይ ይበልጥ ተዘውትረው የሚታዩት መለስተኛ (ያልጠኑ) የሕመም ስሜቶች ትኩሳት፣ የቆዳ ሽፍታ፣ የመገጣጠሚያ ሕመምና የዓይን መቅላት (ኮንጀንክቲቫይቲስ) ናቸው። ሌሎች የሕመም ስሜቶች ደግሞ የጡንቻ ሕመምና ራስ ምታት ይገኙባቸዋል። የዚካ ሕመም ስሜቶች ከሁለት እስከ ሰባት ቀናት ይቆያሉ።

የዚካ ቫይረስ በታማሚው ሰው ደም ውስጥ ብዙ ጊዜ የሚቆየው ለአንድ ሳምንት ብቻ ነው። በአንዳንድ ሰዎች ውስጥ ከዚያ ለረዘመ ጊዜ ሊቆይ ይችላል።

አንዴ በዚካ ቫይረስ የተያዘ ሰው ከዚያ በኋላ ወደፊት በዚካ ቫይረስ ደግሞ እንደማይያዝ ይታመናል።

የዚካቫይረስበሽታበምርመራየሚለየውእንዴትነው?

የዚካ ቫይረስን ማግኛ የሲሮሎጂና የሞለኩይላር ቴክኖሎጂ ዘዴዎች አሉ።

- የዚካ ቫይረስ በሽታ ከያዘ በኋላ በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ከደም ውስጥ ስለሚጠፋ ወይም በጣም ስለሚቀንስ የሲረም ረቨርስ ትራንስክሪፕሽን ፖሊመሬዝ ሪአክሽን (አር ፒሲአር ) ላያገኘው ይችላል። ሽንት ውስጥ ግን እስከ ሁለት ሳምንት ስለሚቆይና በሽታው ከጀመረበት ጊዜ እስከ ሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ ስለሚታይ የሽንት አር ፒሲ አር ሊያገለግል ይችላል፡፡ የደም ወይም የሽንት አር ፒሲ አር ምርመራ ‹‹አለ›› (ፖሲቲቭ) ካለ የዚካ ቫይረስ በሽታ ተረጋግጧል ማለት ነው።

- የዚካ ቫይረስ በሽታ ከያዘ ከአንድና ሁለት ሳምንታት በኋላ ሲረምና በሽንት ውስጥ የሚገኘው የቫይረስ መጠን በጣም ሲቀንስ በሽታው እያለ የፒ ሲ አር ምርመራ ፖሲቲቨ ላይሆን ይችላል። በዚህ ጊዜ ውስጥ የሲሮሎጂ (የፀረ-አካል) ምርመራ ሊደረግ ይችላል። ቢሆንም ምርመራው ከደንጊና ከቢጫ ወባ (የሎው ፊቨር) ከመሳሰሉ ሌሎች ፍላቪ ቫይረሶች ፀረ-አካሎች አጋር ሊያምታታ ይችላል። ይህንን ችግር ለመቀነስና በተለይ የዚካ ቫይረስን ፀረ አካሎች ለማግኘት ሌላ ምርመራ (ፕሌክ-ሪደክሽን ኒውትራላይዚንግ አንቲቦዲስ) ማድረግ ያስፈልጋል።

የዚካቫይረስበሽታሕክምናእንዴትነው?

በአሁኑ ጊዜ የተለየ የዚካ መድኃኒት ወይም ፀረ-ቫይረስ የለም። ሕክምናው የሚደረገው ቫይረሱ የሚያስከትላቸውን የሕመም ስሜቶች ለመቀነስ ነው። ብዙ ዕረፍት ማድረግ ይጠቅማል። ፈሳሾች በብዙ መጠጣት ያስፈልጋል። ሕመም ለማስታገስና ትኩሳትን ለመቀነስ አሲታሚኖፊን (ታይላኖል) እና ፓራሲታሞልን መውሰድ ነው።

አስፕሪን፣ አይቡፕሮፈን፣ ናፕሮክሰንና የመሳሰሉት መድኃኒቶች (ኖን ስትሮይዳል አንቲ ኢንፍላማቶሪ ድረግስ) የመድማትን ውስብስቦሽ ሊያስከትሉ ወይም ሊያባብሱ ስለሚችሉ አለመጠቀም ነው። በሽታው ከጠና የጤና ባለሙያን ማማከር ያስፈልጋል።

የዚካቫይረስበሽታዋናዋናውስብስቦችየትኞቹናቸው?

የዚካይረስ በሽታ የነርቭ ሥርዓት ውስብስቦች ማይክሮኬፋሊ፣ ጉሊያን ባሬ ሲንድሮምና አኩይት ዲማይሊኔቲንግ ሜኒንጎ ኢንሰፋላይትስን ይጨምራሉ።

ማይክሮኬፋሊምንድነው?

ይህ ከሁሉ የዚካ ውስብስቦች ይበልጥ አሳሳቢና አሳዛኙ ነው። ማይክሮኬፋሊ የጭንቅላት መጠን መቀነስ ሲሆን የሚገለጠውም ከወሊድ ጋር በተያያዘ (ኒዮናታል) ከተመሳሳይ ፆታና ዕድሜ ጋር ካሉ ሌሎች ሕፃናት ጋር ሲወዳደር የራስ ቅል መጠን መቀነስ ነው። ይህ ከአንጎል በሚገባ አለማደግ ጋር ሲጣመር የአካልና የአምዕሮ ዕድገት ጉድለቶችን (ዲቨሎፕመንታል ዲሴቢሊቲስ) ሊያስከትል ይችላል። እነኚህም የመቀመጥ፣ የመነሳት፣ የመሄድ፣ የመንቀሳቀስ፣ ሚዛን የመጠበቅ ድክመቶች፣ የመብላትና የመዋጥ ችሎታ መቀነስ፣ የመማርና ዕለታዊ የሕይወት ሥራዎችን የመፈጸም ችግሮች ሊያጋጥሙቸው ይችላሉ። በተጨማሪም የሚጥል በሽታ (ሲዠርስ)፣ ያለመስማትና የማየት ድክመቶች ናቸው።

የማይክሮኬፋሊ መንስዔዎች ብዙ ሲሆኑ ምክንያቱ ከምርመራዎችም በኋላ ላይታወቅ ይችላል፡፡ የማሕፀን ሕመም (ቶክሶፕላዝሞሲስ፣ ሩቤላ፣ ኸርፒስ፣ ጨብጥ፣ ሳይቶሜጋሎ ቫይረስ፣ ኤችአይቪ)፣ ለመጥፎ ኬሚካሎች መጋለጥ፣ የእናቶች ለከባድ ብረቶች (ሄቪ ሜታልስ) መጋለጥ (አርሰኒክ፣ ሜርኩሪ)፣ በእርግዝና ጊዜ አልኮል ብዙ መጠጣት፣ ጨረር (ራዲኤሽን)፣ ሲጋራ ማጨስ፣ ዳውን ሲንድሮም የመሳሰሉ የአፈጣጠር ጉድለቶች (ጄኔቲክ አብኖርማሊቲስ)፣ በእርግዝና ጊዜ የጠና የምግብ ዕጥረት (ሲቨር ማልኑትሪሽን) መንስዔዎች ከሚሆኑት ውስጥ ናቸው።

ጉሊያንባሬሲንድሮምምንድነው?

የሰው የተፈጥሮ መከላከያ የራሱን ወይም የራሷን ነርቮች የሚያጠቃበት በጣም አልፎ አልፎ የሚታይ ሕመም ነው። በሁሉም የሰዎች ዕድሜ ክልሎች መታየት የሚችል ቢሆንም የሚበዛው አዋቂ (አደልት) ወንዶች ላይ ነው። ከ20 በመቶ እስከ 25 በመቶ በሚሆኑት ውስጥ የደረት ጡንቻዎችን አውኮ የመተንፈስ ችግርን ያስከትላል። በጣም የጠና ሲሆን ሽባነትንና (ፓራልይሲስ) ሞትን ሊያመጣ ይችላል።

አኩይትዲማይሌቲንግሜኒንጎኢንሰፋላይቲስምንድነው?

ሰውነት በራሱ ላይ የሚመጣን ጥቃት ለመከላከል አንጎልንና ሰረሰርን (ስፓይናል ኮርድ) በስፋት የሚጎዳበት መቆጣት (ኢንፍላሜሽን) ነው፡፡ ይህ በሽታ በተለይም ኋይት ማተር የተባለውን የአንጎል ክፍል ያጠቃል፡፡ የዚህ በሽታ አቀራረብ መልቲፕል ስክሌሮሲስ የተባለ የነርቭ በሽታን እንደሚመስልና ስድስት ወራት ድረስ ሊቆዩ የሚችሉ የነርቭ ሥርዓት መዛባቶች ሊኖሩት እንደሚችሉ ተዘግቧል።

የዚካቫይረስበሽታብዙጊዜሞትያስከትላልወይ?

ባለፉት ዓመታት የዚካ ቫይረስ በሽታ ወረርሽኞች የሚያጠቁት ሰዎች ቁጥር አነስተኛ ከመሆናቸው ሌላ፣ የዚካ ቫይረስ በሽታ የሞት አደጋም አድርሶ እንደነበረ የሚያሳይ መረጃ የለም። በአሁኑ ወቅት ወረርሽኙ እጅግ በጣም ተስፋፍቶ የሚገኝና አንዳንድ ጊዜ በጣም የጠና ሕመምና ሞትን ያስከትላል።

ሰዎችራሳቸውንከቢንቢንክሻእንዴትሊከላከሉይችላሉ?

ከሁሉ የሚበልጠው ዕርምጃ የቢንቢ ንክሻን መከላከል ነው፡፡ በተለይ እርጉዞች፣ ለማርገዝ ዕቅድ ያላቸው ሰዎችና የግብረ-ሥጋ ጓደኞቻቸው (ሴክሿል ፓርትነርስ) ከቢንቢ ንክሻ ራሳቸውን ይበልጥ መጠበቅ ይኖርባቸዋል።

  1. የሚለብሷቸው ልብሶች በተቻለ መጠን አብዛኛውን የሰውነት ክፍሎችን መሸፈን አለባቸው።
  2. ቢንቢ አባራሪ ኬሚካሎችን ባልተሸፈኑ የሰውነት ክፍሎች ወይም ልብሶች ላይ መቀባት፡፡ ኬሚካሎቹ ዳይኢታይልቶሉአማይድ ወይም አይአር 3535 የሚባሉትን ነገሮች የያዙ ከመሆናቸው ሌላ፣ የአጠቃቀም መመርያዎች በትክክል መጠቀም ያስፈልጋል። እነዚህ በእርጉዞች ላይ ጉዳት አያስከትሉም።
  3. አካላዊ ከለላዎች ማለትም የታከሙ ወንፊቶችን በበሮችና መስኮቶች ላይ መጠቀም።
  4. በቢንቢ መከላከያ አጎበሮች ሥር መተኛት፡፡
  5. ቢንቢዎች ሊራቡባቸው የሚችሉባቸውን ቦታዎችና ዕቃዎች መለየትና ማስወገድ ለምሳሌ ባልዲዎች፣ የአበባ ማስቀመጫዎችና የመኪና ጎማዎችን መክደን ወይም ማስወገድ።

ለዚካቫይረስመክላለከያክትባትአለ?

በአሁኑ ጊዜ የዚካ ቫይረስ በሽታ መከላከያ ክትባት የለም።

እርጉዞችእንዴትከቢንቢንክሻሊጠበቁይችላሉ?

ዚካ በሚተላለፍባቸው አገሮች ውስጥ ያሉ እርጉዞች እንደ ሌላው ሕዝብ የመከላከያ ዘዴዎችን መጠቀም ይገባቸዋል፡፡ መደበኛ የእርግዝና ክትትል ማድረግና የትኛውም የዚካ በሽታ ስሜት ቢያሳዩ ቶሎ የጤና ባለሙያዎች ክትትል ማድረግ ይገባቸዋል።

እርጉዞችበዚካቫይረስይበልጥይጠቃሉ?

የዚካ ቫይረስ እርጉዞችን ከሌሎች ይበልጥ ሊይዝ እንደሚችል፣ ወይም ከሌሎች ሰዎች ይበልጥ የጠና በሽታ እንደሚሰጣቸው የሚያሳይ መረጃ የለም፡፡

የዚካቫይረስየተገኘባቸውእናቶችጡትሊያጠቡይችላሉ?

የዚካ ቫይረስ አርኤን ኤ በጡት ወተት ውስጥ ቢገኝም፣ በላቦራቶሪ ውስጥ ማሳደግ (ከልቸር ማድረግ) አልተቻለም፡፡ እስካሁን ድረስ ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ በጡት መጥባት ምክንያት እንደተላለፈ የሚያሳይ መረጃ የለም፡፡ የዓለም የጤና ድርጅት ለመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት ሕይወት የጡት ወተት ብቻ መጠቀምን ይመክራል፡፡

እርጉዞችለዚካቫይረስሕክምናሊወስዱይችላሉ?

በተለይ ለዚካ ቫይረስ የሚሆን ፀረ-ቫይረስ ሕክምና እስካሁን የለም። የዚካ ቫይረስ በሽታ ብዙ ጊዜ መለስተኛና ቶሎ የሚተው (ከሁለት እስከ ሰባት ቀናት) ነው። ሕመሙ ካስቸገረ እርጉዞች ብዙ ዕረፍት እንዲወስዱና በቂ ፈሳሾች እንዲጠጡ ይመከራል። ለሕመሙና ለትኩሳቱ ፓራሲታሞል ወይም አሲታሚኖፊን መውሰድና ሌሎችም ሰውነት ማቀዝቀዣዎችን ሊጠቀሙ ይችላሉ።

ፀረ-ሂስታሚኖችበእርግዝናጊዜመውሰድይቻላል?

ሽፍታው የሚያሳክክ ከሆነ እርጉዝ ሴት የጤና ባለሙያ አማክራ ፀረ-ሂስታሚን መውሰድ ትችላለች፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ክሎርፌኒራሚን፣ ሎራታዲን ወይም ሴቲሪዚን ይታዘዝላታል። እነኚህ ቆየት ያሉ ፀረ-ሂስታሚኖች ለብዙ ዓመታት በእርግዝና ጊዜ ስለተወሰዱ ጉዳት እንደማያስከትሉ ይታወቃል።

በግብረ-ሥጋግንኙነትየሚተላለፈውንዚካቫይረስመከላከልየሚቻለውእንዴትነው?

በዚካ ቫይረስ የተያዙ ሰዎች በሙሉና የግብረ-ሥጋ ጓደኞቻቸው (በተለይ እርጉዝ ሴቶች) የዚካ ቫይረሰ በግብረ-ሥጋ ግንኙነት የመተላለፉን አደጋ፣ የእርግዝና መከላከያ ዘዴዎችንና ጉዳት የማያስከትሉ የግብረ-ሥጋ ግንኙነት ዘዴዎችን አስመልክቶ መረጃዎች ማግኘት ይኖርባቸዋል።

በሚቻልበት ጊዜ ኮንዶሞችን ማግኘት፣ በትክክልና የግብረ-ሥጋ ግንኙነት ባደረጉ ቁጥር እንዲጠቀሙበት ማስተማር ያስፈልጋል።

የእርጉዞች የግብረ-ሥጋ ጓደኞች የዚካ በሽታ እየተላለፈባቸው ባሉ ቦታዎች ውስጥ የሚኖሩ ወይም ወደዚያ የተጓዙ ከሆነ ጉዳት የማያስከትል የግብረ-ሥጋ ግንኙነት ማድረግ አለባቸው፡፡ ይህም ግንኙነት ባደረጉ ቁጥር ኮንዶምን ማጥለቅ ወይም እስከ እርግዝና ፍፃሜ ድረስ ከግብረ-ሥጋ ግንኙነት መቆጠብ ሊሆን ይችላል።

የዚካ ቫይረስ በሽታ በሚተላለፉባቸው ሥፍራዎች ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ጉዳት የማያስከትሉ (ሴፍ) የግብረ-ሥጋ ግንኙነቶችን ማድረግ ወይም ከግብረ-ሥጋ ግንኙነት መቆጠብ አለባቸው።

መከላከያየሌለውግብረ-ሥጋግንኙነትየፈጸሙናበዚካቫይረስመያዝሥጋትእርግዝናባይፈልጉምንማድረግይችላሉ?

ሕግ በሚፈቅደው ልክ ሙሉ ሁሉም ሴቶች የድንገተኛ እርግዝና መከላከያ፣ ትክክለኛ መረጃና አቅም የሚመጥን ዘዴዎችን መጠቀም እንዲችሉ መደረግ አለበት።

ዚካሚገኝባቸውቦታዎችየሚሄዱ ምንማድረግአለባቸው?

እርጉዞች የዚካ ቫይረስ እየተላለፈባቸው ወዳሉ ቦታዎች እንዳይጓዙ መመከር ይገባቸዋል። የግብረ ሥጋ ጓደኞቻቸው (ሴክሽዋል ፓርትነርስ) ዚካ በሚተላለፍባቸው ቦታዎች ውስጥ የሚኖሩ ወይም ወደዚያ የሚጓዙ ከሆነ፣ እርግዝናው እስኪፈጸም ድረስ ከግብረ ሥጋ ግንኙነት መቆጠብ ወይም የዚካ ቫይረስ በሽታን የማያስተላልፍ የግብረ ሥጋ ግንኙነት ዓይነትን (ለምሳሌ ኮንዶም) መጠቀም ይኖርባቸዋል።

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የሕክምና ዶክተር ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

Standard (Image)

ትኩረት የሚሻው የብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ልማት ንዑስ ዘርፍ

$
0
0

በዳዊት ወልደ ኢየሱስ

በአገራችን የብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ኢንዱስትሪ ግማሽ ምዕተ ዓመት ያስቆጠረ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ዳሩ ግን ለበርካታ ዓመታት ለዘርፉ ትኩረት ሳይሰጠው ቆይቷል፡፡ በመሆኑም በዘርፉ የነበረው የልማት እንቅስቃሴ ደካማ ነበር፡፡ አገሪቱም ከዘርፉ ልታገኝ የሚገባውን የኢኮኖሚና የቴክኖሎጂ ልማት ሳታገኝ ቆይታለች፡፡

የመንግሥት ለውጥ ከተደረገ በኋላ ሊያሠሩ የሚችሉና ሕዝቡን በየደረጃው ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ተቀርፀው ወደ ተግባር ተገባ፡፡ ይኼም ተቀብሮ ለነበረው የብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ኢንዱስትሪ ትንሳዔ ሆነለት፡፡ ምክንያቱም የኢንዱስትሪ ልማት ስትራቴጂው የግል ባለሀብቱ የኢንዱስትሪው ሞተር መሆኑን በማመኑና ማንኛውም ልማታዊ ባለሀብት በዘርፉ ለመሰማራት ቢፈልግ በሩ ክፍት መሆኑን በማወጁ ነው፡፡

አገራችን ከግብርና መር ኢኮኖሚ ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለምታደርገው የትራንስፎርሜሽን ጉዞ የመጀመርያውን አምስት ዓመታት ለሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን መደላድል ፈጥሮ አልፏል፡፡ በመሆኑም በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን ኢንዱስትሪው መሪነቱን እየተረከበ እንዲሄድ ለማኑፋክቸሪግ ዘርፉ ትኩረት ተሰጥቷል፡፡ ትኩረት ከተሰጣቸው የማኑፋክቸሪግ ዘርፍ አንዱ ደግሞ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ንዑስ ዘርፍ ነው፡፡

ይህ ንዑስ ዘርፍ መሠረታዊ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ በመባል በሁለት ይከፈላል፡፡ የመሠረታዊ ብረታ ብረት ኢንዱስትሪ የብረት ማዕድናትን፣ ውድቅዳቂ ብረቶችና የጠገራ ብረቶችን በመጠቀም ለኢንጂነሪንግ ንዑስ ዘርፍ ግብዓት የሚሆኑ የኢንዱስትሪ ውጤቶችን የሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎችን የሚያካትት ሲሆን፣ በኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ንዑስ ዘርፉ የሚካተቱት ደግሞ የብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ውጤቶችን በግብዓትነት በመጠቀም የተለያዩ የኢንጂነሪንግ ምርቶችን የሚፈበርኩ ናቸው፡፡

በሌላ አገላለጽ መሠረታዊ ብረታ ብረት ኢንዱስትሪዎች ከብረት ማጣራት ጀምሮ የተለያዩ መጠን ያላቸውን የመጀመርያ ደረጃ ምርቶችንና እነዚህን ምርቶች በግብዓትነት በመጠቀም ዝርግና ጥቅል ልሙጥ ብረቶችን፣ የተለያዩ ቅርፅ ያላቸው ድፍንና ክፍት ረጃጅም የብረት ምርቶችን፣ ሽቦዎችን፣ የሽቦ ገመዶችን፣ ቆርቆሮዎችንና ሚስማሮችን የማቅለጥ፣ የማሞቅና የመዳመጥ ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሚያመረቱ ናቸው፡፡ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪዎች የሚባሉት ደግሞ የብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ውጤትን በግብዓትነት በመጠቀም የተለያዩ ቅርፅ ማውጫ ቴክኖሎጂዎችን፣ ማለትም በማቅለጥ ቅርፅ ማውጣት፣ በማነጥ፣ በብየዳ፣ በመቀጥቀጥ መሣሪያዎችንና የተለያዩ መገልገያ ዕቃዎችን የሚያመርቱ ናቸው፡፡

ይህ ንዑስ ዘርፍ ለሌሎች የማኑፋክቸሪግ ዘርፎች በግብዓትነት በማገልገል ለኢንዱስትሪ መስፋፋት ከፍተኛ ሚና የሚጫዎት ሲሆን፣ ለአገሪቱ የምጣኔ ሀብት ዕድገትም የላቀ አስተዋጽኦ አለው፡፡ በመሆኑም ካለው አገራዊ ፋይዳ አንፃር ንዑስ ዘርፉን የሚደግፍ መንግሥታዊ ተቋም መቋቋም ነበረበትና የብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ተቋቋመ፡፡

አገራችን በ2017 ዓ.ም. መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ ለመሠለፍ ከድህነት ጋር ከፍተኛ የሆነ ትግል እያደረገች ባለበት በዚህ ዘመን፣ ከሁሉም ዘርፍ ዕምርታዊ ለውጥ እንደሚጠበቅ ይታመናል፡፡ ይህን መሠረት በማድረግም የብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት በ2017 ዓ.ም. በአፍሪካ ቀዳሚና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ ቀላል የብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኢንዱስትሪ በመገንባት፣ ለከባድ ኢንዱስትሪዎች ልማት መሠረት ተጥሎ ማየት የሚል ራዕይ ሰንቆ መንቀሳቀስ ቀጥሏል፡፡

ራዕዩን ዕውን ለማድረግ ታዲያ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ አቅምን ለማሳደግ የሚያስችል ምርምርና ጥናትን መሠረት ያደረገ የተቀናጀ የኢንቨስትመንት፣ የግብይትና ማኑፋክቸሪንግ ቴክኖሎጂ ድጋፍ ለልማታዊ ባለሀብቱ በመስጠት ተወዳዳሪ ኢንዱስትሪዎች እንዲስፋፉ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ ስለሆነም የሚከተሉት የትኩረት መስኮች ተቀምጠዋል፡፡

ቀዳሚው የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት ማስፋፋት የሚል ነው፡፡ ኢንቨስትመንት ለማስፋፋት የአገር ውስጥና የውጭ ባለሀብቶች በንዑስ ዘርፉ ልማት እንዲሰማሩ ሊስብ የሚችል የተሟላ የመረጃ ሥርዓት መዘርጋት ያስፈልጋል፡፡ በተጨማሪም ለንዑስ ዘርፉ ልማታዊ ባለሀብቶች በፕሮጀክት ዝግጅትና ትግበራ የቴክኒክ ድጋፍ በመስጠት ወደ ማምረት የሚሸጋገሩ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶችን ማሳደግም ይጠበቃል፡፡

በዚህ ረገድ ኢንስቲትዩቱ ከ2005 በጀት ዓመት ጀምሮ አሁን እስካለንበት የ2008 በጀት ዓመት አጋማሽ በብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ንዑስ ዘርፍ ለሚሰማሩ ልማታዊ ባለሀብቶች ከ300 በላይ አዳዲስ የፕሮጀክት ሐሳቦችን፣ ወደ 60 የሚሆኑ የምርት መግለጫዎችንና ከ40 በላይ የሚሆኑ የቅድመ አዋጭነት ጥናቶችን በማካሄድ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ከፍተኛ ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ ከጥናቱም በንዑስ ዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶች መረጃን በመውሰድ፣ ጥናቱን በማሳደግና በማስፋት ተጠቃሚ በመሆን ላይ ይገኛሉ፡፡

ጥናቶቹ የምርት መግለጫ፣ የገበያ ጥናትና የማምረት አቅም፣ የቴክኖሎጂና ኢንጂነሪግ ሥራው (የምርት ሒደቱ፣ የሚጠቀማቸው ማሽነሪዎችና ኢኩፕመንቶች፣ የመሬት፣ የኮንስትራክሽን ሥራውና የአካባቢው  ተፅዕኖ) የጥሬ ዕቃና ሌሎች ግብዓቶች፣ የሰው ኃይልና የሥልጠና ፍላጎት፣ የፋይናንስ ትንተናና ግምገማን ያጠቃለሉ በመሆናቸው ኢንቨስት ለሚያደርጉ ልማታዊ ባለሀብቶች ጠቃሚ መረጃዎችን ያስተላልፋሉ፡፡

ጥናቶቹ ካጠነጠኑባቸው ኢንቨስትመንቶች መካከልም የኤሌክትሪክ ኬብል፣ የአርማታ ብረታ ብረት፣ የሞተር ብስክሌትና መኪና መገጣጠሚያ፣ የውኃ ቱቦ ሥራና የሞባይል አክሰሰሪ መገጣጠሚያዎች ይገኙበታል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም በትግበራ ሒደት የሚገኙ ፕሮጀክቶችን በመደገፍ ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ማድረግ ሌላው ኢንስቲትዩቱ የንዑስ ዘርፉ ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ የሚያከናውነው ተግባር ሲሆን፣ በያዝነው በጀት ዓመት የስድስት ወራት አፈጻጸም እንደሚያመለክተው ለ31 ፕሮጀክቶች የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ስምንት ፕሮጀክቶች ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ኢንስቲትዩቱ ድጋፍ አድርጓል፡፡

እነዚህ ወደ ማምረት የተሸጋገሩት ፕሮጀክቶች በሦስት የተለያዩ የኢንቨስትመንት ዓይነቶች የተሰማሩ ሲሆን፣ ኢንቨስትመንቶችም 3,480 ቶን የማምረት አቅም ያለው የብረታ ብረትና የቤት ውስጥ የማብሰያ ቁሳቁስ ፋብሪካ፣ 8,650 ቶን የማምረት አቅም ያለው የተሽከርካሪ መለዋወጫና ተጓዳኝ አካላት ፋብሪካና በዓመት በቁጥር 30,000 ተሽከርካሪና ሞተር ብስክሌት መገጣጠም የሚችል ፋብሪካ መሆናቸውን በሪፖርቱ ተጠቁሟል፡፡

ሁለተኛው የትኩረት መስክ ደግሞ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪን የማምረት አቅም ማሳደግ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ኢንስቲትዩቱ ከሚያከናውናቸው ተግባራት አንዱና ዋነኛው ንዑስ ዘርፉን ውጤታማ ሊያደርጉ የሚችሉ የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን መስጠት ነው፡፡ ባለሙያ ሲበቃ ምርትና ምርታማነትን ከማሳደጉም በላይ፣ ከሌሎች አገሮች ጋር ተወዳዳሪ የሚሆን ምርትን በሚፈለገው ጥራትና ጊዜ ለማምረት ያስችላል፡፡ በመሆኑም ኢንስቲትዩቱ በቅድሚያ የሥልጠና ፍላጎት የዳሰሳ ጥናት ያካሄዳል፡፡ ኢንዱስትሪዎችም በሰው ኃይላቸው የሚስተዋሉትን የተለያዩ የሙያ ክፍተቶችን በመለየት ፍላጎታቸውን ያሳውቃሉ፡፡

በዚህ የአሠራር ሥርዓትም ከ2006 በጀት ዓመት ጀምሮ ከ2,000 በላይ የንዑስ ዘርፉ ልዩ ልዩ ባለሙያዎች ሥልጠና የወሰዱ ሲሆን፣ ሥልጠናውም ኢአበላሽ (NDT)፣ አውቶ ካድ፣ የጥራት መፈተሻ (Quality Inspection)፣ ማሽኒንግ (ሌዝ፣ ሚሊንግና ሲኤንሲ)፣ የጥራት ሥራ አመራር ሥርዓት (Quality Management System)፣ ቤዚክ ሜታል ወርክስ፣ የካይዘን ሥራ አመራር ሥርዓት፣ ሶሊድ ወርክስ ሶፍት ዌር፣ ዌልዲንግ፣ ሒት ትሪትመንትና ሌሎችንም ያጠቃልላል፡፡

ከማምረት አቅም ጋር ተያይዞ ለኮንስትራክሽን ግብዓትነት ከሚያገለግሉ ዘርፎች ጥቂቶችን እናንሳ፡፡ በአገር ደረጃ 11 የሚሆኑ የአርማታ ብረታ ብረት አምራቾች ይገኛሉ፡፡ እነዚህም ወደ 1.2 ሚሊዮን ቶን የማምረት አቅም አላቸው፡፡ ከእነዚህ በተጨማሪ ስድስት የሚሆኑ ከ1.8 ሚሊዮን ቶን በላይ የማምረት አቅም ያላቸው ፕሮጀክቶች ሲኖሩ፣ ሁለቱ ፕሮጀክቶች 75,062 ቶን የማምረት አቅም ይዘው በሚቀጥለው በጀት ዓመት እንደሚገቡ ይጠበቃል፡፡ እነዚህ ኢንዱስትሪዎች ወደ አገር ውስጥ የሚገባውን ምርት በመተካት ረገድ አስተዋጽኦዋቸው የጎላ ሲሆን፣ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ መጨረሻ ላይ ለመድረስ የታቀደው የአምስት ሚሊዮን ቶን መሠረታዊ ብረታ ብረት ምርት ለማሳካት አመላካች ይሆናሉ፡፡

ቆርቆሮ ሌላው ለኮንስትራክሽን ግብዓትነት ከሚያገለግሉ ዘርፎች መካከል የሚጠቀስ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ኢንስቲትዩቱ የሚደግፋቸው ከ25 በላይ የቆርቆሮ አምራች ድርጅቶች በአገራችን እንዳሉ የሚታወቅ ሲሆን፣ ሁለት ደግሞ በፕሮጀክት ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ኢንዱስትሪዎች ታዲያ በዓመት ከ700 ሺሕ ቶን በላይ የማምረት አቅም አላቸው፡፡ ይኽም በአገር ውስጥ ያለውን የቆርቆሮ ፍላጎት ለማርካት የሚያስችል አቅም መፈጠሩን ያሳያል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ የትቦላሬን (Hollow Section) የማምረት አቅምን እንመለከታለን፡፡ መረጃዎች  እንደሚያሳዩት ዘጠኝ የትቦላሬ አምራች ኢንዱስትሪዎች በአገራችን ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ድርጅቶች ታዲያ ከ269 ሺሕ ቶን በላይ የማምረት አቅም ያላቸው ሲሆኑ፣ ከዚህም ውስጥ 50 በመቶ ምርቱ ብቻ የገበያውን ፍላጎት ማርካት ይችላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም አንድ ፕሮጀክት 300 ሺሕ ቶን የማምረት አቅም ይዞ ለመግባት በዝግጅት ላይ እንደሚገኝ የተገኘው መረጃ ይጠቁማል፡፡

በመጨረሻም ኤክስፖርት የሚያደርግ ድርጅት ያለበትን የኬብል የማምረት አቅምን ስንመለከት በዚህ ዘርፍ ስድስት ኢንዱስትሪዎች የሚገኙ ሲሆን፣ ወደ 48 ሺሕ ቶን በዓመት የማምረት አቅም ያላቸው ናቸው፡፡ አንድ ፕሮጀክትም ከአምስት ሺሕ ቶን በላይ ማምረት የሚችል በማምረት ሒደት ላይ ካሉ ኩባንያዎች ጋር ለመቀላቀል በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡

የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ምርቶችን የገበያ ድርሻ ማስፋት ሦስተኛውና የመጨረሻው የትኩረት መስክ ሆኖ ተቀምጧል፡፡ በዚህ ሥርም ገቢ ምርቶችን ለሚተኩ ኢንዱስትሪዎች የገበያ ድርሻቸውን ማስፋት የሚያስችሉ የተሟላ ድጋፍና አገልግሎት መስጠት፣ ለንዑስ ዘርፉ ምርቶች የውጭ ገበያ ማፈላለግ የሚሉትና ሌሎች ተያያዥ ተግባራት ይከናወናሉ፡፡ በመሆኑም ንዑስ ዘርፉ ገቢ ምርትን ከመተካት ባለፈ ከ2006 በጀት ዓመት ጀምሮ የንዑስ ዘርፉን ምርቶች ወደ ውጪ በመላክ በወጪ ንግድ ኢንዱስትሪው ተወዳዳሪ እንዲሆን ጥረት ተደርጓል፡፡

በዚህ መሠረት በ2006 ዓ.ም የንዑስ ዘርፉን ምርት ኤክስፖርት ማድረግ ሲጀመር ከአሥር የማይበልጡ ድርጅቶች 3,189,172.99 ዶላር ገቢ ያስገኙ ሲሆን፣ በያዝነው በጀት ዓመት የሰባት ወራት የኤክስፖርት አፈጻጸም የሚያሳየን ደግሞ ኤክስፖርት የሚያደርጉ ኢንዱስትሪዎች ቁጥር ወደ 14 ከፍ እንዳሉና ከኢንዱስትሪዎች የተገኘው የኤክስፖርት ገቢ 11,020,963.59 ዶላር መድረሱን ነው፡፡

ኤክስፖርት ከተደረጉት የብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ምርት ውጤቶች መካከል ሞባይል፣ የኤሌክትሪክ ኬብል፣ የግብርና መሣሪያዎች፣ ቆርቆሮ፣ ጌጣ ጌጦችና የቤት ቁሳቁሶች ተጠቃሽ ሲሆኑ የምርቶቹ መዳረሻ አገሮችም አሜሪካ፣ እስያ፣ አውሮፓና የአፍሪካ አገሮች ናቸው፡፡ በመሆኑም ኤክስፖርት የሚያደርጉ ድርጅቶችና የተገኘው የውጭ ምንዛሪ ከጊዜ ወደ ጊዜ ዕድገት ቢያሳይም ከዚህ በላይ መሠራት እንዳለበት ግን አመላካች ነው፡፡

በአጠቃላይ ኢንስቲትዩቱ ከእነዚህ የትኩረት መስኮቹ በመነሳት ለብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ንዑስ ዘርፍ ድጋፍ እያደረገ ቢሆንም፣ አገሪቱ ከዘርፉ የምትጠብቀውን ውጤት ለማግኘትና ኢንስቲትዩቱም ራዕዩን ለማሳካት ከፍተኛ ሥራ እንደሚጠበቅ ይታመናል፡፡ ለዚህ ደግሞ ሁሉም ባለድርሻ አካላትና ኢንዱስትሪው የመንግሥትን ፖሊሲና ስትራቴጂን በመከተልና ከመልካም አስተዳደር ችግርና ኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትና ተግባር የፀዳ አሠራርን በመዘርጋት ለአገር ዕድገት በጋራ መረባረብ ይጠበቃል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dawit.keha@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

 

 

Standard (Image)

በአገራችን የሕክምና ሙያ ጥፋቶች እየተደጋገሙ ስለሆነ መላ ሊፈለግላቸው ይገባል!

$
0
0

በኢዮቤድ ጥበቡ ልሳነወርቅ
      በዘውዲቱ ሆስፒታል የእንቅርት ታካሚዋ ለሐሞት ከረጢት ጠጠር ሆዷ በቀዶ ጥገና መከፈቱን በተመለከተ አስደናቂ ዜና ተዘግቧል፡፡ የሕክምና ሙያ ጥፋቱን የፈጸሙት ሐኪም ከሥራ መታገዳቸውን፣ ተጎጂዋ በሽተኛም  "የሐሞት ጠጠሩ በነፃ ስለወጣልሽ ዕድለኛ ነሽ"መባሏ ጭምር ተሰምቷል፡፡ የእንቅርት ታካሚዋና የሐሞት ጠጠር ታካሚዋ በቅደም ተከተል "ሰላም ደሞዜ"እና  "ሰላም ኪሮስ"ይባላሉ፡፡ ሁለቱም ታካሚዎች ለየግል ሕክምናቸው ከሆስፒታሉ የተገኙት የወረፋ ቀጠሮ  ስለደረሳቸው ከሕመማቸው የሚፈውሳቸውን ሕክምና ለማግኘት ብለው ነው፡፡ በስም መመሳሰል የእንቅርት ታካሚዋ የሰላም ደሞዜ ሆድ በስህተት በቀዶ ጥገና ሕክምና ተከፍቷል፡፡ በስህተት ያልጠበቀችውና ያልተዘጋጀችበት ቀዶ ጥገና ሲደረግላት በሕይወቷ ላይ ከፍተኛ አደጋ ሊያጋጥማት ይችል እንደነበር ግልጽ ነው፡፡
የኢቢሲ ዜና አገልግሎት ለተጎጂ ግለሰቧና ለሆስፒታሉ ኃላፊዎች ቃለ መጠይቅ  ሲያደርግላቸው በቴሌቪዥን መስኮት ተመልክተናል፡፡ በቃለ መጠይቁ ሆስፒታሉ የሚያስተዳድራቸው ሐኪሞች በሕክምና አፈጻጸማቸው ላይ ጥፋት ከሠሩ በእነሱ ድርጊት ሆስፒታሉም የፍትሐ ብሔር ኃላፊነት ያለበት መሆኑን ሳይገልጽ፣ ጥፋቱ የተፈጸመው በዋናው ሐኪምና በረዳቶቻቸው ጥንቃቄ ጉድለት መሆኑን ብቻ ገልጾአል፡፡ ትልቁንም ጥፋት የፈጸሙት የቀዶ ጥገና ሐኪሙ ስለሆኑ ከሥራና ከደመወዝ ማገዱን፣ የተጎጂዋን በሽተኛ ጤንነት እየተከታተለ እንዳስፈላጊነቱ በነፃ ሕክምና ይሰጣታል ሲል ሆስፒታሉ በተጨማሪ ገልጾአል፡፡
የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ በዚህ ጉዳይ ላይ ብዕሩን ሊያነሳ የቻለበት ምክንያት   ስለጉዳት ሥጋትና መድን ግንዛቤ ለኅብረተሰቡ የሚያስጨብጥ መጽሐፍ በአማርኛ ሲያዘጋጅ ባደረጋቸው ጥናቶችና ምርምሮች፣ በአገራችንም ሆነ በውጭ አገሮች በሕክምና ሙያ ላይ በተደጋጋሚ የተፈጸሙ ጥፋቶችን መዝግቦ በመያዙ ነው፡፡  በዚህ አጋጣሚ ለአብነት ያህል ጥቂቶቹ በዚህ ጽሑፍ ይነሳሉ፡፡ በእግረ መንገድም ሆስፒታሎች በማወቅም ሆነ ባለማወቅ በሕክምና ሙያ ጥፋት ኃላፊነቱ እንደሚመለከታቸው   ለሕዝብ ሳይገልጹ የሚሰጧቸው አስተያየቶች ትክክል እንዳልሆኑ እውነታውን ሕዝብ እንዲገነዘበው ይደረጋል፡፡
ባለሙያዎችን ቀጥሮ የሚያሠራ ሆስፒታል/የሕክምና ተቋም እንደ ጲላጦስ እጁን ታጥቦ ከደሙ ንፁህ ነኝ ሊል አይችልም፡፡ ሕሙማን ከአንድ የሕክምና ባለሙያ ወይም ሆስፒታል/የሕክምና ተቋም ጋር ከሕመማቸው ለመፈወስ ሲሉ የሚፈጥሩት ግንኙነት በ1952 ዓ.ም. የፍትሐ ብሔር ሕግ መሠረት ውል ነው፡፡ አንቀጽ 2641 ይህንኑ እንደሚከተለው ይደነግጋል፡፡
አንቀጽ 2641 የሆስፒታል ውል ትርጓሜ፡፡
የሆስፒታል ውል ማለት አንድ የሆስፒታሉ መሥሪያ ቤት ስለአንድ የታወቀ በሽታ ብዙ ሐኪሞች አንድ ሆኖ ለአንድ ሰው የሕክምና ሥራዎች ሊያደርግለት የሚደረግ ውል ነው"፡፡ የዚህ ድንጋጌ እንግሊዘኛው ትርጉም፡ "Definition of contract of hospitalization. A contract of hospitalization is a contract whereby a medical institution undertakes to provide a person with medical care from one or several physicians in connection with a given illness!"

      ሕዝብ የሕክምና ባለሙያዎችን ምጡቅ የኅብረተሰብ አባላት (the smartest members of society) አድርጎ እንደሚመለከታቸው ግልጽ ነው፡፡ አመለካከቱ  ያለምክንያት የተፈጠረ አይደለም፡፡ አንድ ሐኪም ጥሩ ሐኪም ሆኖ የሚመረቀው በረጅም ጊዜ የትምህርትና የሥልጠና ጥረቱና ድካሙ ብቁ ሐኪም ስለመሆኑም በምዘና ተረጋግጦለት ነው፡፡ በሥራ ዓለምም ከተሰማራ በኋላ ሙያውን በተከታታይ ሥልጠና፣ በአዳዲስ ክህሎቶችና ቴክኖሎጂዎች እውቀቱን ለማዳበርና ለማዘመን ያላሰለሰ ጥረት በማድረግ ብቃቱን ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻሻለ ስለሚሄድ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ሐኪሞች ሰው እንጂ  መለኮታዊ ባህሪ የላቸውም፡፡ እንደ ማንኛውም ሰው በስህተት ወይም በቸልተኝነት በሕክምና ሥራቸው ላይ ማድረግ የሚገባቸውን ባለማድረግ ወይም ማድረግ የማይገባቸውን በማድረግ ስህተቶችን ሊፈጽሙ ይችላሉ፡፡
የዚህ አጭር ጽሑፍ ዓላማ በጥፋት ላይ ስለተመሠረተ ኃላፊነት የፍትሐ ብሔር ድንጋጌዎችን ለማንሳትና በዓለም ላይ በሌሎች አገሮች እንደሚሠራበት ሁሉ፣ ለአገራችን ባለሙያዎችም "የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ዋስትና" (Professional Indemnity/Liability Insurance) ለባለሙያውም ሆነ ለተጎጂው ወገን አለኝታ ሆኖ ሊያገልግል እንደሚችል አንድ ሁነኛ መላ ለመጠቆም ነው፡፡ ስለአጠቃላይ ጥፋት በፍትሐ ብሔር ሕጉ የተደነገጉ ሁለት አናቅጽት አሉ፡፡
አንቀጽ 2028 ጠቅላላ መሠረት
ማንኛውም ሰው ከራሱ ጥፋት የተነሳ በሌላ ሰው ላይ ጉዳት ካደረሰ ላደረገው ጥፋት ኪሳራ መክፈል አለበት (Who so ever causes damage to another by an offense shall make it good)"፡፡
አንቀጽ 2029  የጥፋት ልዩ ልዩነት
(1) አስቦ ወይም በቸልተኝነት በሚሠራ ተግባር ጥፋት ሊደረግ ይችላል፣
(2) እንዲሁም አንድ ተግባርን መፈጸም ወይም ተግባርን አለመፈጸም ጥፋት ሊሆን ይችላል የሚሉ ናቸው፡፡
(የዚህ አንቀጽ ርዕስ የእንግሊዝኛ ትርጉም "Types of Offence"ነው፡፡ ምናልባት የአማርኛው ርዕስ የአጻጻፍ ግድፈት ይኖርበት ይሆን በማለት ጸሐፊው ከመጽሐፉ መጨረሻ ላይ እርማት ቢፈልግ አላገኘም፡፡ ስለዚህ አባባሉን ከእንግሊዝኛው ትርጉም አንፃር አንባቢ እንዲረዳው ያስፈልጋል)
ስለሕክምናና ስለሆስፒታል ውል በፍትሐ ብሔር ሕጉ ከአንቀጽ 2639 እስከ 2652 ዝርዝር ነገሮች ተደንግገዋል፡፡ ሁሉንም በጋዜጣ ዓምድ ላይ መዘርዘር ስለማይቻል፣ ከእነዚያ መካከል በተለይ ሁለቱን አናቅጽት ብቻ ለግንዛቤ እንዲበጅ ይጠቀሳሉ፡፡
"አንቀጽ 2651 ስለ ሆስፒታሉ መሥሪያ ቤት ኃላፊነትና ስለሕክምናው አፈጻጸም፡፡ በሐኪሞች ወይም እነሱ ባሰማሩዋቸው ረዳት ሠራተኞች ጥፋት በበሽተኛው ላይ ለደረሰው ጉዳት የሆስፒታሉ መሥሪያ ቤት በፍትሐ ብሔር ረገድ ኃላፊ ነው"፡፡ (Liability of medical institutions. 1. Medical Treatment. The medical institution shall be civilly liable for the damage caused to a sick person by the fault of the physician or auxiliary staff, which it employs).
አንቀጽ 2652 ስለሆቴሉ ሥራ አፈጻጸም ጥንቃቄ
በሽተኛው ስለሕክምናው ጥቅም በማለት በሆስፒታሉ ውስጥ የተመገበና የተቀመጠ እንደሆነ ስለዚሁ መቀመጥና ስለዚሁ መመገብ ኃላፊነቱንና ግዴታዎቹን የሚመለከት የሆቴል ሥራን ውል በሚመሩት በዚህ ሕግ ደንቦች ጽሑፎች መሠረት ተፈጻሚ ይሆናሉ (ከአንቀጽ 2653 እስከ 2671 ተመልከት)፡፡ (Board and lodging. Where the sick person, for the purpose of his treatment, is lodged and fed by the medical institution, such institution shall, as regards its obligations and responsibility arising from loging and feeding, be subject to the provisions regarding to innkeepers’ contracts፡ Art. 2653-2671). (የአማርኛው ርዕስ አጻጻፍ "ስለሆቴሉ ሥራ አፈጻጸም ጥንቃቄ"የሚለው ከእንግሊዝኛው ትርጉም አንፃር "ስለሆስፒታሉ ሥራ አፈጻጸም ጥንቃቄ"ማለቱ እንደሆነ ልብ ይሏል፡፡)
በዚህ ድንጋጌ መሠረት አንድ ሕመምተኛ በሆስፒታል ውስጥ ተኝቶ በሚታከምበት ጊዜ የመኝታ ምቾቱና አመጋገቡ የሆቴል ሥራ በሚመራበት ደንብና ሥርዓት ተፈጻሚ መሆን እንዳለበት የፍትሐ ብሔር ሕጉ ደንግጓል፡፡
እ.ኤ.አ. በጥር ወር 2015 በወጣው ኢትዮጵያ የሜዲካል መጽሔት (Ethiopian Medical Journal) ላይ የኢትዮጵያ ጤና ባለሙያዎች ሥነ ምግባር ፌዴራል ኮሚቴ (Health Professionals Ethics Federal Committee of Ethiopia) እ.ኤ.አ ከጥር 2011 እስከ ታኅሳስ 2013 ባቀረበው የሦስት ዓመት ሪፖርት በሕክምና ሙያ ላይ ከቀረቡት አቤቱታዎች መካከል 23.3 በመቶ ያህሉ በትክክል ጥፋት ሆነው መረጋገጣቸውን፣ 76.7 በመቶ ያህሉ አቤቱታዎች በትክክል ጥፋት ሆነው እንዳላገኛቸው ተገልጾአል፡፡ ኮሚቴውም ሆስፒታሎች ሕሙማን ላይ ጉዳት እንዳይደርስ በማድረግ ረገድ ግንባር ቀደም ሚና ያለባቸው መሆኑን እንዲሁም ለኦብስቴትሪስ፣ ለጋይናኮሎጂ፣ ለጄኔራልና ለኦርቶፔዲክስ ቀዶ ጥገና ሐኪሞች ስለሕክምና ሙያ ስህተቶች ማነቃቂያ ሥራ እንደሚያስፈልግ (Creation of more awareness) ወደ እነዚህ ሙያዎች ለሚገቡትም ልዩ ሥልጠና እንደሚያስፈልጋቸው ምክሩን ለግሷል፡፡
ስለ ልዩ ሙያ የፍትሐ ብሔር ሕጉ የሚከተለውን ይደነግጋል፡፡
አንቀጽ 2031 በሙያ ሥራ ስለሚደረግ ጥፋት
(1) በልዩ ሙያው አንድ ሥራ የሚፈጽም ሰው ወይም በዚህ በሙያው የሥራ ተግባሩን የሚያካሂድ ሰው፣ የዚሁ የሙያ ሥራው የሚመራበትን ደንብ መጠበቅ ይገባዋል፡፡
(2) በሥነ ጥበብ ወይም ራሱ በሚሠራው ኪነ ጥበብ ደንቦች መሠረት ያሉበትን ግዴታዎች አለመከተሉ ሲገለጽ ባለመንጠንቀቅ ወይም በቸልተኝነት ጥፋተኛ ሆኖ በተገኘ ጊዜ ኃላፊ ይሆናል፡፡
ባለሙያዎች እነማን ናቸው? ለሚለው ጥያቄ ከላይ የተጠቀሰው ድንጋጌ መልስ ይሰጠናል፡፡ በዚሁ ድንጋጌ ንዑስ አንቀጽ (1) መሠረት በቅድሚያ በሙያው አስፈላጊውን እውቀት፣ ልዩ ልምድና ሥልጠና (special skills, experience and knowledge) አግኝቶ የሙያ ተግባሩ የሚመራበትን ደንብና ሥርዓት ጠብቆ መሥራት ያለበት ሰው ባለሙያ ነው፡፡ የሙያ ሥራው የሚመራበትን ደንብና ሥርዓት ሳይጠብቅ በስህተት ወይም በቸልተኝነት ለፈጸመው የሙያ ስህተት ጥፋተኛ ይሆናል፡፡ ንዑስ አንቀጽ (2) ደግሞ በሥነ ጥበብ ወይም ራሱ በሚሠራው ኪነ ጥበብ መሠረት ያሉበትን ግዴታዎች ሳይጠብቅ ተገቢውን ጥንቃቄ አጉድሎ በቸልተኝነት ለሚሠራው የሙያ ተግባር ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ ኃላፊ መሆኑን ሰይገልጻል፡፡
ስለዚህ ልዩ ልዩ የሙያ ተግባራትን የሚያከናውኑ የሙያ ተቋማትና ባለሙያ ሰዎች፣ ለምሳሌ ሆስፒታሎች፣ ሐኪሞች፣ ነርሶች፣ ፋርማሲስቶች፣ አዋላጆች፣ ኢንጂነሮች፣ አርኪቴክቶች፣ የሕግ አማካሪዎች፣ ጠበቆች፣ አካውንታንቶች፣ ኦዲተሮች/ሒሳብ መርማሪዎች፣ የፋይናንስ፣ የማኔጅመንትና ሌሎች አማካሪዎች፣ "የውስጥ አስዋቢዎች" (Internal Decorators)፣ ወዘተ ባለሙያዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ባለሙያዎች ከላይ እንደተመለከተው ተግባራቸውን ሲያከናውኑ የሙያቸውን ደንብና ሥርዓት እንዲሁም አግባብነት ያላቸውን ሕግጋት ሳይከተሉ በቸልተኝነት ለፈጸሙት ጥፋት፣ የፍትሐ ብሔር ኃላፊነት ስላለባቸው ጉዳት ለደረሰባቸው  ወገኖች ተገቢውን የጉዳት ካሳ የመክፈል ግዴታ አለባቸው፡፡
በሪፖርተር ጋዜጣ ቅጽ 21 ቁ. ጥር1677 ግንቦት 17 ቀን 2008 "ምን እየሠሩ ነው?"በሚለው ዓምድ የኢትዮጵያ የግሉ ዘርፍ ሐኪሞች ማኅበር ፕሬዚዳንት በሰጡት ቃለ ምልልስ "አንድ ሐኪም የሕክምና ስህተት ሠራ ተብሎ እጁ ላይ ካቴና ማስገባት ተገቢ አይመስለኝም"ሲሉ የሰጡት አስተያየት አነጋጋሪ ይመስላል፡፡ ፕሬዚዳንቱ አባባላቸውን በደንብ ስላላብራሩት ከፍትሐ ብሔር ወይም ከወንጀለኛ መቅጫ ሕጉ አንፃር አስተያየት ለመስጠት ይቸግራል፡፡
ይሁን እንጂ ስለሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን አንዳንድ ነጥቦችን ከማንሳታችን በፊት፣ በዚህ ጽሑፍ መጀመሪያ ላይ የተገለጸውን ዓይነት የሕክምና ሙያ ጥፋቶች መደጋገማቸው አሌ አይባልም፡፡ ለአብነት ያህል በአገራችን የተከሰቱትን ሁለት  የሕክምና ሙያ ጥፋቶችን፣ እንዲሁም አንድ በውጭ አገር የተከሰተን የሙያ ጥፋት በዚህ ጽሑፍ ላይ ማንሳት የጉዳዩን አሳሳቢነት ሊያጎላው እንደሚችል ጸሐፊው  ያምናል፡፡ የተጠቀሱት የሕክምና ሙያ ጥፋቶች ልብ ወለድ ሳይሆኑ በእውነት የተፈጸሙና በመገናኛ ብዙኃንም በወቅቱ ለሕዝብ የተገለጹ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ የተፈጸሙት ጥፋቶች ቀደም ብለው የተፈጸሙ በመሆናቸው  ፈጻሚዎቹን ሆስፒታሎች በዚህ ጽሑፍ በስም መጥቀስ አላስፈለገም፡፡
"የመሬዋ ልጃገረድ" 

      ከወደ መራቤቴ አንዲት ልጃገረድ ለሕክምና ወደ አዲስ አበባ ትመጣና ከአንድ ታዋቂ ሆስፒታል ውስጥ የማህፀን ሕክምና ትጀምራለች፡፡ የማህፀን ሐኪሙ ተገቢውን ምርመራ ካደረገላት በኋላ "የማህፀን ደጃፍ ፈሳሽ" (Vaginal Smear) ናሙና ተወስዶ በላብራቶሪ እንዲመረመር ያዛል፡፡ የማህፀን ሐኪሙ ረዳት ወይም በዜናው ድሬሰር የተባለው ባለሙያ ናሙናውን በሚወስድበት ጊዜ ያላግባብ የልጅቷን ስሱ ገላ ስለጠነቆለባት ክፉኛ ስትጮህ ሐኪሞች ተረባርበው ሲመረምሯት ክብረ ንጽፅህናዋ ላይ ጉዳት እንደደረሰባትና በዚህ ምክንያትም ደም እንደፈሰሳት ተገልጾ የመጀመሪያ ዕርዳታ ያደርጉላታል፡፡ ጉዳቱን ያደረሰባት መጀመሪያ ካያት ሐኪም ቀጥሎ ከማህፀኗ ናሙናውን የወሰደው ረዳት ባለሙያ መሆኑን፣ እርሱም ከሥራ ታግዶ የገንዘብ ቅጣት እንደተወሰነበት የሆስፒታሉ የወቅቱ ሜዲካል ዳይሬክተር የነበሩት በቴሌቪዥን በተደረገላቸው ቃለ መጠይቅ ገልጸዋል፡፡ ሆስፒታሉና ምርምራውን ያካሄዱት ባለሙያዎች ልጅቷ ለደረሰባት የሕክምና አገልግሎት የሕክምና ሙያ ጥፋት ተጠያቂ መሆናቸው አያከራክርም፡፡ እንደዚያ ባለው ስስ ገላ ላይ የምርመራ ሒደቱን በጥንቃቄ መፈጸም የነበረበት ዋና ሐኪሙ ራሱ ነው ወይስ ረዳቱ  የሚል ጥያቄም በጊዜውም ተነስቷል፡፡ ጉዳዩ ፖሊስ እጅ እንደደረሰና ከዚያ በኋላ የተደረሰበትን ውጤት በተመለከተ በቂ ማስረጃ ማግኘት አልተቻለም፡፡ ቁም ነገሩ ኅብረተሰቡ በሌሎች ሰዎች ጥፋት ጉዳት ሲደርስበት እንደ ቀድሞው "የአርባ ቀን ዕድሌ ነው፣ መቼስ ምን ይደረጋል?"ብሎ በአርምሞ የሚተወው ነገር እንዳልሆነ የመሬዋ ልጃገረድ አረጋግጣለች፡፡
የሞተው ሾፌር

      በደርግ ጊዜ የነበረውን የቀበሌ መጠሪያ ስም ጸሐፊው ማስታወስ ቢቸግረውም፣ አካባቢው በዛሬው ስሙ የየካ ክፍለ ከተማ ከእንግሊዝ ኤምባሲ ጀርባ ከፍ ብሎ ባለው ዳገታማ ቦታ በዘልማድ"ብቅ እንቅ"ከሚባለው ሰፈር፣ አንድ የአዕምሮ ሕመም የነበረበት ሰው ዘጠኝ ልጆቹን፣ ባለቤቱንና እሱን ጨምሮ አሥራ አንድ ቤተሰብ በከባድ መኪና ሾፌርነት ሙያ ያስተዳድር ነበር፡፡ ሕመሙ ሲነሳበት ወደ ተለመደው ሆስፒታል ሄዶ ይታከምና ሲሻለው ወደ ሥራው ይሰማራል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አዘውትሮ ይታከምበት የነበረው ሆስፒታል ለቀበሌ ስልክ ይደውልና "አቶ እገሌ ሞቷልና ቤተሰቡ መጥቶ አስከሬኑን ይውሰድ"ብሎ መርዶ ይነግራል፡፡ ሞቷል የተባለውም ሰው በሠፈሩ በመልካም ባህሪው የሚታወቅ፣ ሰው አክባሪና ደግ ስለነበረ የቀበሌው ሰዎች በጣም ተደናግጠው ለሠፈሩ ዕድር ዳኞች ይነግራሉ፡፡ መርዶውን የሰሙ ጎረቤቶች ሁሉ ሟች ሾፌር ቤት ይሄዱና ባለቤቱን "ወ/ሮ እገሊት ተነሽ፣ ልበሽ፣ አቶ እገሌ ሕመሙ ፀንቶበታል ተብሎ ከሆስፒታል ተደውሏልና ሄደን እንየው፤"ብለው ይነግሯታል፡፡ ሴትዮዋም በጣም ተደናግጣ፣ "እንዴ ምንድንው የምትሉት? እሱኮ ድኖ ከሆስፒታል ወጥቶ ወደ ሥራው ተመልሷል፡፡ ክፍለ ሀገር ከሄደ አንድ ወር ሊሞላው ነው፤"ብላ መልስ ብትሰጥም፣ "አይ ብቻ ተነሽ ልበሽ"ባዩ ስለበዛባትና በድንጋጤም ስለተዋከበች በሠፈር ሰዎች ታጅባ ሆስፒታሉ ዘንድ ትደርሳለች፡፡

የሆስፒታሉም ሰዎች እሷንና አጃቢዎቿን ወደ አስከሬን ማቆያ ክፍል ይወስዷቸውና አስከሬኑን ያሳዩዋቸዋል፡፡ ሞተ የተባለው ሰው ሚስት አስከሬኑን አይታ "እንዴ ይኼ እኮ እሱ አይደለም ምነው ጠቆረብኝ?"ትላለች፡፡  "ሴትዮ ሬሳ ሲቆይ ይጠቁራል ብትወስጂ ውሰጂ አለበለዚያ ማዘጋጃ ቤት ወስዶ እንዲቀብረው እናደርጋለን፤"የሚል ኃይለ ቃል ከሆስፒታሉ ሠራተኞች ይሰነዘርባታል፡፡ አጃቢ ሠፈርተኞችም  በሁኔታው ግራ ቢጋቡም አስከሬኑ ከቆየ ይበልጥ ይበላሻል በሚል ፍራቻና ድንጋጤ  በሳጥን አድርገው አስከሬኑን ሠፈር ያደርሳሉ፡፡ ከዚያም ሟች አቶ እገሌን ቤተ ዘመዱ፣ ልጆቹና ወዳጆቹ እንባ በእንባ እየተራጩ የካ ደብረ ሳህል ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ወስደው ይቀብሩታል፡፡

      ሞተ ተብሎ የተቀበረው ሾፌር አቶ እገሌ በ12ኛ ቀኑ ለተቃረበው የዘመን መለወጫ ቅዱስ ዮሐንስ ዓመት በዓል መዋያ የሚሆኑ ዶሮዎች፣ ቅቤ፣ ከሰል፣ ለልጆቹም ሸንኮራ አገዳውን፣ ወዘተ ይዞ ገና ሲነጋጋ ከቤቱ ከች ይላል፡፡ ዘመዶቹና ልጆቹ ከፍራሽ ላይ ሳሎን ተኝተው ሲያገኛቸው በጣም ደንገጦ፣ "ማነው የሞተው ንገሩኝ ማነው የሞተብኝ ልጅ፤"ብሎ ራሱን ይዞ እዬዬ በማለት መጮህ ይጀምራል፡፡  "ኧረ! አንተ ነህ ሞትክ የተባልከውና የተቀበርከው፤"ቢሉትም አልሰማ ብሎ ጩኸቱን ይቀጥላል፡፡ በስንት ሆይ ሆይታ ለቅሶውም ይቆምና ግርግሩም ይረግብና ‘እግዘአብሔር ያጥናሽ’ ያላት የሠፈር ሰውና ወዳጅ ዘመድ ሁሉ በአግራሞት ቀኑን ሙሉ እየመጣ ‘እንኳን ደሽ ያለሽ’ ይላት ገባ፡፡

      የኋላ ኋላ ጉዳዩ አደባባይ የወጣው ዕድሩ ለሴትዮዋ የከፈላትን ብር 300 መልሽ በማለቱ ነው እንጂ፣ ይኼንን የሚያህል ትልቅ በደል በአንድ ቤተሰብ ላይ ደርሶ  "ጉድ አንድ ሰሞን ነው"እንዲሉ የሠፈር ወሬ ከመሆን አያልፍም ነበር፡፡ ‘የበላሽውን ብር መልሽ’፣ ‘አልመልስም’ የሚል ትልቅ ወዝግብ በዕድሩና በሴትዮዋ መካከል ይነሳል፡፡ በተነሳው ውዝግብም ከፊሉ ሰው ሴትዮዋ ባልዋ ባይሞትም ሞተ ተብሎ በምትኩ የሌላ ሰው ቀብር መፈጸሙና ቤተሰቡም በስህተት በመጣ እክል ተሰቃይቷልና ሴትዮዋ ገንዘቡን መመለስ አይገባትም ሲል፣ ከፊሉ ደግሞ የዕድሩ ገንዘብ እንዴት ሊወራረድ ነው? የሕዝብ ገንዘብ ስለሆነ መመለስ አለባት ይላል፡፡

በዚህ ምስኪን ቤተሰብ ላይ ያን ያህል ጉዳት ከደረሰ በኋላ ከዕድሩ የተከፈላትን ገንዘብ መልሽ መባሏ አግባብ ነው? አይደለም? በሚል በተነሳው ውዝግብ መካከል "ይህ ሁሉ ነገር የደረሰው በማን ጥፋት ነው?"ለሚለው ጥያቄ መልስ ለማግኘት ጥረት የሚያደርጉ የሠፈር ሽማግሌዎችና የዕድሩ ዳኞች ከሴትዮዋ ጋር ሄደው ሆስፒታሉን ለመጠየቅ ይስማማሉ፡፡

"የመጣነው ከዚህ ቀበሌና ዕድር ነው፡፡ በዚህ ቀን በስህተት የዕድራችን አባል የሆነ እገሌ የተባለ ሰው ሞተ ብላችሁ ስልክ ደውላችሁልን ከሬሳ ማቆያ ቦታ ገብተን ስናየው እሱ ለመሆኑ ጥርጣሬ ቢገባንም፣ እዚህ ቆይቶ ሬሳው ከሚበላሽ ብለን ወስደን ቀብረን በኋላ ሞተ የተባለው የዕድራችን አባል ደህና ሆኖ ተገኘ፡፡ ዛሬ የመጣነው ሳይሞት ሞተ የተባለውን የዕድርተኛችን ጉዳይ ለማጣራት ነው፤"በማለት  የዕድሩ ተወካዮች የመጡበትን ጉዳይ ዘርዝረው ለሆስፒታሉ ኃላፊዎች ያስረዳሉ፡፡ የሆስፒታሉ አስተዳደርም "ሲደወልላችሁ መጥታችሁ አስከሬኑን በዓይናችሁ አይታችሁ የእኛ ነው ብላችሁ ወስዳችኋል፡፡ ከዚህ ውጪ እኛ የምናውቀው ነገር የለም፤"  በማለት ቁርጥ ያለ መልስ ይሰጣቸዋል፡፡

      ‘ይህ አስደናቂ ነገር መጀመሪያውኑ እንዴት ሊከሰት ቻለ?’ ተብሎ ነገሩ ሲጣራ እንደተደረሰበት ሞተ የተባለው የሴትዮዋ ባል የተኛበት አልጋ ካርድ ሳይለወጥ ሌላ በድንገት ታሞ የመጣ በሽተኛ ተኝቶ ሲታከም ይቆይና ይሞታል፡፡ ለቀበሌውም አስከሬን ውሰዱ ተብሎ ከሆስፒታሉ የተደወለው በእውነተኛው ሟች አድራሻ ሳይሆን፣ ከእሱ በፊት ተኝቶ ድኖ በወጣው ሾፌር ካርድ ላይ ከተገኘው የቀበሌ ስልክ አድራሻ ነበር፡፡ ጉዳዩ ፖሊስ እጅ የደረሰ ቢሆንም በእውነት የሞተውን ሰው ማንነት ፖሊስ ስለማጣራቱ ወይም በአካራካሪው ነጥብ ላይ የተሰጠ ውሳኔ ስለመኖሩ የተገኘ ተጨማሪ ማስረጃ የለም፡፡ ጉዳዩ በዚያው ተድበስብሶ የቀረ ይመስላል፡፡ ሞተ በተባለው ሾፌር ቤተሰብ ላይ የደረሰው "የአካልና የሞራል ጉዳት፣ እንዲሁም የገንዘብ ኪሳራ"በጣም ከፍተኛ መሆኑ አይካድም፡፡

ከላይ በጠቀስናቸው ሕግጋት መሠረት እነዚህ ጉዳዮች ከፍርድ ቤት ቢደርሱ ለተጎጂ ወገኖች የጉዳት ካሳ ሊከፈላቸው እንደሚችል አያጠራጥርም፡፡ ድርጊቶቹ የተከሰቱት በአደጉት አገሮች፣ በተለይም በአገረ አሜሪካ ቢሆን ኖሮ በሕክምና ሙያ ጥፋት ሕጋዊ ኃላፊነት ሆስፒታሎቹና በውስጡ የሚሠሩ ሠራተኞች በሙያ ቸልተኝነት ተከስሰው ለተጎዱ ወገኖች በብዙ ሚሊዮን ዶላር የሚቆጠር ገንዘብ ካሳ በከፈሉ ነበር፡፡ የሕክምና ሙያ ጥፋት ለተጎጂው ወገን የጉዳት ካሳ በመክፈል ብቻ የሚወሰን ሳይሆን፣ እንደ ጥፋቱ ክብደት የሙያ ሥራ ፈቃድን ሊያስነጥቅ ይችላል፡፡

የአንጎል ቀዶ ጥገና (Brain Surgery)

የሕክምና ሙያ ስህተቶች የሚፈጸሙት በአገራችን ብቻ ሳይሆን በበለጸጉት አገሮች ሳይቀር እንደሚፈጸሙ ከላይ ገልጸናል፡፡  በአገረ አሜሪካ ሮድ አይላንድ ክፍለ ግዛት በታዋቂውና የሐኪሞች ማሠልጠኛ በሆነው ሮድ አይላንድ ሆስፒታል ውስጥ፣ በአንድ ዓመት ሦስት ያህል የአንጎል ቀዶ ጥገና ስህተቶች ተፈጽመዋል፡፡ የመጀመሪያው  ስህተት የግራ ጎኑን የአንጎል ክፍል በቀዶ ጥገና ለመክፈት ታስቦ በስህተት የቀኙን  የአንጎል ክፍል ሐኪሞቹ ከፍተውታል፡፡ ስህተቱ ሲመረመር ቀዳጅ ሐኪሞቹም ሆኑ ነርሶቹ የሥራ ቅደም ተከተል ማጣሪያ ዝርዝር (Checklist) አጠቃቀም ሥልጠና እንደሌላቸው ታውቋል፡፡ በቀዶ ጥገና ሥራ አፈጻጸም ይቅርና ከግሮሰሪ ዕቃዎችን ለመግዛት አንኳን የዕቃዎች ዝርዝር በቅድሚያ ማዘጋጀት ወሳኝነቱ አይስተባበልም፡፡
የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን

Anchorባለሙያ ግለሰቦች/ቡድኖች ወይም የሙያ ሥራ የሚሠሩ ተቋማት በሙያቸው አግባብ ሥራ በሚሠሩበት ወይም አገልግሎት በሚሰጡበት ጊዜ "ስህተቶች" (Errors)፣ ወይም "ግድፈቶች" (Omissions) በቸልተኝነት ፈጽመው ሲገኙና ጥፋታቸውም በሰዎች ላይ ጉዳት ካደረሰ፣ የድርጊቱ ፈጻሚ ባለሙያዎች በሕግ ተጠያቂዎች እንደሚሆኑ ከላይ ተገልጾአል፡፡ አጥፊዎቹ በፍርድ ቤት ተከሰው ለተጎጂው ወገን ካሳ መክፈል ግዴታቸው ነው፡፡ ለዚህ ዓይነቱ የጉዳት ሥጋት ተጋላጭነት (Exposure to Risk) ለባለሙያዎቹ አለኝታ ሆኖ ሊያገለግላቸው የሚችለው የመድን ዋስትና ዓይነት "የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ዋስትና ውል"ነው፡፡ ዋስትናው ለተጎጂው ወገን የሚከፈለውን ካሳ መክፈል ብቻ ሳይሆን ክስን ለመከላከል የሚወጣውን ወጪ ጭምር ይሸፍናል፡፡ በተለይ በአሜሪካ ይህ ዓይነቱ የመድን ውል "የስህተቶችና ግድፈቶች መድን ውል" (Errors and Omissions Insurance) በሚል ስያሜ ይታወቃል፡፡

ልዩ ልዩ የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ዋስትና ውሎች አሉ፡፡ እንደ ባለሙያው ፍላጎትና እንደሚሰጠውም የሙያ አገልግሎት ዓይነት ውሉን መድን ሰጪው ለደንበኛው እንደሚስማማው አድርጎ ሊቀርፅለት ይችላል፡፡ አንዳንድ በውጭ አገሮች የሚገኙ  የመድን ሰጪዎች  የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ውል በተከታታይ የሚታደስ ከሆነ፣  በቀደመው የውል ዘመን የቀረቡ የጉዳት ካሳ ጥያቄዎችን ጭምር በመሸፈን ለመድን ገቢዎች ጥቅም ይሰጣሉ፡፡ የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ዋስትናን ተመሳሳይ ሙያ ያላቸው ሰዎች በቡድን አንድ ላይ ሆነው ሲገዙት የዓረቦን ቅናሽ ያስገኝላቸዋል፡፡
የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ውል የገንዘብ መጠን  ወሰን (Professional Liability Policy Limit)

የሕጋዊ ኃላፊነት መድን ውል የኃላፊነት መጠን ወሰን  አለው፡፡ የውል ኃላፊነት መጠን ወሰን ምን ማለት ነው? በተለይ በሕጋዊ ኃላፊነት መድን ውሎች የኃላፊነት መጠን ወሰን ሲባል "መድን ሰጪው በአንድ የውል ዘመን ውስጥ ለጉዳት ካሳ ለመክፈል የተስማማው ከፍተኛ የገንዘብ ካሳ ኃላፊነት መጠን ወሰን"ማለት ነው (Indemnity or policy limit is the maximum amount that an insurer will pay out for any one claim and usually within any one-policy year (assuming a yearly insurance policy)፡፡

ስለሆነም እንደ ሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ውል "የካሳ ገንዘብ ኃላፊነት መጠን ወሰን"ያላቸው የሕጋዊ ኃላፊነት የመድን ዋስትና  ዓይነቶች፡

    "የምርት ሕጋዊ ኃላፊነት መድን" (Products Liability)፤

    "የሕዝብ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን" (Public Liability) እና

    "የሠራተኞች ጉዳት ሕጋዊ ኃላፊነት መድን" (Workers’ Compensation/Employers Liability/Indemnity insurance) ለአብነት ይጠቀሳሉ፡፡

ከሌሎች የመድን ዋስትናዎች መግቢያ ገንዘብ መጠን (Sum Insured) የሕጋዊ ኃላፊነት ገንዘብ መጠን ወሰን የሚለየው በእያንዳንዱ በደረሰ አደጋ ወሰን ወይም  በዓመቱ ጠቅላላ የኃላፊነት መጠን ወሰን መሠረት ሊገደብ ስለሚችል ነው፡፡ ስለዚህም የሌሎች የመድን ዋስትና ውሎች መድን ዋስትና ገንዘብ መጠን የሙያ ኃላፊነት መድን ውል ገንዘብ መጠን ወሰን አተማመን ለየት እንደሚል ልብ ሊባል ይገባል፡፡  የሚወሰነውም "በደረሰ አደጋ መጠን" (Any One Accident (AOA) Limit) ወይም "በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ በደረሰ አደጋ መጠን" (Any One Year (AOY) Limit) ሊሆን ይችላል፡፡

"በደረሰ አደጋ መጠን"የኃላፊነት ገንዘብ ወሰን በውሉ ዘመን ውስጥ በደረሱ አደጋዎች ለእያንዳንዳቸው የሚከፈለውን "ከፍተኛ የገንዘብ መጠን"የሚወስን ነው፡፡ አወሳሰኑም የመድን ገቢውን የሙያ ሥራ ኃላፊነት በባለሙያው የሥራ አፈጻጸም ሊጎዱ የሚችሉትን የሰዎች ብዛትና የሚጠቀምባቸውን መሣሪያዎች ዓይነት ወይም ብልሽት በአንድነት ሊደርስ የሚችለውን ከፍተኛ የኃላፊነት ወሰን መጠን በቅድሚያ በማስላት ነው፡፡

የሚገርመው በታዳጊ አገሮች በተለይም በአገራችን የሚገኙ ባለሙያዎችና ተቋማት ለሙያ ግዴታቸው የሚሰጡት ትኩረት እጅግ አነስተኛ ነው፡፡ ሕዝብ ግን በጉዳዩ ላይ እያደር እየነቃ እንደሚሄድና ለደረሰበት ጉዳት ካሳ በሕግ አግባብ ጉዳት ፈጻሚውን እንደሚጠይቅ ሊታወቅ ይገባል፡፡

ስለዚህ "በሬ ሆይ ሣሩን አየህና ገደሉን ሳታይ"እንዳይሆን ባለሙያዎች የሆኑ ሰዎችና ተቋማት ሁሉ የሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድን ዋስትና እንዲገዙ ይመከራሉ፡፡ በተለይ የሕክምና ባለሙያዎች ከሚሠሩበት ሆስፒታል ወይም ክሊኒክ ውጪ ለምሳሌ በድንገተኛ ዕርዳታ ወቅት የበጎ ሥነ ምግባር ግዴታቸውን ሲፈጽሙ ስህተት ሊያደርጉ ስለሚችሉ ሊጠነቀቁ ይገባል፡፡

ብዙ አገሮች በተለይ "የሕክምና ሙያ ሕጋዊ ኃላፊነት መድንን"እንደ "ሦስተኛ ወገን አስገዳጅ የተሽከርካሪ መድን ዋስትና"አስገዳጅ አድርገውታል፡፡ በእኛ አገርም ሊታሰብበት እንደሚገባ በተከታታይ የተከሰቱት የሕክምና ሙያ ጥፋቶች ህያው ምስክሮች ናቸው፡፡ አስገዳጅ አዋጁን ለመደንገግ ብዙ ሰዎች እስኪጎዱ መጠበቅ የለበትም።

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው [BA, LLB (GD), Post Graduate Dipl. in Development Administration (India), ACII, Chartered Insurer (UK), ACS (USA)] ለረጅም ዓመታት በመድን ሥራ፣ በሥልጠና፣ በመድን ምርምርና ሥነ ጽሑፍ ልምድና ዕውቀት ያላቸው ናቸው፡፡ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው eyosono@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

የረመዳን ወር የሰላም የመረጋጋት የነፃነትና የክብር መገለጫ ነው

$
0
0

ተሾመ ብርሃኑ ከማል

የዘንድሮ የረመዳን በዓል ከግንቦት 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለአንድ ወር ያህል በጾም ይከበራል፡፡ ረመዳን በተለያዩ አገሮች በተለያዩ መንገዶች፣ ልምዶችና እሳቤዎች ይከበራል፡፡

በረመዳን ወር ሙስሊሙ ኅብረተሰብ በርካታ በረከት የሚያስገኙ መልካም ነገሮች ያከናውናል ተብሎም ይጠበቃል፡፡  በዚህም ምክንያት ሙስሊሞችና የሌላ እምነት ተከታዮች ወሩ መልካም የጾም ጊዜ ሆኖ እንዲያልፍ ምኞታቸውን ይገልጻሉ፡፡ እንደ አሜሪካ፣ እንግሊዝ፣ ፈረንሣይ፣ ጀርመን፣ አውስትራሊያና የመሳሰሉት የአገር መሪዎች ደግሞ ኅብረተሰቡ በሰላም፣ በመረጋጋት፣ በነፃነትና በክብር እንዲያሳልፈው መልዕክታቸውን በልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን ያስተላልፋሉ፡፡  በረመዳን ወር እንደዚህ ያለውን የላቀ ኢስላማዊ  ሥነ ምግባርን ሲያሳይ በአካባቢው የሚገኙ የሌሎች እምነት አባቶችና ተከታዮች የላቀ ከበሬታን ይሰጡታል፡፡ በልዩ ልዩ አገሮች የሚገኙ የክርስትናና የአይሁድ ሃይማኖት መሪዎች ‹‹የእንኳን አደረሳችሁ›› መልዕክት የሚያስተላልፉ ከመሆናቸውም በላይ ለዚህ ወር ትኩረት በመስጠት ስለዓለም ሰላም፣ አብሮ መኖር፣ መቻቻል፣ የእርስ በርስ መተሳሰብና ፍቅር እንዲሰፍን ያስተምራሉ፡፡

በሃይማኖቶች መካከል የአስተምህሮት ልዩነት ቢኖርም፣ ሁሉም ከፈጣሪ ጋር የተያያዘ በመሆኑ እንደሚያመሳስላቸው አበክረው ያወሳሉ፡፡ እንደኩዌት ባሉ አገሮች አብያተ ክርስቲያናት፣ ሙስሊሞች ጾም እንዲይዙባቸው ወይም ጾመው ከዋሉ በኋላ እንዲያፈጥሩባቸው ይጋብዛሉ፡፡ ከሙስሊሞች ጋርም አብረው አንድ ማዕድ ይመገባሉ፡፡ ‹‹በአንድ ማዕድ ስንበላ የበለጠ አንድ እንሆናለን፤›› በማለትም ሐዋርያው ጳውሎስ ሰዎች ለሰላምና ለፍቅር ተቀራርበው መጣር እንዳለባቸው ማስተማሩን በተግባር ያሳያሉ፡፡ እንዲህ በሚያደርጉ አገሮች በተለያዩ ሃይማኖት ተከታዮች መካከል ያለው ግንኙነት ጠንካራ እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ 

በዘር፣ በጾታ፣ በቋንቋ መለያየት ምክንያት ኅብረተሰቡ መለያየት እንደሌለበት ሁሉ በሃይማኖትም መለያየት እንደሌለበት መንግሥታቱ ይመክራሉ፡፡ በአንዳንድ ሙስሊም አገሮች የመጀመርያው የረመዳን ቀን ክብረ በዓል ሆኖ ስለሚከበር ሥራ አይኖርም፡፡ ሱቆችም ሆኑ ምግብ ቤቶች እስከ ማታ ድረስ ይዘጋሉ፡፡ የትምህርትና የሥራ ሰዓታት የሚቀነሱበት አጋጣሚም አለ፡፡ ነጋዴዎች ከተምር ምርት ጀምሮ ብዙ የምግብ ሸቀጦችን ወደ ገበያ ያቀርቡበታል፡፡

ረመዳን በዋነኛነት ከማንኛውም ወር ሁሉ በበለጠ መልኩ ራስን ለሥነ ሥርዓት በማስገዛት፣ በሰላምና በመቻቻል ማለፍ ያለበት ወር መሆኑን በሃይማኖቱ ጥልቅ ዕውቀት ያላቸው አባቶች አበክረው ያሳስባሉ፡፡ ሙስሊሞች ወርሐ ረመዳንን ራሳቸውን ለሥነ ሥርዓት በማስገዛት ያሳልፋሉ ሲባል በሰዎች ውስጥ የሚገኝን የስግብግብነት፣ የራስ ወዳድነት፣ የምቀኝነት፣ የተንኮል፣ የጠብ ጫሪነት፣ የትንኮሳ፣ የሌሎችን መብት የሚፃረር ተግባርና ከመሳሳሉት መጥፎ ባሕርያትን ሁሉ በመቆጣጠር ራሱን ለፈጣሪ ያስገዛል ማለትን ይጨምራል፡፡

ቅዱስ ቁርዓን የሚያስተምረው ኅብረተሰቡ የዘር፣ የጾታ፣ የሃይማኖት፣ የዜግነትና፣ የቀለም ልዩነት ሳያደርግ ከሁሉም ጋር ተቻችሎ እንዲኖር፣ በጥልቅ ሃይማኖታዊ ስሜት፣ በፍቅርና በመደጋገፍ የሰውን ታላቅነት ተቀብሎ አስፈላጊውን ሁሉ ክብር መስጠት በልዩ ልዩ ምክንያቶች የተቸገሩን በመርዳት እንዲያሳልፈውና ከፈጣሪ ጋር ያለውን ግንኙነት እንዲያድስ ነው፡፡ 

የተለያየ እምነት፣ ዘር፣ ብሔር ብሔረሰብ፣ ቀለም ወዘተ ያላቸው ሰዎች በፈጣሪ ዘንድ አንድ መሆናቸውን የሚቀበል ሙስሊም በረመዳን ወር የበለጠ ማሰብ የሚኖርበት ሰዎች በሰውነታቸው አንዳቸው ሌላቸውን ሳይጎዱ በፍቅር፣ በመተሳሰብ፣ በመግባባትና በስምምነት በወንድማማችነት ስሜት እንዴት እንደሚኖሩ በማሰብ መሆን እንዳለበት ቅንጣት እንኳን የሚያጠያይቅ አይደለም፡፡ በራሱ የሚተማመንም በዕውቀት ለመብለጥ እንጅ በኃይል ለማንበርከክ ውጤታማ ሊሆን እንደማይችል ያውቃል፡፡ የፈጣሪን ትዕዛዝ እቀበላለሁ የሚል አማኝም ዕውቀት ተቀዳሚው ሥራ እንደሆነ ይገነዘባል፡፡ ለእምነት ሲባል የሚወጣ ወጪ ቢኖር ከፍተኛው ለትምህርት መዋል እንዳለበት እሳቤ ይሰጣል፡፡ በሌላ አነጋገር እፍኝ በማይሞሉ ጥቂት ሰዎች ከመተማመን ብዙዎችን ለማፍራት ለትምህርት ቅድሚያ መስጠት ማለት ነው፡፡ ሙስሊሙ ኅብረተሰብ በጭፍን በደል እያነሳ ከሚቆዝም ወደፊት ላለው ኅብረተሰብ የሃይማኖት፣ የሳይንስና ቴክኖሎጂ፣ የሕግ፣ የወታደራዊ ጥበብ፣ የኪነ ጥበብ፣ የሥነ ጥበብ፣ የሕክምናና የምሕድስና ወዘተ ምሁራን የመኖራቸው አስፈላጊነት ከምን ጊዜውም የበለጠ ግልጽ ሆኖ ሊታየው ይገባል፡፡ በዚህ ዓመት ረመዳን መታሰብ ያለበትም ይህ እንደሆነ የዚህ ጽሐፍ አዘጋጅ ያምናል፡፡ 

ኢትዮጵያውያንሙስሊሞችበዚህየረመዳንወር

ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች በዚህ የረመዳን ወር ማስታወስ ያለባቸው ሌላው ዋነኛው  ቁም ነገር ኢትዮጵያውያን ሁሉ በራሳቸው ታሪክ፣ ባህል፣ ልምድ፣ ብሔር፣ ብሔረሰብና ክልል ኩሩ የመሆናቸውን ያህል ከሌሎች አገሮች በሚነሳ ማዕበል የማይናጡ ጠንካራ ሕዝቦች መሆናቸውን ነው፡፡ በኢትዮጵያውያን መካከል የእምነት ልዩነት ቢኖርም ሰብዓዊ ፍጡር መሆናቸውን፣ ተመሳሳይ ባህል፣ ተመሳሳይ ታሪክ፣ ተመሳሳይ ልምድና ተመሳሳይ ሥነ አዕምሮ የሚጋሩ በመሆናቸው የበለጠ ቢያዳብር እንጂ አያቀጭጭም፡፡ 

በመሠረቱ በአገራችን ሙስሊሞችና ሙስሊም ያልሆኑ ክፍሎች የሚኖሩት አብረው ነው፡፡ በአንድ ግቢ ብቻ ሳይሆን በአንድ ቤት ውስጥ ሙስሊሞችና ሙስሊም ያልሆኑ ሰዎች አብረው የመኖራቸው ጉዳይ እንግዳ አይደለም፡፡ በትምህርት ቤትም ሆነ በሥራ መስክ አንዱ የሌላው ጓደኛ ነው፡፡ ከዚህም በላይ አንዱ ሌላውን ከእምነቱ ተከታይ የበለጠ ያምነዋል፡፡ ያከብረዋል፡፡ ይህ ጾታን፣ ብሔርን፣ ብሔረሰብን፣ ዘርንና ክልልን የሚለይ አይደለም፡፡ ሐዘን ወይም ደስታ ቢኖር ሙስሊሙ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ የሐዘን ተካፋይ ወይም የደስታ ተካፋይ ቢሆን፤ ወይም ከቤተ ክርስቲያን ጎን መስጊድ ቢሠራ፤ የአንዱን ጸሎት ሌላው ቢያዳምጥ የሚሰማው የከፋ ስሜት የለም፡፡ ከሚያለያዩት ነገሮች ይልቅ የሚያገናኙት ነገሮች እንደሚበዙ ስለሚገነዘብም ተቻችሎ ይኖራል፡፡ ስለዚህም፣ ‹‹ኢትዮጵያ፣ ሕዝቦቿ በሰላም፣ በመከባበር፣ በመፋቀር፣ በመተባበር፣ የሚኖሩባት የተቀደሰች ሥፍራ ናት፤›› ተብሎ የሚነገርላትም ለዚህ ነው፡፡ ከ30 እና ከ40 ዓመታት በፊት በፖለቲካ መሪዎች አነሳሽነት አልፎ አልፎ ሁከት ሲፈጠር በቀላሉ ይቀዘቅዝና ይረሳ የነበረውም ለዚህ እንደነበረ ግልጽ ነው፡፡ 

ኢማም ሐሰን ቃሲም ኦኪኪኦላ የተባሉ ናይጄሪያዊ ሙስሊም ምሁር ባለፈው የካቲት ወር በጻፉት መጣጥፍ ‹‹ምንም እንኳን የሙስሊሞች፣ የክርስቲያኖችና የአይሁዳውያን እምነት ምንጩ አንድ እንደሆነ የታወቀ ቢሆንም፣ በአውሮፓውያንና በአሜሪካውያን፣ እንዲሁም በአንዳንድ አፍሪካውያን ኢስላም እንግዳ እንደሆነ ተደርጎ ይታመናል፡፡ ስለሆነም እንዲህ ዓይነቱን አመለካከት ለመለወጥ ማስተማር ተቀዳሚውን ሥፍራ መያዝ አለበት፤›› በማለት የሃይማኖትን ምንነት ጠልቆ ባለመገንዘብ ምክንያት በዓለማችን የሰፈነውን ሥጋት፣ ጥላቻ፣ አመጽና ጥርጣሬ በማስወገድ የተሻለ መከባበርና መተሳሰብ ዕውን ይሆን ዘንድ ጠንክሮ መሥራት እንደሚገባ ይመክራሉ፡፡ 

በአሁኑ ጊዜ፣ በተለያዩ አገሮች የሚኖሩ ሙስሊሞች ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ሁኔታ ለሕዝቦች በሰላም አብሮም መኖርና መከባበር ጠንክረው በመሥራት ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይም እንደ ኢትዮጵያ፣ ቱርክ፣ ሊባኖስ፣ ግብፅ፣ ኢንዶኔዢያ፣ ፓኪስታን፣ ናይጄሪያና ማሌዢያ ያሉ የተለያየ ሃይማኖት የሚገኝባቸው አገሮች በመጫወት ላይ ያሉት ሚና በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ ይህም ሆኖ ከሃይማኖታዊ ምክንያት ይልቅ ፖለቲካዊ አመለካከት እያየለ አልፎ አልፎ ችግር መስተዋሉ አልቀረም፡፡ ይህም በአገራችን ሙስሊም፣ ክርስቲያንና ኦሪታውያንን እርስ በእርስ በማለያየትና አንዳቸውን ከሌላቸው በማበላለጥ ይጠቀሙበት እንደነበረው ዓይነት መሆኑ ነው፡፡ ኢስላምን በሚመለከት በአልመኢዳህ (5፡48) ‹‹ወደ እናንተም መጽሐፉን ከበፊቱ ያለውን መጽሐፍ አረጋጋጭና በእርሱ ላይ ተጠባባቂ ሲኾን በእውነት አወረድን፡፡ በመካከላቸውም አላህ ባወረደው ሕግ ፍረድ፡፡ እውነቱም ከመጣልህ በኋላ ዝንባሌዎችን አትከተል፡፡ ከአንተ ለሁሉም ሕግና መንገድን አደረግን፡፡ አላህ በሻ ኖሮ አንድ ሕዝብ ባደረግሁት ነበር፡፡ ግን በሰጣችሁ ሕግጋት ሊሞክራችሁ (ለያያችሁ)፡፡ በጎ ሥራዎችንም ለመሥራት ተሽቀዳደሙ፤ መመለሻችሁ በጠቅላላ ወደ አላህ ነው፡፡ በእርሱም ትለያዩበት የነበራችሁትን ነገር ይነግራችኋል፤›› ተብሎ በግልጽ ሰፍሯል፡፡ ነቢዩ መሐመድም (ሱዓወ) ከክርስትናና ኦሪት ሃይማኖት ተከታዮች ጋር ተከባብረው አብረው ኖረዋል፡፡ አቡዳውድ የተባሉት የነቢዩ ሙሐመድ ሐዋርያ እንደጠቀሱት ‹‹ማንኛውም ሙስሊም ያልሆነ ዜጋን የጎዳ እኔን እንደጎዳ ይቆጠራል፤›› በማለት በመጀመርያው የሙስሊም ዓለም የሃይማኖት ነፃነትና ብዝኃነትን ያረጋገጡትም እሳቸው ናቸው፡፡ በሌላ አነጋገር እንኳንስ በተመሳሳይ እምነት ጥላቻን ማናፈስ በተለያየ ሃይማኖት ላይ ተመሳሳይ ችግር መፍጠር ትክክል አለመሆኑን ነው የገለጹት፡፡ ዳሩ ግን ሙስሊሙ በእንዲህ ባለው ጥብቅ መሠረት እምነት የሚመራ እንጂ አክራሪም፣ አሸባሪም አለመሆኑን በተግባር ማሳየት ያለበት ራሱ መሆኑን ነው፡፡  

ዶክተር አስላም ዓብዱላህ የተባሉ የሃይማኖት አባት በረመዳን ጾም መደረግ  ካለባቸው ውስጥ ‹‹ሙስሊም ያልሆኑ ወዳጆቻቸውን ወደ ቤታቸው በመውስድ አብረዋቸው እራት እንዲበሉ መጋበዝ፣ ቤት የሌላቸውን በመመገብ፣ ሕዝባዊ ጠቀሜታ ላለው መልካም ተግባር ገንዘብ አዋጥቶ በመስጠት፣ በሌሎችም ሆነ በራሳችን ምክንያት የተፈጠረ ችግር ቢኖር ይቅርታ በመጠየቅና ይቅርታ በማድረግ፣ ምንም ያህል የሚያስቆጣ ሁኔታ ቢገጥመን ታጋሾች በመሆን ልናሳልፈው ይገባል፤›› ሲሉ መክረዋል፡፡ 

በመቻቻል፣ በመከባበርና በሰላም አብሮ መኖር መርሕ አራማጅነታቸው በዓለም የታወቁት ቱርካዊው ኢስላማዊ ምሁር ፈትሁላህ ጉለን ደግሞ ሙስሊሞች በብሩህ ምሽት ኮለል ብላ እንደምትታይ ጨረቃ አንፀባራቂው የሆነውን የረመዳን ወር እንዴት በሰላም፣ በፍቅር፣ በመተሳሰብና በመረዳዳት ማሳለፍ እንደሚገባቸውና ረመዳን በየልቦናቸው የሚያስተላልፍላቸውን ቅዱስ ብርሃን ተጠቅመው ለነፍሳቸውና ለሥጋቸው ፋይዳ ያለው ኢስላማዊ ተግባር ማከናወን እንዳለባቸው አበክረው ይመክራሉ፡፡ 

ፈትሑላህ ጉለን በጥልቅ ዕውቀታቸውና በተባ ብዕራቸው ስለረመዳን ካሉት ውስጥ የሚከተለው ይገኝበታል፡፡

በአንድ ኢፍጣር ቀን (ማታ የሚበላበት ሰዓት) ስለተደረገው ግብዣ ፈትሑላህ ጉለን ሲገልጡ ‹‹የደራስያንና የጋዜጠኞች ፋውዴሽን በኮንራድ ሆቴል ባዘጋጀው የእራት ግብዣ ሥነ ሥርዓት፣ የተለያዩ አብርሃማዊ ሃይማኖቶች ተከታዮች ተገናኝተው ነበር፡፡ ከነዚህም መካከል የግሪክ ኦርቶዶክስ ፓትርያርክ፣ የቱርክ አይሁዶች መሪ (ራባይ)፣ የአሜሪካ ፓትሪያርኬት ጳጳስ ተገኝተው ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ተመሳሳይ ቋንቋና ቀለም›› በሚል ርዕስ የተዘጋጀው ፊልምና የዕውቅ ገጣሚያን ቅኔዎች ቀርበዋል፡፡ በነዚህም ፊልሞችና ግጥሞች የሰላምና የመቻቻል አስፈላጊነት ተንፀባርቀዋል፡፡ የደራስያኑና የጋዜጠኞች ፋውዴሽኑ ፕሬዚዳንት ‹‹የእያንዳንዱ ሰው የጋራ አካፋይ ሰው መሆኑ በቂ ሆኖ እያለ ሰዎች ይህንን በኃይል ለመለያየት ሲደክሙ ይታያሉ፤›› ያሉ ሲሆን፣ ሌላው ተጋባዥም ‹‹ለመሆኑ ሰዎች ምንም ዓይነት የሃይማኖትም ሆነ የአመለካከት ልዩነት ይኑራቸው አብሮ ከመኖር የተሻለ ነገር አለን?›› በማለት በጽሑፋቸው ገልጸዋል፡፡ ለፈትሑላህ ጉለን ሃይማኖት የግል ጉዳይ ሲሆን፣ የተለያዩ እምነት ያላቸው ሰዎች አብረው ለመኖር የሚያስችሏቸው በርካታ ነገሮች እንዳሉ በተለያዩ ሥራዎቻቸው ይገልጻሉ፡፡ 

በመጪው የረመዳን ወር ልዩ ትኩረት ቢሰጠው ለመላው ኢትዮጵያ ሕዝብና ለዓለም ሕዝብ የሚጠቅም፤ በተለይም ከኢትዮጵያ ተጨባጭ እውነታ ጋር የሚመሳሰል ሐሳብ ፈትሑላህ ጉለን ‹‹የነፍሳችን ሐውልት›› በሚል ካዘጋጁት መጽሐፍ ላይ እናገኛለን፡፡

ጉለን ‹‹መጾም ለመክሳት ሲባል ወይም ከምግብና ከመጠጥ ራስን ለተወሰነ ጊዜ ለመከልከል ሲባል በፍጹም የሚደረግ አይደለም፡፡ በየዕለቱ የሚደረጉ ጸሎቶች ለመቀመጥና ለማጎንበስ ታስበው የተዘጋጁ የአካል ማሠልጠኛ ስፖርቶች አይደሉም፡፡ ምጽዋት መስጠት ካለው ገቢ ትንሽ ግብር መክፈል ወይም በማያውቁት አገር የሚገኙ ለማያውቋቸው ችግረኛ ሰዎች ከችግራቸው ፋታ እንዲያገኙ ሲባልና፣ ለማይታወቅ ዓላማ የሚሰጥ አይደለም፡፡ ሐጅ መሄድ ሲባል ከአንድ ከተማ ወደ ሌላ ከተማ በመጓዝ ያጠራቀሙትን የአገር ውስጥ ገንዘብ ወደ ውጭ ምንዛሪ ለውጦ ማጥፋት አይደለም፡፡ ወይም ወደ ሐጅ ለጸሎት የሚሄዱበትን መሠረታዊ ምክንያት አውቀው ካልሄዱ በስተቀር ‹‹ሐጅ›› የሚለውን ስምና ከዚያ ጋር የሚገኘውን ዝና ለማግኘት ከመሆን አይዘልም፡፡ እነዚህ ሁሉ ድርጊቶች በምሕዋራቸው ዙሪያና በተዘረጋላቸው መስመርና መንፈስ በተግባር ካልዋሉ በስተቀር ከሌላው የዕለት ተዕለት ተመሳሳይ ሥራ እንደምን ተለይተው ሊታዩ ይችላሉ? በአምልኮ ተግባር ውስጥ ቁጥርን ለማብዛት መንቀሳቀስ ከልጅነት ጨዋታ ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ መንፈሳዊ ጥያቄ ለማቅረብ ካልሆነ በስተቀር በከንቱ መጮህና ማንቧረቅ የድምፅ ሳጥንን ከማለማመድ/ከማሰልጠን የተለየ ሊሆን አይችልም፤›› በማለት ያስረዳሉ፡፡

የረመዳንወርየሙስሊሙኅብረተሰብልቦናየሚመለስበት

የረመዳን ወር የሙስሊሙ ኅብረተሰብ ልቦና የሚመለስበት፣ ተክሎች አበባ በሚያወጡበት ወራት እንደሚያምሩት ሁሉ የሙስሊሙም ልቦና የሚያብብበትና የሚያምርበት፣ ራሱን በፈሪሃ እግዚአብሔር (ረቢል ዓለሚን) የሚያስገዛበት፣ ልቡን የሚያጠራበት፣ የደረቀ ቀልቡን የሚያርስበትና የሚያረሰርስበት፣ የፈጣሪ ጥልቅ ፍቅር በልቦናው የሚያድርበት፣ በደግነትና በቸርነት የሚሞላበት፣ ሁለመናው ጥሩ እንዲሠራ ጥረት የሚያደርግበት ነው፡፡ እያንዳንዱ ስለኢስላም የሚያውቅ የሚያደርገው ነገር ሁሉ በረመዳን ወር ከሰባት እስከ መቶ እጥፍ ድርብ ምንዳ (በረከት) እንደሚያገኝበት አጥብቆ ይገነዘባል፡፡ ሙስሊሙ በረማዳን ወር ከመስረቅ፣ ከመቅጠፍ፣ ከማጭበርበር፣ በሐሰት ከመመስከርና ከመመቅኘት ወዘተ ርቆ በፀፀት ያሳልፋል፡፡ ፀፀቱም ዳግም ላለመሥራት መሆኑንም ለራሱና ለፈጣሪው ቃል ይገባል፡፡ ትክክለኛ ነገር ማድረግን ይመርጣል፡፡ የተቀደሱ ተግባራትን ያከናውናል፡፡ 

ከረመዳን ወር በፊት በነበሩት ወራት ያደርገውን የነበረ በጎ ተግባር ያልቃል፡፡ በሽተኛን ይጠይቃል፡፡ የተራበን ያበላል፡፡ የታረዘን ያለብሳል፡፡ የሞተን ይቀብራል፡፡ የታሰረን ይጠይቃል፡፡ እንዲሁም ይፀልያል፡፡ ምህረትንም ይጠይቃል፡፡ የሙስሊሙንና የሌላውን ኅብረተሰብ ሰላም ከሚያደፈርሱ ነገሮች ሁሉ ይርቃል፡፡ በረመዳን ወር ድባቡ ሁሉ ደስ በሚሉና ደስ በሚያሰኙ ተግባራት ይሞላል፡፡ አንዳንድ ሰዎች መጾም እንደሚያደክም ይናገራሉ፡፡ በእርግጥም የሚጾመው ከ13 ሰዓት በላይ ነውና ሊያደክም ይችላል፡፡ ነገር ግን በዚህ ወር ከፍተኛ ምንዳ ለማግኘት ለሚሻ ወሩ እንዲረዝምለት ባይሻም በእያንዳንዱ ቀን፣ ሰዓትና ደቂቃ በጎ ነገር ለማከናወን ይጥራል፡፡ በበጎ ነገር ይደሰታል፡፡ በበጎ ሥራው ይፈነጥዛል፡፡ የቀንም የሌሊትም ሐሳቡ ፈጣሪውንና ሰውን ማስደሰት ነው፡፡ አንድ ቀን አልፎ ሌላው ሲተካ የምኞቱን ያህል ሳይሠራ የሚቀር ስለማይመስለው የበለጠ በጎ ነገር ለመሥራት ይጣደፋል፡፡ ወሩ እየተገባደደ ሲሄድም ‹‹አይ እኔ፣ ለመሆኑ ፈጣሪን የሚያስደስት ተግባር ምን ያህል አከናወንኩ?›› ብሎ ራሱን ይጠይቃል፡፡ ‹‹በሚቀጥለው ዓመት ላይ ደርሼ ተመሳሳይ በጎ ተግባር ለማከናወን እችል ይሆን?›› ብሎም በፍርኃት ፈጣሪውን ያስባል፡፡ የሌላው እምነት ተከታይ በረመዳን ወር ሙስሊም ወንድሙ ሲጾም ማሰብ የሚኖርበትም ይህንን በጎ አመለካከት ነው፡፡ ይህን ሲያደርግም አጸፋውን ከሰውም ከፈጣሪም ያገኛል፡፡

የሙስሊሙናየሌላውእምነትተከታዮችትብብርከምንይመነጫል?

ሙስሊሞችና ክርስቲያኖች የተለያዩ እምነት ተከታዮች ቢሆኑም በአንድ ፈጣሪ ብቻ ማመናቸው፣ በነቢያት፣ በመላዕክት፣ በጾም፣ በመስገድ፣ በምፅዋትና በመጨረሻው ቀን እምነታቸው በተለያየ መንገድ የሚገለጽ ቢሆንም፣ ከሌሎች ሃይማኖቶች በተለየ ሁኔታ የበለጠ ተቀራራቢ ያደርጋቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሁለቱም የፈጣሪ ባሮችና አገልጋዮች መሆናቸውን፣ ሁለቱም በዚች ዓለም ላይ የሚደርስባቸውን የፈጣሪ ፈተና አልፈው ገነት እንደሚገቡ ወይም ካላለፉ ሲኦል እንደሚወርዱ ያምናሉ፡፡ ይልቁንም ሙስሊሞች ኢየሱስ የፈጣሪ ቃል እንደነበረና ያም ቃል በቅድስት ማሪያም ማህፀን አድሮ ሰው ሆኖ መወለዱና በኋላም የፈጣሪን ቃል አስተምሮ ማረጉን ያምናሉ፡፡ ኢየሱስን የማያፈቅርም የተሟላ ሙስሊም ሊሆን አይችልም፡፡ ቅድስት ማርያምን ያከብራል፡፡ ያፈቅራል፡፡ ለክርስቲያኑ ፈጣሪ ‹‹ሕያው ዘይመውት ነው፤›› ለሙስሊሙም እንደዚሁ፡፡ ክርስቲያኑ ‹‹እንአምን በሐዱ አምላክ›› ይላል፡፡ ሙስሊሙም እንዲሁ፡፡ ሁለቱም በጾም፣ በጸሎት፣ ለፈጣሪ በመስገድ፣ በመጨረሻይቱ ዕለትና በፍርድ ቀን ያምናሉ፡፡ ክርስቲያኑ ‹‹ካለኔ በቀር ሌላ አምላክ አታምልክ›› የሚለውን ቃል አጥብቆ ይከተላል፡፡ ሙስሊሙም ከፈጣሪ ጋር ሌላ አያጋራም፡፡ ከእርሱ ጋር ሌላም አያወዳድርም፡፡ በቀጥታ ፈጣሪን ብቻ ይለምናል፣ የሚፈልገውንም እሱን ብቻ ይጠይቃል፡፡

የዚህ ዓይነቱ በጎ አመለካከትና የጠለቀ ዕውቀት ሲኖር የሃይማኖት አባቶች፣ ወላጆች፣ መምህራን ለሥጋና ለመንፈሳዊ ልጆቻቸው አንደኛው ሌላውን ከማንቋሸሽ፣ ስም ከመስጠት፣ ከማጠልሸት፣ ከማዋረድ ይልቅ መከባበር፣ መተሳሰብ፣ መፋቀርና መቻቻል እንዲኖር ማስተማር የላቀ መሆኑን ማስገንዘብ ይኖርባቸዋል፡፡ በእርግጥም የነገው ብሩህ ተስፋ፣ የመቻቻልና የመፋቀር ዓለም በዛሬ ልጆች ላይ የተመሠረተ ነውና በቤት ውስጥም ሆነ ውጭ ስለሌላው ሃይማኖት ሲናገሩ በአክብሮት እንጂ በማንቋሸሽና በማጥላላት እንዳይሆን መጠንቀቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ከተቻለም ልዩነቶችንና ተመሳሳይነቶችን አውቆ ማስረዳት ይገባል፡፡ በተለይም በረመዳን ወር ሙስሊሙ ለክርስቲያኑ ደግነትን፣ መከባበርን፣ መቻቻልን፣ በአጠቃላይ በጎ አርዓያነት ማሳየት፣ አስተምህሮቱን፣ መለያ ምልክቱን፣ ቤተ አምልኮቱንና እሴቱን ማክበር ሲኖርበት ክርስቲያኑም ለሙስሊም ወንድሙ ተመሳሳይ ሁኔታ ማሳየት ይጠበቅበታል፡፡ ይኽም ማለት ‹‹ትክክል ነው? አይደለም፤ ፀዳቂ ነው? አይደለም፤›› የሚሉትን ሁሉ ለራሱ ለፈጣሪና ለእምነቱ ተከታይ በመተው በሰውነቱ ሊቀበለው፣ ሊያውቀውና ሊያከብረው ይገባል፡፡ 

ሙስሊሙ ፀሎት የሚያደርገው ለራሱና ለሙስሊሙ ኅብረተሰብ ብቻ ሳይሆን በአንድ ፈጣሪ ለሚያምኑ ሁሉ ነው፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ የሌላው እምነት ተከታይ በአንድ ፈጣሪ ለሚያምነውና በራሱ መንገድ የፈጣሪን ትዕዛዝ ለሚፈጽመው ሙስሊም ኅብረተሰብ ቢቻል በፀሎት፣ ይህ ካልሆነ በጎ ነገር በማድረግና ደግ በመሆን በሚቻለው መንገድ ሁሉ መርዳት ይጠበቅበታል፡፡ ለመሆኑ አንደኛው ሌላውን ሲረዳና ሲያከብር ማየት ይሻላል? ወይስ አንደኛው ሌላውን ሲያጠቃና ሲያንኳስስ? አንደኛ ሌላው ተደስቶ ሲያይ ቢደሰት ይሻላል? ወይስ በአንዱ ደስታ ሌላው ቢከፋ? ሁለቱ ሃይማኖቶች ምቀኝነትን፣ ክፋትንና መጥፎ ምኞትን ይሰብካሉን? ሁለቱም ሃይማኖቶች መከባበርን አይሰብኩምን? ለመሆኑ እንኳንስ ስለሌሎች ስለራሳችን እምነት ምን ያህል ጠልቀን እናውቃለን? አንደኛው ወደሌላው የሚሳበው በፍቅር ወይስ በጥላቻና በእብሪት? መመራት የሚገባውስ በመጻሕፍቱ ወይስ በስሜት? ስሜታችንን ስንከተል ልንሳሳት እንችላለን፡፡ በመጻሕፍቱ ስንመራ ግን የመረዳዳትንና የመከባበርን ትሩፋት ልንጎናጸፍ እንችላለን፡፡ በኃይል፣ በጥላቻ፣ በመናናቅና በጦርነት ለመሳብ ወይም ለማንበርከክ የሚሻ ቢኖር ዘመኑ ያለፈበት አስተሳሰብ መሆኑን መረዳት ይኖርበታል፡፡ ዘመኑ በሞተበት፣ ዘመኑ በተቀበረበት፣ ዘመኑ ከአካልነት ወደ ምንም በተቀየረበት ሌላ አዲስ ዘመን ሆኖ በዘልማድ ለመቀጠል መሞከር ፋይዳ የለውም፡፡ እርባናም የለውም፡፡ ለማንም አይጠቅምም፡፡ ስለዚህ የሃይማኖት አባት መስለው ሲታዩም ሆነ ጥብቅ የሃይማኖት ተከታይ መስለው ሲታዩ ከዘልማድ አስተሳሰብ ማለትም ከመጻሕፍቱ ውጪ በሆነ መንገድ አንዱ ሌላውን ማጥላላት፣ መናቅና ያለ ስሙ ስም መስጠት ከቶ የሚገባ አይደለም፡፡ ይህን ካደረግን ወደ ልማት፣ ወደ ዕድገት፣ ወደነበርንበት ትልቅነት ልንመለስ አንችልም፡፡

የሌላእምነትተከታዮችለሙስሊሞችምንሊያደርጉላቸውይችላሉ?

ሌላው እምነት ተከታይ የራሱን ጾም ሲጾም የሚሰማው ሁሉ ሙስሊሙ ኅብረተሰብም በተመሳሳይ ሁኔታ ሊሰማው ስለሚችል በሚከተሉት መንገዶች ርህራሔንና ደግነትን ማሳየት ይጠበቅበታል፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ከሁሉ አስቀድሞ ራስን ከጥላቻና ከንቀት ማራቅን ይጠይቃል፡፡ በእርግጥም ዓለም ከተፈጠረና ዘመን ከተቆጠረ ጀምሮ ያለውን ሁኔታ ስናስበው ከጥላቻና ንቀት መርዝ የሚመነጨው አጸፋው ነውና ራስን ከጥላቻና ከንቀት ራስን ማላቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ከዚያም ሙስሊሙ ጾመኛ መሆኑን ወይም መሆኗን በመቀበል እንደራስ ማሰብ፣ በፍቅርና በአክብሮት ማየት ይገባል፡፡ ይህንንም በሚመለከት የተለያዩ የሃይማኖት መሪዎችና ተከታዮች አበክረው ያሳሰቡ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ ‹‹በራስህ ላይ ሊደረግብህ የማትሻውን በሌሎች ላይ አታድርግ፤›› የሚለውን ወርቃማ ቃል ማስቀመጥ ይቻላል፡፡

ሰዎች በእምነታቸው የተለያዩ ቢሆኑም በማኅበራዊ ሕይወታቸው ችግረኞች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ስለሆነም የሙስሊሙ ጎረቤት የሆነ ክርስቲያን ደሃ ወይም የሙስሊም ጎረቤት የሆነው ክርስቲያን ሀብታም ሊሆኑ ስለሚችሉ፣ አንዳቸው የየትኛውም ሃይማኖት ተከታይ ቢሆኑ ሌላቸውን መርዳት እንዳለባቸው የታወቀ ነው፡፡ ስለሆነም የሌሎች እምነት ተከታዮች ሙስሊሙ ጎረቤታቸው የሚበላ ነገር የለውም ወይም የላትም ብለው ካሰቡ፣ በሚቻል መንገድ ሁሉ የሚበላና የሚጠጣ ነገር መርዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ባህል በኢትዮጵያ ሥር ሰዶ የቆየ ቢሆንም፣ በአንዳንድ አላዋቂዎች በመመራት እንዳይበረዝም መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡

ከ30 እና ከ40 ዓመታት በፊት በነበረው ባህላችን እንኳንስ በጾም የደከመና በዕድሜ የሚበልጥ ከባድ ሸክም ተሸክሞ ሲሄድ ካዩ፣ ወይም መቀመጫ አጥቶ ሲቆም ካዩ በሸክም ማገዝና አክብሮ ማስቀመጥ የተለመደ ነበር፡፡ ዛሬ ይህ ኢትዮጵያዊ ባህል የተረሳ ይመስላል፡፡ በዚህ ረገድ ተጠያቂዎች የሚሆኑት ስለ ሥነ ምግባር የማያውቁ ልጆች ሳይሆኑ ሥነ ምግባር ያላስተማሩ ወላጆች ናቸው፡፡ የሃይማኖት አባቶችና ትምህርት ቤቶችም ቢሆኑ በዚህ ረገድ ተጠያቂ ከመሆን ከቶ ሊድኑ አይችሉም፡፡ ለመሆኑ ኢትዮጵያዊ ባህልን ከአባቶች ለመማር ካልተቻለ ከማን መማር ይቻላል? ወይስ በፈረንጆች ልቅ ሕይወት መሰደድ እንደ መልካም ባህል ቆጥረነዋል? ምነው እንዲህ ለመጥፎ ነገር ፈጣን ከምንሆን ለሳይንስና ቴክኖሎጂያቸው ፈጣን በሆንን? ያም ሆነ ይህ በጾም ላይ የሚገኙ ሙስሊሞች ከባድ ሥራ የሚሠሩ ቢሆን ወይም ከባድ ዕቃ ይዘው ብናይ ማገዝ በእጅጉ አስፈላጊ ሲሆን፣ በፈጣሪ ዘንድም በረከት የሚያስገኝ ተግባር ነው፡፡ 

የፍትሕ አካላት ልዩ ልዩ ፍትሐዊ ጉዳዮችን ሲያስፈጽሙ ከረመዳን ጋር በተያያዘ ሁኔታ ማከናወን ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለምሳሌ በማረሚያ ቤት ያሉ ሙስሊሞች በተቻለ መንገድ በተመቸ ሁኔታ እንዲጾሙ ማድረግ፣ የፍርድ ቤት ጉዳይ ቢኖራቸው በጧት ማድረግ፣ ወህኒ ቤቶች ሥራ ቢኖራቸው ቀላል ሥራ ማሠራትና መርማሪዎች ጠበቅ ያለ ምርመራ ማድረግ ቢኖርባቸው ረመዳንን ከግንዛቤ ውስጥ ማስገባት፣ በአጠቃላይ ሙስሊም የሕግ ታራሚዎች በረመዳን ወርም ፍትሕ መኖሩን እንዲያምኑ በሚያደርግ ሁኔታ መያዝ ግንባር ቀደም ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡ በመሠረቱ ለሌላው ሰው ደግ እንዲሆን የሚመኙትን ያህል ለሙስሊሞችም ደግ ሆኖ መገኘት ነው፡፡ ከሁሉ አስቀድሞ ገነት የምትገኘው ደግ ነገር መሆኑን የሚያምን፣ የሌላውን እምነት ተከታይ መብት በመጋፋት ወይም ክፉ በመሆን ገነትን ለመውረስ አይመኝም፡፡ ስለሆነም ደግ ሆኖ ለሙስሊሙ ኅብረተሰብ ደግነትን ማሳየት ይገባል፡፡ 

በብዙ የመንግሥትና የግል መሥሪያ ቤቶች ለሃይማኖት ተከታዮች የማይመቹ ሁኔታዎች ይታያሉ፡፡ ለምሳሌ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት ተከታዮች በዓቢይ ጾም እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ ሲጾሙ ከስድስት እስከ ዘጠኝ ሰዓት በቤተ ክርስቲያን ቢቆዩ የሚመርጡ ቢሆንም፣ የመንግሥትም ሆነ የግል መሥሪያ ቤቶች አደረጃጀት ይህንን በሚያስተናግድ ሁኔታ ስላልተዋቀረ ብዙ ክርስቲያኖች ሲቸገሩ ይታያል፡፡ አንዳንድ ኃላፊዎች ችግሩን ከግምት ውስጥ ቢያስገቡ ሌሎቹ ባለማስገባታቸው ፈተናው እንዲህ የዋዛ አይደለም፡፡ ስለሆነም በረመዳን ወር የቤት ወይም የመሥሪያ ቤት ሠራተኞች ቢሆኑ በወቅቱ እንዲሰግዱና ወደ ቤታቸው እንዲሄዱ መፍቀድ፣ ያባከኑት ጊዜ ቢኖር በሌላ ጊዜ እንዲያካክሱ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ተገቢ ነው፡፡

ሙስሊሞች በቤትም ሆነ በመሥሪያ ቤት በተለይም ከሰዓት በኋላ ባለው ጊዜ በጣም ሊደክሙ ስለሚችሉ፣ ድካሙም አንዱ ቀን አልፎ ሌላው በተተካ ቁጥር እየጨመረ ስለሚሄድ ከባድ ሥራ እንዳይሠሩ ማድረግ፣ በፈጻሚውም ሆነ በአስፈጻሚው ዘንድ ጥቅም እንጂ ጉዳት አይኖረውም፡፡ እንዲያውም ጥሩ ግንኙነትንና መተሳሰብን በመፍጠር የበለጠ አምራች እንዲሆኑ ያስችላል፡፡ ከዚህም ሌላ በሙስሊም ድርጅት የሚሠሩ የሌሎች እምነት ተከታዮች ቢኖሩ በሚቻለው መንገድ ሁሉ የሙስሊሙን ባህል ቢጠብቁ የበለጠ ተመራጭነት ይኖረዋል፡፡ ‹‹መከበር በከንፈር‹‹ እንዲሉ በምላስ መልካም ነገርን እየተናገሩ፣ በተግባር አርኪ ውጤትን እያሳዩ፣ ከሙስሊም አሠሪዎች ጋር በረመዳን ወር ማሳለፍ ለራስም ጠቃሚ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡

ብዙ ጊዜ እንደሚታየው በረመዳን ወር አንዳንድ ነጋዴዎች ከመደበኛው ዋጋ የበለጠ ሲጨምሩ ይታያሉ፡፡ ይህ በእውነቱ አግባብ አይደለም፡፡ የምርት እጥረትን መፍጠርም ሆነ ዋጋን መጨመር ፈጣሪ ከቶ የሚወደው አይደለም፡፡ ስለሆነም የሌሎች እምነት ተከታዮች ነጋዴዎችና ገበሬዎች በረመዳን ወር ዋጋ አለመጨመር ባህላቸው እንዲሆን ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

የሁሉም ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሠራተኞችና መምህራን የሙከራም ሆነ የዋና ፈተና ቀናትን ቢቻል በረመዳን ወር እንዳይሆን፣ ካልተቻለም ከሰዓት በፊት እንዲሆኑ ማድረግ ሲኖርባቸው ለጿሚዎች ግምት ባለመስጠት ሙሉ ቀን ሲያደርጉ ይስተዋላሉ፡፡ የዘንድሮ ረመዳን በአብዛኛው ትምህርት በሌለበት ወር የዋለ ቢሆንም ወደፊት ይህ ጉዳይ ከግምት ውስጥ ሊካተት ይገባል፡፡

ሙስሊሙ በረመዳን ወር በልዩ ልዩ ጉዳዮች ባልተለመደ ሁኔታ ቸልተኛ ቢመስልና ጉዳዩ ባልሆነ ነገር ጣልቃ ባይገባ ከጾምና ከፀሎት ጋር የተያያዘ መሆኑን በመገንዘብ ሁኔታዎችን መቀበል ያስፈልጋል፡፡ ሙስሊሙ’ኮ ለራሱ ብቻ ሳይሆን ለሌላውም የሚያስብ ነው፡፡ ሲመርቅም ‹‹አገራችንን ሰላም አድርግልን፣ ረሃብና እርዛትን አስወግድልን፣ ክፉን ነገር ሁሉ አርቅልን፤›› በማለት ለሁሉም የሚፀልይና የሚመኝ ነው፡፡ ስለዚህም የሚደረግለት ትብብር ለጋራ ዓላማም ጭምር ነው፡፡

መንግሥትበረመዳንወርምንሊያደርግይችላል?

እርግጥ ነው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) መንግሥት በሕገ መንግሥቱ መሠረት ከማንኛውም ሃይማኖት ገለልተኛ ነው፡፡ ስለሆነም በማንኛውም ሃይማኖት ጣልቃ አይገባም፡፡ የዜጎቹን መብትም እኩል ያከብራል፡፡ ይኽም ሆኖ የረመዳን ወርን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ዴሞክራሲያዊ ገጽታውን የበለጠ ገልጾ በተግባር ማሳየት ይኖርበታል፡፡ ዜጎች ከማንኛውም ሥጋት ድነው የረመዳን ጾማቸውን በሰላም እንዲጾሙ በገጠርም ሆነ በከተማ ማስቻልም አንዱ ሥራው ነው፡፡ በተለይም በአፋር፣ በሶማሌ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝና በሌሎችም ቆላማ አካባቢዎች የሚኖሩ ሙስሊሞች እርስ በርስ ተከባብረውና ተፋቅረው እንዲኖሩ ማድረግ ሊታሰብበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ በከተማም ሆነ በገጠር ቢሆን ከመስጊድ አምሽተው የሚመጡት ሙስሊም ሴቶች ልዩ ልዩ አደጋዎች እንዳይገጥሟቸው ፀጥታውን በማስጠበቅ፣ በሕዝቡ መካከል መተሳሰብና መተጋገዝ የሚያስችል ሁኔታ በማመቻቸት፣ አስፈላጊውን ትኩረት መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ መንግሥት በማንኛውም ኢስላማዊ ዘርፍ ወገን እንደማይዝ ያሳወቀ ቢሆንም፣ የመንግሥትን ጥረት የሚያጎድፉ በዚህም በዚያም ያሉ ክፍሎች እንከን እንዳይሆኑ የፀጥታ ክፍሎች ነቅተው መጠበቅ አለባቸው፡፡

ችግር ሲፈጠር የፀጥታ ኃይሎችን ማሰማራትና ማረጋጋት ብቻ ሳይሆን፣ ምንና እንዴት ማድረግ እንዳለባቸው ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ይህንን ጉዳይ በክርስትናው እንመልከተው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዲገባ የሚፈቀድለት ፀጥታ አስከባሪ አለ፡፡ ሚስጥር ወዳለበት ክፍል መግባት አጥብቆ የተከለከለ ነው፡፡ በሙስሊምም ጫማ አድርጎ ወደ መስጊድ መግባት ወይም ወደ ሴት ክፍል መግባት ወይም የሴትን እጅ መያዝ አይፈቀድም፡፡ ስለዚህ ችግር ሲፈጠር ‹‹ሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ›› እንዲሉ በአጣዳፊ ወይም በደመ ነፍስ የፀጥታ ኃይል ማሰማራትና ዕርምጃ መውሰድ ብቻ ሳይሆን አመች ሁኔታን መፍጠር ይገባል፡፡ በድሮ መንግሥታት ማለትም በአፄ ኃይለ ሥላሴና በደርግ ጊዜ ፀጥታን ለማስከበር የሚላኩ ፖሊሶች በሥልጠና ላይ የነበሩ ናቸው፡፡ እነዚህም ምልምል ወታደሮች ሁከቱን የሚጋፈጡት እንደ ፊጋ በሬ በመሯሯጥ እንጂ ተረጋግተው፣ አልመውና አስበው አልነበረም፡፡ ስለሆነም ዛሬ በሠለጠነው ዘመን ደግሞ ለምሳሌ ሙስሊም ፀጥታ አስከባሪን ወደ ቤተክርስቲያን፣ ክርስቲያን የፀጥታ አስከባሪን ደግሞ ወደ መስጊድ ከማሰማራት እንደየእምነቱ ማሰማራት ይገባል፡፡ ተረጋግቶ መረጋጋት ተቀዳሚ ሁኔታ መሆን ይኖርበታል፡፡ 

ማጠቃለያ

አገራችን በሰላም ለመገንባት፣ የበለጡ የድል ውጤቶችን ለማስመዝገብ፣ ከድህነት ማጥ ለመውጣት፣ አንገታችንን ቀና አድርገን ለመጓዝ እንችል ዘንድ መተባበር፣ መፋቀር፣ መቻቻልና መተጋገዝ ይኖርብናል፡፡ መንፈሳዊ ፍላጎቱ ያልሞላለት በቁሳዊ ተግባር ሊፈተን አይችልምና ረመዳንም አንዳች ጥሩ ነገር ለማከናወን የምንችልበት ለልማታችን የሚበጅ መልካም አጋጣሚ አድርገን ልናየው እንችላለን፡፡ ውዲቱ አገራችንን፣ በታሪክ የበለፀገችና የብዙ አገሮች ባለውለታ የሆነችው አገራችንን፣ ሁሉም ብሔር ብሔረሰብ ተፋቅሮና ተቻችሎ የኖረባት አገራችንን  ለማያውቁና በውስጣቸው ባዕድነት ለሚሰማቸውም ሀቁን እንዲገነዘቡ ልናደርግ የምንችለው ባላገሮች መሆናቸውን በተግባር በማስተማር ነው፡፡ ለዚህም የእርስ በርስ ፍቅራችንን ስናደረጅ ነው፡፡ ለኔ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ወንድሜ፣ እህቴ፣ ልጄና ዘመዴ ነው፡፡ ፈጣሪ ፍቅር፣ መተባበር፣ መረዳዳት፣ መቻቻል፣ መተሳሰብና መከባበር ይስጠን፡፡ አገራችንን በሁሉም ረገድ የበለፀገች ያድርግልን፡፡ ረመዳን ሙባረክ፡፡ ረመዳን ከሪም፡፡ አሚን፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው bktesheat@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

 

 

Standard (Image)

ሦስቱ የኔትወርክ ባህሪያትና አደጋቸው

$
0
0

በልማትም በኩል በአገሪቱ ታሪክ  በመንገድ፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በገጠር ግብርናው ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ውጤታማ ሥራዎች እየተሠሩ ይገኛሉ፡፡ ተጨባጭም ሆነው በመታየታቸው የለውጥ አካል ሆኖ ለሠሩ ሁሉ ምሥጋና ይገባቸዋል፡፡ በዴሞክራስ ሥርዓት ግንባታም ነፃ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ ምርጫ በማካሄድም ሆኔ ሕዝቡ የሥልጣን ባለቤት እንድንሆን ከሕገ መንግሥቱ ጀምሮ እስከ አፈጻጸሙ ጥሩ ሥራዎች ተሠርተዋል፡፡ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩ በሒደት የሕዝቡ ግንዛቤ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በመድበለ ፓርት ሥርዓት ግንባታ ረገድም የተለያዩ የፖለቲካ አቋም ያላቸው ፓርቲዎች በነቂስ ወጥተው አቋማቸውን ለሕዝቡ ለማንፀባረቅ ችለዋል፡፡ በፍትሕ ረገድም ጥሩ ነገሮች እየተሠሩ ይገኛሉ፡፡  እንደ መነሻነት ይህንን ካልኩ ጥሩ የሆነውን ጥሩ ማለት ተገቢ እንደሆነ ሁሉ ጥሩ ያልሆነውንም ጥሩ አይደለም፣ ይቀረዋል ማለት ለተሻለ ለውጥ የሚያነሳሳ ከመሆኑም በተጨማሪ፣ ለፈጻሚውና ለአስፈጻሚው አካል ትልቅ የቤት ሥራ መስጠት ነው፡፡

መድኃኒት እንደ ለመደ በሽታ የሚጠበቀውን ያህል ስኬት ያልተመዘገበበት ጉዳይ ቢኖር መልካም አስተዳደር ነው፡፡ ሕዝቡም ይናገራል፣ መንግሥትም ያምናል፣ ችግሩ የማን እንደሆነ አይታወቅም፡፡ ዝም ብለን በሒደት ይሻሻላል እየተባለ አንደኛውን የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ጨርሰን ሁለተኛውን እየጀመርን እንገኛለን፡፡ አሁንም ከመሪው ድርጅት አሥረኛ ድርጅታዊ ጉባዔ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ የመልካም አስተዳደር ጉዳይ  ትኩረት የሚሻ ነው ሲባል እንሰማለን፡፡ መልካም አስተዳደርን በማጉዳል እስከ ዛሬ ድረስ ተጠያቂ የሆነ ባይኖርም፡፡ መቼ ይነካሉ? ለሚለው ጥያቄ የሚመለከተው አካል መልስ የሚሰጥበት ጉዳይ ይሆናል፡፡ ወደ ዋናው የጽሑፌ ጭብጥ ‹በአርሰናሎች ኔትወርክ› እና በዴሞክራሲያዊ ብሔርተኝነት አደጋው ላይ ያተኩራል፡፡ የኔትወርክ ትስስር በምን ዓይንት መልኩ መልካም አሰተዳደር ያጓድላል? ማሳያዎቻቸውና የድርጊቱ ፈጻሚ  መደበቂያዎችን ለመዳሰስ እሞከራለሁ፡፡

የመልካም አስተዳደር መጓደል መንስዔ

 የመልካም አስተዳደር ችግሮች መጠኑና ባህሪው ይለያይ እንጂ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ ተቋማት እንደሚስተዋል ግልጽ ነው፡፡ በተለይ በአንዳንድ የመንግሥት ተቋማት በሁለት የፋይናንስ ሥርዓት በመተዳደራቸው ምክንያት የመልካም አስተዳደር ችግሮች መቆጣጠር እንዳልተቻለ፣ አንዳንድ የመገናኛ ብዙኃን እየገለጹ ይገኛሉ፡፡ ሁለት የፋይናንስ ሥርዓት መኖር በሠራተኛው መካከል የተለያዩ አከፋፈሎች  ይፈጥራል፡፡ በተጨማሪም በሠራተኛው መካከል የአመለካከትና የሞራል ልዩነት እንዲፈጠር ያደረጋል፣ ተስፋ የመቁረጥ ስሜት ያስከትላል፣ ያለማቋረጥ የሠራተኛ ፍልሰትን ያስከትላል፡፡ የተቋማት መደበኛ አገራዊና መንግሥታዊ ተልዕኮ ክንውንና ጊዜ ወደ ሠራተኛ መልቀቅና መቅጠር ይቀየራል፡፡ በዚህ ወቅት ለሕዝቡ የሚሰጠው አገልግሎት መንገጫገጭ ይጀምራል፣ በሒደት ወደ መጓደል ይመጣል፡፡ ከፍልሰት ጋር ተያይዞ የአንዳንድ ተቋማት አመራሮች ሠራተኛው ለምን ይፈልሳል? ተብለው ሲጠየቁ የተሻለ ገቢ ፍለጋ ነው በማለት ለሚድያ መልስ መስጠታቸው፣ የፋይናንስ አሠራር ልዩነት የወለደው መሆኑን መገመት አይከብድም፡፡ በአንድ መንግሥት በሚተዳደሩ ዜጎች መካከል የተሻለ ገቢ ፍለጋ በማለት መልስ መስጠት በራሱ ሌላ ጥያቄን ይጭራል፡፡ ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል መርህን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ቢታሰብበት፡፡

ሁለተኛው ሥልት መመርያዎች ሲወጡና ስሻሻሉ የመልካም አስተዳደር ጉድለቶች እንዲፈጸሙ ያደርጋሉ የሚል ሥጋት አለኝ፡፡ አንዳንድ ጊዜም የተቋም ከፍተኛ አመራር ሲቀየር ይስተዋላል፡፡ ምክንያቱም ባላቸው የመምራት አቅምና ፖለቲካዊ ቁርጠኝነትን ልክ ሠራተኛው ሲተዳደርባቸው የነበረውን መመርያ ያለመቀበል ወይም ለማሻሻል ሲባል በሚደረጉ ሙከራ ሒደቶች መልካም አስተዳደርን የመሸራራፍ ሁኔታዎች ይፈጠራሉ፡፡ ከተጠያቂነት ለማምለጥና ለማስመለጥም መመርያ መቀየር ይኖራል የሚል ሥጋትም ይኖራል፡፡ አንዳንዴ ሕዝቡም በተደጋጋሚ  ተጠያቂ ናቸው ብሎ የሚጠብቃቸው አንዳንድ የአመራር አካላት፣ በፍትሕ ተጠያቂ ከማድረግ ይልቅ ወደ ተሻለ ደረጃ ሲሾሙ ይታያሉ፡፡ የነበረው አጥፍቶ ሲሄድ ተተኪው  ደግሞ ነባሩን ኔትወርክ ለመበጣጠስ ሥራና የሥነ ምግባር መርሆዎችን በተለይ ‹ኪራይ ሰብሳቢነት› የምትለውን ሐረግ ይደጋግማል፡፡ ነባሩን ኔትወርክ ለመበጣጠስ አዲሱን ኔትዎርክ ለመዘርጋት ሲታገል ቆይቶ መጨረሻ ላይ የመልካም አስተዳደር ችግር ነው ይባላል፡፡ 

ስለዚህ መመርያዎች የሚቀየሩት ለምንድነው? መመርያ በተቋም ደረጃ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል አይቀየርም? ከሚለው ጋር እንደማልስማማ እግረ መንገዴን መግለጽ እወዳለሁ፡፡ ሌላው ደግሞ በተለይ በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጉዳይን ባለማመላለስ፣ በተወሰነ መልኩ አገልግሎት ማቋረጥ፣ አላስፈላጊ ክፍያን ማስከፈል፣ ኔትወርክ መዘርጋት፣ ዶክመንት ማሸሽ፣ አድርባይነት፣  በተለያዩ ድረ ገጾች ገንቢ ባልሆኑ አላስፈላጊ ሙገሳና ትንኮሳ በኅብረተሰቡ አመለካከት ላይ ጫና በመፍጠር፣ መልካም አስተዳደርን ለማጓደል የሚጥሩ የማኅበራዊ ድረ ገጽ አርበኞችም አይጠፉም፡፡

ማሳያዎቻቸው

ለሕዝብና ለመንግሥት ምንም ጥቅም ሳይሰጡ በልማት ስም ታጥረው  ዓመታትን ያስቆጠሩ ከመሀል አዲስ በአባባ ጀምሮ በአገሪቱ የሚታዩ በርካታ መሬቶች አለመጥቀማቸው ብቻ ሳይሆን፣ ልማታዊ ባለሀብቱ እንዳያለማ የተደረጉበት ሁኔታዎች መፈጠራቸው አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ከዚህ በፊት በግንባታ ግብዓት ዋጋ ንረትና  ሲሚንቶ እጥረት ምክንያት ግንባታዎችን ማፋጠን እንዳልተቻለ ይገለጽ ነበር፡፡ ዛሬ ግን ይህ ሁሉ ችግር ተቀርፎ ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያላቸው ፖሊሲዎችና የማስፈጸሚያ መሣሪያዎች በመንግሥት ተቀርፀው ሥራ ላይ በዋሉበት አጋጣሚ፣ አንዲት ስንዝር መሬት ያለ ልማት ታጥሮ ለዓመታት መቀመጡ ያሳዝናል፡፡ ማን ያላቅቀው? ይህ ብቻም አይደለም፡፡ ሥራ ፋጣሪው ባለሀብት የሚለማ መሬት አጥሮ ተቀምጦ እየጨመረ የመጣውን የሥራ አጥነት ቁጥር እንዴት መቀነስ ይቻላል? ይታሰብበት፡፡

በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት በጥቅማ ጥቅም ፈላጊ ሰዎች ምክንያት የብዙኃኑ ሕዝብ ጥቅም ሲቋረጥ፣ ሲስተጓጎልና ሲጓተት ችግሮቹ በግልጽ እየታዩ ዕርምጃ ያልተወሰደበት ምክንያት እንድ ትልቅ ትልቁ ማሳያ መውሰድ ይቻላል፡፡ በጣም የሚገርመው ጉዳይ ችግሩ እየታየ የችግሩ ፈጣሪ አለመታየቱ ነው፡፡ ስለዚህ ይታሰብበት፡፡

በትምህርት ቤት ክፍያ ዙሪያ በተለይ የግል ትምህርት ቤቶች ጉዳይ አለ፡፡ አንፃራዊ ክፍያ በማያስከፈሉ የትምህርት ተቋማት ላይ የተወሰደ ዕርምጃና የዕርምጃ አወሳሰድ ሒደቱን እንደ አንድ የመልካም አስተዳደር ማሳያ መውሰድ ይቻላል፡፡ የኅብረተሰቡንና የአገሪቱ ገቢ በማያገናዝብ በነፃ ገበያ ስም ብቻ ኅብረተሰቡን የሚያማርሩ ትምህርት ቤቶች አሉ፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ ከተማ ከትምህርት ዋጋ ክፍያ ንረት ጋር ተያይዞ አንዳንድ የሚዲያ ተቋማት በምርመራ ዘገባቸው ያስነበቡዋቸውን አዳጋች አካሄዶች ቃል በቃል ላስነብባችሁ፡፡ የሚከተሉትን ግራ የሚያጋቡ አስተያየቶችን እንይ፡፡

‹‹የተጋነነ ክፍያ የሚጠይቁ የግል ትምህርት ቤቶች ጉዳይ እልባት አልተበጀለትም ያለ የሕግ ባለሙያ 70 ትምህርት ቤቶች ላይ ክስ ተመሥርቷል፤›› ባለሥልጣኑ፣ ‹‹ክስ የተመሠረተባቸው ትምህርት ቤቶች የሉም፤›› የአቤቱታ ምርመራና ክስ አቀራረብ ዳይሬክቶሬት፣ ‹‹‹ዕርምጃው ለምን እንደዘገየ ከባለሥልጣኑ ጋር እመክርበታለሁ፤›› የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ አካላት መልስ በጥቅሉ ይህንን ይመስላል፡፡ አንባቢያን ማንን እንቀበል? ማንን እንስማ?

በገጠር አከባቢ የሚካሄዱ የመሠረተ ልማት ግንባታዎችን በተፈጥሮ ክስተትና በተቋራጭ አማካኝቶ ማጓተትና መንጠባጠብ ይታያል፡፡ ለምሳሌ ተቋራጩና አቋራጩ በሚሰጡት መልስ መለየት በማይቻልበት ደረጃ ላይ  ደርሰናል፡፡ ‹አለት ሆኖብኝ ነው፣ ሙሉ ዓመት ዝናብ ነውና ድንበር የማሰከበር ችግር ነው› የመሳሰሉ ምክንያቶች በማቅረብ ኅብረተሰቡን ያማርራሉ፡፡ ይታሰብበት፡፡

በሠራተኞች ቅጥር ዙሪያም ሲታይ የሥራ ልምድን የሚጠይቁ የሥራ መደቦች እንደተጠበቁ  ሆነው፣ በአንዳንድ ተቋማት የቅጥር ማስታወቂያ ሲወጣ  በዝቅተኛ ደመወዝ ከፍትኛ የሥራ ልምድ በመጠየቅ በቁጥራቸው ትንሽ የማይባሉ ወጣቶች በሥራ አጥነት ወለል ውስጥ እንዲወድቁ ይደረጋል፡፡ በተጨማሪም ተስፋ በመቁረጥ ለሕገወጥ ደላላ ሰለባ በመሆን ከአገራቸው ይሰደዳሉ፡፡ ለአካልና ለሕይወት ሕልፈት ይዳረጋሉ፡፡ የአገር ገጽታን ያበላሻሉ፡፡ ተቋሙም ከተጠያቂነት ለማምለጥ ሲባል የቅጥር ማስታወቂያ ቢያወጣም፣ የሚፈለገው የሰው ኃይል ሳይገኝ ሥራ ፋላጊውም ሥራ ሳያገኝ በጀትና ክፍት የሥራ መደብ ባለበት ሥራ አጥነትን ይነግሳል፡፡ ሲያስፋልጋቸው ደግሞ አንድ ወይም ሁለት እርከን ገባ ብሎ እያከሉበት የሚያወጡም አይጠፉም፡፡ በአንዳንድ መሥሪያ ቤቶች ደግሞ በቅጥር መመርያ ላይ ግልጽነት አለመኖር አልፎ አልፎ ይስተዋላል፡፡ በማስታወቂያቸው ላይ የማይሠራ ስልክ ቁጥር ያስቀምጣሉ፡፡ በግለሰብ ስሜት የሚወሰኑ የፈተና አወጣጥ አሠራር በመከተል ይቀጥራሉ፡፡ ሥራ አጥ ወጣት ያልተቀጠረበትን በጀት  ወደሚፈለግበት ርዕስ በመቀየር የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ይፈጥራሉ የሚል የግል አስተያየት አለኝ፡፡ እናንተስ? የሚመለከተው አካልስ ምን ይላል?  

በዋናነት ደግሞ የኔትወርክ ትስስር ዋሻ በሒደት እየተፈጠረ መምጣቱ ለመልካም አስተዳደር መጓደል ብቻ ሳይሆን፣ የዴሞክራሲያዊ ብሔርተኝነትን መርህ እያስተጓጎለ ይገኛል፡፡ የእነ እከሌ ቤተሰብ ተቋም ከመባሉም ባለይ ተቋሙን የመሸሽ አዝማሚያ የሚያሳዩ በላጉዳዮች አይጠፉም፡፡ በእኔ እምነት ኔትወርኪንግ በሦስት መንገድ የሚፈጠር ይመስለኛል፡፡ አንደኛው በብሔር ደረጃ የሚፈጠረው ሲሆን፣ ሁለተኛው ተመሳሳይ ሆኖ በጎጥ ደረጃ የሚፈጠር ነው፡፡ ሦስተኛው ደግሞ በምንም በማይገናኙ ጥቅምን መሠረት ያደረገ እከክልኝ ልከክልህ የሚባለውን አቀራረብ ማዕከል ያደረገ ኔትወርክ ነው፡፡ ለአብነት ከጎጥ ኔትወርክ ጋር በተያያዘ አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የሚፈልግ ሰው እንደ ነገረኝ፣ ከአዲስ አበባ 100 ኪሎ ሜትር በማይሞላ ርቀት ላይ በአንድ የሥራ ሒደት ውስጥ ከሚገኙት 21 ሠራተኞች መካከል፣ 19 የአንድ መንደር ወይም አካባቢ ተወላጆች ናቸው፡፡ 19 የአንድ አካባቢ እንዴት በአንድ የሥራ ሒደት እንዴት እንደተሰበሰቡ ለምርመራ ጋዜጠኛ ዘገባ እግረ መንገዴን እየጠቆምኩ፣ የሥራ ሒደቱ  በዚህ ምክንያት ‹የአርሰናሎች ኔትወርክ› እስከ መባል ቅፅል ስም እንደ ተሰጣቸው አጫውቶኛል፡፡ በከተማውም ‹የአርሰናሎች ሠፈር› ብሎ ኅብረተሰቡ ሰይሞላቸዋል፡፡ እስካሁንም እንደ ነበረ መቀጠሉን ነው የሚናገረው፡፡

ለዚህ ሁሉ እንደዚህ መሆን ማን ነው መንስዔው? አልገባኝም፡፡ መልሱን ለአንባቢያን እየተወኩ መፍትሔውን በትንሹ በመጥቀስ እቀጥላለሁ፡፡

መፍትሔ

አንድን ተቋም በሁለት የፋይናንስ አሠራር እንዳይተዳደር ማድረግ ዋነኛ መፍትሔ ይሆናል፡፡ በተቋም ደረጃ የመመርያ ማሻሻያና መቀየሪያ ሒደቶች ቢፈተሹ መልካም ነው፡፡ የተቋም አመራር ሲቀየር በሠራተኛው እርካታ መሠረት ቢሆን፣ ሲሻርም በተቋም ሠራተኞች ፊት ቢሆን ይመረጣል፡፡ የሥራ ፈጠራ አቅጣጫ እንደተጠበቀ ሆኖ ሥራ አጥነትን በሚቀንስ መንገድ የቅጥር መመርያና ሕጎች ቢፈተሹ መልካም ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ልምድ በማይጠይቁ ሥራዎች ላይ ሊሠሩ የሚችሉ ወጣቶችን ሥራ አጥ ስለሚያደርግ፡፡ በሕዝቡ ላይ መልካም አስተዳደርን ያጓደሉ አካላት ተጠያቂ የሚያደርግ ሥርዓት ቢኖርም፣ እስከ ዛሬ ተጠያቂ የሆኑ አካላት አለመኖራቸው የመልካም አስተዳደር ጉዳይን መድኃኒት የለመደ በሽታ አድርጎታል፡፡ 

ስለዚህ ተተኪው አካል የሚማርበት ተመጣጣኝ ዕርምጃ በኔትወርክ በተሳሰሩ ጥቂት ግለሰቦች ላይ መውሰድ ይገባል፡፡ በልማት ስም ለዘመናት ታጥረው የቆዩ በአዲሰ አበባና በክልል ከተሞች የሚገኙ መሬቶች በአፋጠኝ በልማታዊ ባለሀብት እጅ እንዲገቡ ማድረግ፣ የተጋነነ ክፍያን በማስከፋል ኅብረተሰቡን በሚያማርሩ በማንኛቸውም የትምህርት ተቋም ላይ አስተማሪና ተመጣጠኝ ዕርምጃ መወሰድ ያስፈልጋል፡፡ ትምህርት ተቋማትም በነፃ ገበያ ስም የፈለጉትን ማስካፍል የሚያስቀር ወጥ የአከፋፈል ሥርዓት ሊበጅለት ይገባል፡፡ በመጨረሻም ኅብረተሰቡ የመልካም አሰተዳደር ጉድለቶችን ከሚዲያ ተቋማት ጋር በመሆን የሚያጋልጥበት አሠራር ሊፈጠር ይገባል፡፡ ሚዲያም ጥቆማ እስኪደርሰው ድረስ ከመጠበቅ ኅብረተሰቡ ዘንድ ወርዶ መጠየቅ፣ መከላከልና ማጋለጥ አለበት፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው kedirgemechu43@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

Standard (Image)

አስተዳደሩ ለባለሥልጣናቱ የሰጠውን መኪናና መኖሪያ ቤት ግለሰቦች ርስት ሲያደርጉ ለምን ዝም አለ?

$
0
0

በምንተስኖት ጎበና

ክቡር ከንቲባ ይህችን መልዕክት በጥሞና አንብበው ተገቢውን የእርምት ዕርምጃ ይወስዳሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ምክንያቱም ካለብዎት ኃላፊነት የተነሳ እያንዳንዱን ቀዳዳ ለማየት ፍላጐት ቢኖርዎትም፣ ጊዜ አይኖርዎትምና ያለውን ሐቅ እንዲያውቁ ነው፡፡ በሕዝብ ሀብት ላይ ያለአግባብ እየደረሰ ላለው ጥፋት አፋጣኝ ምላሽ እንደሚሰጡ ተስፋ አለኝ፡፡

ክቡር ከንቲባ አዲስ አበባ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ያሉባት ከተማ ነች የሚለው ያስማማናል፡፡ ይህንንም ታሳቢ በማድረግ እርስዎ የሚመሩት የከተማው አስተዳደር በተለይም ጎልተው በሚታዩ ችግሮ ላይ አትኩሮ እየሠራ ነው የሚገኘው፡፡ ከከተማዋ ዋና ዋና ችግሮች መካከል ትልቁ ለነዋሪዎቹ ምቹ ያለመሆን እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ለዚህም ነው አስተዳደሩ ለነዋሪዎቹ ምቹና ተመራጭ ከተማ አደርጋታለሁ የሚል ራዕይ የሰነቀው፡፡ ቢሆንም ብዙዎች ይህንን የከተማውን አስተዳደር አባባል ከመፈክርና ከምኞት ያለፈ አይደለም ሲሉ ያምናሉ፡፡ ለዚህ ጥርጣሬና እምነት ማጣት ምክንያቱ ምንድነው ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ በእርግጥ በርካታ ምክንያቶች እንዳሉ ቢታወቅም አንዱና ዋናው የተጠያቂነት ማነስ ነው፡፡ በሕዝብ ግብር የተገዛ መኪናና የተገነባ መኖሪያ ቤት ለግለሰቦችና ለጉበኞች ሲሳይ ሲሆን የከተማው አስተዳደር ማስቆም አልቻለም፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ዓይኑ ሥር የሚፈጸሙ በደሎችንና አድሎአዊ አሠራሮችን አይቶ እንዳላየ አልፏል፡፡ በተለይ የሕዝብ ቁጥር እየጨመረ ፍላጎት እያደገ ሲሄድ አዲስ አበባ አድሎአዊ አሠራር እየተስፋፋና የጉቦ የሥርዓቱ መገለጫ የሆነባት ከተማ ሆናለች፡፡ ፍትሕ እየራቃትና ተጠያቂነት ቀርቷል የተባለ ይመስል፣ አጥፊዎች ስለማይጠቁ የከተማዋ ነዋሪዎች ችግሮች ተዘርዝሮ የማያልቅባት ከተማ በመሆኗ፣ በየቦታው የሚሰማው ሮሮ እየተበራከተ ይገኛል፡፡

የአዲስ አበባ አስተዳደር በኃላፊነት ለሚመደቡ ሰዎች ቤት የሚሰጠው ሕጋዊ አሠራርን ተከትሎ ሳይሆን ለሚፈልገው ነው፡፡ ይህ ለምን ይሆናል ብሎ ጠይቆ ምላሽ ማግኘት ይቸግራል፡፡ የከተማው አስተዳደር የሚቆጣጠረውና የሚያዘው ሀብት እያንዳንዱ የከተማው ነዋሪ ከሚከፍለው ግብር የሚገኝ ነው፡፡ ሕዝብ ግብር የሚከፍለው መንግሥትን ኃላፊነቱን እንዲወጣ፣ ፀጥታ እንዲከበር፣ ልማቱ እንዲፋጠን፣ አገሪቱ የምትመኘውን የከፍታ ማማ ወጥታ ለማየት ነው፡፡ እየሆነ ያለው ግን በተቃራኒው ነው፡፡ ፍትሕ አጣን፣ ዲሞክራሲው በጉቦና በአድሎአዊ አሠራር ተጠላልፏል የሚሉ ጩኸቶች ሰሚ እያገኙ አይደለም፡፡ ወጥ አሠራር የለም፡፡ ባለፈው ሳምንት የከተማው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ የከተማው አስተዳደር ዕርምጃ እየወሰደ ያለው ታች በወረዳ ደረጃ ባሉ ትናንሽ አመራር ላይ ብቻ ነው፤ ትልልቆቹ ሲያጠፉ ዝም ይባላሉ፤ ይህ ለምን ሆነ? ብሎ የሕዝብ ተወካይ ሲጠይቅ ለዚህ በቂ ምላሽ ሳይሰጠው መታለፉ ክፍተቱን ያሳያል፡፡

ምክንያቱም ከላይ ያለው አመራር ትኩረት በታችኛው ላይ እንጂ አጠገቡ ያለውን መንካት ስለማይፈልግ፣ እንጠቃቀም መርህ ስለሚከተል ነው፡፡ የአዲስ አበባ አስተዳደር እስከ ዛሬ ድረስ አንድም ባለሥልጣን በሥልጣን ብልግና ጥፋት ከሥልጣን አውርዶ፣ በሕዝብና በከተማው ላይ ላደረሰው ጉዳት ፍርድ ቤት ከሶ ያቀረበበት ጊዜ የለም፡፡ ምንም ጥፋት የለም ማለት ሥራ አልነበረም ማለት ነው፡፡ የሚሠራ ሰው ያጠፋል፣ ይሳሳታል፡፡ ግን በጥፋቱ የተጠየቀ የለም፡፡ የሚያጠፉት ጥፋት የማያስከስስ ሆኖ አይደለም፡፡ ተጠያቂነት በመላላቱና ፍትሕ በመዛባቱ፣ ሕገወጥነት በመንገሡ ነው፡፡

የከተማው አስተዳደር የሚመድባቸው ግለሰቦች የከተማው ነዋሪ በሚከፍለው ግብር የተገዛን መኪናና የተገነባ መኖሪያ ቤት ከታለመለት የመንግሥት ሥራ ውጪ በግለሰቦች ላልተገባ ጥቅም ሲውል ዝም ብሎ ያያል፡፡ በዚህም ከሕዝብ የተሰጠውን ኃላፊነቱን በተገቢው መንገድ እየተወጣ አይደለም፡፡ በመንግሥት አሠራር ለአንድ በኃላፊነት ሥራ ለሚመደብ ሰው የሚቀርቡ እንደ መኖሪያ ቤትና መኪና ያሉ ሥራውን በአግባቡ እንዲወጣ የሚረዱ ናቸው፡፡ ይህ በክልልም፣ በፌዴራል ደረጃም ይሠራል፡፡ ለምሳሌ መንግሥት አንድን የሥራ ኃላፊ ሲሾም ከኤጀንሲ ሥራ አስኪያጅ እስከ ሚኒስትር ላሉ የመኖሪያ ቤት ቪላ ወይም አፓርታማ፣ የኃላፊነት ደረጃውን የሚመጥን በትንሹ እስከ ሦስት የመኝታ ክፍሎች ያሉትና ለሥራ የሚጠቀመው መኪና፣ እንደ አስፈላጊነቱ ደኅንነት ጠባቂ ይመደብለታል፡፡

በቢሮ አካባቢ ደግሞ ከረዳት ጀምሮ የተሟላ የቢሮ ግብዓት እንዲኖር ይደረግለታል፡፡ በየጊዜው ኃላፊነቱን እንዲወጣ የሚያግዙ የውጭ ጉዞ እንዲያደርግና አዳዲስ አሠራሮችን እያቀረበ ሕዝብን በኃላፊነት እንዲያገለግል ይፈቅድለታል፡፡ እነዚህ ሁሉ የመንግሥት ሥራ በኃላፊነትና በተጠያቂነት እንዲወጣ ለማድረግ የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ ከዚህ ውጪ የግለሰቡን የግል ምቾቱን ለመጠበቅ የሚያደርጉት አይደለም፡፡

ምቾትና ጥቅማ ጥቅሞች በኃላፊነት ለሚመደብ ሰው የሚቀርብበት ምክንያት አለ፡፡ የሕዝብን ኃላፊነት በብቃት እንዲወጣ ነው፡፡ የሕዝብ አገልጋይ ስለሆነ ነው፡፡ ምቾቱ የሚጠበቅለት ከሕዝብ በተሰበሰበ ግብር ነው፡፡ ስለዚህ በአግባቡ ለታለመለት ዓላማ ማዋል አለበት፡፡ ከዚህ ውጪ በሕዝብ ሀብት ላይ የሚኖር አሠራር ሕዝብን መበደል ነው፡፡ ምክንያቱም ለራሱ በእግር እየሄደና በታክሲ እየተጋፋ እንደዚሁም ጾሙን እየዋለና እያደረ፣ ነጭ ላቡን አፍስሶ ካገኘው ገቢ መንግሥት ኃላፊነቱን በአግባቡ እንዲወጣ የከፈለው ግብር ባከነ ማለት ነው፡፡ ግብር ከፋዩ እየተራበ፣ እየተጠማ፣ አገልግለኝ ብሎ ኃላፊነት የሰጠው የመንግሥት ሰው እንደፈለገ እንዲሆን አደረገ ማለት ነው፡፡

ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነው በቅርቡ በከተማችን መነጋገሪያ የሆነው በሕዝብ ገንዘብ የተገነባ ኮንዶሚኒየም 98 ሕንፃዎች ከነሕይወታቸው መጥፋት ጋር ተያይዞ የተጠያቂነት ክፍተትና ግልጽነት መጓደል ጣሪያ ነካ እየተባለ ስለሆነ የማውቀውን ሐቅ በዜግነቴ ለመግለጽ ነው፡፡ ከዚህ ሌላ በከተማው ውስጥ ያለውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከሚደረገው ጥረት ባሻገር፣ የሕዝብ ሀብት ላይ እየተፈጸመ ያለን ብክነት ሁላችን ስለሚያሳስበን ጭምር ነው፡፡ እኔና መሰሎቼ በየቀኑ አከራይ ዋጋው በሚጨምር የግለሰብ ቤት ተከራይተን እየኖርን በምንከፍለው ግብር የተሠራ ኮንዶሚኒየም ለጥቂቶች መንደላቀቂያ በመሆኑ የሕዝብ ሀብት ለምን ይባክናል የሚል ቁጭት አለን፡፡ ተጠያቂነት እንዲሰፍንና ፍትሐዊ አሠራር ለማየት እንፈልጋለን፡፡

የአዲስ አበባ አስተዳደር በከተማው በቢሮ ደረጃ ለሚሾማቸው የሥራ ኃላፊዎች ደረጃውን የሚመጥን የመኖሪያ ቤትና ለሥራ የሚጠቀሙበትን መኪና ያቀርባል፡፡ የመኖሪያ ቤትና የመኪና አቅርቦት ተሿሚዎች ተረጋግተው ሥራቸውን እንዲወጡ ትኩረታቸውን በሥራ ላይ እንዲያውሉ ጊዜአቸውንና ጉልበታቸውን ለሕዝብ ጥቅም በሚሰጥ መልኩ እንዲሆን ለማድረግ ነው እንጂ፣ የተለየ ምቾት ስለሚያስፈልጋቸው ወይም ልዩ እንክብካቤ ስለሚገባቸው አይደለም፡፡

ሕዝብን ለማገልገል ከተሰጣቸው ኃላፊነት ሲነሱ በእነሱ ምትክ የሚሾም ኃላፊ በተመሳሳይ መልኩ ኃላፊነቱንና ግዴታውን እንዲወጣ ለሥራው የሚያስፈልጉ ሁሉ ይሟላሉ፡፡ ይህ በዓለም ላይ የተለመደ አሠራር ነው፡፡ ለምሳሌ በአሜሪካ በየአራት ዓመቱ በሚደረግ ምርጫ አሸናፊ ፓርቲ ሁለት መቶ ሺሕ ባለሙያዎችን ይዞ ወደ ታላቁ ቤተ መንግሥት ያመራል፡፡ የሥልጣን ዘመኑን ጨርሶ በምርጫ ሲሸነፍና አሸናፊ ፓርቲ ሲመጣ፣ እነዚያ ሁለት መቶ ሺሕ ሰዎች ጨርቄን ማቄን ሳይሉ ሁሉንም ነገር ለተተኪያቸው አስረክበው ይሄዳሉ፡፡

በዚህም ረገድ በአዲስ አበባና በፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች ያለው አሠራር ለየቅል ነው፡፡ የፌዴራል መንግሥት ተሿሚዎች ከኃላፊነት ሲነሱ ወደ ሌላ ሥራ ምድብ ያዞራቸዋል፡፡ ነገር ግን የያዙትን ቤት ይዘው ይቀጥሉ መኪናውም በእጅዎ ይሁን አይልም፡፡ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነን የቀድሞ የፍትሕ ሚኒስትር የነበሩት የደሕዴን ሰው ከኃላፊነት ሲነሱ የሚኖሩበትን መኖሪያ ቤት ለኪራይ ቤቶች፣ መኪኖችን ለመኖሪያ ቤቱ ንብረት አስተዳደር በነፋስ ፍጥነት አስረክበው ወጥተዋል፡፡ የቀድሞ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ክቡር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በተመሳሳይ መልኩ የመንግሥት ኃላፊነትን ሲለቁ ሁሉንም ነገር መልሰዋል፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ባለቤትም ቢሆኑ በጭቅጭቅ ቤተ መንግሥትን ለቀው ለመውጣት ተገደዋል፡፡ በአጠቃላይ ለመንግሥት ሥራ የሚፈቀድ መኖሪያ ቤትና መኪና ርስት አይደለም፡፡ ማንም ሰው እንደፈለገው የሚጠቀመው የሕዝብ ሀብት አይደለም፡፡ ለታለመለት ዓላማ በአግባቡ መዋል አለበት፡፡ በፌዴራል ደረጃ ያለው ይህንን አሠራር በግልጽ ያሳያል፡፡

በአዲስ አበባ አስተዳደር በሥራ ምድብ ምክንያት የሚሰጥ መኖሪያ ቤትና መኪና እንደ ግለሰብ ርስት እየተቆጠረ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ሰዎች እንደ ምንም ብለው በኃላፊነት ደረጃ ተመድበው የመኖሪያ ቤት ካገኙና መኪና ከተሰጣቸው በኋላ ከተመደቡበት የሥራ ኃላፊነት ሰበብ ፈጥረው ይነሳሉ፡፡ ግዴታ ስለሚሆንባቸው የመንግሥትን መኪና ይመልሱና መኖሪያ ቤቱን የግል ርስት ያደርጉታል፡፡

የሚገርመው ነገር ከኃላፊነት ሲነሱ የመንግሥት ቤት አለመመለሳቸው ብቻ አይደለም፡፡ ቀደም ሲል ለመኖሪያ ቤትና ለመኪና ያበቃቸውን መሥሪያ ቤት ለቀው ሲሄዱም የከተማው አስተዳደር ተከታትሎ የመንግሥትን ቤት አያስመልስም፡፡ በዚህ የተነሳ የመንግሥት መኖሪያ ቤቱን የግል ያደርጉታል፡፡

አስተዳደሩ በዚህ ጥፋቱ ከፍተኛ ደረጃ ተጠያቂ መሆን ነበረበት፣ አለበትም፡፡ ምክንያቱም ግለሰቦች የመንግሥትን ቤት እንደ ርስት ሲቆጥሩ እያየ ዝም ማለቱ አግባብ አይደለምና፡፡ በዚህ የተነሳ በርካታ ሰዎች ዛሬ በመንግሥት ኃላፊነት ላይ ሆነው የተረከቡትን ቤት ከኃላፊነት ተነስተውም ሳይለቁ ይዘው ይቀጥላሉ፡፡ በሌላ በኩል አዲስ የሚመደቡ ኃላፊዎች ቤት አጥተው ይንከራተታሉ፡፡ ይህ የከተማው አስተዳደር እንዝላልነት አንዳንዶችን ሁለትና ሦስት የመንግሥት ቤቶች ባለቤት አድርጓቸዋል፡፡ በዚህም ብዙዎች በአጋጣሚ ያገኙትን በቁጥጥራቸው ሥር አድርገው ይገኛሉ፡፡ መልሱ ሲባሉ በመንግሥት ኃላፊነት ላይ እያለሁ የተሰጠኝ ነው አልመልስም ይላሉ፡፡ ይህንን የሚጠይቅ የለም፣ አስተዳደሩ ችላ ብሏል፡፡ እያንዳንዱ ዜጋ በሚከፍለው ግብር ጥቂት ሰዎች እንደፈለጉ እየሆኑ ነውና የአስተዳደሩ ባለሥልጣናት ይጠይቁልን፡፡

በአዲስ አበባ አስተዳደር የቢሮ አስተባባሪ ሆነው የሚሠሩ አንድ ሰው ባለሦስት ክፍል መኖሪያ ቤትና በወር 200 ሊትር መኪና ከነሾፌሩ ተሰጣቸው፡፡ ቤቱን እጃቸው መግባቱን እንዳረጋገጡ ከቦርዱ ጋር ጭቅጭቅ በመፍጠር ሥራ እየበደሉ ሲያስቸግሩ ብዙ ከታገሳቸው በኋላ ቦርዱ አሰናበታቸው፡፡ ከዚያም ለሥራ የተሰጣቸውን መኪና አስረከቡ፣ ባለሦስት ክፍል ቤቱ ግን ርስታቸው እንደሆነ አለ፡፡ የሚገርመው እኚህ ግለሰብ ዛሬ የአዲስ አበባ ሃይማኖት ተቋማትን ሥራ ለቀው በሌላ መሥሪያ ቤት ተቀጥረው እየሠሩ ነው፡፡ መሥሪያ ቤቱን ሙሉ ለሙሉ ለቀው ወደ ሌላ መሥሪያ ቤት ቢሄዱም፣ መኖሪያ ቤቱን እንደ ርስት ቆጥረውት ወደ ግላቸው ሲያዛውሩ አንድም ጠያቂ የለም፡፡ ዝም ብሏቸዋል፡፡ እኚህን ግለሰብ ለአብነት አነሳን እንጂ በዚህ መልኩ ብዙ የሕዝብ ሀብት በየቦታው እየባከነ ነው፡፡ የመንግሥት ያለህ ያሰኛል፡፡ ለመሆኑ ለሥራ የተሰጠ መኖሪያ ቤት ርስት ይሁን የሚል ደንብ አዲስ አበባ አስተዳደር አውጥቶ ይሆን?

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡ 

 

Standard (Image)

አፋጣኝ ትኩረት የሚሻው የፀረ ተባይ ኬሚካል ቁጥጥርና አስተዳደር ሥርዓት

$
0
0

ከአገሬ አወቀ

አንድ ወቅት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቀረበው ሪፖርት ከኢትዮጵያ ወደ ጃፓን አገር የተላከ ቡና ውስጥ የፀረ ተባይ የኬሚካል ዝቃጭ (Pesticide Residue) በመገኘቱ ምክንያት ተመላሽ ስለመደረጉና እስራኤልም ከኢትዮጵያ የሚላከው ሰሊጥ በውስጡ ያለው የፀረ ተባይ የኬሚካል ዝቃጭ መጠን ከፍተኛ ነው በሚል ላለመግዛት መወሰኗ ይታወቃል፡፡ ሩሲያና ሞሮኮ በፊናቸው የተላከ ሰሊጥ ይሁን ሌላ ምርት በውስጡ የማይፈለግ የፀረ ተባይ ኬሚካል ዝቃጭ ተገኝቷል በሚል ተመላሽ እንዳደረጉ ከባለሥልጣናት ሪፖርት ተደምጧል፡፡

በእርግጥ እነዚህ የየአገሮቹን የጥራት ደረጃን ባለማሟላታቸው ከውጭ ተመላሽ የተደረጉት (ቡናና ሰሊጡ) ከዛ በኋላ የት እንደደረሱ አላውቅም!!!፡፡

በቅርቡ ደግሞ በኦሮምያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ዝዋይ ከተማ ፋብሪካውን የተከለው አንድ ድርጅት፡-

  1. የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈበት ዳይሜቶይት የተባለ የፀረ ተባይ ማምረቻ ጥሬ ዕቃ በመጠቀም 48,000 ሊትር ዳይሜቶይት የፀረ ተባይ ኬሚካል ምርት አምርቶ መሸጡን፤
  2. በአክሲዮን ማኅበሩ ተመርቶ ግን ሳይሸጥ በመጋዘን ውስጥ እያለ የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈበት ከ13,000 ኪሎ ግራም በላይ ማንኮዜብ የተባለው የፀረ ዋግ ኬሚካል ምርት ስለመሸጡ፤
  3. በህንድ አገር 14,000 ሊትር ምርት ጥቅም ላይ ውሎ 4,000 ያህል ሰዎች ላይ ጉዳት እንዳደረሰና ወደ 730 ያህል ሰዎችን ለህልፈት የዳረገ፤ በባንግላዲሽ እንዲሁ ከአሠርት ዓመታት በፊት ጥቅም ላይ ውሎ ከፍተኛ ጉዳትና እስከ ዛሬ የዘለቀ ፀፀት ጥሎ እንዳለፈ የተነገረለትና ኢንዶሰልፋን የተባለ ፀረ ተባይ ምርት ለማምረት የሚውል ከ90,000 ኪሎ ግራም በላይ የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈበት ጥሬ ዕቃ ገዝቶ በአገራችን የሕግ አግባብ ሥልጣን ከተሰጠው የእርሻና የተፈጥሮ ሀብት ሚኒስቴር ዕውቅና ውጪ ጉምሩክን እንዲያልፍ በማድረግ ወደ አገር ውስጥ እንዳስገባ፤
  4. ከፍ ሲል የተጠቀሱት የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈበት የፀረ ተባይ ጥሬ ዕቃና የፀረ ተባይ ምርት ከአክሲዮን ማኅበሩ እንዲወገድ ሲታገል የነበረውና የተፈጸመውን ድርጊት ያጋለጠው፤ የአክሲዮን ማኅበሩ የጥራት ማረጋገጫ ባለሙያ፤ በዚህ የመንግሥት ልማት ድርጅት ውስጥ የታየውንና አካባቢን ብሎም የሕዝብን ጤና ለከፍተኛ አደጋ የማጋለጥ አቅም ያለውን ምግባረ ብልሹና ኃላፊነት የጎደለው አሠራር ያጋለጠው ባለሙያ ከድርጅቱ ስለመባረሩ፤

ፋና ብሮድካስት ኮርፖሬት ሬዲዮ በተከታታይ ባሠራጫቸው ዜናዎች ተደምጧል፡፡

አበው ሲተርቱ ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ እንዲሉ ይህ ባለሙያ አካባቢንና ሕዝብን ሊመጣ ከሚችል አደጋ በመታደጉ ሊሾምና ሊሸለም ሲገባ በተቃራኒው መንግሥት በአንድ በኩል አረንጓዴ ልማትን ዕውን ለማድረግና በሌላ ወገን ደግሞ ይህን መሰል የመልካም አሰተዳደር ችግር የህልውና ጉዳይ ነው በማለት ባወጀበት ማግሥት እንዲህ ያለ ለሕግም ለሞራልም ተቃራኒ የሆነ ተግባር ሲፈፀም መመልከታችን የመንግሥትን አዋጅ ዘመቻ መሰል ግንጥል ጌጥ አድርጎታል፡፡

በተመሳሳይ የፌደራል ኦዲት መሥሪያ ቤት በቅርቡ የዘጠኝ ወር የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበበት ወቅት አስደንጋጭ ጉዳይ በማለት የግብርና ግብዓት አቅራቢ ድርጅት የተባለው ሌላው የመንግሥት የልማት ድርጅት የተለያዩ ፀረ ተባይ ኬሚካሎች የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ካለፈ ከሁለትና ሦስት ወራት በኋላ ለተጠቃሚው ኅብረተሰብ እየሸጠ እንደነበረ አጋልጧል፡፡

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ክስተቶች አገራችን በፀረ ተባይ ቁጥጥር ረገድ ያለችበትን የከፋ ሁኔታ በቁንፅል ለማሳየት የቀረቡ ማሳያዎች እንጂ የችግሩን ስፋት በሙላት ለመተንተን አይደለም፡፡ የቀረቡት ማሳያዎች በአገራችን ውስጥ በርካታ የፀረ ተባይ ኬሚካል አስመጪ ድርጅቶች ከመኖራቸውና ከደካማ የቁጥጥር ሥርዓቱ አንፃር ሲታሰብ ምናልባት ከዚህም የከፋ ኃላፊነት በጎደለው/በጎደላቸው አስመጪ/አስመጪዎች እስካሁን ላለመፈጸሙና አሁንም እየተፈጸመ ላለመሆኑ ምንም ዋስትና የለንም፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ ሊነሳ የሚችለው ብርቱ ጥያቄ በእውነት እዚህ አገር የፀረ ተባይ ኬሚካል ቁጥጥርና አስተዳደር ሥርዓት አለ ወይ የሚል ይሆናል፡፡ እኔ እስኪገባኝ ድረስ ለጥያቄው ያለን መልስ አሉታዊ ነው፡፡ እንዲያው ለምናልባቱ የፀረ ተባይ ኬሚካል ቁጥጥርና አስተዳደር ሥርዓት አለ ከተባለ ደግሞ የፀረ ተባይ ኬሚካል ቁጥጥርና አስተዳደር ሥርዓት ባለቤት ማነው? ባለቤቱስ በባለሙያ ተደራጅቷል? ብቃት ባለው ሁኔታ እየተመራ ነው ወይ? የሚል ጥያቄ ማስነሳቱ አይቀርም፡፡ ምክንያቱም ሥርዓትና የሥርዓቱ አስተዳዳሪ የሆነ አካል ባለበት አገር እንዲህ ያለ ሥር የሰደደ ችግር ሊፈጠር አይችልምና!!!፡፡

መንግሥት በአገሪቷ የአረንጓዴ ልማት ፖሊሲ በመቅረፅና ተግባራዊ እንዲሆን በማድረጉ ምክንያት ሁሉም የዘላቂ ልማት ሥራዎች በአንፃሩ እንዲተገበሩ ማድረግን ይጠይቃል፡፡ አረንጓዴ ልማት ፖሊሲ መከተል ያስፈለገበት ዋናው ዓላማ በአገሪቷ የሚከናወኑ ማናቸውም የልማት ሥራዎች ዘላቂነት ባለው ሁኔታ ለሰው ልጅና ለተፈጥሮ አካባቢ ተስማሚ እንዲሆኑ ለማስቻል ነው፡፡ በአገሪቷ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች የተፈጥሮ አካባቢን የማይበክሉና ጪስ አልባ እንዲሆኑ ማስቻል ብቻውን አረንጓዴ ልማቱ ሙሉ እንዲሆን አያደርግም፡፡ የዘርፉ ምሁራን የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ አስፈላጊነት ሲተነትኑ የምንኖርባት ምድር የተፈጥሮ ሚዛን እንዳይዛባ፣ ለሰው ልጆች ምቹ እንድትሆን፣ ለጤና ተስማሚ የሆነ ምርት ማምረት፣ ተስማሚ የሆነ አየርና አካባቢ እንዲኖር ማድረግ ከብዙ በጥቂቱ ሊጠቀሱ የሚችሉ ዓላማዎች መሆናቸውን ያስረዳሉ፡፡

የዚህ ጽሑፍ ዋናው ዓላማ ስለ አረንጓዴ ልማት ትንተና ለመስጠት ሳይሆን በመጀመሪያ እርሻችን አረንጓዴ ነውን? የሚል ጥያቄ በፖሊሲ አውጪዎችና ያገባኛል በሚሉ ሁሉም ባለድርሻዎች መካከል እንዲነሳ ለማድረግና እርሻችን አረንጓዴ እንዲሆንና የአረንጓዴ ልማት ፖሊሲ መርሕን የተከተለ እንዲሆን የበኩሌን አስተያየት እንደዜጋ ለመስጠት ነው፡፡

እንደ ዓለም አቀፉ የምግብና እርሻ ድርጅት /FAO/ ጥናት መሠረት አብዛኛው የአገራችን የግብርና ሥነ ምኅዳር (አግሮ ኢኮሎጂካል ዞን) በእርሻ ላይ ለሚከሰቱት ለተለያዩ ተባዮች ምቹ በመሆኑ ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በማቅረብ ብቻ ያለ ፀረ ተባይ ኬሚካል በቂ ምርት ማግኘትም ሆነ በምግብ ራስን ለመቻል አዳጋች ነው፡፡ በመሆኑም የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተለያዩ እርሻ ላይ ለሚከሰቱት ተባዮች፣ ዋጎችና በሽታዎች መቆጣጠሪያነት የተለያዩ ኬሚካሎችን መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን ያመላክታል፡፡

በአሁኑ ጊዜ አብዛኛው ትርፍ ምርት አምራች በሆነው የአገሪቱ አካባቢ ያሉት አርሶ አደሮች የተለያዩ ኬሚካሎች አስፈላጊነት በመገንዘብ በአግባቡ ባይሆንም ጥቅም ላይ እያዋሉት ነው፡፡ በእርግጥ እዚህ ላይ ምን ዓይነት ኬሚካሎች ናቸው ለተጠቃሚው እየቀረቡ ያሉት? ማነው በአብዛኛው የፀረ ተባይ ኬሚካል ንግድ፣ ሽያጭና ችርቻሮ ሥራ ላይ ተሰማርቶ ያለው? በማንና በምን አግባብ ነው የፀረ ተባይ ኬሚካሎች ጥቅም ላይ እየዋሉ ያሉት? ምን ዓይነት የፀረ ተባይ ኬሚካል ቁጥጥር፣ አስተዳደርና ክትትል ሥርዓት አለ? የሚሉት ጥያቄዎች ወቅታዊ ምላሽ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ውጭ አገር ሄደው ተመላሽ የተደረጉ የግብርና ምርቶቻችን በምናይበት ጊዜ፤ ዓብይ ሊባሉ የሚችሉ ችግሮችን ስንፈትሽ፤

  1. የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈበት፣
  2. የተከለከለ ወይም፣
  3. ጥቅም ላይ የዋለው ፀረ ተባይ ዝቃጭ በምርቱ ውስጥ ከተፈቀደው መጠን በላይ ተከማችቶ መገኘቱ በዋነኛነት ተጠቃሽ ናቸው፡፡

ይህም በአሁኑ ጊዜ በአገሪቱ ውስጥ ጥራቱን ያልጠበቀ ኬሚካል ጥቅም ላይ እየዋለ ስለመሆኑ ወይም ኬሚካል ጥራት በጎደለው ሁኔታ ጥቅም ላይ እየዋለ እንደሆነ ወይም ሁለቱንም ባላሟላ አኳኋን ኬሚካል ጥቅም ላይ እየዋለ ስለመሆኑ ማሳያ ናቸው፡፡ ውጭ ሄደው ተመላሽ የተደረጉትን ትተን እዚህ አገር ውስጥ በየቀኑ ገበያ እየቀረቡ ያሉት የግብርና ውጤቶች ከዚህ ዓይነት ችግር ነፃ ስለመሆናቸው እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ በአገራችን በየቀኑ ገበያ ላይ የሚቀርቡ የግብርና ውጤቶች ምን ዓይነት ፀረ ተባይ መድኃኒትና ምን ያህል የፀረ ተባይ ዝቃጭ እንደያዙ ማወቂያ መንገድ ሥራ ላይ ባለመኖሩ እንጂ ወደ ውጭ ከተላከው የከፋ እንደሆነ ማን ያውቃል? ዓለም የደረሰችበት ወቅታዊ የሳይንስ ሃቅ እንደሚያረጋግጠው ማንኛውም ፀረ ተባይ ኬሚካል በአግባቡ ጥቅም ላይ ካልዋለ ውሎ ሲያድር ከፍተኛ የሆነ የኅብረተሰብ የጤና ቀውስ ወይም ችግርና የተፈጥሮ አካባቢ ብክለትን ያስከትላል፡፡ ለዚህም ነው አገሮች የተቀናጀ የተባይ መቆጣጠርያ ሥርዓት በመዘርጋት ከፍተኛ ቁጥጥርና ክትትል የሚያደርጉት፡፡

ስለዚህ በአገራችን ግብርና የአረንጓዴ ልማት ፖሊሲን የተከተለ ሆኖ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ የተባይ መቆጣጠርያ ሥርዓት (Integrated Pest Management) የመዘርጋት ሥራ አስፈላጊነት እንዳለ ሆኖ፣ ሊያስከትሉ የሚችሉትን የጎን ጉዳት በመቆጣጠርና በመቀነስ የፀረ ተባይ ኬሚካሎችን ጥቅም ላይ ማዋል የሚያስችል ሥርዓትን መዘርጋት የሚያጠያይቅ አይደለም፡፡ ለዚህም ፀረ ተባይ ኬሚካሎችን በተመለከተ የግብይት ሰንሰለቱን ትኩረት ሰጥቶ በመመርመርና በተገቢው ለማደራጀት፤

  1. ትክክለኛና ጥራቱን የጠበቀ ኬሚካል ወደ አገር ውስጥ ስለመግባቱ ጥብቅ ቁጥጥር ማድረግ፤
  2. የአገር ውስጥ ፀረ ተባይ አምራቾችም ቢሆኑ ትክክለኛና ጥራቱን የጠበቀ ኬሚካል አምርቶ ወደ ገበያ ስለማውጣታቸው መቆጣጠርና ማረጋገጥ፤
  3. በተለይም ፀረ ተባይ ኬሚካሎች ዕውቀቱ ባላቸው ባለሙያዎች ብቻ እንዲነገዱና እንዲሸጡ ማድረግ፤
  4. በእርሻ ላይ ለሚከሰተው ተባይ ወይም በሽታ ጥራቱን የጠበቀና ትክክለኛው ኬሚካል በትክክለኛው መጠን በአሠራር ደንብ መሠረት በባለሙያ የተደገፈ ርጭት መፈጸም፤
  5. ኬሚካል የተረጨበት የግብርና ምርት ለምግብነት ከመዋሉ በፊት ወይም ገበያ ከመውጣቱ በፊት ከሰው ንኪኪ ነፃ ሆኖ መቆየቱን መቆጣጠርና፤
  6. ወደ ገበያ የሚቀርበው የግብርና ምርቶች በተለይም አትክልትና ፍራፍሬ፣ የቅባት እህሎች፣ ጥራጥሬ እህሎች፣ ቡና፣ ጫትና የመሳሰሉት በውስጣቸው ያለው የፀረ ተባይ ዝቃጭ መጠን መለካትና በጤናና በአካባቢ ላይ ጉዳት የማያስከትል መሆኑን በመቆጣጠር መሥፈርቱን የማያሟሉ የእርሻ ምርቶችን ማስወገድ የሚቻልበት ግልጽና ተጠያቂነት ያለው አሠራር ተግባራዊ ማድረግ ለነገ የማይባል ጉዳይ ነው፡፡

በመጨረሻም በአገራችን ወጥ፤ ከሌሎች የሕዝብና አካባቢ ጤና ከሚመለከቱ ሕጎችና ፖሊሲዎች ጋር የሚስማማ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ያረጋገጠ በተለይም ሕዝብን ሁለንተናዊ ተሳትፎ ያማከለ የሕዝብና አካባቢ ጤና በመጠበቅና በመንከባከብ ዋና ዓላማ ሥር ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት የፀረ ተባይ ቁጥጥርና አስተዳደር ሥርዓት መቋቋም በተለይም የቁጥጥርና አስተዳደር ሥርዓቱን ውጤታማነት ለማረጋገጥ የተሟላ የፍተሻ ሥራ የሚከናወንበት ላቦራቶሪ እውን ማድረግ ከፖለቲካ ተፅዕኖ የፀዳ በዘርፉ ዕውቀት ባላቸው ባለሙያዎች የሚመራ እንዲሆን ማስቻልና ለአስመጪዎች፣ ለአምራቾች፣ ለነጋዴዎች፣ ለግብርና ሠራተኞችና ለተጠቃሚዎች ተገቢና ተከታታይ ግንዛቤን ለመፍጠርና ለማጎልበት የሚረዱ ሥልጠናዎችን ማደራጀት፣ መተግበርና በየጊዜው ውጤታማነታቸውን ባለድርሻዎችን ባሳተፈ መንገድ በመፈተሽና አስፈላጊ የሆኑ ማሻሻያዎችን ያካተተ ስትራቴጂን በመፈለግ ተግባራዊ ማድረግ ወቅቱ ግድ የሚላቸው ገሃድ ሃቆች ናቸው፡፡

አለበለዚያ ዛሬ በአገራችን የሚስተዋለው የተዝረከረከና ፋይዳ ቢስ የፀረ ተባይ ቁጥጥርና አስተዳደር ሥርዓት የሕዝብ ጤናና አካባቢን አደጋ ላይ እንዳይጥልና ምናልበትም የአረንጓዴ ልማት ሐሳባችን ከፖለቲካዊ ፍጆታ ባሻገር የሕዝብን ሁለንተናዊ ደኅንነትና ጥቅም ማስከበርን ማዕከል አድርጎ መንቀሳቀስና ትልሞችን ተግባራዊ ማድረግ አርቆ አስተዋይነት ነው፡፡ ቸልተኝነታችን ውሎ አድሮ ለትውልድ የሚተርፍ የከፋ መዘዝ ይዞ መምጣቱ አይቀርምና ልብ ያለው ልብ ይበል!!!!!!!!

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

Standard (Image)

የግንቦት 20 ትሩፋቶችና የፀረ ሙስና ትግል እውነታ

$
0
0

በፀዳሉ ንጉሡ

ይህችን ጽሑፍ ለመሞነጫጨር የተነሳሳሁት ሪፖርተር በግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ዕለተ እሑድ፣ ዕትሙ፣ ‹‹የግንቦት 20 ትሩፋቶችና የፀረ ሙስና ትግል›› በሚል ርዕስ፣ በፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን በጽሑፍ የቀረበ ሐሳብ ነው፡፡

በጽሑፉ በቀረበ ሐሳብ ላይ ያለኝን አስተያየት ወደኋላ ላቆይና ስለፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ጥቂት ልበል፡፡

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግሥት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአዋጅ ቁጥር 235/1993 የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽንን ሲያቋቁም በአዋጁ መግቢያ የሰፈረው ሐሳብ እንዲህ ይነበባል፡፡

  • የኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝቦች ሙስናና ብልሹ አሠራር የአንድን አገር ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዕድገት የሚገታ ተግባር መሆኑን የተገነዘቡ በመሆናቸው፣
  • አገሪቱ የተያያዘችውን የዕድገት ጎዳናና የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ለማፋጠንና ቀጣይነት ያለው እንዲሆን ሙስናንና ብልሹ አሠራርን በቁጥጥር ሥር ለማዋል አስፈላጊ በመሆኑ፣
  • ሙስናንና ብልሹ አሠራርን ለመሸከም የማይፈልግና ይህንኑ በብቃት ለመዋጋት ዝግጁ የሆነ ኅብረተሰብ መፍጠር አስፈላጊ በመሆኑ፣
  • ሙስናና ብልሹ አሠራርን ለመመርመርና ለመክሰስ፣ ለመቆጣጠርና ለመከላከል መልካም ሥነ ምግባር በኅብረተሰቡ ውስጥ እንዲስፋፋ በማድረግ ሙስናንና ብልሹ አሠራርን መዋጋት የሚችል ነፃና ራሱን የቻለ መንግሥታዊ አካል ማቋቋም አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፣ ይላል፡፡

በተመሳሳይ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ጉዳዮች የፖሊሲ ሰነድ፤ ‹‹ሙስና በዬትኛውም አገር ቢሆን መቶ በመቶ የተወገደበት ሁኔታ የለም፡፡ ይሁንና በቁጥጥር ሥር ሲገባ በዝቅተኛ ደረጃና መጠን አልፎ አልፎ የሚከሰት ችግር ብቻ ሊሆን ይችላል፡፡ በእኛ አገር ሁኔታ ሙስና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ወደ ምርትና ልማት ከማተኮር ይልቅ ወደ ማጭበርበርና አየር በአየር ንግድ እንዲያዘነብል በማድረግ ልማታችንን ክፉኛ ሊጎዳ ይችላል፡፡ የመንግሥት አሠራር በአድሎና ጉቦ ተጨማልቆ፣ መንግሥት በልማት ተግባር ላይ በጎ አስተዋፅኦ ማድረግ ተስኖት የልማት ችግራችን የመፍትሔ አካል መሆኑ ቀርቶ ዋነኛው ችግር ሊሆን ይችላል፡፡ መንግሥት ሕዝባዊ አገልግሎት የሚበረከትበት ሳይሆን ዝርፊያ የሚከናወንበት መድረክ ይሆንና የመንግሥት ሥልጣን ለመያዝ የሚደረግ ፉክክር በዘራፊዎች መካከል የሚደረግ የሞት ሽረት ትግል እንዲሆን፣ ስለሆነም ዴሞክራሲ ከሥረ መሠረቱ እንዲናድ በር ሊከፍት ይችላል፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች ሁሉ ሙስና ልማታችንን አደናቅፎ፣ የዴሞክራሲ ሥርዓታችንን ከውስጡ እንዲበሰብስ አድርጎ የልማትና የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ተስፋችን እንዲጨልም ማድረግ ይችላል፡፡

‹‹በመሆኑም ሙስናን በሰፊውና በብቃት የመዋጋት ሥራ አንድ አስነዋሪ ሥራን የማውገዝና የመቃወም ሥራ ብቻ አይደለም፡፡ በአገራችን መልካም አስተዳደርን በማስፈን የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታና የልማት ራዕያችን እውን እንዲሆን የማድረግ ጉዳይም ጭምር ነው፤›› ይላል፡፡

በእነዚህ ሁለት ጥቅሶች ከሰፈረው ሐሳብ የኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝቦች ለፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን የሰጡትን ተግባራትና ኃላፊነቶች በጥልቀት ለመረዳት አያዳግትም፡፡ ጥያቄው ኮሚሽኑ ኃላፊነቶቹን ተወጥቷል ወይ ነው? የአደባባይ ሚስጥር የሆነውን የዚህን ጥያቄ መልስ ለመመለስ አልዳዳም፡፡ ‹‹ብዙ ከተናገሩት ትንሽ የሠሩት የበለጠ ይናገራል›› እንዲሉ ብዙ ከመናገር ትንሽ መሥራት ዋጋ እንዳለው ኮሚሽኑ መመከር እንዳለበት ግን እግረ መንገዴን ሳልጠቁም አላልፍም፡፡

በጋዜጣው ወደ ቀረበው ጽሑፍ ልመለስ፡፡ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን በጽሑፉ መነሻ የግንቦት 20 ትሩፋቶችን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፎች በሚል ጠቅለል አድርጎ በማቅረብ መዘከሩ መልካም ነገር ነው፡፡ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ራሱም የግንቦት 20 ፍሬ መሆኑ ሳይዘነጋ፡፡

እንቆቅልሹ ግን የትግሉ መሪና ፊትአውራሪ የሆነው የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ‹‹የዕድገታችን ማነቆ በመሆን ሲፈታተኑን ከቆዩ ዋና ዋና ችግሮች መካከል ደግሞ የኪራይ ሰብሳቢነት፣ የመልካም አስተዳደር፣ የሙስናና የብልሹ አሠራር ችግሮች በዋነኛነት ይጠቀሳሉ፤›› ሲል መደመጡና ወረድ ብሎ ደግሞ በአንቀጽ ሦስት፣ ‹‹የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽንም ባለፉት ዓመታት በአንድ በኩል የግንቦት 20 ድል ትሩፋቶችን ከሙስናና ብልሹ አሠራር አደጋዎች በመጠበቅ ለልማቱ ስኬታማነት የበኩሉን ሲወጣ የቆየ ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ በመልካም ሰብዕና የተገነባ፣ ሙስናና ብልሹ አሠራርን መሸከም የማይችል ኅብረተሰብ እንዲፈጠር ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል፤›› በማለት ሁለት የሚጋጩ ሐሳቦች በጽሑፉ አስተናግዷል፡፡

እዚህ ላይ ልብ ሊባል የሚገባው ጉዳይ ባለፉት ዓመታት የግንቦት 20 ድል ትሩፋቶች ከሙስናና ብልሹ አሠራር ተጠብቀው ቢሆን ኖሮ፣ በመልካም ሰብዕና የተገነባ፣ ሙስናና ብልሹ አሠራርን መሸከም የማይችል ኅብረተሰብ እንዲፈጠር ተገቢው ጥረት ተደርጎ ቢሆን ኖሮ፣ ዛሬ መሬት ላይ የሚታየው እውነታ ሌላ መልክ በኖረው ነበር፡፡ ዛሬ በአገር አቀፍ ደረጃ ዋና ዋና ችግሮች የሚባሉት የመልካም አስተዳደር እጦት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት፣ ሙስናና ብልሹ አሠራር የመነጋገሪያ አጀንዳዎች ባልሆኑ ነበር፡፡ የግንቦት 20 ድል ትሩፋቶችም አሁን ከተገኙት እጥፍ ድርብ በሆኑ ነበር፡፡

የግንቦት 20 ድል ትሩፋቶች የበርካታ አካላት የጥረት ውጤቶች ናቸው፡፡ ስለሆነም የተወሰነ አካል የአንበሳውን ድርሻ የሚወስድበት አግባብ የሚኖር አይመስለኝም፡፡ ለዚህም ነው ገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ የግንቦት 20 ትሩፋቶችን መንግሥትና መላው ኅብረተሰባችን ያስገኟቸው ድሎች እንደሆኑ በሚዲያዎች የሚያዘክረው፡፡ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ‹‹ዋናው እኔ ነኝ›› እያለ ከሆነ ሊታረም ይገባል፡፡ ይህ ማለት ግን እያንዳንዱ አካል (ተቋም) አገራዊ ራዕዩን ከማሳካት አኳያ ምን ያህል ድርሻዬን ተወጥቻለሁ? በማለት ራስን መጠየቁ ተገቢ ነው፡፡ አገራዊ ራዕይን ከግብ ለማድረስ ደግሞ እያንዳንዱ አካል (ተቋም) የራሱን ራዕይ ለማሳካት በሚያደርገው ጥረት ይወሰናል፡፡ ምክንያቱም አገራዊ ራዕዩ የተለያዩ አካላት (ተቋማት) ራዕይ ድምር ውጤት ስለሚሆን፡፡

ስለራዕይ ከተነሳ አይቀር የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ካስቀመጠው ራዕይ አኳያ በጊዜ ቀመር አፈጻጸሙን ማየቱ ተገቢ ስለሚሆንና ይኼው ከራዕይ አኳያ አፈጻጸም ደግሞ በግንቦት 20 ትሩፋቶች ላይ ድርሻን ማየት ስለሚያስችል ከተቀመጠው ራዕይ አኳያ አፈጻጸሙ እንዲህ ይስተዋላል፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ራዕይ ‹‹በ2015 ሙስና ለልማትና መልካም አስተዳደር እንቅፋት ከማይሆንበት ደረጃ በማድረስ በዓለም ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ከሆኑ የፀረ ሙስና ተቋማት አንዱ ሆኖ መገኘት፤›› ይላል፡፡ ከዚህ ኮሚሽኑ ካስቀመጠው ራዕይ ሁለት ዓበይት ሐሳቦችን መንቀስ ይቻላል፡፡ እነሱም፡-

  • በ2015 ሙስና ለልማትና መልካም አስተዳደር እንቅፋት ከማይሆንበት ደረጃ ማድረስ፣
  • በ2015 በዓለም ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ከሆኑ የፀረ ሙስና ተቋማት አንዱ ሆኖ መገኘት፣

እነዚህን ሁለት የራዕዩን ዋና ዋና ጉዳዮች 100 በመቶ ለማሳካት 22 ዓመታት እንደሚያስፈልጉ በ2015 ከሚለው አገላለጽ መረዳት ይቻላል፡፡ በእስካሁኑ (ላለፉት 15 ዓመታት) የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን የራዕዩን 68.18 በመቶ አሳክቷል ማለት ነው፡፡ በመጪዎቹ ሰባት ዓመታት ውስጥ ደግሞ ቀሪ 31.81 በመቶ  በማጠናቀቅ በ2015 ሙስና ለልማትና መልካም አስተዳደር እንቅፋት ከማይሆንበት ደረጃ በማድረስ በዓለም ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ከሆኑ የፀረ ሙስና ተቋማት አንዱ ሆኖ ይገኛል ማለት ነው ኮሚሽኑ፡፡

ይህ እንግዲህ ኮሚሽናችን ዕይታውን በማቋቋሚያ አዋጁ (ከላይ ለማሳየት እንደተሞከረው) ከሕዝብና ከመንግሥት የተሰጠውን ኃላፊነት፣ ራሱ ኮሚሽኑም ባስቀመጠው ራዕይ ላይ በማድረግ ተንቀሳቅሶ ቢሆን ኖሮ ሊመዘገብ የሚችል የአፈጻጸም ውጤት ነበር፡፡ እንዲህማ ቢሆን ኖሮ በየሥልጠና መድረኮች ከሠልጣኞች፡-

  • ሙስና በአገራችን ምን ደረጃ ላይ ይገኛል?
  • የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ከተቋቋመ ወዲህ ሙስና ጨምሯል ወይስ ቀንሷል?
  • ራሱ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ከሙስናና ብልሹ አሠራር ነፃ ነው?

በሚል ለሚነሱ ጥያቄዎች ደረት ነፍቶ፣ አፍ ሞልቶ መልስ መስጠት በተቻለ ነበር፡፡

ነገር ግን የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን በዚህ ቁመና ላይ ይገኛል ወይ? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ ይህን ጥያቄ ለመመለስ ደግሞ መሬት ላይ ያለውን እውነታ ማየት ግድ ይላል፡፡ ዛሬ ኅብረተሰቡ በመልካም አስተዳደር እጦት በሚናጥበት፣ ዛሬ በኪራይ ሰብሳቢዎች አመለካከትና ድርጊት ልማታዊ መስመሩ ቆም ብሎ በማስተዋል ነገሮችን እንዲመለከት በተገደደበት፣ ዛሬ ሙስናና ብልሹ አሠራር ሥር የሰደዱ ችግሮች በሆኑበት ፈታኝ ወቅት ‹‹… በበላበት ይጮኻል›› እንዲሉ አንዳንድ ጥቅመኞች የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን እንዲህ አደረገ፣ እንዲያ አደረገ እያሉ በፈጠራና እንቶ ፈንቶ ወሬ ሚዲያውን ያጨናንቃሉ፡፡ ይኼ መልካም አይደለም፡፡ ሊታረም ይገባል፡፡ ሚዲያዎች ለኅብረተሰሰቡ በእውነት ላይ የተመረኮዘ መረጃ ነው መስጠት ያለባቸው፡፡

ይልቁንስ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ‹‹ድክመቴ ምን ላይ ነው?›› ብሎ በመጠየቅና መላ ሠራተኛውን በማሳተፍ ችግሩን በመለየት ለመፍታት ጥረት ቢደረግ ሕዝባችንን መታደግ የሚያስችል ሥራ መሥራት በተቻለ ነበር፡፡ ድክመትን ለመሸፋፈን የባጡን የቆጡን መቀባጠሩ የትም አያደርስም፡፡ ‹‹የግንቦት 20 ትሩፋቶችና የፀረ ሙስና ትግል›› በሚል ርዕስ ሥር የቀረበውም ከተራ ወሬና ማስመሰል የዘለለ ሚዛን የሚደፋ ቁም ነገር የለውም፡፡ ደግነቱ መንግሥትና ኅብረተሰቡ እውነታውን ጠንቅቀው የሚያውቁ መሆናቸው በጀ እንጂ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው 6nigusse@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

ታላቋ ብሪታንያ ወደ ታናሽ እንግሊዝነቷ ስትመለስ

$
0
0

በአሰፋ እንደሻው (ዶ/ር)፣ ለንደን

ሰኔ 16 ቀን 2008 ) ዓ.ም. (በአውሮፓውያን አቆጣጠር ሰኔ 23 ቀን 2016) አብዛኛው የብሪትን ሕዝብ ከአውሮፓ ኅብረት አባልነት ለመውጣት የሰጠው ድምፅ በጣም አስገራሚ ነው። በትልልቆቹ ከተሞች የሚኖረው ሕዝብ (ጥቁሮችን ጨምሮ) ከአውሮፓ ጋር ለመቀጠል ፍላጎቱን ቢገልጽም ብዙኃኑ አሻፈረኝ ብሏል። ክርክሩ ከላይ ከላይ ራሳችንን በነፃነት መምራት ይገባናል፣ የአውሮፓ ማኅበር እየተጫነን እስከመቼ እንኖራለን የሚል ሆኖ በውስጡ ግን ሥር የሰደዱ ሌሎች ነገሮች አሉት (ነበሩት)።

የታላቋ ብሪታንያ አነሳስ

እንግሊዞች ደሴት ላይ በመኖራቸው ከጥንት ጀምሮ ሁልጊዜ በውጭ ኃይሎች እንወረራለን፣ እንጠፋለን፣ እንዋጣለን የሚል ሰቀቀን አዕምሯቸው ውስጥ ሰርጿል። አገሪቱን ወረው የተቆጣጠሯት የሰሜን አውሮፓ ጎሳዎች በፊት የሰፈሩትን የኬልት

ሕዝቦች (ዌልስ፣አይሮችና ስኮቶች)  አሽንፈው ስለነበር ሌላ ባለተራ ይመጣብናል የሚል ፍራቻቸው በተደጋጋሚ በተከስቱ ድርጊቶች ሥር ሰዶ ኖሯል። ሮማውያን አስቀድመው፣ ከዚያ ከሰሜን ፈረንሣይ (ኖርማንዲ) እኤአ በ1066 የተሻገረው ወራሪ፣ ስፓኞች በባህር ኃይላቸው፣ ናፖሊዮንና ሂትለር በተጠናከሩ ዘመናዊ ጦር ሠራዊቶቻቸው አማካይነት ብሪትንን ለማንበርከክ ሞክረዋል። በምላሹ ብሪትኖች ከተከታተለው የውጭ አደጋ ለመከላከል ሲሉም የባህር ኃይላቸውን ገንብተው ጭራሽ ባካባቢያቸው ብሎም ዓለም ላይ ገናና ሆኑ። በብሪትን ግዛት ፀሐይ አትጠልቅም እስከ ማለት ደረሱ።

የብሪትን  የባህር ኃይል ባለቤትነት ቅኝ ግዛቶችን ለማብጀት ከነሱም ስፍር ቁጥር የሌለው ጥሬ ሀብትና ባሪያ ወደ ደሴቲቱ ለማጋዝ፣ በእነሱም  አማካይነት ከግብርና ኢኮኖሚ ወደ ኢንዱስትሪ ኃያልነት ለመሸጋገር በቃች። አፍሪካውያንን በተለይ በቅኝ ግዛትነት ጥሬ ሀብታቸውን ለማጋበስ ከመቻሏም በላይ ነዋሪዎቿን በባርነት እየፈነገለች ዛሬ አሜሪካ ወደ ሚባለው አገር  እያጓጓዘች ጉልበታቸውን ለጥጥና ሌላም ምርት በማዋል ውጤቱን ለራሷ ደሴት ማበልጸጊያ አድርጋለች። ከሷ ቀደም ብለው ቅኝ ግዛት ለማቋቋምና የሌሎች ሕዝቦችን ሀብት  ለመዝረፍ የሞከሩትን ስፔንና ፖርቱጋልን በልጣና ወደ ጎን ገፍትራ ፈረንሣይ እግር እግሯን እየተከተለቻት በዓለም ደረጃ የኢንዱስትሪያዊ ሽግግር ያከናወነች አገር ሆነች። ናፖሊዮን በንቀት ዓይን "የሱቅ ጠባቂዎች አገር"እንዳላት ተሸብባ ሳትቀር በንግድ መተዳደሩን አልፋ የኢንዱስትሩ አብዮት ባለቤት ሆነች። (ሟቹ አለሜ እሸቴ የመጀመርያውን አብዮት ማለትም እሳትን መጠቀም የቻሉት የኢትዮጵያውያን ቅድም አያቶቻችን ናቸው ያለውን ልብ ይሏል። ለምን ሁለተኛውን አብዮትም ከብሪትን ይልቅ እኛ ማድረግ እንደተሳነን በዚያው ማሰላሰል ይገባል።)

ብሪትን ከፈረንሣይ ጋር የነበራት ፉክክር ቀጥሎ በቅኝ ግዛት ማስፋፋቱም ሆነ በጥሬ ሀብት ማጋበሱ በኩል ግን ይበልጥ ተሳካላት። ሰሜን አሜሪካ ላይ የሃይማኖት ጭቆናን ሸሽተው የተሰደዱትንና የሰፈሩትን ዜጎቿን መረማመጃ አድርጋ ዝርያዎቿን በብዛት አጎረፈች፣ አሰማራች። ቀይ ህንድ ብለው የሰየሟቸውን ያካባቢውን ሕዝቦች እያስጨፈጨፈችም ዘሮቿን ማለትም አንግሎ ሳክሰኖችን አባዛች። ከሌሎች አውሮፓ አገሮች ሰፋሪዎች እየፈለሱ ወደ ሰሜን አሜሪካ ቢጎርፉም በብዛታቸውና የተቋቋመውን አገዛዝ እንዲሁም ሀብት በጃቸው ያስገቡት አንግሎ ሳክሰኖች ስለነበሩ፣ ሰሜን አሜሪክ እስካሁን ድረስ የእንግሊዝ ቁራሽ አካል ሆኖ ቀጥሏል። በኋላ ላይ በአውስትራሊያ፣ በኒውዚላንድ ተመሳሳይ የአንግሎ ሳክሶን ወረራና ሰፈራ ሲከናወንም የእንግሊዝ ቁራጭ አካሎች መብዛት በዓለም ላይ የአንግሎ ሳክሶንን ግዛት የቆዳ ስፋትና አቅም ከፍተኛ አደረገው። በደቡብ አፍሪካ በአጠቃላይና በሌሎች ቅኝ ግዛቶች የተደረገው ተመሳሳይ የሕዝብ ማስፈር ሙከራ ግን ሙሉ በሙሉ አልተሳካም።

ይሁንና ብሪትን በእንግሊዝ መሪነት በሄደችበትና በረገጠችበት አካባቢ ሁሉ የጥሬ ሀብት ዘረፋ ከማካሄዷ ውጪ፣ የለም መሬት ቅሚያ፣ የከተማ ርስት ግንባታ ተያይዛ ስለነበረ ቅኝ ግዛቶቹ ነፃ ከወጡም በኋላ እነዚያን ይዞታዋቿን ሳታስነካ እስካሁን ድረስ ዘልቃለች። በኬንያ፣ በዚምባብዌ፣ በዩጋንዳ፣ በሆንግ ኮንግ፣ በሲንጋፖር ስንቱ አገር ተዘርዝሮ ያልቃል ሰፋፊ ለም መሬትና የከተማ ርስት ከቅኝ ግዛትነት ዘመን ጀምሮ በብሪትን ዜጎች እጅ እንዳለ አለ። በቅኝ ግዛቶች ውስጥ በተከፈቱ የንግድና ኢንዱስትሪ ተቋማት ውስጥም የብሪትን (በይበልጥም የእንግሊዝ) ዜጎች የዳጎሰ ድርሻ ነበራቸው፣ እስከዛሬም እየተንከባለለ መጥቷል፡፡

ብሪትን የባህር ኃይል አቅሟን ገንብታና በዓለም ዙሪያ አሰማርታ፣ የባዕድ (ውጭ) ሕዝቦችን ጥሪቶችና ሀብቶች በቅሚያና በንግድ እያግበሰበሰች በመሄዷ ከግብርናና ንግዳዊ ኢኮኖሚ ወደ ኢንዱስትሪያዊ ኃያልነት መሸጋገሯ ለተወሰኑ ዓመቶች ከፈረንሣይ በስተቀር ተፎካካሪ የሌላት ብቸኛ የዓለም ልዕለ ኃያል እንድትመስል አድርጓት ነበር፡፡ ነገር ግን ከእንግሊዝና ከፈረንሣይ ወደ ኢንዱስትሪ መግባት ተከትለው በሁለተኛ ደረጃ ብቅ ያሉት አሜሪካ፣ ጀርመንና ሩሲያ የዓለምን የኃይል ሚዛን ከ19ኛው መቶ ዓመት ማብቂያ ወዲህ መለወጥ ተያያዙ። የእንግሊዝና የፈረንሣይ ገናናነት በአዲሶቹ የኢንዱስትሪያዊ አገሮች መፈታተንና መፎካከር ሲደርስበት ሰላማዊ ሽግሽግ ከማድረግ ይልቅ በጦርነት መጋጠምን አዘወተሩ። በፊት በፊት አንድ ለአንድ ይደረግ የነበረው የገናናዎቹ ጦርነት (እንግሊዝ ከአሜሪካ፣ ከሩሲያ፣ ከኦቶማን ቱርኮች፣ ከሰፔን እንዲሁም ከፈረንሣይ)፣ በጅ አዙርና በተዘዋዋሪ መልክ የሚከናወነውን ጨምሮ እያደር እየቀረ በቡድን መልክ ተደራጅተው ወደመጋጠም ላይ ደረሱ። ቀደም ያሉትን አናሳ መቧደኖች ትተን የመጀመርያውና ሁለተኛው የዓለም ጦርነት የተሰኙት ትንቅንቆች በዚህ አኳኋን የተከሰቱ ነበሩ። የጦርነቶቹ ቀስቃሾች (ከሞላ ጎደል አዳዲሶቹ የኢንዱስትሪ ኃያላን) ፈረንሣይና እንግሊዝ በዓለም ላይ ገንብተው ያቆዩትን የባላይነት ሽረው፣ ከሁለተኛ ደረጃነት ወጥተው ከፍ እንዲሉ፣ የእነሱንም ጥቅም የሚያስጠብቅ ዓለም አቀፋዊ ሥርዓት ለመፍጠርና በመካከላቸው አቻነትን ለማስፈን ያለሙ ነበሩ።

የታላቋ ብሪታንያ ኃይል ማሸቆልቆል

በመጀመርያውም ሆነ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ከብሪትንና አባሪዎቿ (በይበልጥ ሩሲያ፣ ፈረንሣይና አሜሪካ) ጋር የተፋለሙት ኦስትሪያ ሃንጋሪ፣ ጀርመን፣ የኦቶማን አገዛዝና በኋላም ጃፓን ከፍተኛ ወድቀትና መፈረካከስ ቢደርስባቸውም፣ ብሪትን ይኼ ነው የማይባል ኪሳራ (ዕዳ) ውሰጥ ገብታ ቀዳሚ የዓለም ኃያልነቷ ተናግቷል፡፡ ከዓመት ገቢዋ በአንደኛው ዓለም ጦርነት 150 ከመቶ በሁለኛው ዓለም ጦርነት ደግሞ 200 ከመቶ ደርሶ ስለነበር፡፡ በሌላም በኩል ከመጀመርያው የዓለም ጦርነት በኋላ ባላንጣዎቿ አሜሪካና ሩሲያ በይዞታቸው ላይ መሠረታዊ ለውጥ ተከሰተባቸው፡፡ አሜረካ በባህር ኃይሏና በኢኮኖሚዋ ከሁሉም ኢንዱስትሪያዊ አገሮች ልቃ ስትገኝ ሩሲያ በአብየት እሳት ተበልታ ወደ ሶሻሊዝም አምርታ በርካታ የምሥራቅ አውሮፓ አገሮችንና ቻይናን አጋር አድርጋ፣ ከምዕራባውያን ኃያላን ጋር ታይቶ ለማይታወቅ ግብግብ ተዘጋጀች፡፡ አሜሪካ (በፕሬዚዳንት ውድሮው ዊልሰን መሪነት) የእንግሊዝና የፈረንሣይን የቅኝ ግዛቶች ወደ ነፃነት እንዲያመሩ በሰጠችው ፍንጭና ግፊት የኢንዱስትሪና የወታደራዊ ጡንቻዎቿን ተመክታ ጥላዋን በያቅጣጫው ስትዘረጋ የብሪትንን የበላይነት ሰፍራ ያላንዳች ጦርነት ለመረከብ በቃች፡፡ የግብፁ ናስር የስዊዝን ቦይ እ.ኤ.አ. በ1956 በቁጥጥር ሥር ሲያደርግ አሜሪካዎች የብሪትንና የፈረንሣይን መልሶ ማጥቃት ሙከራና መሸነፍ ሲኮንኑ በብሪትን ግዛት ፀሐይ እንደጠለቀ አበሰሩ፡፡ ጥቂት ቆይቶም የብሪትኑ ጠቅላይ ሚኒስቴር ሃሮልድ ማክሚላን የለውጥ ንፋስ እንደመጣ እ.ኤ.አ. በ1960 በይፋ ባወጀበት ወቅት ይኼን የብሪትንን ቦታ መነጠቅ ማወጁ ነበር፡፡

ለ400 ዓመታት በብሪትን ሲዘረፍና ሲቀጠቀጥ የኖረው የህንድ ሕዝብ ትግል አስቀድሞ ድል መቶ እ.ኤ.አ. በ1947 ነፃ ሲሆን ብሪትን እንዳለቀላት በቂ ምልክት ቢሆንም፣ ስትንገታገት በኬንያ የማኦ ማኦን እንቅስቃሴ፣ በማላያም የፋኖ ጦርነት ገጠማት፡፡ ፈረንሣይም ብትሆን በአልጄሪያው የነፃነት ትግል ተለብልባለች፡፡ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሳይቀር (እ.ኤ.አ. በ1960 ላይ) ቅኝ የሆኑ አገሮች በሙሉ ነፃ እንዲወጡ ታወጀላቸው፡፡ ሶቭየት ኅብረትና ቻይና የሚደግፏቸው የነፃነት እንቅስቃሴዎች በዓለም ዳር እስከዳር ይንፈቀፈቁ ገባ፡፡ የባሰ ሳይመጣ በሚል ብሪትንና የፈረንሣይ ቅኝ ግዛቶቻቸውን አንድ ባንድ ነፃ ለቀቁ፡፡ ብሪትን በምንተፍረት የዱሮ ቅኝ ግዛቶቿን በወዳጅነት አብረው እንዲቆዩ ተማጽና እስከዛሬ ያልፈረሰ የጋራ ጥቅም ኅብረት አቆመች፡፡

ሄዶ ሄዶ ብሪትን የዱሮውን ክብሯንና አቅሟን አጥታ እንደሌሎች የአውሮፓ አገሮችና ጃፓን ከአሜሪካ ሥር መግባቷ አልቀረም። ሁለታችንም የአንግሎ ሳክሶን ዝርያ ነን የሚለውን ትረካ ተገን አድርጋ ልዩ ዝምድና መሥርተናል እያሰኘች ብታንቧርቅም፡፡ ይኸው ዝምድና በብዙ መልክ እየተተረጎመ ውሉ የጠፋ ቢሆንም፣ አስተሳሰቡ የበላይና የበታች የሌለበት ባልደረባነት እንደሆነ ያህል ያስመስሉታል፡፡ በውስጠ ታዋቂነት ግን እንግሊዝ በዓለም ዙሪያ በነበራት ገዥነት ያካበተችው ልምድ (እና የቀበረቸው ፈንጂ!) ስላለ የአሜሪካውን ጥሬ ኃይል በማለስለስና በመሞረድ ለጋራ ጥቅማቸው አብረው መንቀሰቀስ እንዳለባቸው የመስበኪያ መሣሪያ ነው፡፡ ብሪትን ከአሜሪካ ጋር በበርካታ የዓለም አወዛጋቢ ጉዳዮች ላይ የወሰደቻቸውን አቋሞች ልዩነት በዚህ መሣሪያ አማካይነት እየተነተነች የአሜሪካኖችን መሳሳት፣ ችኩልነትና ልምድ ማነስ ብሎም ጥሬ ጉልበተኛነት እንደሚያመለክት አድርጋ ስታስተጋባ ኖራለች፡፡ በሚስጢር የሚባባሉትን የመስሚያ ቀዳዳ በተፈጠሩ ወቅቶች በተገኙት መረጃዎች መሠረት፡፡

የብሪትን የአውሮፓ የጋራ ገበያ አባልነት

አሜሪካና ሶቭየት ኅብረት (ከነጋሻ ጃግሬዎቻቸው) በሚተናነቁበት ዘመን ብሪትን ታላቅነቷ እያቆለቆለ የአሜሪካም ቡችላ እየሆነች ስትሄድ፣ ኢኮኖሚያዋም ሲወዳድቅ፣ ከአውሮፓ ጋር የጋራ ገበያ ለመፍጠር እንድትስማማ የአሜሪካ መንግሥት ተፅዕኖ አርፎባት እስከ እ.ኤ.አ. 1972 ድረስ ለ20 ዓመታት ያህል ስታቅማማ ቆይታ ጥልቅ አለች። (የአሜሪካ ስለላ ድርጅት ይኼንን ልዩ ተልዕኮ አድርጎ ሲሠራ እንደነበር በቅርቡ ይፋ ወጥቷል፡፡) በውስጧ ግን ከአሜሪካ ላይ ተንጠላጥላ ወይም ብቻዋን ሆና እንደ ታላቅ ኃይል ለመቀጠል መጓጓቷ አልጠፋም ነበር። ምንም ብንቀጥን ጠጅ ነን ዓይነት። ብሪትን ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ ዓለምን ስትገዛ ኖራ ከማንም ትንንሽ አገር ጋር እንዴት በእኩልነት ቆማ ልትታይ ይሁንና የፈሩት ይደርሳል ሆነና የኢኮኖሚያዊ አጋርነቱን አስፈላጊነት ተቀብላ በወግ አጥባቂው ፓርቲ በኤድዋርድ ሂት ጠቅላይ ሚኒስቴርነት መሪነት የአውሮፓ የጋራ ገበያ ማኅበር አባል ሆነች፡፡

የአውሮፓ የጋራ ገበያ መነሻ አስተሳሰቡ በተደጋጋሚ ጦርነት የዳሸቁትን አገሮች አንድ ላይ በሰላማዊ መንገድ አስተባበሮ በመያዝ ወደፊት ከሚመጣ ተመሳሳይ አደጋ ለማዳን ነበር፡፡ በተለይ በጀርመንና በፈረንሣይ መካከል የማይበርድ መነቋቆርና መናናቅ በታሪካቸው ሥር ስለሰደደ ከዚያ ችግር ለመውጣት አዲስ ጎዳና መከተላቸው ይበጃቸዋል የሚል ግምት ነበር፡፡ የጋራ ገበያ ዕቅዱ ቀስ በቀስ በስምምነት እየተለወጠ ወደ አውሮፓ ማኅበርነት ከፍ ሲልና የአውሮፓ ፖለቲካዊ ሥርዓት ወደ መፍጠር ጥድፊያው ሲሸጋገር፣ ብሪታንያ  በውጭ ኃይሎች የመዋጡ የቆየ ፍራቻ በሽታ አገርሽቶባት ሁሌ የርስ በርስ መነታረክ አመንጪ ሆነች። በሟችቷ ታቸር ዘመን ጭቅጭቁ አይሎ እኛ የጋራ ገበያ እንጂ ፌዴራል መንግሥት አንፈልግም የሚለው መፈክር ዘወትር ይሰማ ነበር።

ከዚያ ወዲህ ግን የዓለም ኢኮኖሚ እየተገለባበጠ፣ ከዳር እስከዳር መጠቃለሉ እየፈጠነ ከአሜሪካው ግዛታዊ መንግሥት በስተቀር ነፃ የሚባል አገር እየጠፋ ሲሄድ የብሪትን መወራጨት ቅጥ አጣ። ሶቭየት ኅብረት ተፈረካክሳ ጀርመኖች ተዋህደው፣ የአውሮፓው ኅብረት በብዙ አቅጣጫዎች መጠነኛ ስምምነቶች እየፈጠረ እንደ አንድ የዓለም ልእለ ኃያል ብቅ ማለቱን እያየች እንኳን፣ ብሪትን በአውሮፓውያን መካከል እያደር እንደ በጥባጭና አደናቃፊ መታየቷን አላቆም አለች፡፡ እንዲያውም ከአውሮፓ ውጪ ራሳችንን ችለን ታላቅ ሆነን እንቀጥላለን የሚለው ፉከራ ከንቱ መሆኑ በታሪክ ቀብረው እንደተሰናበቱት ማመን አቅቷቸው፣ ይኸውና ገዥዎቿ ለውሳኔ ሕዝብ አቅርበውት ቅዠት ይሁን ሕልም በማይለይ አኳኋን የብሪትንን ዕድል፣ የሕዝቧን ዕጣ ፋንታ ሜዳ ላይ ዘረሩት።

የብሪትን ከአውሮፓ ኅብረት መውጣት መዘዝ

የብሪትን ከአውሮፓ መውጣት መዘዙ ባብዛኛው ለራሷ ነው። ኦኮኖሚዋ ጭራሽ ያሽቆለቁላል። ብዙ ሰው የማያስተውለው እነሱም ሽፋፍነው የሚይዙት ግን የብሪትን አቅም ቁልቁል ከወረደ 30 እስከ 40 ዓመታት አድርጓል። ዛሬ ከአውሮፓ ኃያላን ከጀርመን፣ ከፈረንሣይና ከሩሲያ በታች ወርዳ ከጣሊያንና ከስፔን እኩያ አካባቢ ናት። የማሽን ፋብሪካዎቿ ከፊሎቹ ከስመዋል ሌሎቹ ተነቃቅለው ወደ ቻይናና መሰል አገሮች ሸሽተዋል። የዕቃ ማምረቻዎች ክፉኛ ተንደው ቻይናና ሌሎች አዳጊ ኢኮኖሚዎች ጋ ገብተዋል። የከተማ ርስቶችና ታላላቅና ዕውቅ ሕንፃዎች ሳይቀሩ በውጭ ባለ ሀብቶች እጅ ገብተዋል፡፡ ዝነኛው በለንደን መሀል ላይ ያለው የቢቢሲ መናኸሪያ ሕንፃ (ቡሽ ሃውስ የሚሉት) ባለቤትነት ወደ ጃፓኖች ከዞረ ስንት ዓመታት አልፈዋል!

በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍም ቢሆን ማሽቆልቆሏ ያለቀለት ጉዳይ ነው። ለትምህርትና ለምርምር የምትመድበው ከቅርቡ (እ.ኤ.አ. 2008) ቀውስ ወዲህ መሬት ወርዷል፡፡ የከፍተኛ ትምህርት ተፎካካሪዎቿ አውሮፓውያን በሙሉ እንደ ኢኮኖሚያቸው ማንሰራሪያ ከማድረግ ይልቅ በገቢ መልቀሚያነት ስለመደበችው፣ የሚያስፈልጋትን የሠለጠነ የሰው ኃይል ማፍራት እየተሳናት ነው፡፡ ወደ መረጃ አኪኖሚ ለመሸጋገር የሚያሰችለውን ሥልጡን ሠራተኛ ካላፈራች በተለይ በዓለም መጠቃለል ሒደት ራሷም እየተሸመለለች የዱሮውን ዝና መቸብቸቡ ምን ፋይዳ ይኖረዋል? በኢንዱስትሪ አብዮቱ ቀዳሚ የሆነችበት ወቅትና ምክንያቶች ሁሉ ስለጠፉ ከሌሎች መካከለኛ ደረጃ ያሉ ኢንዱስትሪያዊ አገሮች ጎን ተሰልፋ የሚደርሳትን ዕጣ በጥሞና እንደመከታተል ቡራ ከረዩ ውስጥ ገብታ ስትዋኝ ሕዝቧን ለመከራና ለባሰ ውድቀት ልትዳርገው ነው፡፡

እስከዛሬ ድረስ የብሪትን አስተማማኝና ታላቁ የገቢ ምንጯ የገንዘብ ተቋሞቿ ነበሩ። የካፒታል ገበያዋ ከኒውዮርክ ቀጥሎ የዓለም ማዕከል ነው፡፡ በቁጥጥሯ ሥር ባሉ አሁንም ነፃ ባልወጡ ቀኝ ግዛቶችና ጥገኛ ደሴቶች አማካይነት በስውር የገንዘብ መሸሸጊያ ጓዳዎችም አብጅታ በሰፊው ትገለገላለች፡፡ በአደባባይ ላይ እነስዊስና ሌሎችን ስትወነጅል የሷን ጓዳ ሚስጢር ግን በጥብቅ ታስጠብቃለች፡፡ ከአውሮፓ በመውጣቷ ግን ፍራንክፈርት (ጀርመን) ለንደንን አሽቀንጥሮ የአውሮፓን የገንዘብ ታላቅ መናኸሪያነት ማዕረግ መረከቡ አይቀርም። ቻይና በቅርቡ ያገሯን የውጭ ገንዘብ (ዩዋን የሚባለውን) ለንደን ላይ በነፃ እንዲሸጥ እንዲለወጥ ለማድረግ ውስጥ ለውስጥ ከብሪትን ጋር ስትስማማ፣ የአውሮፓ አባልነቷን እንደምትቀጥል ገምታ ስለነበር አዲሱ ይዞታዋ ግን ያንን እንድታጣ ያደርጋታል፡፡ ይባስ ብሎም በየሱቆቿ የተደረደሩት የቻይናና የመሰል አገሮች ውጤቶች ፓውንዱን ወደ ውጭ የሚመዙ እንጂ ያገሪቱን ገቢ የሚያግዙ አይደሉም። የብሪትን ዕዳ ከዓመት ምርቷ ወደ 820 በመቶ አካባቢ መድረሱም የተሳካ ጎዳና ላይ አለመሆኗን ያስረዳል፡፡

ሲጠቃለል የዱሮው የብሪትን ታላቅነት ጉራ የሕዝቧን ጭንቅላት አሳብጦት አሁንም ለምታመርታቸው ዕቃዎች የአውሮፓ ገበያ የሚሰጣትን ጥቅም ብሎም በኅብረቱ አማካይነት የሚደርሷትን ልዩ ልዩ ዕድሎች አሽቀንጥራ ጥላ ለመውጣት በቃች። ብሪትን የቀራት ብቸኛ ችሎታና አቅም ከአሜሪካ ሥር ተሸጉጣ ሌሎችን አገሮች ማተራመስ ብቻ ይሆናል። (ቶኒ ብሌር ለጆርጅ ቡሽ ልጅየው በሰጠው የመካከለኛውን ምሥራቅ የማፈራረስ ግልጋሎት ዓይነት፡፡) ያም ቢሆን ከአሜሪካ የኢኮኖሚና ወታደራዊ አቅም እያደር መኮሰስ አንፃር ብዙም የሚያወላዳት አይሆንም፡፡ ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት ወዲህ በተለይም ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት እ.ኤ.አ. በ1976 ዓ.ም. ብሪትን ብድር ከተቀበለች በኋላ፣ ስትፈራና ስትከበር የኖረችበት ዘመን ማክተሙ ሁሉም ያወቀው ጉዳይ ሆኖ ለራሷ ጆሮ ግን ሳይደርስ ዘገየ፡፡

የብሪትን ከአውሮፓ ማኅበር መውጣት በሌላ በኩል ሲታይ የብሪትን እንቅፋትነት ስለተወገደ አውሮፓ በፍጥነት ወደ ፌዴራላዊ መንግሥት መገስገሱ ይቀጥላል። በአንፃሩም ብሪትን በአሜሪካ 53ኛ ያካባቢ መንግሥትነት ደረጃ ተዋውላ እንድትገባ ትገደድ ይሆናል። እናት ለጡረታ ወደ ልጅ ቤት እንደምትገባው ዓይነት። ስኮትላንድ በበኩሏ ያለ ጥርጥር ከብሪትን ተገንጥላ ወደ አውሮፓ መመለሷ የማይቀር ይመስላል። ሰሜን አይርምእንደዚሁ፡፡

አንዳንዶች የብሪትን ከአውሮፓ መውጣት ሌሎች አገሮችን ለተመሳሳይ ዕርምጃ ይገፋፋል ይላሉ፡፡ ነገር ግን መሀል፣ ምሥራቅና ደቡብ አውሮፓ ያሉ ትንንሽ አገሮች ሕዝቦች እንደ እንግሊዙ የተወሰሰበና የተመሰቃቀለ የነፃነት ታሪክ ስለሌላቸው፣ የአውሮፓን ልዕለ መንግሥት መፈጠር በብርቱ የሚቃወሙ ግዙፍ ንቅናቄዎች የሚወለዱ አይመሰልም። እንዲያውም የውህደቱን ፍጥነት ጨምረው ከጭቅጭቅ ለመገላገል ሳይቸኩሉ ይቀራሉ? የአውሮፓ ትላልቅ ኩባንያዎች ትስስርና የጀርመን ኢንዱስትሪ ተፅዕኖ ከአሜሪካኖች ዳተኝነት ጋር ተዳምረው ቢያንስ ቢያንስ የጠነከረ ኅብረት እንዲቀጥል ማድረግ ይሳናቸዋል? አሜሪካኖች ፌዴራል አውሮፓን ባይወዱም የእንግሊዞች ሰንካላ ብሔረተኝነት የከፈተውን ቀዳዳ ለመድፈን ሳይተጉ ይቀራሉ? የኦባማ ጥረት ለሱ እንደነበር፣ አለመሳካቱም ብዙ ብሽቀትንና ብሶትን በአሜሪካውያን በኩል መፍጠሩ ይኼን ይጠቁማል።

በእርግጥ አሜሪካ የአውሮፓን ኅብረት በምትፈለገው ፍጥነት፣ መልክና አቅጣጫ እንዲገሰግስ ለመቆጣጠር ከውስጥ ሆኖ የሚያግዛት ሌላ ተተኪ አገር ወይም አገሮች ላታጣ ትችላለች፡፡ ካሁን በፊት በተለያዩ ዘርፎች ለአሜሪካ በመላላክ ያግዙ የነበሩት የስካንዲኔቪያ አገሮች (በተለይ ዴንማርክ) የብሪትንን ቦታ ተክተው የጋራ የውጭ መመርያና የመከላከያ ጉዳይን ለመሸበብ ይተጉ ይሆናል፡፡ ቢሳካላቸውም ባይሳካላቸውም፡፡ ነገር ግን የአውሮፓም ሆነ የዓለም ኢኮኖሚ መዘውር እንደ ዱሮው በአሜሪካና በጥቂት አባሪዎቿ እጅ መሆኑ እየቀነሰ ስለሆነ፣ ብሪትን ባካሄደችው የቅርቡ ሕዝበ ውሳኔ ዋና ምክንያት በአዲስ ሁኔታ እየተዘጋጀ ላለው የሰንጠረዥ ጨዋታ ተጋባዥ የመሆን ዕድል ማጣቷ እጅግ አሳዛኝ ነው፡፡ የቀበጡ ዕለት…

 

ከአዘጋጁ፡- ዶ/ር አሰፋ እንደሻው ቦረና ትምህርት ቤት፣ ጄኔራል ዊንጌት፣ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና ለንደን ዩኒቨርሲቲ ተምረው ሲንጋፖርና ኢንግላንግ ዩኒቨርሲቲዎች በፕሮፌሰርነት ሕግ ያስተማሩ ሲሆን፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው a_endeshaw@yahoo.co.ukማግኘት ይቻላል፡፡ 

Standard (Image)

የሁለት ትውልድ ተጠቂ የነበሩት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በ124ኛ ዓመት ልደታቸው ሲታወሱ

$
0
0

በደረጀ ተክሌ

ኢትዮጵያን ከ1923 እስከ 1967 ዓ.ም ድረስ የመሩት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በዚህ ወር ሐምሌ 16 ቀን 2008 ዓ.ም አንድ መቶ ሃያ አራተኛ ዓመት የልደት በዓላቸው በአድናቂዎቻቸው ዘንድ ይከበራል፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ከዚህ በፊት ስለ ንጉሠ ነገሥቱ በተጻፉት ጽሑፎች ላይ ተጨማሪ ጽሑፍ በማቅረብ ታሪካቸውን ለመደረት ሳይሆን፣ በሚወዷቸውና በሚጠሏቸው ጸሓፍት ግራና ቀኝ ተወጥሮ የተጻፈውን የፍቅርና የጥላቻ ስሜት በማያንፀባርቅ ሁኔታ፣ በክፉም ሆነ በደግ በታሪክ የተመዘገበውን የንጉሠ ነገሥቱን ገጽታ በአጭሩ ለመዳሰስ ነው፡፡
በ1884 ዓ.ም ሐረርጌ ውስጥ ኤጀርሳ ጎሮ በምትባል መንደር የተወለዱት ተፈሪ መኮንን በኋላ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እናታቸውን ወ/ሮ የሺእመቤትን በጨቅላነታቸው፣ አባታቸውን ራስ መኮንንን ደግሞ በአሥራ ሦስት ዓመት የሕፃንነት ዕድሜያቸው ያጡ አብሮ አደግ ወንድምና እህት ያልነበራቸው ሲሆን፣ ከአባታቸው ልጅ ከደጃዝማች ይልማ መኮንን ጋርም የሕፃንነት ዘመን አላሳለፉም፡፡
በወቅቱ የሐረርጌ ገዢ የነበሩት አባታቸው ራስ መኮንን ወልደ ሚካኤል (አባ ቃኘው) ከሣህለ ሥላሴ ንጉሠ ሸዋ ከሚወለዱት እናታቸው ከልዕልት ተናኘ ወርቅ ሣህለ ሥላሴና ከአባታቸው ከአቶ ወልደ ሚካኤል ጉዲሳ የሚወለዱ ሲሆኑ፣ በተመሳሳይ የትውልድ ሐረግ ከንጉሥ ኃይለ መለኮት ሣህለ ሥላሴ ለሚወለዱት ለዳግማዊ አፄ ምኒሊክ (አባ ዳኘው) የአክስት ልጅ ነበሩ፡፡ ራስ መኮንን ተፈሪን ገና ትምህርት ሲጀምሩ የፈረንሣይኛን ቋንቋ እንዲያጠኑ በማድረጋቸው ንጉሡ በሥልጣን ዘመናቸው ከአማርኛ ቀጥሎ ፈረንሣይኛን እንደ አንድ መግባቢያ ቋንቋ ይጠቀሙበት እንደነበር ይታወቃል፡፡
በልጅነታቸው የጭምትነት ባህርይ ይንፀባረቅባቸው እንደነበር የሚታወቁት ተፈሪ፣ በ1897 ዓ.ም አባታቸው በማረፋቸው ምክንያት የሐረርጌ ግዛት ለወንድማቸው ለደጃዝማች ይልማ መኮንን ሲተላለፍ እሳቸው ከሐረርጌ ወደ አዲስ አበባ እንዲመጡ ተደርጎ፣ ለአምስት ዓመታት ያህል አዲስ አበባ በዳግማዊ አፄ ምኒሊክ ቤተ መንግሥት ውስጥ የቤተ መንግሥት ሥርዓት በቅርብ እየተከታተሉ አድገዋል፡፡
ታላቅ ወንድማቸው ደጃዝማች ይልማ መኮንን ከሦስት ዓመታት በኋላ ሲያርፉ ሐረርጌ ከሲዳሞ ጋር እንዲቀላቀል ተደርጎ በወቅቱ የሲዳሞ ገዥ ለነበሩት ለደጃዝማች ባልቻ ሳፎ (አባ ነፍሶ) ተላልፎ በተደራቢነት ሲተዳደር ቆየ፡፡ ይሁን እንጂ ከሁለት ዓመታት በኋላ በ1902 ዓ.ም በእቴጌ ጣይቱ አሳሳቢነት ሐረርጌ ለደጃዝማች ተፈሪ እንዲተላለፍ በመወሰኑ፣ በ18 ዓመት ዕድሜያቸው ወደ ሐረር በመዛወር እስከ 1909 ዓ.ም የልጅ ኢያሱ መንግሥት መውደቅ ድረስ ግዛቱን ሲያስተዳድሩ ቆዩ፡፡ በ1909 ዓ.ም የልጅ ኢያሱ መንግሥት በሸዋ መኳንንት ሴራ እና በቀሳውስቱ ድጋፍ ሲገረሰስና ዘውዲቱ ምንሊክ በንግሥተ ነገሥታትነት ሲሾሙ፣ ከዚያ በፊት ባልተለመደ ሥርዓት ተፈሪ መኮንን የንግሥቲቱ አልጋ ወራሽ ሆነው በመሾም በ25 ዓመት ዕድሜያቸው ወደ አዲስ አበባ ጠቅልለው መጡ፡፡
ተፈሪ መኮንን በአልጋ ወራሽነት ሥልጣን ላይ በነበሩበት የ13 ዓመት ተኩል ጊዜ ውስጥ በውጭ ፖሊሲ በኩል አገሪቱን ወደ ዘመናዊ አስተዳደር ለማምጣት፣ በአውሮፓ ለመጀመርያ ጊዜ በከፍተኛ ባለሥልጣን ደረጃ ጉብኝት በማድረግና በአገር ውስጥ ከነበሩ ኤምባሲዎች ጋርም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በማጠናከር ከፍተኛ ስኬት ያስመዘገቡ ታላላቅ ተግባራትን አከናውነዋል፡፡ በተጨማሪም ኢትዮጵያን በዓለም አቀፉ የመንግሥታቱ ማኅበር ቀደምት አፍሪካዊት አገር በማድረግ በአባልነት አስመዝግበዋታል፡፡
በአገር ውስጥም አንፃራዊ ዘመናዊነት እንዲፈጠር ለማድረግ ያደረጉት ጥረት በቀላሉ የሚገመት አልነበረም፡፡ ይሁን እንጂ ያከናወኗቸው አብዛኛዎቹ ስኬቶቻቸው በቆየው የባሕላዊ የአስተዳደር ሥርዓት ውስጥ ለኖረ ኅብረተሰብ ተቀባይነታቸው አናሳ ከመሆኑም በላይ፣ በንግሥቲቱ ዘንድ በጥርጣሬ ሲታዩ በመሳፍንቱና በመኳንንቱ ዘንድ ደግሞ በሥውርም ሆነ በግልጽ የመረረ ተቃውሞ ይገጥማቸው እንደነበር ይታወቃል፡፡
በ1921 ዓ.ም የንግሥቲቱን አስተዳደር የአስገዳጅነት መንፈስ በተላበሰ የማሳመን ዘዴ ከራስነት ወደ ንጉሥነት ማዕረግ ከፍ ያሉት ንጉሥ ተፈሪ በነበሩበት የአልጋ ወራሽነት መንበራቸው ከዲፕሎማሲያዊ ስኬታቸው በተጨማሪ፣ ሁለት የአገር ውስጥ ማለትም የሰገሌንና የአንቺም ጦርነቶችን በማሸነፍ የልጅ ኢያሱንና የንግሥት ዘውዲቱን ደጋፊዎች አንበርክከዋል፡፡ ከዚህም በላይ የውስጥ ተቃዋሚዎቻቸውን አንድ በአንድ ከጨዋታ ውጭ እያደረጉ በመምጣታቸውና በታሪካዊ አጋጣሚም ሥልጣናቸውን በጥርጣሬ ይከታተሉ የነበሩት ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስና አቡነ ማቴዎስ በተከታታይ በማረፋቸው የተነሳ፣ በ39 ዓመት ዕድሜያቸው ወደ ንጉሠ ነገሥትነት ሥልጣን ሲመጡ በሙሉ የአሸናፊነት ስሜት ነበር፡፡
በትዳራቸውም በኩል ለወሎው ንጉሥ ሚካኤል የልጅ ልጅ ለእቴጌ መነን አስፋው ሦስተኛ ባል ሲሆኑ፣ ከእኚሁ በቁንጅናቸውና በደርባባነታቸው ከሚታወቁ ወይዘሮ ስድስት ልጆች ወልደዋል፡፡ በቁመት አጭር ከሚባሉት ተርታ የሚሠለፉት አፄ ኃይለ ሥላሴ እጅግ መልከ መልካም ሲሆኑ በእነዚያ በጣም ረጃጅም በሆኑት ክብር ዘበኞቻቸው መካከል ሲታዩ የእሳቸው ግርማ ሞገስ ጎልቶ መታየቱ አስገራሚ ነበር፡፡ የ43 ዓመታት ረጅም ዘመን የንጉሠ ነገሥትነት አመራራቸው በአብዛኛው የተረጋጋና ሰላም የሰፈነበት ሲሆን፣ በግላቸውም የሚከተሉት ፍልስፍና እንዲሁ የሰከነ ነበር፡፡
ማለዳ ቤተ ክርስቲያንን ከመሳለም የሚጀምረው የየዕለቱ ተግባራቸው የውጭ አገር ከፍተኛ ባለሥልጣኖችን በመቀበል የልማት መሠረት ለመጣል፣ በሕዝባቸው መሀል በመገኘት የተመራቂዎችን ልብስ ለብሰው ወጣቶችን በመመረቅ፣ በዓለም አቀፍም ሆነ በአገር አቀፍ ስብሰባዎች ላይ በመገኘት ጋዜጣዊ መግለጫ የመስጠት ተግባሮቻቸው ጎልተው የሚታዩ ነበሩ፡፡ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን ለየት የሚያደርጋቸው ታድያ ይኼ ሁሉ ሲከናወን የባህርይ መለዋወጥ አለመታየቱ ነበር፡፡
ንጉሡ አዲስ አበባ ካሉ ከማለዳ ቤተ ክርስቲያን ፀሎትና ከእራት በኋላ የሚታዩ የምሽት ፊልም ፕሮግራሞች ምንግዜም አይቀሩም፡፡ አመጋገባቸው በዛ ያለ ቁርስና ለስለስ ያሉ አትክልት የሚበዛባቸው መጠነኛ ምሳና ራት ሲሆኑ፣ መጠኑ አነስተኛ የሆነ ሻምፓኝ ወይም ወይን ይጠቀማሉ፡፡ ጥሬ ሥጋ ባይመገቡም የሚመገብ ሰው ማየቱ ያስደስታቸዋል፡፡ ፀሐይ ረገብ ስትል በቤተ መንግሥቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ የእግር ጉዞ በማድረግ ሰውነታቸውንም ሆነ አዕምሮአቸውን ያዝናናሉ፡፡ የጠቅላይ ግዛት ጉዞ ካደረጉ ደግሞ እዚያው በሚያድሩበት ቤተ መንግሥት ማምሻውን ከሚቀርቧቸው ዕውቅ ሰዎች ጋር (ከ1953 ዓ.ም. በፊት እቴጌይቱንና አባ ሃናን ይጨምራል) በጥቂት ብሮች ካርታ በመጫወት ጊዜያቸውን ያሳልፋሉ፡፡ በንግግራቸው ውስጥ መረር ያለ ቃል ላለመናገር በእጅጉ የሚቆጠቡት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፣ ፈገግ ያሉለትም ሆነ ወስላታ በሚል ቃል የሸነቆጡት ባለሥልጣን ሁለቱም ተደስተው እንዲውሉ የማድረግ ተፅዕኖ ነበራቸው፡፡

የብዙ ኢትዮጵያውያንን ልብ ለማማለልና የግል ሰብዕና ለመገንባት የጋዜጦች የፊት ዓምድና የሬድዮ ግንባር ቀደም ዜና የመሆንና ራሳቸውንና ራሳቸውን ብቻ ከፍ የማድረግ ፍቅር እንደነበራቸው የሚታወቁት ንጉሠ ነገሥት፣ ስሜታቸውን የመቆጣጠር ብቃትና ጠላታቸውን ሚስጢራዊ በሆነ ሁኔታ ጠልፎ ለመጣል ያላቸው ልዩ ችሎታ በቀላሉ የሚገመት አልነበረም፡፡ ይኼ ልዩ ችሎታቸው እንደሳቸው ለውጥ አፍቃሪ በነበሩት ልጅ ኢያሱ ላይ በሰላም ወቅት ባከናወኑት መረጃን የማሰባሰብና የማሰባጠር፣ ከዚያም በችግር ጊዜ አቀናጅቶ በመጠቀም የማሸነፍ ብቃታቸው ተረጋግጧል፡፡ ከዚህም አልፎ የሚቀናቀኑዋቸውንና እኛም የንግሥ ዘር አለን የሚሉትን በዝምድና መረብ ውስጥ በማስገባት ዋነኞቹን በቅርብ ለመቆጣጠር፣ ከአልጋው አጠገብ አስቀምጠው ግዛቱን በእንደራሴ ማስገዛታቸው ለየት ያደርጋቸዋል፡፡ የሥልጣናቸውን አንዲት ነቁጥ መስጠት እንደማይፈልጉ ለማስታወስ ደግሞ ጸሐፌ ትዕዛዝ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስን አንስተው የመወርወር ያህል ከሥልጣን ሲያነሱ የተጠቀሙባቸው ሥልቶች ስለጃንሆይ ማንነት መመስከር ይችላሉ፡፡
በአጨካከናቸው ደግሞ ደጃዝማች በላይ ዘለቀን ከእነ ወንድማቸው በአደባባይ ለመስቀል ከባንዶች ጀርባ መሠለፋቸው፣ በእነ ቢትወደድ ነጋሽ በዛብህ መዝገብ ቀርበው ከ1943 እስከ 1966 ዓ.ም. ድረስ ለ23 ዓመታት በብረት ሰንሰለት ታስረው የነበሩትን የእነ አለቃ ፈጠነን እስር ማስታወሱ፣ እንዲሁም በጄኔራል መንግሥቱ ንዋይ መዝገብ ተከሰው ፍርድ ቤት እስር የፈረደባቸውን ሻምበል ክፍሌ ወልደ ማርያምንና የመቶ አለቃ ድጋፍ ተድላን በሞት መቅጣታቸው ከብዙ በጥቂቱ ናቸው፡፡ እስካሁን መላ ያልተገኘላቸው የንግሥት ነገሥታት ዘውዲቱ፣ የሌተና ጄኔራል መርዕድ መንገሻ፣ የሠዓሊ አገኘሁ እንግዳ፣ የተማሪ ጥላሁን ግዛውና የጋዜጠኛ አሳምነው ገብረ ወልድ ድንገተኛ ሕልፈቶች፣ መሰል ሚስጢራዊ ግድያዎችና አፈናዎች የእሳቸው ዕውቀት እንዳለባቸው ይጠረጠራል፡፡
ጃንሆይ የአገሪቱን የወደፊት ፖሊሲ ለመቅረፅም ሆነ የተቀረፀውን ወደ ግብ ለማድረስ በአማካሪነት የሚጠቀሙባቸው ኃይሎች በሁለት ይከፈላሉ፡፡ እነዚህም በአንድ ወገን በነባሩ የባላባት አስተዳደር ታቅፈው ከጥንቱ ከመሠረቱ አብረዋቸው የመጡት ሲሆኑ፣ በሌላው ወገን በኩል ደግሞ በእሳቸው ዘመን ተምረው ለሥልጣን የበቁና በአንፃራዊነት ወጣት የሆኑት ናቸው፡፡ ጃንሆይ እነዚህን ሁለት በዘመንና በአመለካከት ልዩነት በጣም የሚናናቁ ክፍሎች በተለያየ ሁኔታ በመያዝና ቅራኔያቸውን በመጠቀም፣ ከእነሱም ሆነ ከሌላ ከማይታወቅ አቅጣጫ ወደሳቸው የሚወረወረውን ትችት አቅጣጫ ሲያስቱና “እሳቸው ምን ያድርጉ” የምትሰኘውን አማላይ ሐረግ ሲያንሸራሽሩ ኖረዋል፡፡
በዘመናቸው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እንደ ሰው ደስታም ሐዘንም ጎብኝቶዋቸዋል፡፡ ሐዘናቸው ግን ከሌሎች ሐዘኖች ይለያልም ይከብዳልም፡፡ እናታቸውንና አባታቸውን በሕፃንነት ወራቸው የተነጠቁት ንጉሠ ነገሥት ባልተሟላ የቤተሰብ ፍቅር ውስጥ በብቸኝነት ማደጋቸው ሳያንስ፣ በዕድሜ ጎልምሰው ትዳርም ሥልጣንም ከያዙ በኋላም ይኸው ሐዘን ከቤታቸው ባለመውጣቱ መሪር ሐዘን በማስተናገድ አብዛኛዎቹን ልጆቻቸውን በተከታታይ ቀብረዋል፡፡ በተደጋጋሚ በሐዘን የተጎዱት እኚህ ሰው ልጅን መቅበር ምን ያህል ፈታኝ እንደሆነ በሚያሳይ ሁኔታ እንደ ንጉሥ ሳይሆን እንደ አባት ወላድ ይፍረደኝ ብለው በአደባባይ አልቅሰው አስለቅሰዋል፡፡ እሳቸው ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ በሕይወት የነበሩት ልጆቻቸው ሁለት ብቻ ነበሩ፡፡ በተጨማሪም የብዙ ዘመን ባለቤታቸውን ለረጅም ዓመታት በፅናት ሲያስታምሙ ቆይተው በሞት ሲለዩዋቸው፣ በመጨረሻዎቹ የአዛውንት ዕድሜያቸው ለ13 ዓመታት በብቸኝነት ኖረዋል፡፡

ጃንሆይ በቀደመው የአልጋ ወራሽነትና የንጉሠ ነገሥትነት ዘመናቸው ከብዙ መኳንንቶቻቸውና መሳፍንቶቻቸው አንፃር ሲታዩ (ልዑል ራስ እምሩን አይጨምርም) አንፃራዊ ዘመናዊ አመለካከት ነበራቸው፡፡ በዚህም አመለካከታቸው ብዙዎች ባለሥልጣኖች ለንጉሡ በጎ ስሜት አልነበራቸውም፡፡ ይኼ ስሜት ሰብዕናን ከመፈታተንም አልፎ እስከ ማስወገድ በሚደርስ ጥረት ተመንዝሯል፡፡ ይኼንን ለመከላከልና የዚህ የተራማጅ አስተሳሰባቸው ደጋፊ የሚሆን ምሁር ለመፍጠር ባልተለመደ ሁኔታ፣ የትምህርት ሚኒስትርነቱን ሥልጣን ደርበው በመያዝ በአገሪቱ ትምህርትን በማስፋፋት ሥራ ላይ ተጠምደው ኖረዋል፡፡ በማብቂያ ዘመናቸው ግን ያለመታደል ሆኖ እንዲያግዙዋቸው የፈጠሯቸው ምሁራን ተራማጅ ሆነው እሳቸውን በአድኅሮት ጎራ መድበው ታገሉዋቸው፡፡ ይኼ ሁኔታ ንጉሡን የሁለት ዘመን ትውልድ አጣብቂኝ ውስጥ በመክተት በቀደመው ዘመን ተራማጅ፣ በአዲሱ ዘመን ደግሞ አድኃሪ አድርጎ ወገን አልባ አደረጋቸው፡፡
ሰው ለሰው መድኃኒት እንደሆነ ሁሉ ቁስልም ይሆናል፡፡ የጃንሆይ አስተዳደር ወደ ውድቀት እያዘመመ መምጣቱን በማሳየት ለለውጥ እንዲዘጋጁ የሚጠቁሙዋቸው ኃይሎች የመኖራቸውን ያህል፣ ከሕልፈታቸው በኋላም እንኳን ቢሆን ይህቺኑ አገር በአጥንታቸው እንደሚመሩ እየማሉና እየተገዘቱ የሚነግሩዋቸው ዜጎችም ነበሩ፡፡ ይሁን እንጂ በትክክል ከተመዘነ ለንጉሠ ነገሥቱ ክብርና ለአገሪቱ ሰላም የማሰኑት የመጀመርያዎቹ ጠቋሚዎች ነበሩ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የ1948ቱ የጸሐፌ ትእዛዝ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ ዘመናዊ አደረጃጀት ምክረ ሐሳብ፣ የ1953ቱ የጄኔራል መንግሥቱ ንዋይ መፈንቅለ መንግሥት አንግቦ የተነሳው ሕገ መንግሥታዊው የፓርላማ ሥርዓትና የ1958ቱ የአምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ የምክር ደብዳቤ ዋና ዋናዎቹ ነበሩ፡፡ ጃንሆይ ግን እነዚህንና በተለይም የገጠሩን ሕዝብ እግር ከወርች ጠፍንጎ የያዘውን የመሬት ሥሪት እንዲያሻሽሉና የመንግሥታቸውንም ፍፃሜ ዘመናዊ በሆነ መንገድ እንዲያሸጋግሩ ከቅርብ ወገኖቻቸው ጭምር የተሰጣቸውን ማሳሰብያ በክህደት መዝግበው፣ አገሪቱንም ሆነ ራሳቸውን ወደ ጥፋት ለመሩ አድናቂዎቻቸው አጉል ምክር ተገዙ፡፡ መጨረሻቸው ከፋ፡፡
ያም ሆነ ይኼ ግን ኢትዮጵያን ከምሥራቁም ሆነ ከምዕራቡ ዓለም በመወዳጀት የ1950ዎቹንና የ1960ዎቹን የቀዝቃዛው ጦርነትና የሁለቱን ልዕለ ኃያላን ጫና በመቋቋምና ለአገራቸው በሚጠቅም መንገድ በማጫወት የሚደነቁት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አገር የሚመሰክርላቸው፣ ከአንደበታቸው ክፉ የማይወጣ በስሜት የማይነዱ ጨዋ ሰው ነበሩ፡፡ ንጉሡ አዛውንት ነበሩ፡፡ የረጅም ታሪክ ባለቤት የሆነች አገር መሪ ነበሩ፡፡ የአፍሪካም አባት ነበሩ፡፡ ለአንዳንዶቹም የምድር ላይ አምላክ ነበሩ፡፡ ባሳደጉዋቸው ወታደሮች እጅ ተጎሳቁለው ማለፋቸውና ከረጅም ጊዜ በኋላም እንኳን ኦፊሴላዊ ሥርዓተ ቀብር መነፈጋቸው ፈጽሞ ትክክል አልነበረም፡፡
አጭር ማስታወሻዬን ሳጠቃልል ለታሪክ ጸሐፍትና ለሐያስያን፣ እንዲሁም ለቀድሞው መንግሥትና ለገዢው መንግሥት ባለሥልጣናት ማሳሰቢያ በመስጠት ነው፡፡ በቅድሚያ የታሪክ ጸሐፍትና ሐያስያን ንጉሠ ነገሥቱን እንደ ሰው በማየት ለአስተዋፅዎቻቸውም ሆኑ ለስህተቶቻቸው እኩል ዕውቅና ቢሰጡ፡፡ አስተዋፅዎቻቸውን ስናደንቅ ስህተቶቻቸው በሌሎች ደግመው እንዳይፈጸሙ በገሃድ ቢኮነኑ፡፡
በመቀጠልም ሚስጥራዊ ለሆነው ሕልፈታቸውና ከመሞታቸውም በፊት ለደረሰባቸው የሕሊና ጉዳትና የአካል መጎሳቆል ኃላፊነቱን ወስደው የቀድሞ መንግሥት ባለሥልጣናት በጋራ ወይም በተወካዮቻቸው አማካይነት በገሃድ ይቅርታ ቢጠይቁ፡፡

ሥርዓተ ቀብራቸውን በተመለከተም አሁን በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ኦፊሴላዊ በሆነ መንገድ እንደ አንድ ንጉሥ ነገሥት ራሳቸው ባሳነፁት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ውስጥ ሥርዓቱን በሙሉ ንጉሣዊ ክብር ቢያስፈጽም፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ይኸው መንግሥት ከማንም በላይ ተጋድሎ አድርገው በፈጠሩት የአፍሪካ ኅብረት ሕንፃ ውስጥ መታሰቢያቸውን በጉልህ እንዲቀመጥ ቢያደርግ ለሚቀጥለው ትውልድ በጎነትንና መከባበርን ከነሙሉ ግብሩ በማስተላለፍ ለአገሪቱ መልካም ገጽታ ለመፍጠር መንደርደሪያ ይሆነናል ብዬ አምናለሁ፡፡
ሰላም እንሁን

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dereje460@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

Standard (Image)

ይድረስ ለክቡር አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ

$
0
0

‹‹የሠራዊት ግንባታ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ›› የሚለው መጽሐፍ ይታገድ!

በአበበ ተክለሃይማኖት (ሜጀር ጄኔራል)
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር
በተለያዩ ጊዜያት ለመጠቆም እንደሞከርኩት አንዳንድ ጊዜ እንደ ተቋም ሌላ ጊዜ በከፍተኛ መኮንኖች ፀረ ሕገ መንግሥት የሆኑ ድርጊቶች እየተስተዋሉ ነው፡፡ የአገራችን መከላከያ ተቋም ሕገ መንግሥቱና ሕገ መንግሥቱን ብቻ መሠረት አድርጎ መንቀሳቀስ ሲገባው በግላጭ ሕገ መንግሥቱን የመጣስ ክስተቶች እየታዩ ነው፡፡ አንድ ፀረ ሕገ መንግሥት ተግባር ሲጠቆም በማረም ፈንታ በማናለብኝነትና በኅብረት በባሰ ሁኔታ እየተደገመ ነው፡፡ ለምን? የሠራዊቱ አመራሮች ሕገ መንግሥቱን ጠንቅቀው አያውቁም ብሎ ለማመን አስቸጋሪ ነው፡፡
አንዳንድ ጊዜ አሁን ሥራ ያሉ ከፍተኛ መኮንኖች ሌላ ጊዜ በጡረታ የተሰናበቱ ‹‹እንዲሁም እንከን በሌለው መተካካት›› የተገለሉ ከፍተኛ መኮንኖች ጋር ለመወየያት ዕድል አጋጥሞኛል፡፡ ከወርቃማው የ1997 ዓ.ም. አጠቃላይ ምርጫ በኋላ ሕዝቦችን ለመቆጣጠር እንደ ተወሰዱት ፀረ ዴሞክራሲያዊ ፖለሲዎች፣ መመርያዎች፣ አሠራሮችና ተግባሮች በመከላከያ ተቋም ገብተዋል እንዴ? የሚል ጥያቄ ሲያጭርብኝ ቆይቷል፡፡ ሕገ መንግሥቱን መፃረር የሠራዊቶችን ሕዝባዊነት፣ ጀግንነትና ብቃት የሚሸረሽር በመሆኑና ሰላማዊ ፖለቲካዊ ትግሉን የሚያበላሽ በመሆኑ ለማንኛውም ኢትዮጵያዊ የሚያሳስብ ነው፡፡ ‹‹የሠራዊቱ ግንባታ በአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ›› የሚለውን ጽሑፍ ሳነብ ግን መሠረታዊ ችግሩ በከፊልም ቢሆን የት ላይ እንደሆነ ሊገለጥልኝ ቻለ፡፡ ሠራዊቱ የገዥው ፓርቲ ርዕዮተ ዓለም አራማጅ የኢሕአዴግ ‹‹የመጨሻው ምሽግ›› እንዲሆን ወይም ‹‹ቀባሪው›› እንዳይሆን መገንባት ከተጀመረ አገሪቱን ወደ ከፍተኛ ችግር ማስገባት ግድ ሆኗል፡፡ የፓርቲው ውስጣዊ ፖለተካዊና ዴሞክራሲያዊ ሕይወት በተዳከመበት ሁኔታ ደግሞ የተወሰኑ አመራሮች ‹‹የመጨረሻ ምሸግ›› ይሆናል ማለት ነው፡፡ በመከላከያ ሚኒስቴር ሥር የሚገኙው ‹‹ብራና ማተሚያ ድርጅት›› የታተመው መጽሐፍ 209 ገጾች ያሉት ሲሆን፣ ሕገ መንግሥቱንና ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› የሚለውን ርዕዮተ ዓለም በማደባለቅና በማምታት ስለሠራዊት ግንባታ ይዘባርቃል፡፡
ክቡር የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ
መጽሐፉ ‹‹የሠራዊት ግንባታ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ›› ነው የሚለው፡፡ ሰነዱ ከእሱ ጀምሮ ምን ማለት መሆኑ ቢታወቅም የበለጠ ግልጽ ለማድረግ የተለያዩ ጥቅሶችን ማስቀምጥ ይበጃል ከሚል ስለሆነ እንዲፈቀድልኝ በትህትና እጠይቃለሁ፡፡ በገጽ 20(2፡3) የመከላከያ ኃይል ግንባታ ዓላማችን በሚል ርዕስ፣ ‹‹እኛ የያዝነው ዓላማና ተግባራዊ ያደረግነው ያለመደብ በአገራችን አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ለውጦች እንዲካሄዱ ይህ ሥርዓት ሥር እንዲሰድ ማድረግ ነው፡፡›› በገጽ 22 ‹‹እኛ የምንገነባው የመከላከያ ኃይል ለአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችን ዘብ ነው ብለን በግልጽና በጥሬው ማስቀመጥ አስፈላጊ ነው፤›› ይላል፡፡ ምን ዓይነት እብሪት ነው? ‹‹ለአንድ ፓርቲ ዘብ በመሆን መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ ከፓርቲው ውጭ ሆነም ሥርዓቱን እንደ ሥርዓት ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በመጠበቅ አንፃር ሊገለጽ ይችላል፡፡ (23)››
‹‹በእኛ ተጨባጭ ሁኔታ በአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችን ደኅንነት መከላከል ማለትና የአገር ደኅንነት መከላከያ ማለት በመሠረቱ አንድ ነው ማለት ይቻላል፡፡ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ከሌለ ፈጣንና ቀጣይነት ያለው ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ ልማትና ዴሞክራሲያዊ አንድነት፣ ወዘተ. አይኖርም፡፡ ይህ ከሌለ ደግሞ አገሪቱ መጨረሻ ወደሌለው ቀውስና ግጭት ገብታ መበታተን ነው፡፡ ስለሆነም አገሪቱ እንደ አገር መቀጠል የምትችለው በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ነው ማለት ይቻለል፡፡ ከዚህ አኳያ ሲታይ አገራችንን መከላከልና አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን መከላከል አንድና የማይነጣጠሉ ነገሮች ናቸው ማለት ይቻላል፡፡›› (25.26)
‹‹ስለሆነም ለእኛ የአገራችን አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችን ደኅንነት መከላከል (መጠበቅ) የተለያዩ ነገሮች አይደሉም፡፡ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችን ከሌለ እኛ የምንላት አገር አትኖርም፡፡›› (27) የምንገነባቸው በመከላከያ ኃይል ዓላማው የሥርዓታችንን ደኅንነት መጠበቅ ነው ሲባል የሚገነባውና የሚመራው የሥርዓቱ መሪ የሆነው አካል ብቻ መሆን አለበት ነው፡፡›› (28) ‹‹የመከላከያ ኃይላችን ግንባታ ሥራ ዓላማው ምን እንድሆነና ከዚህ የሚመነጩ የመከላከያ ኃይላችን ባህሪያት ምን እንደሚሆኑ በግልጽ ለያይቶ ማስቀመጥ በዚያች ቁርጥ ቀን ማለት የሥርዓታችን ሕልውና በመከላከያ ኃይላችን ብቃትና ምንነት ላይ በምትንጠላጠልበት ጊዜና ወቅት አስተማማኝ መከላከያ ምሽግ መሆኑን በማረጋገጥ በኩል ወሳኝ ሚና ያለው ጉዳይ ነው፡፡ (ገጽ 31) ‹‹ጉዳዩ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ሥርዓቱ በመጨረሻ መከላከያ ምሽግ የሌለው ሥርዓት ሆኖ እንዳይቀር በማድረግ ወይም በመከላከል ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፣ ጠባቂዬና አለኝታዬ ብሎ የሚለው ሠራዊት ተመልሶ ቀባሪው ሆኖ እንዳይገኝ የማድረግ ጭምር ነው፡፡›› (ገጽ 81)
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር
የኢትዮጵያ መከላከያ ተቋም የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ብሎም የኢሕአዴግ ‹‹ጠባቂ›› እንዲሆን፣ በሌላ አነጋገር የጥቂት ሰዎች ‹‹ጠባቂ›› እንዲሆን በተለያየ መንገድ፣ በጭንቀት፣ በልመና የተደጋገመው ጸሎት አይሉት ምህላ በጣም እንደሚሰለች ይገባኛል፡፡ ይቅርታ ይደረግልኝ፡፡ እኔም ስልችት እያለኝ ነው ደጋግሜ ያነበብኩት፡፡ የመከላከያ ተቋም በምን መልኩ ከሕገ መንግሥታችን ተፃራሪ ሆኖ እየሠራ መሆኑን እንዲያሳይ ነው እንጂ፡፡ ሕገ መንግሥታችን በውል መጠቀስ የተጀመረው በገጽ 87 ነው፡፡ የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ‹‹የቁርጥ ቀን›› መከላከያ መሆኑን በተደጋጋሚ ካስረገጠ በኋላ፣ በ2.1 ሕገ መንግሥታችን እንደ ሠራዊታችን ግንባታ መነሻ በማለት ማብራራት ይጀምራል፡፡ መዘባረቁን በሚያሻማ ሁኔታ እየቀጠለ ፀረ ዴሞክራቲክ አስተሳሰብ ደግሞ ከደርግነት ባላነሰ መንገድ ሲገልጸው እንደገና፣ ‹‹ኢሕአዴግ ከሌለ ይህች አገር የለችም›› በሚለው አባባል ሲያመላልሰው ይታያል፡፡ እባክዎ በስፋት እንድጠቅስ እንደገና ይፍቀዱልኝ፡-
‹‹ሕገ መንግሥታችን ለሠራዊት ለፖለቲካ ግንባታ ሥራችን ወሳኝ መነሻ ነው በምንለው ሕገ መንግሥታችን፣ ሠራዊቱ የሕገ መንግሥቱ ታማኝ ጠባቂ መሆን አለበት በማለት በግልጽ ስለሚያስቀምጥ ብቻ አይደለም፡፡ ሌሎች ዴሞክራሲያዊ ሥርዓቶች እንዲህ ዓይነት አካሄድ ስላልተከተሉም አይደለም፡፡ ይልቁንም ይህ አባባል በሕገ መንግሥታችን በግልጽ እንዲቀመጥ የተደረገበት ዋነኛ ምክንያት ሕገ መንግሥቱ የአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ጠባቂ የሆነ ሠራዊት ለመገንባት ለሚካሄደው የፖለቲካ ግንባታ ሥራ በቂና ብቁ መነሻ እንዲሆን ስለታመነበት ነው ማለት ይቻላል፡፡
ቀደም ብሎ እንደተመለከትነው በሁሉም አገሮች በመከላከያ አቅም በሚገነባው አንድን ሥርዓት ከውስጥና ከውጭ ጠላቶች ለመከላከል ተብሎ ነው፡፡ በእኛ ሁኔታም የተለየ ዓላማ ሊኖርው አይችልም፡፡ እኛ የምንገነባው ሠራዊት አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችንን ከውስጥና ከውጭ ጠላቶች ለመከላከል ተብሎ በሚገነባ ሠራዊት ብቻ ነው መሆን የሚችለው፡፡ በአሁኑ ወቅት አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችንና ኢሕአዴግ ተለያይተው ሊታዩ የሚችሉ አይደሉም፡፡ የሊበራል ዴሞክራሲ አስተሳሰብ የበላይነት በነገሠበት ወቅት ሁሉም ፓርቲዎች ማለት ይቻላል መሠረታዊ የሊበራል ዴሞክራሲ አስተሳሰቦችን ተቀብለው፣ በዚህ ዙሪያ ብቻ ነው የሚለያዩት በየጊዜው እየተቀየሩ ወደ ሥልጣን ቢመጡም በሥርዓቱ ላይ የሚመጣ መሠረታዊ ለውጥ የለም፡፡ ስለሆነም ሥርዓቱ ከእያንዳንዱ ፓርቲ ተለይቶ የሚታይና ሊታይ የሚገባው ይሆናል፡፡›› (ገጽ 88 እስከ 89)
ክቡር የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ
የ1997 ምርጫ ሕዝቦቻችን ዕድል ሲያገኙ ምን ማድረግ እንደሚችሉ ያሳየ ነው፡፡ በቀጣዩ ምርጫ ለምሳሌ መድረክ ቢያሸንፍ የመከላከያ ሠራዊታችን በኢሕአዴግ የቁርጥ ቀን በመሆን መድረክን ሥልጣን እንዲቆጣጠር ይከላከሉ? ጠመንጃቸውን በሕዝቦች በተመረጠና በሕዝቦች ላይ ያዞራሉ ማለት ነው? መድረክ በሊበራል አስተሳሰቦች ዙሪያ የተደራጀ በመሆኑ በምርጫ ካሸነፈ አሁን ያለውን መከላከያ ተቋም እንዳለ አፍርሶ ሌላ የራሱን ሊገነባ ማለት ነው? የሆነ ፓርቲ በሰላማዊ መንገድ ባሸነፈ ቁጥር በሚፈርስና የሚገነባ የመከላከያ ተቋም ታይቶም ተሰምቶም አያውቅም፡፡ ለተወሰኑ ሰዎች ለኢሕአዴግ ኃላፊዎች ሲባል አገራችንን ለማፍረስ መዘጋጀት ማለት እኮ ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ አብዮታዊም ዴሞክራሲያዊም አይደለም፡፡ በእኔ አረዳድ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ‹‹ሊበራል ዴሞክራሲ መራመድ እስከሚችለው ጫፍ መውሰድ ነው፡፡›› በሌላ አነጋገር አብዮታዊ ዴሞክራሲ ከሊበራል ዴሞክራሲ በላይ ዴሞክራሲያዊ ነው፡፡ የሕዝቦቻችንን የመወሰን ሥልጣን በተሻለ የሚያምን ነው፡፡ እኛ ካልተመረጥን አገሪቱ ገደል ትግባ የሚል የጽንፈኞች አስተሳሰብ መሆን አልነበረበትም፡፡
ክቡር የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ
በዚህ መጽሐፍ ውስጥ በእውነትና በቅንነት የታመነበት ቢሆን አብዮታዊ ዴሞክራሲ ምን ማለት እንደሆነ ትርጉም ይሰጠው ነበር፡፡ በአሀኑ ጊዜ የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ምንነት በአንዳንድ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ደረጃ ሳይቀር የማይታወቅ መሆኑን በየቀኑ በቴሌቪዥንም በአካል እያስተዋለ ነው፡፡ አንድ ቀን ያጋጠመኝን ላካፍልዎ፡፡ ሦስት ሆነን ስለኢትዮጵያ ሁኔታና ስለአንድ መሪ ስናወራ የልማት መሪም አርበኛም (Champion) ናቸው በሚለው ተስማማን፡፡ አንዱ ተነስቶ የልማት አርበኛ ብቻ ሳይሆኑ የዴሞክራሲ ሻምፒዮን ናቸው አለ፡፡ ሦስተኛው ተነስቶ እስኪ አብራራው አለው፡፡ በጥርነፉ (Centralism) ያምናል አለን፡፡ አፈርን፣ ተሳቀቅን፡፡ ግን ስለዴሞክራሲ ያለው አመለካከት እስከዚያ ድረስ የወረደ መሆኑን በየቀኑ የምናየው ክስተት በመሆኑ አዝነን ይህች አገር ወዴት እየሄደች ነው አልን፡፡
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር
አሁንም በተለያዩ መንገዶች የአገር መከላከያ ተቋምና የኢሕአዴግ አባላት የሥራቸውና የአኗኗራቸው ሁኔታ የተለያየ በመሆኑ መጠነኛ የአቀራረብ ልዩነት ይኖር ይሆን እንጂ አንድ ናቸው ለማለት ከገጽ 100 እስከ 101 እንዲህ ይለዋል፡፡ ‹‹በሠራዊታችን የምናካሂደው የፖለቲካ ሥራ የአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ፖለቲካዊ ግንባታ ሥራ ነው፡፡ ስለሆነም መሠረታዊ የአፈጻጸም አግባብ በድርጅታችን ውስጥ ከምናካሂደው የግንባታ ሥራ የተለየ አይሆንም፡፡ ይህ እናዳለ ሆኖ ሠራዊቱና የኢሕአዴግ አባላት የሥራቸውና የአኗኗራቸው ሁኔታ የተለያየ መሆኑ አይቀርም፡፡ ከዚህ የተነሳ በሁለቱም የግንባታው ሥራ አፈጻጸም አንዳንድ ልዩነቶች ሊኖሩት የግድ ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ የአብዮታዊ ዴሞክራሲ በፖለቲካ ግንባታ ሰፊ መሠረታዊ አፈጻጸሞች እንዳለ ነው የምንወስደው፡፡ የሚዲያው ሥራ በገዛ ራሱ ለኅብረተሰቡ በሚዘረጋውና ሠራዊቱም እንደማንኛውም ሰው በሚሰማው ወይም ገዝቶ በሚያነበው በመንግሥትና በድርጅት ሚዲያ አማካይነት ሊፈጸም ይችላል፤›› ገጽ 116 የግል፣ የሌሎች ድርጅቶች፣ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃንስ?
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር በመጽሐፉ የተለያዩ ጥያቄዎችን ለማንሳት የሚያስችሉ የተዘበራረቁ ጉዳዮች አሉ፡፡ ‹‹እኛ›› ብለው ስለሠራዊታችን ግንባታ የሚጽፉት አመራሮች ‹‹የቁርጥ ቀን›› ደራሽ እንዲሆንላቸው በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ሽፋን በማላወስ እኛን አገልግሉ ከማለት ውጪ፣ ያስቀመጡዋቸው የተለዩ የግንባታ ዓላማዎችና አቅጣጫዎች የሉም፡፡ ከሞላ ጎደል ‹‹በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይና የብሔራዊ ደኅንነት ፖሊሲ›› የተቀመጡ ናቸው፡፡ በአደባባይ ለሕዝብ በቀረበው ፖሊሲ ግን ‹‹የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ወይም የኢሕአዴግ የመጨረሻ መከላከያ ምሽግ አይልም፡፡›› ለምን? ሕገ መንግሥቱ በሰላም እስከታገሉ ድረስ ሕገ መንግሥቱን ራሱን የማሻሻል መብት የሚያስቀምጥ ነው፡፡ ከበላይ ሕጋችን አኳያ ሁሉም በሰላም የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎችና የኅብረተሰብ ክፍሎች እኩል ናቸው፡፡ በሠራዊቱ ልዩ ጥበቃ የሚያስፈልገው ፓርቲ ወይም የሚገለል ወይም የሚመታ ፓርቲ የለም፡፡ የሚገርመው ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ አብዛኛዎቹ የተቃዋሚ ፓርቲዎችና የኅብረተሰብ ክፍሎች ሕገ መንግሥቱ ይከበር ሲሉ የሕገ መንግሥቱ አቀንቃኝ የነበረው ኢሕአዴግ በግላጭ ሲሸረሽር ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› እንደ አድኃሪያን መሸሸጊያ ሲጠቀምበት በጣም ያሳዝናል፡፡ ገዥ ፓርቲ በመሆኑ ደግሞ ያስፈራል፡፡
አብዮታዊ ዴሞክራሲ የሚል ‹‹ምትሀተኛ›› አስተሳሰብ እንዳለና እጅግ የላቀ ልዩ ነገር ‹‹Mystify›› ተደርጎ የማይተነተን የማይታወቅ ሰው በጭፍን እንዲያምነው የሚደረግ ሙከራ አሳሳቢ ነው፡፡ እኔ እስከሚገባኝ ድረስ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ይሁን ሊበራል ዴሞክራሲ ሁሉም ካፒታሊስታዊ ሥርዓት ለመገንባት ዓላማ አድርገው ነው የሚንቀሳቀሱት፡፡ ያውም እስከ ‹‹ነጭ ካፒታሊዝም›› ተብሎ ነበር፡፡ በካፒታሊስት ሥርዓት ከማንም በላይ ተጠቃሚዎች ካፒታሊስቶች ናቸው፡፡ እስከሚገባኝ አብዮታዊ ዴሞክራሲ በሚገባ ከተተገበረ የገበሬዎች፣ የላብአደሮችና የሌሎች ዝቅተኛ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጥቅም በሚረጋገጥበት መንገድ ሥርዓቱን ሊመራ ይችላል፡፡ ሀብት በመፍጠር ሒደት ክፍፍሉ በተቻለ መጠን ፍትሐዊ ማድረግ ነው፡፡ እንደዚያውም ሆኖ አሁንም ዋናው ተጠቃሚ ካፒታሊስቱ ነው፡፡ አሁን እየተመዘገበ ያለውን ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ብቻ እንኳን ብናይ ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚዎች ቢሆኑም፣ በሀብታምና በደሃ መካከል ያለው ልዩነት በጣም እየሰፋ ከመሄድ አላገደውም፡፡ ባልሆነ ተስፋ በማይመስል አስተሳሰብ አገር እንዳይጎዳ መጠንቀቅ ጥሩ ነው፡፡
በገጽ 126 ያለውን እስኪ እንየው፡፡ ‹‹ሁሉም በተራ ውትድርና እንዲያልፍ የሚደረግ አሠራር ከሠራዊታችን ባህሪ ጋር የሚሄድ ብቻ ሳይሆን ለሠራዊታችን የተለያዩ ጥቅሞችም የሚያስገኝ ይሆናል፡፡ ከሁሉ አስቀድሞ ይህ አሠራር ከአብዮታዊ ዴሞክራሲ በከፍተኛ ደረጃ የማይጠቀሙ ወገኖች ወደ ሠራዊቱ በመግባት ፍላጎት እንዳይኖራቸው የሚያደርግና በአንፃሩ በሥርዓቱ በከፍተኛ ደረጃ ተጠቃሚ የሆኑ ወገኖች ብቻ ሠራዊቱን እንዲቀላቀሉ የሚያደርግ አካሄድ ነው፡፡››
ይህ ደግሞ ሌላ አስመሳይነት ይመስለኛል! ከሥርዓቱ በከፍተኛ ደረጃ የማይጠቀሙ ወገኖች ሲባሉ እነማን ናቸው? መሳፍንት? አሁን የሉም የመሳፍንት ልጆች፡፡ ኧረ ተዉ! ኢሠፓ የነበሩ እነሱም ወሳኝ ሚና የላቸውም፡፡ የሚቀሩት ገበሬ፣ ላብአደር፣ ምሁር፣ ካፒታሊስት፣ ወዘተ. ናቸው፡፡ ገበሬው መቼም አይታሰብም፡፡ ላብአደር ተጠቀሚ ተብሏል፡፡ ካፒታሊስቱ የለም፡፡ እሱማ ዋናው ተጠቃሚ ነው፡፡ ምሁሩ ኧረ እንጃ፣ እንዳይፈነግላቸው እየፈሩ ካልሆነ እሱም በጣም ተጠቃሚ ነው፡፡ ታዲያ በከፍተኛ ደረጃ የማይጠቀሙ ወገኖች እነማን ናቸው? ፖለቲካዊ ሥርዓቱ የራሱን ችግር ላለማየት (Externalize) ለማድረግ የሚደረድራቸው ጠላቶች እንዳይሆኑ፡፡ ትምክህትና ጠባብነት በኅብረተሰቡ በሚታዩ ኋላቀር አስተሳሰቦች ናቸው፡፡ የተወሰኑ ልሂቃን ይህን በኅብረተሰቡ ውስጥ ያለውን ኋላቀር አስተሳሰብ መሠረት አድርገው ለራሳቸው ጥቅሞች ሲሉ ሰላማዊ ፖለቲካዊ ሥርዓቱን እንዲናጋ ያደርጋሉ፡፡ እነዚህንም ቢሆን በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ለእነሱ መሠረት የሚሆነው የዴሞክራሲ አስተዳደር እጥረት ነው፡፡ እነዚህን ለማግለል ደግሞ የሠራዊቱን ሙሁራዊ አቅም እየገደለ እንዳይሆን መፈተሹ ተገቢ ነው፡፡
ወደ ሠራዊታችን በመጀመሪያ የሚሠለፈው ከ18 እስከ 23 ዓመት አከባቢ ያለ ወጣት ነው፡፡ የወላጆቹን የመደብ ጀርባ እያዩ ላለማስገባት አሥረኛ ክፍል አስገብቶ በሠራዊቱ በሚደረግ ግንባታ ከፍተኛ አመራር ለመፍጠር በሚደረግ እንቅስቃሴ አደገኛ እንዳይሆን መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ የተማረ ሰው የመጥላት አዝማሚያ እንዳይሆን፡፡
‹‹እኛ›› በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አነጋገር አንድ ሰው ነው፡፡ ምናልባትም ንጉሣዊ ቤተስብ ይሆናል፡፡ ‹‹እኛ›› ማለት ከአንድ ሰው በላይ ቢሆን ማነው? 36ቱ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ? የኢሕአዴግ ምክር ቤት አባላት? ሰባት ሚሊዮን የሚሆኑ አባላት ቢሆኑስ? የአብዮታዊ ዴሞክራሲ አስተሳሰብ ልዕልና እንዳልነገሠ መጽሐፉ በተደጋጋሚ ይገልጽልናል፡፡ ስለዚህ ቢያንስ 100 ሚሊዮን የሚጠጋ ሕዝብ ሠራዊታችን የአብዮታዊ ዴሞክራሲ የመጨረሻ ምሽግ እንዲሆን አልወሰነም፡፡ የሠራዊት ግንባታ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ያለው ‹‹እኛ›› አድኃሪ ነው፣ ፀረ ዴሞክራቲክ ነው፣ ፀረ ሕገ መንግሥት ነው፡፡
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትርና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ
በእኔ አመለካከት ሠራዊታችን የሕዝቦቻችንና የአገራችን አለኝታ የሚሆነው ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥቱን መሠረት ተደርጎ የሚወጣ ፖሊሲ፣ መመርያ፣ አሠራራርና ግንባታ ሲኖር ነው፡፡ የአብዮታዊ ዴሞክራሲ የመጨረሻ ምሽግ ነው ሲባል ግን የሠራዊቱ ምልመላ፣ ሥልጠና፣ ዝውውር፣ ዕድገትና ጡረታ ማራዘም፣ በመተካካተት የሚገለሉት፣ እንዲሁም አጠቃላይ ግንባታ ‹‹በአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ›› መዝሙር በሚዘምሩና ‹‹የአብዮታዊ ዴሞክራሲ›› ወሬ በሚያቀብሉ ሕገ መንግሥቱን በግላጭ የሚጥሱ አባላት ያሉበት ሠራዊት እንዳይሆን ሥጋት አለኝ፡፡ በአጠቃላይ ከሕዝቦቻችን በተለይም ደግሞ ከፖለቲካ ድርጅቶች የሚኖረው ግንኙነት በጣም አሳሳቢ ያደርገዋል፡፡
የኦሮሞ ሕዝቦች ለመብታቻው ባደረጉት ዴሞክራሲያዊ እንቅስቃሴ ለደረሰው ጉዳት እርስዎ ይቅርታ ሲጠየቁ በኢትዮጵያ ውስጥ ባልተለመደ መንገድ ሕዝብን የሚያከብር በመሆኑ፣ ለሕዝብ ይቅርታ በማለት ፈር ቀዳጅ በመሆንዎ ብዙዎቻችን ኮርተናል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የተወሰደው ዕርምጃ ‹‹ተመጣጣኝ›› ነው ሲል እንደገና አፈርን፡፡ ፓርላማው ሲያፀድቀው የባሰ ተሸማቀቅን፡፡ ዴሞክራሲያዊ አስተዳደርን በማበላሸት ዋናው ተጠያቂ የኢሕአዴግ መንግሥት ሆኖ እያለ፣ በዜጎች ላይ የደረሰው ጉዳት ተመጣጣኝ ሲባል ያሳዝናል፡፡ እነዚያ የሞቱት፣ የቆሰሉት፣ የታሰሩት በሙሉ አሸባሪዎች ናቸው ማለት ነው?
በአጠቃላይ የሥርዓቱ ጉዳይ ግን እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤታችን ስለመከላከያ በየጊዜው የሚገመግመው ‹‹እንደ መከላከያ የለም የሚያሰኝ ነው››፡፡ እንዲህ ያለመሠረታዊ የግንባታ ዶክመንትና ሕገ መንግሥቱን በሚፃረር መንገድ የሠራዊቶቻችን ግንባታ ሲካሄድ ‹‹ዓይኑ እንዳላየ›› ‹‹ጆሮው እንዳልሰማ›› ማወደስ የማይሰለቸው ተቋም መሆኑና በእርስዎም የሚመራው የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤቱም ከዚህ አኳያ ቢፈተሽ መልካም ይመስለኛል፡፡
ሠራዊታችን የአብዮታዊ ዴሞክራሲ የመጨረሻ መከላከያ ምሽግ ነው የሚለው አስተሳሰብ፣ ኢሕአዴግ ከሌለ የኢትዮጵያ ሕዝቦች የሉም፡፡ የዚህች አገር ችግሮች በኢሕአዴግ ብቻና ብቻ ይፈታሉ፡፡ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ከሌለ አገር የምንለው የለም፡፡ የሕገ መንግሥት ምሰሶ ከሆኑት አንዱ ተቋም የሆነው መከላከያችን ከየትኛውም ዓይነት የፖለቲካ ድርጅት ወገንተኝነት ነፃ ይሆናል የሚለውንና የሕገ መንግሥቱ አንኳር የሆነውን የመድብለ ሥርዓት ግንባታ የሚፃረር ይሆናል የሚለውን አስተሳሰብ የወለደ በመሆኑ፣ እነዚህ የግንባታ ጽሑፎች እንዲወገዱ ነገር ግን የሕገ መንግሥት ጠማማ አተረጓጎም ለአገር ጥፋት እንዴት እንደሚውል የሚያሳይ በመሆኑ ግን እኛም ልጆቻችንን እንድንማርበት በሙዚየም ውስጥ እንዲቀመጡ፡፡ በአስቸኳይ የማስተካከያ ዕርምጃ እንዲወሰድና በአጠቃላይ መከላከያ እንደ ተቋም እንዲፈተሽና ሥርፀት (Reindoctration) እንዲደረግ እንደማንኛው ዜጋ በትህትና እጠይቃለሁ፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የቀድሞ የኢሕአዴግ ታጋይና የአየር ኃይል ዋና አዛዥ የነበሩ ሲሆን፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

Standard (Image)

ትናንትን ስናስብ ነገን እናጣለን

$
0
0

በጌታቸው አስፋው
ለነገ የሚጠቅም ትናንት አለ፡፡ ለነገ የማይጠቅም ትናንትም አለ፡፡ ወደ ነገ ስለሚያራምደው ትናንት ዛሬ ማሰብ ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም፡፡ ለዛሬና ለነገ የማይጠቅመው ትናትን እንደ ታሪክነቱ መጠናት፣ መጻፍና መታወቅ ቢኖርበትም የትናንትን እያወራን በትናንቱ ዛሬ ከኖርንበት ከተጨቃጨቅንበት፣ ለነገ ሳንሠራ በከንቱ ካሳለፍነው ጊዜ ቆሞ አይጠብቀንምና የሚጠቅመውን ነገን እናጣለን፡፡
‹‹የገደለው ባልሽ የሞተው ወንድምሽ ሐዘንሽ ቅጥ አጣ ከቤትሽ አልወጣ›› ሆነች የዚህ ዘመን ኢትዮጵያ፣ ከጭቅጭቅም አልፈን መሣሪያ ተማዘናል፡፡
የፖለቲካ ሰዎች ‘ጎበና እንዲህ አደረገ፣ ምኒልክ እንዲህ አደረገ፣ ጦና እንዲህ አደረገ፣ ኃይለ ሥላሴ እንዲህ አደረገ…’ እያሉ እርስ በርስ ይጎነታተላሉ፡፡ ሞሶሎኒ ሰው ስላልገደለባቸው ሳይሆን ዛሬ የሞሶሎኒ ልጆች መሬታቸውንና ሥልጣን ስለማይጋሯቸው፣ የሞሶሎኒን ስም በዓመት አንዴ የድል በዓልን ለማክበር ካልሆነ በክፉ አያነሱም፡፡ ወይም ጣሊያን የቆቃ ግድብን ለደም ካሳ ገድባ የሙት ስም በከንቱ እንዳይነሳ አደረገች፡፡
ከመቶ ዓመት በፊት የሞተን ሰው ስም እያነሱ ለራሳቸው የዛሬን ሥልጣን ለማመቻቸት ሰውና ሰውን በማጋጨት በፖለቲካ የሚነግዱ ሰዎች፣ ዛሬ ለሕዝብ ጥቅም መሥራት የሚገባቸውን አልሠሩምና ነገ የእነሱ አይደለም፡፡
ከዚህ በላይ የቀረበው መንደርደሪያ ሐሳብ ፖለቲካዊ ንድፈ ሐሳብን ከኢኮኖሚያዊ ቁሳዊ ሕይወት ውጪ በመመልከት፣ ለግል ሥልጣን ሲሉ ሕዝብን ከሕዝብ ለማጋጨት የሚመር የፀብ መርዝ የሚረጩ ሐሳባውያን ፖለቲከኞች ራሳቸው ተጎድተው ሕዝብንም እንዳይጎዱ የማሳሰቢያ ጽሑፍ መግቢያ እንዲሆነኝ ነው፡፡
አገር በቀል ሐሳባዊ ፖለቲካ
በአገር ውስጥ የሚገኙ ሐሳባውያን ፖለቲከኞች በሚናገሩትና በሚጽፉት የፖለቲካ ወሬና መርዘኛ የፀብ ሐሳብ፣ ለዛሬና ለነገ የሚጠቅምና ዛሬና ነገን የሚገልጽ የኢኮኖሚ ጉዳይ ወይም የቁሳዊ ሕይወት መነሻ አጣሁበት፡፡
ሕዝቡን በሚቀልቡት በአዕምሯቸው ውስጥ በተፈጠረ ሐሳባዊ ፖለቲካ ወሬ ሲሻቸው የግል አርነትን ይሰብካሉ፣ ሲሻቸው በቡድን ይጠይቃሉ፣ ሲሻቸው የዛሬውን ፖለቲካ ትተው የትናንቱን ታሪክ መዝዘው ይጨቃጨቃሉ፡፡
‘እኔ የአክስቱ ልጅ እያለሁ ለምን ባዕድ ያስተዳድረዋል?’ በሚል ጠባብ ፍልስፍናቸው ኢኮኖሚውን ትተው ስለፖለቲካው ብቻ እያወሩ፣ ለሕዝቡ ዳቦ የሚያስገኝ የኢኮኖሚ ኑሮ ብልኃት ይቅርና ቂጣ እንኳ መጋገር የማያስችል የኢኮኖሚ ዕውቀትና ብልኃት እንደሌላቸው ይጋለጣሉ፡፡
በሚሊዮን የሚቆጠሩ አያት ቅድመ አያቶቻቸው በመርዝ ጭስ ያለቁባቸው አይሁዶችና ጀርመኖች በደላቸውን ረስተው በኢኮኖሚ ጥቅም ተሳስረው አብረው ይኖራሉ፡፡ በአንደኛውና በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በመርዝ ጭስ የተጨራረሱ አውሮፓውያን አንድ የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ ፈጥረዋል፡፡
ጃፓን የሂሮሺማና የናጋሳኪን የኃይድሮጂን ቦምብ ዕልቂት ረስታ ከአሜሪካ ጋር ጥብቅ ወዳጅ ሆናለች፡፡ ምዕራብ አፍሪካውያን ከቀድሞ ቅኝ ገዥዎቻቸው ፈረንሣዮች ጋር የጠበቀ ግንኙነት አላቸው፡፡ ምሥራቅ አፍሪካውያንም ከእንግሊዝ ጋር እንደዚሁ፡፡ የአፍሪካ ደም ያላቸው ባራክ ኦባማ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነዋል፡፡
ቁስላቸውን የጠገኑት በደም መላሽነት መልሰው በማቁሰል ወይም ሕዝብ ከሕዝብ ጋር ተጋጭቶ የትናንቱን በደል በዛሬ በቀል በማወራረድ ሳይሆን፣ ሠልጥነው ይቅር ለእግዚአብሔር ብለው በመተው ከፀብ ይልቅ ፍቅር እንደሚያሸንፍ ተረድተው ያመኑትን በመተግበር ነው፡፡
ከመቶ ዓመት በፊት ከሞተ ሰው ጋር ታግለው ለራሳቸው የዛሬን ሥልጣንና የነገን በታሪክ ታሳቢነት እየተመኙ ሰውና ሰውን በማጋጨት በፖለቲካ የሚነግዱ ሰዎች፣ ዛሬ ለሕዝብ ጥቅም መሥራት የሚገባቸውን አልሠሩምና ሥልጣንም አያገኙም፣ ነገም በታሪክ አይታወሱም፡፡ ከትናንት ወላጆቻቸው፣ ከዛሬ ቲፎዞዎቻቸው፣ ከነገ ልጆቻቸው በቀር ማንም አያውቃቸውም፡፡
ወንዝ ተሻጋሪ ሐሳባዊ ፖለቲካ
ሌሎች ደግሞ አሉ፡፡ ከፈረንጆች ጋር አብረው ኖረው የፈረንጆቹን ሥልጣኔ ከእግር እስከ ራሱ የሚያውቁ ፖለቲከኞች እነሱ በኢንዱስትሪ ብልፅግና ከመሬትና ከተፈጥሮ ጥገኝነት ወደተላቀቁት አውሮፓውያን እንጀራ ፍለጋ ፈልሰው፣ በዘርም በቀለምም በማይመስሏቸው ነጮች አገር ይኖራሉ፡፡
የፈረንጆቹን ሥልጣኔ የአዕምሮ ብስለትና ትዕግሥተኛነት እንዳልሰሙ፣ እንዳላዩ፣ እንዳላወቁ ሆነው አያቶቻችን ተገዳድለዋል በሚል መርዛዊ የበቀል ቡድንተኝነት ተሰባስበው ሕዝብን ከሕዝብ ያጋጫሉ፡፡ እነሱ የፈረንጅ አገር የዜግነት ፓስፖርት ይዘው በነፃነት ሠርተው እየኖሩና በሰላም ወጥተው እየገቡ፣ እኛ በመንደር እንድንከፋፈል በቀበሌ መታወቂያ ላይ በሚጻፍ ብሔር ስም እንድንታወቅ ይሰብካሉ፡፡
ሰውና መሬት እንደ ወንድና ሴት ናቸው፡፡ እንደ ባልና ሚስት ካልተጋቡ ፍሬ አያፈሩም፡፡ እነሱ በፈረንጆች አገር የፈረንጆች መሬት አግብተው ለፈረንጅ አፈር ግጠው ላባቸውን አንጠፍጥፈው ጉልበታውን ሸጠው ፍሬ ያፈራሉ፡፡ ፈረንጆቹም ካፒታላቸውን እኛ አገር ይዘው መጥተው የእኛን መሬት አግብተው መኖር እየጀመሩ ነው፡፡
ሐሳባውያን ፖለቲከኞች ግን የደቡብም ሆነ የሰሜኑ ኢትዮጵያውያን ሰዎችና መሬት የሚያለማና የሚለማ አጥተው ፍሬ ሳያፈሩ መካን እንዲሆኑ ወንድማማቾች በጦርነት እንዲፋጁ ይሻሉ፡፡ የትናንቱን ታሪክ እየኮረኮሩ ሕዝባችን ስለሳይንስና ስለኢኮኖሚ አስቦ የትናንቱን ቁስል ረስቶ ወደ ነገ እንዳይራመድ ያደናቅፋሉ፡፡
አባ ሲመልና አመለካከታቸው
እነ ዶክተር ፕሮፌሰር ማንትሴ የዚህ ዘመን ፖለቲከኞች ከሃምሳ ዓመት በፊት አርጅተው ከሞቱት ማንበብና መጻፍ ካልተማሩት፣ በሰብዕናቸው ግን የመንደር ሳይሆን ዓለም አቀፋዊ ሰው መሆን ከሚችሉት አባ ሲመል ስላነሱብኝ ነው ይህን ፖለቲካ መሳይ የሰላ ትችት ጽሑፍ ላቀርብ የተገደድኩት፡፡
ዛሬ ያለውን ቁሳዊ ሕይወት የትግላቸው መነሻ ሳያደርጉ ከመቶ ዓመት በፊት የተፈጸመን ድርጊት የትግላቸው መነሻ ቢያደርጉ፣ የትግላቸው መድረሻ መቶ ዓመት ወደኋላ ይሆናል፡፡ በዛሬው ቁሳዊ ሕይወታቸው የሆዳቸውን ልክና የኑሮ ደረጃቸውን የዓለም ባንክ ሳይነግራቸው ራሳቸው ለክተው የትግላቸው መነሻ ካላደረጉ፣ መነሻና መድረሻ ያለው ትግል አይኖራቸውም፡፡ የትግላቸው መነሻም መድረሻም ከመቶ ዓመት በፊት ተፈጽሟል አብቅቷል ያለፈ ታሪክ ሆኗል፡፡
እናትና ልጅ ባለ ሁለት ውሻ ውስኪ ‹‹ከን ሰሬ ለማ›› ሙሉ ጠርሙሱን አሥር ብር በማይሞላ ዋጋ ማውረድ ያልቻሉ እነ አባ ሲመል፣ አዋቂዎችና የጅማ ከተማ ልጆች ‹‹ለማ ሰዲ›› በምንልበት በሃያ አምስት ሳንቲም ሦስት ብርሌ ንፁህ የማር ጠጅ በምንጠጣበት ጠጅ ቤት ነበር የምንገናኘው፡፡
ሕፃን አዋቂ ጥቁር ነጭ ደቡብ ሰሜን ተባብሎ መከፋፈል አልነበረም፡፡ ‘ኢሳ ጢሲ ዳዲ ቡሲ’ ይሉ ነበር አባ ሲመል እንደ ዛሬዎቹ ፖለቲከኞች ጠጅ ሊቀዳ በመጣ ቁጥር የፖለቲካ ወሬ ጣል ማድረግ የማይሰለቸው ጠጅ ቀጂ የፖለቲካ ወሬ እያበዛ ሲያላዝንባቸው፡፡
አባ ሲመል ፖለቲካ የማይገባቸው ሰው ሆነው አይደለም፡፡ የእሳቸው ፖለቲካ ማን ከየት መጣ ሳይሆን ሰው በሰላም ሠርቶ ኑሮውን በፈለገው መልክ መርቶ የመኖር ነፃነት አለው ወይ ብቻ ነው፡፡ እንደ አባ ሲመል የማር ጠጅ እየጠጣን ያደግን የጅማ ልጆችም አብሮ በመኖር አስተሳሰባችን ከዛሬ ዶክተር ፕሮፌሰር ፖለቲከኞች እንሻል ነበር፡፡
ዕድገቴ ማንነቴ ነው
ወደ አያት ቅድመ አያት ሳልረማመድ በእናትና አባቴ ብቻ የሦስት ብሔረሰቦች ተወላጅ አባል መሆኔን በኢሕአዴግ ዘመን ባውቅም፣ ትውልዴና ዕድገቴ ከመላው የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች የተውጣጡትን ወልዳ ባሳደገችው ጅማ ከተማ ውስጥ ስለሆነ፣ እስከዛሬም ድረስ የምታወቀው የጅማ ልጅ በመባል ነው፡፡
በስምንት ዓመት ዕድሜዬ በጅማ ዙሪያ ወረዳ ትውልድ መንደሬ ቀይ አፈሯ ዲቱ ከተማ አጠገብ ላንጂቦ ድፍርስ ወራጅ ወንዝ ውስጥ ስንዋኝ፣ ከደራሽ ውኃ ያተረፈኝን ዛሬ በሕይወት የሌለውን የልጅነት ጓደኛዬን ቡልጉ አባ ጎጃምንና ጅማን እንዴት እረሳለሁ?
ከዚህም የተነሳ በብሔር ብሔረሰብ ስም መጥራትና መጠራትን ነፍሴ ስለማትፈልግ፣ ይህን ለሐሳባውያን ፖለቲከኞች ማሳሰቢያ ጽሑፌን የማቀርበው ሰሜን ደቡብ በሚል የቦታ መጠሪያ ነው፡፡
የዚያን ዘመን ልጆች ስለከተሞቻችን ውበት ማውራትና ከተማን ከከተማ ማወዳደር በጣም እንወድ ነበር፡፡ በተለይ ደግሞ በዚያን ዘመን የከተማ አንበሳ አውቶቡስና በርካታ ዘመናዊ አውቶሞቢል ታክሲዎች የሚሽከረከሩባት ጅማ፣ በውበት ከኢትዮጵያ ከተሞች አራተኛዋ መሆኗን ለመስማትና ለማውራት በጣም ደስ ይለን ነበር፡፡
ጅማ ከአዲስ አበባ፣ ከአስመራ፣ ከድሬዳዋ ቀጥላ አራተኛዋ ውብ ከተማ መሆኗን መስማት እህል ከመብላት በላይ ያስደስተናል፡፡ ጅማ የውበት ከተማ እያልንም ዘምረናል፡፡
ዛሬማ ያኔ ጋቢ ከለበሰ በቀር ከተሜ ሰው አይታይባቸው የነበሩ እነ ሽሬ፣ መቀሌ፣ ጎንደር፣ ባህር ዳር፣ ደብረ ብርሃን፣ ሐዋሳ ቅልጥ ያሉ ከተሞች ሲሆኑ የኔዋ ጅማ ከነበረበችበት አንሳ የገጠር ከተማ መስላለች፡፡ ዛሬ የከተሞች ደረጃ ቢወጣ አርባኛ ደረጃም አታገኝም፡፡ ከአንድ ትውልድ በኋላ ደግሞ በከተማነት ደረጃ አራት መቶኛ ሆናለች፡፡
አባ ሲመል ሞቱ እንጂ በሕይወት ቢኖሩ ኖሮ በቀጭን ትዕዛዛቸው እንደ ጠጅ ቀጂው ‘ኢሳ ጢሲ ዳዲ ቡሲ’ ብለው ለትናንት ወሬ እንጂ ለነገ ሥራ ያልተፈጠረ ምላሳቸው፣ ከእጃቸው የረዘመ ፖለቲከኞችን ልክ ልካቸውን ይነግሯቸው ነበር፡፡
አባ ጂፋርና ፍልስፍናቸው
ለጅማ ካለኝ ፍቅር እኩል እስከ ዛሬም ድረስ በኩራት የማስታውሰው ነገር የፈላስፋው አባ ጂፋር ታላቅነት ነው፡፡ ‘ሰሜኖች መሬታችንን ገዝተው ጨረሱብን’ ብለው ደቡቦች አቤቱታ ቢያቀርቡላቸው፣ ‘ምንቸገራችሁ ያልሙላችሁ ነቅለው ይዘውት አይሄዱ’ ብለው መለሱላቸው፡፡
እንዳሉትም የራስ መስፍን ስለሺ የነበረ አርባ ጋሻ የለማ የቡና መሬት ዛሬ የደቡብ ልጆች ንብረት ሆኗል፡፡ በአባ ጂፋር ፍልስፍና ሰው ተፈጥሮን (መሬትን) ያለማል እንጂ የመሬት ዕዳ ሆኖ አያውቅም፡፡
አራጋቢ ጠፍቶ አልተራገበላቸውም እንጂ የተናገሩትን ዘመን ተሻጋሪ ፍልስፍናዊ ንግግር ለዓለም ጆሮ የሚያደርስ ቢኖር ኖሮ፣ ከማንዴላ በፊት ሰዎች ዘር ቀለም ሳይለዩ ተስማምተው ቢኖሩ እንደሚጠቅማቸው የተናገሩት የእኛው አባ ጂፋር ናቸው፡፡
ኔልሰን ማንዴላ ነጮችና ጥቁሮች ሀብት አፍርተው በአንድነት እንዲኖሩ አድርግው የተደነቁበትን ሐሳብ የእኛው አባ ጂፋር ከመቶ ዓመት በፊት ተናግረዋል፡፡ የአያት ቅድመ አያቶቻችንን ጠቃሚ የፍልስፍና እሴቶች ለዓለም ጆሮ ማድረስ አልቻልንም፡፡
የተሰረቀው የቀድሞ ተማሪዎች ትግል
ከእነዚያ ደረታቸውን ለጥይት ለመስጠት ካልፈሩ የንጉሠ ነገሥቱን ዙፋን ከገረሰሱ የ1960ዎቹ ወጣቶች ጀግና ትውልድ ውስጥ፣ ብዙዎች የአፍላ ዕድሜ ሐሳባቸውንና የትግል ሥልታቸውን ትክክለኛነትና ስህተት ሊገነዘቡ የሚያበቃ ዕድሜ አላገኙም፡
ቢሆንም ግን የቀድሞ ተማሪዎች እንቅስቃሴ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እስከ ምሥራቅ ከጫፍ እስከ ጫፍ በኅብረት የተደረገ በመሆኑ ኢኮኖሚን ከፖለቲካ ቁሳዊ ሕይወትን ከንድፈ ሐሳብ በማጣመሩ ውጤቱ ባያምርም ግቡን መቷል፡፡ የመሬት ለአራሹ መፈክር በደርግም ቢሆን ተግባራዊ ተደርጓል፡፡
ከትግራዩ መለስ ተክሌ እስከ ወላይታው ሰለሞን ዋዳ፣ ከራያና አዘቦ የፊውዳል ዘሩ ጥላሁን ግዛው እስከ የበረንዳ እህል ነጋዴው የደሴ ልጅ ዋለልኝ መኮንን፣ ከኃይሌ ፊዳ የወለጋ ልጅ እስከ ግርማቸው ለማ የሰሜን ሸዋው፣ ሰሜኑ ከደቡብ ሁሉም በአንድነት አብረው ሲጮሁ አይተናል፡፡
የትግላችን መነሻ በመሬት ለአራሹ መፈክር ሥር ነቀል የሥርዓት ለውጥ ማድረግ፣ መድረሻችንም ለሕዝቡ ዘውዳዊና ባላባታዊ ሥርዓቱን ገርስሶ የቁሳዊ ሕይወት ለውጥ ያለው ፖለቲካዊ ኢኮኖሚ መገንባት ነበር፡፡
ነገር ግን ከውስጣችን የመደብ ትግሉን በጠባብ የብሔር ትግል፣ ኢኮኖሚያዊ ትግሉን በፖለቲካዊ ትግል ሊቀይሩና አገር ሊገነጣጥሉ የከጀሉ ውስጥ ውስጡን የሚያሴሩ በቅለው ትግሉ ግቡን መቶ ሥርዓቱ ቢገረሰስም ፍሬ ሳያፈራ አመከኑት፡፡ ብዙዎችም ይህን የዓላማ ቅልበሳ ሳያዩ ሕይወታቸው አለፈች፡፡
ከጥላሁን ግዛው በቀር ሌሎቹን ሁሉ በአካል አውቃቸዋለሁ፡፡ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከመግባቴ ከሁለት ዓመት በፊት በትግል የተገደለውን ጥላሁን ግዛውንም ቢሆን ጅማ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪ ሆኜ ለወራት ትምህርት አቁመን ሰላማዊ ሠልፍና ትዕይንትን በማድረግ፣ እንደ ዛሬው በጥይት ሳይሆን በአርጩሜ እየተገረፍን ሐዘናችንና አንድነታችንን ገልጸናል፡፡
የግርማቸው ለማንና የመለስ ተክሌን ዲስኩር በዩኒቨርሲቲው ቆይታዬ እንደ ውኃ ጠጥቼአለሁ፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ስሙን ከወረሱለት መለስ ተክሌ ጋር ከሰባ ደረጃ በላይ ናዝሬት የልጃገረዶች ትምህርት ቤት አጠገብ በሃምሳ ሳንቲም ዋጋ በባልትና ባለሙያ በጥንቃቄ ተዘጋጅቶ ለሞጃ የሚቀርብ የዶሮና የሥጋ አልጫና ቀይ ወጥ የሆቴል ምግብ ለወራት በአንድነትም ተመግበናል፡፡
ከትግሉ ጋር በተያያዘ በዩኒቨርሲቲው መረበሽ ምክንያት ትምህርቴን ለአንድ ዓመት አቋርጬ ቦሌ ጉምሩክ ስሠራ፣ ዋለልኝ መኰንን የአውሮፕላን ጠለፋ አድርጐ የተገደለ ዕለት አውሮፕላን ሲሳፈር የሰውነት ፍተሻ አድርጌ አሰናብቼዋለሁ፡፡ ተባብረሃልም በሚል በጊዜው ኮሎኔል ሰለሞን ከድር በሚመሩት ሰሜን ማዕከላዊ ምርመራ በሃያ ዓመት ዕድሜዬ ለሃያ ቀን ያህል ታስሬም ነበር፡፡
በጊዜው እንደ ፈላስፋ ይቆጠር የነበረውና ተከታዮቹ ከደቡብ ጫፍ እስከ ሰሜን ጫፍ፣ ከምሥራቅ ጫፍ እስከ ምዕራብ ጫፍ በሙሉ በእሱ ስም ፊዲስቶች ተብለው የሚጠሩበትን በስመ ገናናነቱ የማደንቀውን ኃይሌ ፊዳም በአካል አይቼዋለሁ፡፡
እነኚህ ከላይ የጠራኋቸው ጀግኖች በሙሉ ታግለው አልፈዋል፡፡ እኔ በእግዚአብሔር ፀጋ በሕይወት ቆሜ ስማቸውንና ሥራቸውን በአንዳንድ አጋጣሚዎች ይኸው ለማንሳት በቃሁ፡፡
ዛሬ ግን አንድነቱና ኅብረቱ ጠፍቶ ደቡቡ ሲመታ ሰሜኑ ይስቃል፣ ሰሜኑ ሲመታም ደቡቡ ይስቃል፡፡ የ1960ዎቹን ጀግኖች ትግል ያሸነፈው የዛሬው ጥፋት ተልዕኮ ክፉ መንፈስ የዚያው ዘመን መሰሪ ርዝራዦች ቡድንና ውላጁ ናቸው፡፡
ርዝራዦቹና ውላጆቹ ዛሬም የኢትዮጵያ ሕዝብ በዛሬው ቁሳዊ ሕይወት ዙሪያ ተሰባስቦ እንዳይታገል፣ በትናንቱ ፀብ እያላዘኑ ትርጉም የሌለው የቁራ ጩኸት ይጮሃሉ፡፡ ምላሳቸው እየረዘመ እጃቸው የሚያጥር ዶክተር ፕሮፌሰር ፖለቲከኞች በትናንቱ የእርስ በርስ ግጭት ነገር እያኘኩ ይኖራሉ፡፡
ሳይተዋወቁ እኔን የሚባባሉ ሰዎችን አጣሏቸው
እንቅፋት የመታው ሰው ሲያጋጥም ከደቡብ ይሁን ከሰሜን፣ ከምዕራብ ይሁን ከምሥራቅ ሳይለዩ እኔን የሚባባሉ ሰዎችን ተማርን ያሉ ዶክተር ፕሮፌሰር ከፋፋዮች ሊለያዩዋቸው ፈልገው ብዕራቸውን አሾሉ፡፡
በአንተ ወይም በአንቺ ምትክ እኔን እንቅፋት ይምታኝ መባባል ቀላል የፍቅር ማሳያ አይደለም፡፡ በማኅበረሰባችን የሚታወቁ ሌሎችም ፍቅርና አዘኔታ የሚገለጽባቸው ቃላት አሉ፡፡
እኔን አፈር ይብላኝ ይባባላሉ በተለይም ሴቶች ለማያውቁት የተጎዳ መንገደኛ ሐዘኔታቸውን ሲገልጹ፡፡ በኦሮሚኛ ‘ደቼ አና ሀኛቱ’ በወላይትኛም ‘ታና ቢታ ሞ’ ይባባላሉ ሰሜኖችና ደቡቦች ለሰው በሰውነቱ ሲተዛዘኑ፡፡ በትግርኛም ‘ቅድመኸ ይስጠኸኒ’ ይላሉ ለክፉ ነገር ከአንተ በፊት ያድርገኝ ለማለት ሲፈልጉ፡፡
ሕዝብን በብሔር ከፋፍሎ አንዱ ለሌላው በተፈጥሮ ባህርይው መጥፎ እንደሆነ ጭራቅ አድርገው የሚስሉ ፖለቲከኞች፣ በእጅጉ ታሪክን ያጣምማሉ በማቀራረብ ፋንታ ያራርቃሉ፡፡
ክፉን እንጂ ደግ ደጉን ለመናገር ያልታደሉ ከፋፋይ ፖለቲከኞች በገሀድ በዓይን የሚታዩትን የዘመናት የሕዝብ ወንድማማችነት ሀቆችን ክደው እርስ በርስ ለማጋጨት የሚያደርጉት ግፊት ወደ ነገ ለመራመድ የሚደረገውን ጉዞ ያጓትታል፣ የሰውን ነፍስ ይቀጥፋል እንጂ ለማንም አይበጅም፡፡
ሐሳባዊ መርዝን በቁሳዊ መድኃኒት ማርከስ
የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በየዓመቱ በየካቲት ወር አዘውትሮ የሚያሳየው አንድ የ1960ዎቹ የተማሪዎች እንቅስቃሴ አለ፡፡ ራሴን በምሥሉ ውስጥ ባላይም በጊዜው በቦታው እንደነበርኩ በዓይነ ልቦናዬ አያለሁ፡፡ እኔን ብቻ ሳይሆን ከዘመኑ መሪዎቻችንም አንዳንዶቹን አያቸዋለሁ፡፡
ፖሊስ እንዳይገባበት ሉዓላዊ በሆነው ዩኒቨርሲቲያችን በአራት ኪሎ ግቢ ውስጥና አጥር ላይ ተንጠላጥለን እንዘምር የነበረውና የዕለቱ መፈክራችንም ‘ጉልቻ ቢለዋወጥ ወጥ አያጣፍጥም’ ነበር፡፡
ንጉሡ ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድን ከጠቅላይ ሚኒስትርነት አውርደው የትራንስፖርትና መገናኛ ሚኒስትር የነበሩትንና በዕድሜያቸው ገና ጎልማሳ የነበሩትን ልጅ እንዳልካቸው መኰንንን ስለሾሙ፣ ስደተኛው መድኃኔዓለምን ለመሳለም ከቤተ መንግሥት ወደ ስድስት ኪሎ በአራት ኪሎ በኩል ሲያልፉ እንዲሰሙን ነበር በመፈክሩ የጮህንባቸው፡፡
ሁለቱም ጠቅላይ ሚኒስትሮች የሰሜን ሸዋ ሰዎች ቢሆኑም እኛ በብሔርና በዘር ሳንከፋፈል በሥርዓት ጉድለት ሁለቱንም አልፈለግንም፡፡ በዘራቸው ሳይሆን በሚያገለግሉት ሥርዓት ማንነታቸው ነበር ያልፈለግናቸው፡፡
ሁለቱም ሰዎች እጅግ የተማሩና በዓለም አቀፍ ደረጃ የተመሰከረላቸው አዋቂዎች ነበሩ፡፡ ልጅ እንዳልካቸው ለተመድ ዋና ጸሐፊነት ዕጩ ተወዳዳሪ ሆነውም ነበር፡፡ ጥቂት ጉልቻዎች ይውረዱ ብለን የሹመት ንግግራቸውን በሙስናና በኪራይ ሰብሳቢነት ዲስኩር የሚያሟሹ ብዙ ሺሕ ጉልቻዎችን ፈጠርን፡፡
የቀድሞ ሚኒስትሮች ከአገር ማገልገል ወደ አኅጉር፣ ከአኅጉር አገልግሎት ወደ ዓለም አቀፍ አገልግሎት ነበር የሚጠሩት፡፡ ብር አምላኪ የዘንድሮ ሚኒስትሮች ከአገር አገልግሎት ወደ ቀበሌ ሊቀመንበርነት ወይም የክፍለ ከተማ መሬት አስተዳደር ሹምነት ሆነው የሚጠሩትና የሚያድጉት፡፡ ኃይለ ሥላሴን የጣለው የጭሰኛው ሥርዓት ቁሳዊ ኑሮ ሁኔታ ጫፍ ደርሶና የሕዝቡ ንቃተ ህሊናም በዚያው ልክ ሆኖ ነው፡፡ ደርግንም የጣለው የሶሻሊዝም መፍረክረክ ቁሳዊ ሕይወት ሁኔታ ጫፍ ደርሶ ነው፡፡
ኢሕአዴግንም የሚጥለው የኑሮ ውድነት፣ ሥራ አጥነት፣ ድህነትና የሀብት ክፍፍል መዛባት ቁሳዊ ሁኔታዎች ጫፍ ደርሰው እነዚህን ተረድቶ ለመተርጐም የሚያስችል በቁሳዊ ሕይወት ሁኔታ ላይ የተመሠረተ የኢኮኖሚ ንድፈ ሐሳብ ሲፀነስና ሕዝብም ተቀብሎ ሲታገልለት ነው፡፡
የግብርና ኢኮኖሚን መምራት ያቃተው፣ ያልተማሩ ሰዎችን መምራት ያቃተው፣ በጥቂቱ የሚረኩ ሰዎችን መምራት ያቃተው፣ ኋላቀር ኢኮኖሚን መምራት ያቃተው፣ ኢንዱስትሪውን፣ የተማሩ ሰዎችን፣ ብዙ የሚፈልጉ ሰዎችን፣ ዘመናዊ ኢኮኖሚን መምራት ይሳነዋል፡፡ ያኔ ሳይገፈትሩትም ‘የእናቴ ቀሚስ አደናቀፈኝ’ ብሎ ራሱ ይወድቃል፡፡
ሐሳባውያን እርም በሉ፡፡ እኔ እንደ ኢኮኖሚስት ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ሆኜ የምነግራችሁ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ለውጥ የሚመጣው ሕዝቡ ቁሳዊ ሕይወቱ ጎድሎ በኢኮኖሚው ሁኔታ ተማሮ አሻፈረኝ ሲል እንጂ፣ በእናንተ መርዝ ያዘለ በዘር ክፍፍል የተመሠረተ የሰከረ የፖለቲካ ሽኩቻ አይደለም፡፡
ሥርዓትን በጋራ መታገያ ጦሩ የኢኮኖሚውን ሁኔታ ለሕዝብ ማስረዳት እንጂ፣ ደጋግሞ የጎበናንና የምኒልክን የጦናንና የኃይለ ሥላሴን ስም መጥራት አይደለም፡፡ በእነ ምኒልክ ጭንቅላት ውስጥ ገብተን ትናንትን በትካዜ ስናስብ ነገን እናጣለን፣ ለሕዝቡም የነገውን ብርሃን እናጨልማለን፡፡
ሰላማዊ ፍልሰት ከደቡብ ወደ ሰሜን ከሰሜን ወደ ደቡብ
ትምህርቴን ጨርሼ ከውጭ ከመጣሁበት ከ1977 ዓ.ም. ጀምሮ የኢትዮጵያ ጦር ልቅም ብሎ ወጥቶ ሻዕቢያ ኤርትራን ከተቆጣጠረ በኋላ ስድስት ወራት ያህል የጥይት ባሩድ የሌለበት አየር እየተነፈስኩ አስመራ ቆይቼአለሁ፡፡ ባንዲራ ወርዶ ሌላ ባንዲራ ሲሰቀል በዓይኔ ሳይሆን በልቤ አልቅሼና እርሜን አውጥቼ፣ በዓሉ ግርማ ኦሮማይን ከጻፈበት መኖሪያ ቤቴ ወጥቼ ከተከበሩ የመቶ አለቃ ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ ጋር ጠዋት ጠዋት የዕርምጃ ስፖርት የሠራንባቸውን የአስመራን ጎዳናዎች ለቅቄ በኅዳር ወር 1984 ዓ.ም. ነው ወደ አዲስ አበባ የመጣሁት፡፡
በኤርትራ ቆይታዬ እንደሰማሁት የኤርትራን ትግል የወለደው እድሪስ ዓወተ፣ ከብቶቹ ሱዳን ድንበር የሰው ማሳ ገብተው በአፈላማ ተይዘውበት ለአስመራ ሹማምንት እንዲያስለቅቁ ቢያመለክት የሚሰማው ሰው አጥቶ አንድ ጥይት ተኩሶ ወደ ሽፍትነት መግባቱ ነው፡፡ ቆይታ ቆይታ ይህች አንዲት ጥይት ብዙ ሺሕ የኢትዮጵያና የኤርትራ ልጆችን ሕይወት ከቀጠፈች በኋላ በኤርትራ ከኢትዮጵያ መገንጠል ተደመደመች፡፡
አያት ቅድመ አያቶቻችን ‘ቁጭ ብለው የሰቀሉት ቆሞ ማውረድ ያስቸግራል’ የሚሉት እንዲህ ለመሳሰለው ነገር ነው፡፡ ሐሳባውያን ፖለቲከኞች ቁጭ ብላችሁ የሰቀላችሁት ቆሞ ለማውረድ እንዳያስቸግራችሁ ተጠንቀቁ፡፡
ሃያ አምስት ዓመታት የዘለቀው የአባትህን መሬት አርሰህ ብላ የኢሕአዴግ የግብርና ፖሊሲ ሰዎች ለኑሮአቸው ከመሬት ጥገኝነት እንዳይላቀቁ አደረገ፡፡ የእናት የአባትህ ርስት ወዳልሆነ ያለ ክልልህ መጣህ ተባብለውም ሰዎች እንደ ጠላት ተያዩ፡፡ የመሬት አልሚ ሳይሆን የመሬት ዕዳ ሆነው ተቆጠሩ፡፡
አንድ የደብረ ማርቆስ ጓደኛዬ ሲያጫውተኝ አንድ ብዙ መሬት የነበራቸው የከተማዋ አዛውንት፣ መሬት ሳትበዪኝ ልብላሽ ብለው ሸጠው ቅርጥፍ አድርገው በልተው ቀልባቸውን አስደስተው ቀናቸው ደርሶ ሞት መጣና መሬት በተራዋ በላቻቸው ብሎ ነገረኝ፡፡ እሳቸው የመሬቷን አገልግሎት ሸጠው በሉ እንጂ መሬቷን ለሚቀጥለው ትውልድ እንዳትጠቅም ይዘዋት አልሄዱም፡፡ ሰው መሬትን ያለማል እንጂ መሬትን ነቅሎ ይዞ አይሄድም፡፡
የደቡብ መሬታችሁን ሰሜኖች ተሻሟችሁ ወይም የሰሜን መሬታችሁን ደቡቦች ተሻሟችሁ ብለው ጥላቻና ፀብን የሚሰብኩ ፖለቲከኞች በአሳሳች ፍልስፍናቸው፣ ደቡቦች መሬትን ከነፍሬዋ ሳይበሏት በመሬት እያስበሏቸው ነው፡፡ ለማያውቁት ቅድመ አያቶቻቸው እያለቀሱ የሚወዷቸውን ልጆቻቸውን እንዲቀብሩ አደረጓቸው፡፡
መርዘኛው የሐሳባውያን ፖለቲከኞች ጠባብ አስተሳሰብ የሚረክሰው በቁሳዊ ሕይወት ለውጥ ትግል መድኃኒትነት ነው፡፡ መታገል ለቁሳዊ ሕይወት ለውጥ እንደ የሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ሰው ለመኖር በመጠየቅ ሲሆን፣ ይህም የሚሆበት ጊዜ የራሱ ሒደት አለው፡፡ እኛ ከሞትን በኋላ ቢሆን ሥልጣንና ስምን በታሪክ ማጻፍ እናጣ ይሆናል ብለው እንደፈሩት ወደ ነገ የሚሸጋገርም ሳይሆን ጊዜው ዛሬም ሊሆን ይችላል፡፡
በቴክኖሎጂ ዕድገት ሰዎች መሬትን ለእርሻ ሥራ ብቻ መፈለጋቸው ቀርቶ፣ ለኑሮ በመሬት ላይ ያለው ጥገኝነት ሲቀንስና ለእርሻ የማይጠቅመው ድንጋያማ የሰሜን መሬት ለኮንስትራክሽንና ለኢንዱስትሪ ተፈላጊ ማዕድን ሲሆን፣ ሰሜኖች ወደ ደቡብ ብቻ ሳይሆን ደቡቦች ወደ ሰሜንም ሰላማዊ ፍልሰት ያደርጋሉ፡፡ የአርሶ አደር መደብ በወዛደር መደብ ይተካል፡፡ የሕዝብ ንቃተ ህሊናም በዚያው መልክ ይለወጣል፡፡
ከመቶ ዓመት በፊት የነበረው በጦርነት የታጀበ የሀብት ፍለጋ ፍልሰት በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የፋብሪካ ሥራ ፍለጋ ሆኗል፡፡ ኢሕአዴግ ግብርና ግብርና እያለ ባያጓትተው ኖሮ በዚህ ሰላማዊ እንጀራ ፍለጋ ፍልሰት ሕዝባዊ ቅልቅሉና የወንድማማችነት ስሜቱ ዛሬ ወይም ከዛሬ ቀደም ብሎ በተፈጠረና በዘር ላይ የተንተራሰ የእርስ በርስ መጠላላቱ በቀረ ነበር፡፡
አንድ የፋብሪካ ባለቤትና ከልዩ ልዩ ብሔረሰቦች የተውጣጡ ሺሕ ወዛደሮች አብረው ሲሠሩ ሺዎቹን የሚያፋቅር፣ የሚያስተሳስርና በጋራ የሚያታግላቸው ዓላማ ይፈጠራል፡፡ ይህ ዓላማም ከኢኮኖሚያዊ ጭቆናና ከብዝበዛ ቀንበር ነፃ መውጣት ነው፡፡
በኢኮኖሚም በፖለቲካም ለውጥ እንዳይመጣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነቀርሳ ሆኖ አላፈናፍን ያለው የፖለቲከኞች ፍልስፍና ከደቡብ ወደ ሰሜንና ከሰሜን ወደ ደቡብ በሚደረግ ሰላማዊ ፍልሰት ሲረክስ፣ ያኔ በኢትዮጵያ ውስጥ የቁሳዊ ሕይወት ፖለቲካዊ ኢኮኖሚ ሕዝባዊ አመፅ ተቀስቅሶ የጭቆናና የብዝበዛ ሥርዓት ተወግዶ የሥርዓት ለውጥ ይመጣል፡፡
በቅርብ ጊዜ መካከለኛ ገቢ ውስጥ የመግባት ህልም እየከሸፈ ነው፣ ወሬው ከጠፋ ሰነባበተ፡፡ እንደ አቡነ ዘበሰማያት ጠዋት ማታ ይደገም የነበረው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ከተረሳ ከራረመ፡፡ የጋዜጦች ትኩስ ወሬ ክስረትና ጉድለት ሆኗል፡፡ የሴክተር መሥሪያ ቤቶች ለፓርላማው በሚያቀርቡት ሪፖርቶች ጭቅጭቅ ነጋ ጠባ ሆነ፡፡ የውጭና የአገር ውስጥ ኢንቬስተሮች አቤቱታ ፓርላማ ደርሷል፡፡
ኢሕአዴግ ብዙ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማርሽ ቀያየረ ከግብርና ወደ ጥቃቅን ከጥቃቅን ወደ የውጭ ኢንቨስተር ከውጭ ኢንቨስተር ወደአገር ውስጥ ኢንቨስተር ማርሽ መለዋወጡ ብዙም አልሠራም፡፡ እሳት የማጥፋት ማርሽ ስለሆነ እሳቱ በአንድ በኩል ሲጠፋ በሌላ በኩል ይቀጣጠላል፡፡
ምንም እንኳ በዚህ ዝቅተኛ የምርት ደረጃ ላይ ሆኖ የማምረት አቅም ጣሪያ ላይ ተደርሷል ለማለት ባይቻልም፣ የኢኮኖሚ ፖሊሲው ሊያሠራ ከሚችለው የማምረት ጣሪያ ጠርዝ ላይ ተደርሷል ሊባል የሚችልበት ሁኔታ ግን አለ፡፡
ሁለቱም የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዶች ውስጥ የሚታየው ሀቅ መንግሥት የአገር ሀብት አስተዳዳሪ መሆኑንና ለግል ባለሀብቶች እየቆነጠረ እንደሚሰጥ ነው፡፡ የመሥሪያ ቦታ የሚሰጠው መንግሥት ነው፡፡ የመሸጫ ቦታ የሚሰጠው መንግሥት ነው፡፡ የባንክ ወለድን ጣሪያና ወለል የሚወስነውም መንግሥት ነው፡፡ ብድር የሚያመቻቸው መንግሥት ነው፡፡ የገበያ ትስስር የሚፈጥረው መንግሥት ነው፡፡ ይህ ሁሉ የሶሻሊዝም መርህ በካፒታሊዝም ውስጥ አልሠራ ማለት ሁኔታዎች ለለውጥ መብሰላቸውን የሚያመለክት ነው፡፡
ያልታገልንለትና ሕዝቡን በኢኮኖሚያዊ ኑሮው ዙሪያ ንቃተ ህሊናውን ሳናሳድግ በፊት ጊዜው ከፍቷል፡፡ የአገራችን ወቅታዊ ጉዳይ እጅግ አሳሳቢ ሆኗል፡፡ የኢኮኖሚ አርነት ይቅደም ወይስ የጥንቱን የሚያስታውስ የፖለቲካ ሽኩቻ? ፖለቲከኞች የማንኛችሁም አካሄድ ፈሩን ሳይለቅ በፊት ሳይመሽ ሕዝብ እርስ በርስ በፀብና በክፉ ሳይፈላለግ በፊት ወስኑ፡፡ አቋማችሁን ግልጽ አድርጋችሁ ለሕዝብ አሳውቁ፡፡
በ1966 ዓ.ም. ጮኸን ተጯጩኸን ንጉሡን ስናወርድ ተረካቢ መኖር አለመኖሩን አላየንም ነበር፡፡ ትግላችንን ለወታደራዊ መንግሥት አስረክበን አረፍነው፡፡ በኢሕአፓና በመኢሶን አባልነት ተከፋፍለንም እርስ በርሳችን በቀይ ሽብርና በነጭ ሽብር ተላለቅን፡፡
ዛሬም ተመሳሳይ ሁኔታ ይታያል፡፡ የአሁኑ ከበፊቱም ይብሳል፡፡ የቀድሞ አንድነትና ኅብረት የለም፡፡ በብዙ ነገሮች ተከፋፍለናል፡፡ ጠንቀቅ እንበል፡፡ ልናደርገው ስለማንችለው ስላለፈው ትናንት እያሰብን ነገን እንዳናጣ፡፡ ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ቆሞ ለማውረድ ያዳግታል፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው Getachewasfaw240@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

Standard (Image)
Viewing all 231 articles
Browse latest View live